Saturday, 02 January 2021 12:26

10ኛው የባህልና የኪነ ጥበብ ሳምንት በጎንደር ይካሄዳል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   በጎንደር ከተማ ከጥምቀት በፊት ባለው አንድ ሳምንት የሚካሄደውና ዘንድሮ ለ10ኛ ጊዜ የሚከበረው የባህልና ኪነ-ጥበብ ሳምንት በጎንደር ከተማ እምደሚካሄድ የጎንደር ከተማ ባህል ማዕከል ደይሬክተር አቶ ገብረማሪያም ይርጋ አስታወቁ፡፡
ጥምቀት ሀይማኖታዊ በዓል ቢሆንም ጥምቀትን ለመታደም ወደ ጎንደር የሚመጣው ቱሪስት የጎንደርን ታሪክ፣ባህላዊ ትውፊትና ኪነ-ጥበብ እግረ መንገዱን አይቶ እንዲመለሰ ታስቦ ለ10 ዓመት በፊት ከጥምቀት በፊት እነዚህን ትውፊቶች የሚያሳይ የባህል ሳምንት መጀመሩን ያስታወሱት ዳይሬክተሩ ዘንድሮም ለ10ኛ ጊዜ በተለያዩ ባህላዊና ኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች የባህል ሳምንቱ በድምቀት ይካሄዳል ብለዋል፡፡
በዚህ የባህል ሳምንት ከሚካሄዱት ባህላዊና ኪነ- ጥበባዊ ክንውኖች ውስጥ የሲራራ ንግድ ምንነትና ታሪክ፣ ግጥም በመሰንቆ፣ አዝማሪ ማርቺንግ ባንድ፣ ከ250 ዓመት በፊት የእነ አፄ ፋሲልና ሌሎች ነገስታቶች አኗኗር፣ አለባበስና ሌሎች ስርዓቶችን የሚያሣይ ”ህይወት በአብያተ መንግስታት የተሰኘ ቅንጭብ የጎዳና ላይ ትርኢት፣ የአፄ ቴዎድሮስ 202ኛ የልደት በዓልና ሌሎች ባህላዊና ኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶ እንደሚቀርቡ  አቶ ገብረ መማሪያም ይርጋ ጨምረው ገልጸዋል፡፡
እነዚህ ዝግጅቶች በከተማው በሚገኙ የኪነ ጥበብና የባህል ቡድኖች የሚከናወኑ ሲሆን ከፍተኛ ዝግጅት አየተደረገባቸው እንደሆነ ገልፀው ጥምቀትን ለመታደም ያቀደ ሰው ቀደም ብሎ ወደ ከተማው በመምጣት እነዚህን የኪነ-ጥበብ ዝግጅት እንዲታደም ግብዣ አቅርበዋል፡፡   

Read 11652 times