ማንምን ከለመድሽ
ለእኔ ግድ ካጣሽ
(ካመታት በኋላ መስታወት ፊት ቆሜ)
አንቺን እየፈለኩ
እኔን አየዋለሁ
የምትወጂው አይኔን
ባይንሽ እያየሁት
እብሰለሰላለሁ!
ዛሬማ ደፍርሷል
ብርሃን መርጨት ትቷል
ናፍቆት አሟምቶታል
እንባ አበላሽቶታል
ስል እተክዛለሁ
--
ስብሃት! ለማማሩ
ስብሃት! ለጣዕሙ
ያልሽለት ከንፈሬን
በድድር መዳፌ እየደባበስኩት
ባይንሽ አየዋለሁ
“ሲጃር አጥቁሮታል
ማጣት ሰንጥቆታል. . .”
ስትይ እሰማለሁ
አብዝቼ አለቅሳለሁ
--
የማይቻል ሰጥቶት
ያላቅሙ አሸክሞት
የጎበጠ ጫንቃዬን
የምትወጂው ትከሻዬን
በመስታወቱ ውስጥ ባይንሽ አየው እና
“ይሄስ ኮስማና ነው!” ስትይ እሰማለሁ
ወዮ ለእኔ እላለሁ።
--
እምወዳት እኔ እንጂ ምትወዳቸው
የሉም
ስለዚህ አትመጣም
ብትመጣም አትቆይም
የሚል ድምፅ እሰማለሁ
እነፈርቃለሁ
ወዮ ለእኔ እላለሁ።
ናሆም አየለ
Published in
የግጥም ጥግ