በኢንተርኔት የቀጥታ ስርጭት ከ20ሺ በላይ ተመልካቾች እንደሚታደሙ ይጠበቃል
ዛዮን ሬጌ የተሰኘ የሬጌ ሙዚቃ ኮንሰርት ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ቦሌ በሚገኘው ፋና ፓርክ ይካሄዳል፡፡
በኮንሰርቱ ላይ የሬጌ ሙዚቃ አቀንቃኞቹ ጆኒ ራጋ፤ ስታቲክ ሊቫይ፤ ቤንጃሚን ቢትስ፤ ግደይ እና ሊሊ ስራቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን ዲጄ ኪንግ ዳርዮስም ታዳሚውን ያዝናናል ተብሏል። የመግቢያው ዋጋ 300 ብር ሲሆን በመላው ዓለም በቀጥታ የኢንተርኔት ስርጭት ለሚታደሙ ቨርችዋል ትኬቶች ለሽያጭ መቅረባቸው ተገልጿል፡፡ “ከሴ ኢቨንትስ” የሚል ልዩ የኢንተርኔት መተግበርያ መፈጠሩን ለአዲስ አድማስ የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ በኢንተርኔት ቀጥታ ስርጭት ለሚታደሙት የትኬት ዋጋ 5 ዶላር ወይም 100 ብር መሆኑንም ገልፀዋል፡፡ ኮንሰርቱን ከ20ሺ በላይ ተመልካች በኢንተርኔት ቀጥታ ስርጭት ይታደሙበታል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ሙሉ ገቢውን በጥቁር አንበሳ ለሚገኘው የኢትዮጰያ ህጻናት ልብ ህሙማን ማዕከል ለማበርከት መታሰቡም ታውቋል።
“ከሴ ኢቨንትስ” በየወሩ ተመሳሳይ ኮንሰርቶችን ለማካሄድ ማቀዱን የገለፀ ሲሆን፤ በአገር ውስጥ በብዙ እንቅስቃሴያቸው የሚታወቁ የሬጌ ሙዚቀኞች ተሰጥኦዋቸውን፤ አገራቸውን፤ ባህላቸውን እንዲያስተዋውቁ ይፈልጋል፡፡ በቀጣይ በአፍሪካ ደረጃ የኬንያ፤ የናይጄርያ እና ሌሎች ሬጌ ሙዚቀኞችን የሚያሳትፉ ዝግጅቶች ይኖራሉ፡፡
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና