የአፍሪካንና የቻይናን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንዳሸጋገረ የተነገረለትና በቻይናውያን ተገንብቶ ለአፍሪካ ህብረት በስጦታ የተበረከተው 200 ሚ. ዶላር የወጣበት አዲስ ህንፃ ሰሞኑን በጣለው ዝናብ ጣራው ማፍሰስ ጀመረ፡፡ ህንፃው ባለፈው ጥር ወር በተካሄደው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ መመረቁ የሚታወቅ ሲሆን የህንፃው ውበትና ጥራት ተደጋግሞ ሲወራለት እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ሆኖም ገና በስድስት ወሩ ነው ማፍሰስ የጀመረው፡፡ በአሁኑ ወቅት እየተካሄደ ያለው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ በማላዊ መካሄድ የነበረበት ቢሆንም አስተናጋጅ አገሯ ማላዊ፤ የሱዳኑን ፕሬዚዳንት ኦማር ሃሰን አልበሽርን አላስተናግድም በማለቷ ነው ጉባኤው በአዲስ አበባ እንዲደረግ የተወሰነው፡፡ባለፈው ረቡዕ ከሰዓት በኋላ የጣለው ንፋስ የቀላቀለ ከባድ ዝናብ አዲሱን የህብረቱን ህንፃ የጥራት ደረጃ የተፈታተነ ሲሆን ወደ ዋናው አዳራሽ መግቢያ ሎቢ ላይ ዝናብ ሲያፈስ እንደነበር ታውቋል፡፡
ህንፃው በማፍሰሱ ግራ የተጋቡት ቻይናውያን የህንፃው የጥገና ሠራተኞች፤ ውሀውን በመወልወል ላይ የነበሩትን የፅዳት ሠራተኞች ቆሞ ከመመልከት ውጪ ምንም ማድረግ አልቻሉም የጥገና ሠራተኞቹን ለማነጋገር ሙከራ ብናደርግም ቻይናውያኑ እንግሊዝኛ ቋንቋ መናገር ባለመቻላቸው ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ህብረቱ ህንፃ ውስጥ ሆነው ሁኔታውን የተመለከቱ አንዳንድ ታዛቢዎች፤ ያ ሁሉ አድናቆት የጐረፈለት አዲሱ ህንፃ፤ ዓመት እንኳን ሳይሞላው ማፍሰሱ እንዳስገረማቸው ተናግረዋል፡፡ “አሁን በእርግጥም የቻይና ህንፃ መሆኑ ታወቀ” ብለዋል ሎቢው ውስጥ ሲፈስ የነበረውን ዝናብ ቆመው ሲመለከቱ የነበሩ ታዛቢ፡፡ ሌላ ተመልካች ደግሞ “የስጦታ ፈረስ ጥርሱ አይታይም” የሚለውን አባባል ጠቅሰዋል - በስጦታ የተበረከተው ህንፃ ለወቀሳ እንደማይመች ለማመልከት፡፡