Saturday, 21 March 2020 12:34

የተራዘመ ምጥ

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(1 Vote)

      ‹‹….ትዝ ይለኛል፡፡ ጊዜው ወደ 45 አመት ይሆነዋል፡፡ የተወለደችው ልጅ አሁን 45ኛ አመቷን ይዛለች፡፡ እኔ ሳረግዝ እድሜዬ ገና 16 አመት ነበር:: እርግዝና በመከሰቱም ቤተሰብ በግራም በቀኝም ያሉት ማለትም የእኔም የባለቤቴም ቤተሰቦች እንዲሁም እኔና ባለቤቴ ተከራ ይተን በምንኖርበት አካባቢ በጉርብትና የሚኖሩ ሁሉ ተደሰቱ፡፡ ከዚህም በላይ ባለቤቴ እጅግ በጣም ነበር የተደሰተው፡፡ በዚያ ጊዜ ክትፎ በሁለት ብር ይበላ ነበር፡፡ ውድ ነው ቢባልም የእኔ እርግዝና ግን ስላስደሰተው በአዲስ አበባ ክትፎ መሸጥ ከጀ መሩት ጉራጌ ሴት ቤት እየወሰደ ይጋብዘኝ ነበር፡፡ በዚያ ላይ ቢራ ይጠጣል:: ከዚህ በተጨማ ሪም ቤተሰቦቼ እንዲሁም ጎረቤቶቼ የገንፎ እህል ስላዘጋጁ አስቀድሞ መበላት ተጀመረ፡፡
እርጉዝ የሆንኩት ሴት ገና በህጻንነቴ ያረገዝኩ በመሆኑ ምግብ በየአይነቱ ቀርቦልኝ ከመብላት በስተቀር ይህ ሊደረግ አይ ገባም የሚለኝ ሰው አልነበረም፡፡ ስለዚህም እኔም ጽንሱም ወፈርን:: በእርግጥ ለጊዜው የሚታ የው የእኔ ውፍረት ቢሆንም ሰውነቴ ባጠቃላይ ግን በጣም ስለገዘፈ ልክ ዘጠኝ ወር ስገባ መላ ሰውነቴ አበጠ፡፡ ፊቴ፤እጄ፤እግሬ በእጅ ሲነኩት ወደውስጥ ሰምጦ መቅረት ሆነ፡፡ ስለዚህም ለመውለድ አስራ አምስት ቀን ሲቀረኝ አስቀድሜ ከሆስፒታል እንድገባ ተደረገ:: በሆስፒታል ከሚቀርበው ምግብ ውጭ ምንም ነገር እንዳልመገብ በዶክተሩ ታዘዝኩ፡፡ ክትፎ የለ፤ገንፎ የለ፤ ሌሊት ተነስቶ መብላት የለ፤ ሁሉም ነገር በትእዛዝ የተመራ…. ጨው የሚባል ነገር የሌለው ሆነ፡፡ በእርግጥ ሰውነቴ እብጠቱ ጎደለ፡፡
ቀኑን ቆጥሮ አይቀርምና ምጥ መጣ፡፡ ዛሬ ቢሆን ኖሮ በምንም አይነት መንገድ በወለድኩበት ሁኔታ ልወልድ እንደማልችል እገምታለሁ፡፡ አርብ እለት ምጥ የጀመረኝ እስከ እሁድ ድረስ ቆየሁ፡፡ ምጡ ሲመጣ ሲሄድ…እኔም እንደጮህኩ ሶስተኛው ቀን ላይ ምጡ ጭርሱንም ሲተወኝ ጽንሱ ታፈነ በሚል ሐኪሞቹ ተሯሯጡ፡፡ ሐኪም ተጠርቶ መጥቶ በሚያዋልድበት ዘዴ አዋለደኝ፡፡ እንዲህ እንደዛሬው በኦፕራሲዮን መውለድ የሚባለው ነገር ያኔ እንደዛሬው በቀላሉ የሚገባበት ሳይሆን በጣም እሩቅ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ወሬውም አልነበረም፡፡ ሐኪሞቹ ቶሎ ቶሎ እየተመለከቱ ብቻ በትእግስት ጠብቀው መጨረሻ ላይ ሁኔታው ወደ አደጋ ሊለወጥ ሲል ያውም በኦፕራሲዮን ሳይሆን በብልት አካባቢ በሚደረግ እስቲች በሚባለው እና ሐኪሙ በተመሳሳይ ሰአት ጽንሱን በመግፋት ልጅቷ እንድትወለድ አደረጋት፡፡ ልጅቱም በምጥ ስትገፋ ቆይታ በሁዋላ ደክሞአት ሰለነበር ከማህጸን ስትወጣ አላለቀሰችም፡፡ ድምጽዋን ያሰማችው እግርዋን ይዘው ቁልቁል ዘቅዝቀው ሲመቷት ነበር፡፡
እኔን ዛሬ የሚገርመኝ ገና ምንም ምጥ ሳይጀምራቸው ጭምር የኦፕራሲዮን ቀጠሮ የሚይዙ መኖራቸው ነው፡፡ በእርግጥ ምጥ ሲራዘም ብዙ ነገር እንደሚያበላሽ ዛሬ በስፋት እየተነገረ ነው፡፡ ቢሆንም ግን እኔ በወለድኩበት ዘመን የነበሩት ባለሙያዎች ለእርጉዝ ሴት በተለይም ምጥ ላይ ለሆነችው ያደርጉ የነበሩት ክትትል በጣም ጥሩ ነበር የሚል ምስክርነት እሰጣለሁ፡፡ ዛሬ ህክምና የለም ለማለት አይደለም፡፡
አቻምየለሽ ጥሩነህ ከጎፋ
ወ/ሮ አቻምየለሽ ጥሩነህ እንደሰጡት ምስክርነት በዚያን ዘመን በኦፕራሲዮን ልጅን መገላገል እጅግ በጣም አስቸጋሪ ነገር ካልገጠመ በቀር የማይደረግ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በዚህ ዘመን ግን በተለይም በሕክምና ባለሙያው ሲታመንበት ጊዜ ሳይሰጠው የሚሰራ ስለሆነ ሴቶች በተለይም የህክምና ተቋማት ባሉበት አካባቢ ለተራዘመ ምጥ የማይጋለጡበት አጋጣሚ ይስተዋላል፡፡ ቢሆንም ግን ተቋማቱ እንደልብ ቅርብ ባልሆኑባቸው ወይንም በተለያዩ ምክን ቶች ሴቶች ለተራዘመ ምጥ የሚዳረጉበት እና እናትም ሆነች የሚወለደው ልጅ ለጉዳት የሚዳ ረጉበት ሁኔታ ይስተዋላል፡፡
አንዲት ሴት በምጥ ለሁለት ሰአትና ከዚያ በላይ የምትቆይ ከሆነ የተራዘመ ምጥ ሊባል ይችላል፡፡ ይህ ሰአት ለመጀመሪያ ጊዜ ልጅ ለምትወልድ ሴት ሲሆን ለሁለተኛ ወይንም ከዚያ በላይ ለወለደች ሴት ደግሞ አፋፍሞ የመጣ ምጥ ከአንድ ሰአት በላይ ከቆየ የተራዘመ ምጥ ይባላል አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፡፡ ይህ በወልድያ ዩኒቨርሲቲ በማዋለድ ሙያ ላይ ከተሰማሩ ባለሙያዎች የቀረበ ጥናት ሲሆን እነሱም Henok k.*, Balem D., Gelawdyos G. * Department of Midwifery, Woldia University በሚል ስማቸው በጥናቱ ላይ ተጠቅሶል፡፡
ባለሙያዎቹ እንደሚሉት ከሆነ ከ19ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ይህንን በሁለተኛ ደረጃ የተራዘመ ምጥ በሚመለከት የአሰራር መመሪያ ቢኖርም በአለም አቀፍ ደረጃ ግን የተራዘመ ምጥ በሚ ለው ከስምምነት አልተደረሰም፡፡ የእናቶች እና አዲስ የሚወለዱ ህጻናት ጤንነት ከምጥ ጋር በተያያዘ በእጅጉ የተገናኝ መሆኑም እሙን ነው፡፡
በኢትዮጵያ አዲስ የተወለዱ ህጻናት ሞት በእጅጉ የቀነሰ ሲሆን እሱም ከ1000 በሕይወት ከሚወለዱ 29 ሆኖ ተመዝግቦአል፡፡ ዋናው ለሕጻናቱ ሞት ምክንያት የሚባሉት፤
በወሊድ ጊዜ መታፈን (31.6%)
መመረዝ ወይንም Infection (18.5%) ነው፡፡
የተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ በእናትየው ላይ የተለያዩ የጤና ችግሮችን ቢየስከትልም በአዲስ በሚወለዱ ሕጻናት ላይ ግን በምጡ ሰአት ሲታፈኑ ከፍ ላለ ችግር እንደሚጋለጡ እውነተዎች ያሳያሉ:: በምጥ ሰአት ልጽንሱ የቆይታ ጊዜውን ጨርሶ ከማህጸን ለመውጣት ግፊት የሚያደርግበት ሰአት በመሆኑ የእናትየው ሰውነት ላላ ብሎ ልጁን እንዲወለድ ምቹ ካልሆነ አየር እንደሚያጣ እሙን ነው፡፡ ምናልባትም የመወለድ እድል እንኩዋን ቢኖረው በምጥ  ላይ በመቆየቱ ምክንያት የሚከሰቱ አንዳንድ የጤና ጉድለቶች ስለሚኖሩ ሕክምናን እንዲያገኙ የሚጋብዝ፤የጨቅላ ህጻናትን በተለያዩ ምክንያቶች እንዲመረዙ ማድረግ፤የመሳሰሉትን ችግሮች ሊያስከትልባቸው ይችላል፡፡
በዚህ ጥናት የሚገኘው መረጃ የጤና አገልግሎት ለሚሰጡ ባለሙያዎች መረጃ ላይ የተመሰረተ ስራ እንዲሰሩ እና ወደፊትም ጥናት ለሚያደርጉ መነሻ ሀሳብ ይሆናል የሚል እምነት እንዳ ላቸው ጥናት አቅራቢዎቹ ይገልጻሉ፡፡ ጥናቱ በተደረገበት ሆስፒታል ወደ 11.896 እናቶች በትክክለኛው መንገድ Normal የሁለተኛ ደረጃ ምጥ ልጃቸውን ተገላግለዋል፡፡ 264 እናቶች ግን በተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ ልጃቸውን ወልደዋል፡፡
በጥናቱ የተካተቱት እናቶች አማካይ እድሜ 25 ሲሆን የተራዘመው የሁለተኛ ደረጃ ምጥ የገጠማቸው እናቶች አማካይ እድሜ 26 አመት ነው፡፡
በተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ የወለዱት 233 ሴቶች እና 712 የሚሆኑ እንዲሁም በኖርማል የሁለተኛ ደረጃ ምጥ የወለዱ ሴቶች አማካይ እድሜ ከ20-34 አመት መሆኑን ጥናት አቅራ ቢዎች ገልጸዋል፡፡
መኖሪያ አካባቢን በሚመለከት 76.9% የሚሆኑት በተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ የወለዱት እና 87% የሚሆኑት በኖርማል ምጥ የወለዱት የከተማ ነዋሪዎች ናቸው፡፡
በተለያዩ ሀገራት የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ የተራዘመ ምጥ የሚያስከትላቸው የእናቶችና የጨቅላ ህጻናት ጤንነት መጉዋደል እና እስከ ሕልፈት ሊያደርስ የሚችል ውስብስብ ነገርን እንደሚያስከትል እሙን ነው፡፡ ይህንን ለመከላከል ገና ከእርግዝና በፊት ጀምሮ የሚደ ረገው ክትትል የተፈጠረው ችግር ምን አይነት እንደሆነ አስቀድሞ ከማወቅ እና ሰፊ ጊዜ ሰጥቶ እናትየውን ከመጎብኘት የተያያዘ ስራ መሰራት እንደሚገባው በካናዳ እና አሜሪካ የተገኙ ውጤ ቶች እማኞች ይሆናሉ፡፡
እናቶች በተራዘመ ምጥ ምክንያት ከሚደርስባቸው የጤና እክል አንዱ  የማህጸን መተርተር ነው፡፡ ይህ የጤና እውክታ በተለያዩ ሀገራት ማለትም ባደጉትም ይሁን በማደግ ላይ ባሉ አገራት በተደረጉ ጥናቶች ተጠቁሞአል፡፡ ይህም የሚከሰተው በተራዘመ ምጥ ምክንያት የማህጸን ፤የብልት ወይንም የጡንቻዎች መጎዳት ሊደርስ ስለሚችል ነው፡፡
የተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ ከእናቶችና አዲስ ከሚወለዱ ህጻናት ሁኔታ ጋር በተቃራኒ መንገድ የሚመደብ አደገኛ ሁኔታ ነው፡፡
ስለሆነም ይህንን የተራዘመ የሁለተኛ ደረጃ ምጥ እናትየውም ትሁን የሚወለደው ችግር ውስት ሳይገቡ እና ጊዜውም ሳያልፍ ጠንከር ባለ የህክምና ክትትል አፋጣኝ መፍትሔ በመስጠት ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት ማስቀረት ይቻላል፡፡   


Read 13903 times