Saturday, 15 August 2020 14:59

በማኮን ኢንጂነሪንግ 10ሚ. ብር የሚያወጡ ኦክስጅን መሰብሰቢያዎችን ለገሰ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 ባማኮን ኢንጂነሪንግ ከእህት ኩባንያዎቹ ጋር በመተባበር ለኮቪድ 19 ህሙማን ከፍተኛ አገልግሎት የሚሰጡ ኦክስጂን ኮንስትሬተሮችን ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለፈው ረቡዕ ነሐሴ 6 ቀን 2012 ዓ.ም ለገሰ፡፡ ኩባንያው ያበረከታቸው እነዚህ 100 ኮንሰንትሬተሮች እያንዳንዳቸው ለሁለት ታማሚ በበቂ ሁኔታ ኦክስጂን መሰብሰብ የሚችሉ ሲሆን፤ ለዚሁ ተግባር ታቅደው በልዩ ሁኔታ መታሰራቸውን የባማኮን ኢንጂነሪንግ ኩባንያ ባለቤትና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢ/ር ግርማ ገላ አስታውቀዋል፡፡
የኦክስጅን መሰብሰቢያ ማሽኖቹ በሶኬት የሚሰሩና ትልቅ ጠቀሜታ ያላቸው ሲሆን፤ ከ10 ሚ ብር በላይ ወጪ እንደወጣባቸውም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ኩባንያው አገራችን አሁን ያለችበትን ተጨባጭ ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባትና ከኮቪድ 19 ወረርሽኝ ጋር የተገጠመውን ትንቅንቅ ታሳቢ በማድረግ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት እነዚህን መሳሪያዎች መለገሱንም ኢ/ር ግርማ ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ከተማ አስተዳደሩም ለተደረገለት ልገሳ ለኩባንያው ኃላፊዎች ምስጋና አቅርቧል፡፡ ባማኮን ኢንጂነሪንግ በሀገራችን የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የረጅም ዓመታት ልምድ ያለው የደረጃ 1 ተቋራጭ ሲሆን፤ በስራቸውና እየሰራቸው ባሉ በርካታ ደረጃቸውን የጠበቁ የህንፃ ግንባታዎች ይበልጥ የሚታወቅ ሲሆን፤ ከዚህም በተጨማሪ የሃይል ንዑስ ጣቢያዎችንና ሃይል ማስተላለፊያ አውታሮችንም የሚሰራ ኩባንያ መሆኑም ታውቋል፡፡


Read 3056 times