Sunday, 24 October 2021 00:00

ከፌስቡክ ገጾች በጨረፍታ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 ከትናንቱ ስህተት ምን ያህል ተምረናል?
                                 ሙሼ ሰሙ


            ከ5 በላይ ትልልቅ ስታዲየሞችና ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በርካታ ኳስ ሜዳዎችን ያስገነባችው ኢትዮጵያ፣ አንዱም ስታዲየሟ ደረጃውን የጠበቀ ስላልሆነ፣ ብሔራዊ ቡድናችን ጨዋታውን ከኢትዮጵያ ውጭ እንዲያደርግ መወሰኑን ከስፖርት ዞን አነበብኩ። ክስተቱ ለስፖርት ማህበረሰብም ሆነ ለሀገር ሀዘንና ውርደት መሆኑ ግልጽ ነው። ይህ ለምን ሊሆን ቻለ?!
አደይ አበባ ስታዲየም በጊዜ አልተጠናቀቀም!
ባህር ዳር መስፈርቱን አላሟላም!
ሀዋሳ ስታዲየም በሜዳው ብልሹነት ስራ አቁሟል!
ድሬዳዋ ከዓለም አቀፍ መስፈርት በታች ነው
አበበ ቢቂላ የመጫወቻ ሜዳ ከደረጃ በታች ነው
አዲስ አበባ ስታዲየም በእድሳት ላይ ነው (መረጃ፡- ስፖርት ዞን)
በቢሊየኖች ወጭ ተደርጎባቸው የተገነቡ ስታዲየሞቻችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ውድድር ማሰናዳት የማይችሉ እንደሆኑ ካፍ ባደረገው ፍተሻ ስላረጋገጠ፣ ጨዋታችንም በሌላ ሀገር እንዲሆን ተገደናል።
ሜዳዎቹ ደረጃቸውን የጠበቁ ለማድረግም ከመነሻቸው በላይ ወጭ እንደሚፈልጉ ተገምቷል።  ያለፈው ስርዓት የልማት ትርክቱ የተዘጋ በር ገርበብ ባለና መጋረጃው በተጋለጠ ቁጥር ኢትዮጵያ እንደ ሀገር የወረደባት የዘረፋ መዓት ህልቆ መሳፍርት የሌለው መሆኑ አሳዛኝ ነው። በእልፍ ፕሮጀክቶች መነሻነት በሀገራችንና በሕዝቧ ስም እያናጠረብን ያለው የውጭ ሀገር ብድር፣ ቀጣዩ ትውልድ እንኳን ለዝንተ ዓለም ከፍሎ የሚጨርሰው አይደለም።
በየዘርፉ ያለው ጉድ መጨረሻው ይናፍቃል። ያልተዘረፈ፣ ከደረጃ በታች ያልሆነ፣ ተጀምሮ መቋጫ ያላጣ፣ ባለቤቱ የማይታወቅና ቀሪ ሀብቱ የት እንደገባ የማይነገርለት ፕሮጀክት የትየለሌ ነው። የትናንቱ ልማት በአብዛኛው ላዩ እንጂ ውስጡ ቀፎ እንደነበር በተደጋጋሚ ታይቷል። ዛሬስ ልማቱ የት ደርሷል? ወዴትስ እየተገፋ ነው?! ከትናንቱ ስህተትስ ምን ያህል ተምረናል? አሁንም ጥያቄው ይህ መሆን አለበት!?





Read 1724 times