Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 08 September 2012 11:19

መሃመድ እና አበባ ዳይመንድ ሊግን አሸነፉ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በ2012 የሳምሰንግ ዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ ኢትዮጵያውያኖቹ አትሌቶች መሃመድ አማን በ800 ሜትር ፤ አበባ አረጋዊ በ1500 ሜትር አሸናፊ ሆኑ፡፡ መሃመድ እና አበባ ከሳምንት በፊት ዙሪክ ላይ በተካሄደ  ውድድር ላይ በተሳተፉባቸው ርቀቶች በአንደኛነት ደረጃዎቻቸውን በመምራት አሸናፊነታቸውን በማረጋገጥ እያንዳንዳቸው የዳይመንድ ሊግ ዋንጫ እና የ40ሺ ዶላር ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ ሁለቱ አትሌቶች ከወር በፊት ተካሂዶ በነበረው 30ኛው የለንደን ኦሎምፒያድ በተሳተፉባቸው የመካከለኛ ርቀት ውድድሮች የነበራቸውን የሜዳልያ ተስፋ ማሳካት ባይችሉም በዳይመንድ ሊግ ያገኙት ስኬት አካክሷቸዋል፡፡አትሌት መሃመድ አማን በ800 ሜትር የ2012 ዳይመንድ ሊግ ውድድር በ14 ነጥብ ሊያሸንፍ የበቃው ዙሪክ ላይ በተካሄደ ውድድር በርቀቱ የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆነውና ሪከርዱን የያዘውን ኬንያዊ አትሌት ዴቪድ ሩዲሻን በምርጥ የአጨራረስ ብቃት በመርታት መሆኑ አድናቆት አትርፎለታል፡፡

በውድድሩ ላይ መሃመድ አማን ዴቪድ ሩዲሻን በመቅደም ሲያሸንፍ ያስመዘገበው 1 ደቂቃ ከ42.53 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜ በርቀቱ የኢትዮጵያ አዲስ ሪኮርድ ሆኗል፡፡ ዘንድሮ በ800ሜ የዓለም የቤት ውስጥ ውድድር ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው እና በ30ኛው የለንደን ኦሎምፒያድ 6ኛ ደረጃ ያገኘው አትሌት መሃመድ አማን የርቀቱ ንጉስ የሚባለው ዴቪድ ሩዲሻ ባለፉት ሁለት አመታት ለሁለት ጊዜያት ማሸነፉ በተለያዩ የዓለም ሚዲያዎች ከፍተኛ ውዳሴ አትርፎለታል፡፡ በስዊድን ስቶክሆልም እና በስዊዘርላንድ ዙሪክ የተካሄዱ የዳይመንድ ሊግ ውድድሮችን ያሸነፈው መሃመድ አማን በ800ሜትር 1377 ነጥብ በማስመዝገብ በዓለም 2ኛ ደረጃ እንዳለው  ኦልአትሌቲክስ  በድረገፁ አመልክቷል፡፡በሌላ በኩል አትሌት አበባ አረጋዊ በሴቶች 1500ሜትር ዳይመንድ ሊጉን ለማሸነፍ የበቃችው በ22 ነጥብ የደረጃ ፉክክሩን በመምራት ሲሆን ዙሪክ ላይ በተደረገው ርቀቱን በ4 ደቂቃ ከ05.29 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር፡፡በዳይመንድ ሊጉ በጣሊያን ሮም ፤በኖርዌይ ኦስሎና በስዊዘርላንድ ዙሪክ  የተካሄዱ 3 ውድድሮችን ያሸነፈችው አበባ አረጋዊ ኦል አትሌቲክስ በድረገፁ በሰራው አሃዛዊ መረጃ በ1500ሜ ሴቶች በ1359 ነጥብ ከዓለም 1ኛ ደረጃ ይዛለች፡፡በዶሃ ከተማ ኳታር ውስጥ ተጀምሮ ትናንት በቤልጅዬም መዲና ብራስልስ የሚጠናቀቀው ዳይመንድ ሊጉ ዘንድሮ ለ3ኛ ግዜ ሲካሄድ በ14 ከተሞች 32 ውድድሮች በተለያዩ የስፖርት መደቦች ተካሂደውበታል፡፡

 

 

 

Read 2687 times Last modified on Saturday, 08 September 2012 11:22