Sunday, 11 July 2021 18:27

ጠይም ፎቶግራፍ

Written by  ሳሙኤል በለጠ (ባማ)
Rate this item
(5 votes)

  የተዘቀዘቀ ሕይወት በፎቶ ካልተነሳ ትዝታው ባዶ መሆኑ አይቀርም:: እኔ ከነፍስ በነፍስ ለነፍስ ስለ ነፍስ ወደ ምድር ስለመጣሁ ለፎቶ የሚሆን ሥጋ አልያዝኩም፤ መንፈስ ነኝ መሰለኝ፤ የቆሰለ አንጀቴ ተራራ ሲያጥረው፣ ለፈውስ ሳንካ ሲያደናቅፈው፣ ድቅድቅ ሌሊት፣ ቀን፣ ዐመት እርስ በርስ ይናከሳሉ። ማን በማን ተበላ? ማን አለቀ? ማን በርባሮስ ጠለቀ? ማን? በዘላለማዊ የኅልውና መስኮት አሾለቀ ነው። ጥያቄው ይህ እስቲፈታ ትኩስ አረንጓዴ ቅጠሎች ልባችን ቅርንጫፍ ላይ፣ በቅንፍ ዐይናችን ቅርንጫፍ ላይ ቅጠሎቹ ይበልላሉ፤ ቅንፉ ይዘጋል። በሰሜንና በምስራቅ ማዕዘን ቅስሟ ቆሟል። ቅስሟም በንፋስ ሲበተን...
“አንገት ደፊ መከራ አቃፊ” ተሰበረ ቅስሙ ወዘናው ተንጠባጠበ፣ ይወዳታል፣ ፍቅር ልቡ ላይ ቂጥ አለበት፤ የምወድሽ ከሕልም ወዲያ ከተፈጠርንበት ወዲያ ሄጄ እዛ ባለው በልብሽ መቅደስ ውስጥ ዝማሬ አሰምቼ መለስ ቀለስ አልሁ ይላል፤ በልቡ አታውቅም! ጠይም ምስሏ አለቅ አለው፤ አርምሞ ጎደለበት፤ በስስት ላይ ፍቅር ይሁን ውሕደት? አታውቅም! በቁሙ ታመመ፤ ልቡ እንደ ጉልበቱ አላውቅህም ቻው! አለው። ይህ አፍታ ለእርሱ እንደ ጦሞና ውስብስብ ነበር፤ ነገው ከዝምታ ይንቀረፈፍበታል፣ በእንጥሏ ጫፍ ስትስመው፤ ሲሰማው፣ የድመት ጅራት ሲዳስሰው ይነቃል፣ ይቃትታል፤ ከልቡ ቅዠቱ ይሰፋል፣ ራቁት ቅዠቱን በቀጭን ልብስ የሚሸፍንለት ያጣል። ጥልቅ ባህር መሰረቱ አይገኝም የሚንጠለጠል እሳት ምናምን እያለ ያንጎላጃል። ጨለማው ነገን ለማስታወክ የሰሜንን ጉሮሮ በብርሃን ጣት ይጓጉጣል፤ ጩኸት የዝምታን ጡት ይለዘልዛል።
ትንሽ ቤት
ትንሽ በር  (ሰው ባዶ)    ዝም
                     ተብሎ የተተወ
...በልቦናው ቅርንጫፎች ላይ ሲረጭ ተሰማው፣ አሰበ፤ በልቡ ተሰቃይ ያለው ገላ እንዲያው ደርሶ ይሰቃያል። ሃጫ ነፍሱ ላይ ጥቁር ቁስል ይንጎራደዳል። ዝናብ ቆሞ ከሩቅ ሠማይ አንድ የዜማ ብርሃን ጭል-ጭል ጭልጭልታን ሲያይ፤
 “ቀኑንም ትደግመው” የሚል ድምጽ ዶሮውን ጠቅ አደረገው፡፡
“ዝም፤”
“አንተ? አንተን አይደለምዴ ?”
ልዝዝ ያለ ሕልም በደመናና በብርሃን ሲለቃለቅ፣ በንፋስ አውታር ሽቅብ ተሰቅዬ፣ ከተሰነቀርኩበት ሽቅበት ቁልቁል ስመዘዝ፣ ወንድ አዝማሪ መሰንቆውን እየመታ፣ ሴቲቷ በአንገቷ እስክስታ እየመታች ትወርዳለች። እንባዬ በአንገቴ ትንኳለላለች፤ ጸጥታ ጸንቷል። ሽፍንፍን ለጥ፤ ማንንም አልሰማ፡፡
ከሁሉም በፊት
“እንዲህ ነው ሕይወት”
“እንዴት?”
ከእናትህ ማሕጸን በቅጽበታት ሂደት የጀመርከው መንገድ፣ ከሕይወት አልፎ የሞት ድልድይን ተሻግሮ እስከ ማያውቀው ይጓዛል።
“ምን ? ምን ይጓዛል?”
“ሞትም ሕይወትም! የማይቆም ጉዞ ከ-እስከ እግርን በመንገድ እያለፉ፣ መሬት ለቆ መንፏቀቅ። እንዲህ ነው።”
“ምኑ?”
“ፍልስፍናው ሀሁ”
“ምነው ባልተኛሁ፤ ምነው ሕልምን በፈራሁ”
አሁን ወይ ....
እንደ ሀምሌ ውኃ አድፌያለሁ፣ ዐደቴ ተሳክሯል፤  የጠገገው አንጀቴ ቆስሏል፤ ሀዘን ያንጠራራኛል ሰይጣን ይጠራኛል፡፡ ምንም እንኳ ቢጎነቸር ታሪኩ እወዳት ነበረ፤ ይህ በደም የተጻፈ ቁንጽል የገጽ ግንጣይ ነው። ላባ ጠብ ሳይልብኝ ዐይኗ ሳይዳስሰኝ፣ ክምዶቿ ላይ ሳልቀልጥ፤ ጭኖቿ ሳይሞቀኝ፣ ከንፈሯን ሳልቀነጥበው፣ ሲቃዋን ሳልደቃው፣ ጭቃ ሜዳዋን ሳረግጠው፣ ወይንነቷ ይቅር ግድ የለም፤ ቅራሬነቷን ፉት ሳልለው በመንፈስ አውርተን ሞተች፤ ሙትትትት ሙትትትት!
እሷ ቀስተ ደመና ሥር ሆና የሞት ምጥ ቅሪቷ እኔ ነበርኩ፤ ስታጣጥር የእኔን ፎቶ አሰቀለች፤ ጠይም ፊቴን ቅዝዝዝ ብላ እያየች፣ እያየች በሞት አፍ ተላመጠች፡፡
ማን ነኝ? ማን ነበርኩ? ምንድነኝ? ወዴት ነኝ? ወዴት ነው  የምሄደው?
ምናልባት ጥልቅ እንቅልፍ ግማሽ ሞት ይሆናል። እርጥብ ላብ ግንባሬ ላይ ተንሳፏል። የማልወጣው፣ የማልወርደው ሸለቆ ወደ እኔ ይንደረደራል። ዘላለም የምጻትን ሥጋ መንጥቃ ስትወራጭ፤ ወገግ ብሎ ይታየኛል።
ሰው ባዶው ቤት ውስጥ ንፋስ ተጠቅጥቆ፤ ሽውሽውታን እየሰማ የክብ ይደንሳል። የቫንጎን “Stary Night” በግራ ዐይኔ ያየሁ ይወስል፣ ሥጋዬ ላላ፣ ነፍሴ ተመሰቃቅላ፣ ጭውውው ብሎብኝ ቆምኩ፡፡ ይህ ቤት፤
ሀ) የለዘበው ምሰሶ መረሬው ንቃቃት ውጦ አንቅዞታል።
ለ). ተወለጋግዷል።
መ) ትዝታ እንዳይሆን ሌጣ ቀለሙ ለቋል።
ሠ) መ እና ሀ
መ) ሠ ነው መልሱ!
 “ከማንጯለቅ መስኮት መክፈት” ቀስ ብዬ ገባሁ፤ ፈዘዝ ያሉ ቀያይ መብራቶች ዐይኖቼ ላይ ቃተቱ፤ በቀጭን ገመድ የተሰቀሉ ነፍስ ያላቸው መልኮች ተንጠልጥለዋል። አሃ ፎቶ ማጠቢያ ቤት ነው። ግማሾቹ ቆስለዋል፣ ግማሾቹ ተጎሳቁለዋል። (መልካቸውን አጥተዋል።) ግን ታጥበዋል። ሥጋ ይዘዋል። ነፍስ እንጃ እንጂ!
አንዴ ይህንን የመሳሰሉና ሌሎችም ፊልሞችን ዐይቻለሁ፤ እንደ Till death ዐይነት ወይን ጠጡ፤ በስካር ናውዘው ሲነሱ፣ ራስ ምታትቷ ላይ ደም የሌላው  ድንጋጤ ተደፋባት፤ እሱ ራሱን ይገድላል፤ በሞቱና በሞቱ አምሳያ ጥግ ያንን ልዩነት ነበረው። የሚል ጥያቄ ይነሳል፤ እርግጥ ነፍሷ ባፏ ሊወጣ ምንም አልቀረው፤ ቀለም ዐልቦ፣ የጥፍር ቀለም (ጥፍረ መጥምጥ የራቀው) የሰማይ ማማ ሲጫናት አድባር ሲርቃት ግን ሁለቱም ጭጋግ ይፈራሉ፣ ጉሙን ይሸሻሉ፤ ጅማሮአቸውን ግን ጭጋግ ነው፣ ማብቂያቸውም ጭጋግ በጭጋግ ጀምሮ በጭጋግ ያበቃል።
“*ሸለቆውን ተሻግሮ ያለው እጅጉን የተለየ ነው። ክብደትም ሚዛንም የለም፤ ከአፍቃሪሽ ጋር ትሆኛለሽ የኔ ፍቅር! በሕዋው ውስጥ የናኘሽ የፍቅር ጠረን፣ ለኔ የተዘረጋቹ ክንፎች እስኪ ንገሪኝ በልቤ ጸጥታ አንሾካሽኪሊኝ፤ አንቺም እንደ እኔ ትፈልጊኛለሽ፤ ከእኔስ መለያየት ሕመም ነው። ለአንቺ  እኔስ እራሴ በሕዋው የተስፋፋው መአዛና ክንፎች እሆን! የወንድሙ ቢጤ በሌላ አለም፣ ከሕይወት ወደ ሞት ጠርቶሽ ግን ተዐምር የሚሉት እህት፣ ጓደኞችሽ አሉ እንዴ፤ እጥፍ ጭካኔ በሃሴት ውስጥ የሚፈፀም” እስኪ ንገሪኝ?” ይህ ዘላለም የሚከተላት ፍቅራዊ ቃላት ተውሶ የጻፈላት፣ በወይን ያወራረደችው ደብዳቤ ነው።
ይህንን በሰመመን እያሰብኩ፣ ዐፎች ሲነቃነቁ ለጆሮ እረፍት የሚያስናፍቅ ቀጭን የማያቋርጥ ድምጽ የሚያወጣ ባዶነት ሲሰማኝ። ነጭ ሱሪ ልልበስ...? በጎዳናው ላይ እንደ ቀበጥ ሕጻን  ዝናብ... ያረስርሰኝ? ከአጠገቧ ቆሜ ጠያይም ፎቶዎችን ልነሳ እንጃ!
(*Khalil gibran)
አሁን ንገሪኝ፣ ይኖር ይሆን የክፋት መንትያ!

Read 1701 times