የትዊተርና ፌስቡክ አካውንታቸው የተዘጋባቸውና በዚህም እልህ የተጋቡት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ከሰሞኑ ትሩዝ ሶሻል የተባለ ማህበራዊ ድረገጽ አፕሊኬሽን የከፈቱ ሲሆን፣ በከፍተኛ ሁኔታ ተወዳጅ የሆነው ይህ አፕሊኬሽን ይፋ በተደረገበት ዕለት ብቻ ከ170 ሺህ ጊዜ በላይ ዳውንሎድ መደረጉ ተነግሯል፡፡
ትራምፕ ባለፈው እሁድ ምሽት በሰጡት መግለጫ፤ ትራምፕ ሚዲያ ኤንድ ቴክኖሎጂ ግሩፕ የተባለ አዲስ ኩባንያ በማቋቋም ትሩዝ ሶሻል የተሰኘ ማህበራዊ አፕሊኬሽን ያስተዋወቁ ሲሆን፣ እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተመዝጋቢዎች እውቅና ለማግኘት ወረፋ በመጠበቅ ላይ መሆናቸውን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
ትሩዝ ሶሻል ከትዊተር ጋር ተመሳሳይነት ያለውና የተለያዩ መረጃዎችን ለማጋራት የሚል አፕሊኬሽን እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ በአሜሪካ ዳውንሎድ እንዲደረግ በአፕል አፕ ስቶር ላይ መጫኑንም አመልክቷል፡፡
ትራምፕ ባለፈው አመት ጥር ወር ላይ በዋሽንግተን ዲሲው ካፒቶል ሂል ላይ ከተፈጸመው ጥቃት ጋር በተያያዘ የትዊተር፣ የፌስቡክ እና የዩቲዩብ ገጻቸው እንደታገደባቸውም ዘገባው አስታውሷል፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ