Monday, 15 March 2021 00:00

ሴት መሪ ያላቸው አገራት ቁጥር ዘንድሮ በ2 ብቻ ጨምሮ 22 ደርሷል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

 የአለማችን ሴቶች ከፓርላማ ወንበር የያዙት ሩብ ያህሉን ብቻ ነው

           በአለማችን በሴት ፕሬዚዳንቶች ወይም ጠቅላይ ሚኒስትሮች የሚመሩ አገራት ቁጥር ባለፈው የፈረንጆች አመት ከነበረበት በ2 ብቻ ጨምሮ 22 መድረሱንና በአለማችን ፖለቲካ ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ በመጠኑ ቢጨምርም፣ የጾታ ልዩነቱ አሁንም ሰፊ መሆኑንና በአለማቀፍ ደረጃ ሴቶች በብሔራዊ ፓርላማዎች ውስጥ ያላቸው ድርሻ 25.5 በመቶ ያህል ብቻ መሆኑን ከሰሞኑ የወጣ አንድ ሪፖርት አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ኢንተርፓርላሜንታሪ ዩኒየን ባለፈው ረቡዕ በጋራ ባወጡት አመታዊ ሪፖርት እንዳሉት፣ በአሁኑ ወቅት በሴት ፕሬዚዳንቶች ወይም ጠቅላይ ሚኒስትሮች ከሚተዳደሩ 22 የአለማችን አገራት መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በአውሮፓ የሚገኙ ናቸው፡፡
ሴቶች በሚኒስትርነት ስፍራዎች ግማሽ ወይም ከዚያ በላይ ድርሻ የያዙባቸው አገራት ቁጥር በአንጻሩ አምና ከነበረበት 14 ዘንድሮ ወደ 13 ዝቅ ማለቱን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ 12 የአለማችን አገራት አንድም ሴት ሚኒስትር እንደሌላቸውና አገራቱም አርሜኒያ፣ አዘርባጃን፣ ብሩኒ፣ ሰሜን ኮርያ፣ ፓፓ ኒው ጊኒ፣ ሴንት ቪሰንት፣ ግሪናዲንስ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ታይላንድ፣ ቱቫሌ፣ ቫኑዋቱ፣ ቬትናም እና የመን መሆናቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡ በአፍሪካ ባለፈው አመት የሴት ሚኒስትሮችን መጠን በከፍተኛ መጠን በማሳደግ ቀዳሚዋ አገር የሆነቺው ናሚቢያ መሆኗን የገለጸው ሪፖርቱ፣ በአገሪቱ የሴት ሚኒስትሮች ድርሻ ከ15 በመቶ ወደ 39 በመቶ ማደጉንና የሴት የፓርላማ ድርሻ ከፍተኛ የሆነባት ቀዳሚዋ አገር ደግሞ ሩዋንዳ መሆኗን አመልክቷል፡፡

Read 9701 times