Saturday, 16 April 2022 15:28

የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት አስተዳደራዊ ታሪክ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   መግቢያ
ኢትዮጵያ በአለም ላይ ከሚገኙ ጥቂት የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት ሀገራት ውስጥ አንዷ መሆኗ እውን ነው። የረጅም ዘመን የስልጣኔ ባለቤት እንደመሆንዋ መጠን የረጅም ዘመን የሀገረ-መንግስትና አስተዳደራዊ ታሪክ ያላት መሆንዋንም መገንዘብ ያሻል። እንደሚታወቀው የሀገረ-መንግስት ምስረታውና የመንግስታዊ አስተዳደር መነሻው የአክሱም ዘመን በመሆኑ የአስተዳደር ወሰን የራሱ የሆነ ታሪክ ነበረው። በታሪክ አጋጣሚ ጎረቤት የሆኑት የትግራይና የሰሜን-በጌምድር የግዛት አስተዳደር የአካባቢን መልክዓ-ምድር፣ ተመሳሳይ ቋንቋና የዘር ሐረግ ያላቸውን ህዝቦች የሰፈሩበትን ቦታ መሰረት ያደረገ እንደነበር የታሪክ ማስረጃዎችና መረጃዎች ያሳያሉ።
የዚህ ምዕራፍ ዋና ዓላማ በረጅሙ የኢትዮጵያ የሀገረ-መንግስትና የአስተዳደር ታሪክ ውስጥ የወልቃይት፣ጠገዴና የጠለምት አካባቢዎች የግዛት አስተዳደር ምን ይመስል እንደነበር ማሳየት ነው። አፃፃፍና ትንታኔውም የታሪክ ሀቅ ላይ የተመሰረተና በመረጃ የተደገፈ ነው።
2.1 ወልቃይት፣ጠገዴና ጠለምት
የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት ህዝብ በኢትዮጵያ ታሪክ ወስጥ በተለይ በሀገረ-መንግስት ግንባታ፣ በዳር ድንበርና ወሰን ጥበቃ ላይ የጎላ ድርሻ እንደነበረው በርካታ የታሪክ ማስረጃዎች ያሳያሉ። የዚህ ምዕራፍ ዋና ዓላማ የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት ህዝብ በሀገረ-መንግስት ግንባታ፣ በዳር ድንበርና ወሰን ጥበቃ የነበራቸውን ሚና ማሳየት ባይሆንም፣ ከ1983 ዓ.ም በኋላ በአካባቢው ላይ ለተነሳው የማንነት ጥያቄና ህወሓት በአማራ ተወላጆች ላይ የፈፀመውን እልቂት ለመረዳት ይጠቅማል።
2.1.1 በአክሱም ዘመነ መንግስት
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የብዙ ጉዳዮች መነሻ የአክሱም ዘመን ነው። በአክሱም የሀገረ-መንግስት የአስተዳደር ታሪክ ውስጥ የ14ኛው እና የ15ኛው ክፍለ ዘመን ነገስታት አጼ ኢዛናና አፄ ካሌብ ሰፊ ድርሻ አላቸው። በሁለቱ ነገስታት የታሪክ ሂደት ውስጥ የትግሬና የሰሜን-በጌምድር የወሰንና የግዛት አስተዳደርን በተመለከተ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ወልቃይት፣ጠገዴና ጠለምት በመልክዓ ምድርና በህዝብ አሰፋፈር የተለየ ነበር። ለማዕከላዊ መንግስት (ለአክሱም ነገስታት) ግብር የሚከፍለው የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት አካባቢ የራሱ ማንነት ያለው ህዝብ ሆኖ የግዛት አስተዳደሩም ከትግሬው ግዛት በመልክዓ ምድራዊው አቀማመጥ የተለየ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ለዚሁም በአርኪዮሎጂ ጥናት ላይ  የተመሰረተ የButzer Hunting Ford ጥሩ ምሳሌ ነው። እነኚህ አጥኚዎች  “The Rise and Fail of Axum, Ethiopia: A GeoArchaeological Interpretion” እንደሚያሳዩት፤ የማዕከላዊ መንግስታት ዋና መቀመጫ ከሆነው አክሱም የወልቃይትን የአስተዳደር ግዛት የሚለየው ተከዜ ወንዝ ነው። ይህም ጥንታዊ የኢትዮጵያ የግዛት አስተዳደር በመልክዓ-ምድርና የህዝብ አሰፋፈርን መዋቅር ያደረገ እንደነበር ያስገነዝባል።
በትግሬና በአማራ መካከል የነበረው የአስተዳደር ወሰን ተመሳሳይ ቋንቋና የዘር ሀረግን መሰረት ያደረገ የህዝብ አሰፋፈር ላይ የተዋቀረ እንደነበር መገንዘብ ያሻል። ይህ ሲባል ግን በተለያየ መልክዓ ምድር ላይ የሰፈሩ ህዝቦች አይገናኙም ማለት ግን አይደለም። አንድ ማህበረሰብ በሚኖርበት አካባቢ ጦርነት፣በሽታና ሌላ የተፈጥሮ አደጋ ችግሮች ሲፈጠሩ ወደ ሌላ አካባቢ ፈልሶ የሌላ ማህበረሰብ የአስተዳደር ግዛት ውስጥ ይኖር ነበር። ይህ በጊዜ ሂደት በማህበረሰብ መካከል ትስስርን ፈጥሯል። ይህ የህዝቦች መስተጋብር ግን በትግሬና በአማራ መካከል የየአካባቢዎችን የግዛት አስተዳደር ወሰን አልቀየረውም። ስለዚህ በአክሱም ዘመን በአማራውና በትግሬ ማህበረሰብ አብሮ የመኖር መስተጋብርና ትስስር ቢኖርም፣ የሁለቱ ማህበረሰቦች የአስተዳደር ወሰን የሚለየው የተከዜ ወንዝ እንደሆነ ታሪካዊ ሂደቱ ያስረዳል።
የአክሱም መንግስት በሀገር ውስጥ በተፈጠረው ሽኩቻ እየተዳከመ ሄዶ በመጨረሻ አረቦች ቀይ ባህርን ሲቆጣጠሩ የፍፃሜው ውደቀት ላይ ደረሰ። የአክሱም ዘመን በ8ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ገደማ ሲያከትም ስርወ -መንግስቱ ወደ ላስታ ሮሃ በ1150 አካባቢ ተዛወረ። በላስታ ሮሃ ውስጥም የዛግዌ ስርወ -መንግስት ተመሰረተ። በዚሁ ስርወ መንግስት ዘመንም የወልቃይት፣ጠገዴና ጠለምት የግዛት የአስተዳደር ወሰን መለያ ተከዜ ወንዝ እንደነበር የታሪክ መረጃዎችና ጥናቶች ያሳያሉ። ለምሳሌ ተሰማ ሀብተ ሚካኤል በ1951 ባሳተሙት የአማርኛ መዝገበ ቃላት ላይ እንዲህ ይላል፡- ከአክሱም መንግስት ውድቀት በኋላ ስርወ መንግስት ወደ ላስታ ሮሃ በተዛወረበት ጊዜ ከተከዜ ወንዝ ማዶ የሰሜን ግዛት አስተዳደር ክፍል ነው። በቦታው የሰፈሩትም አማሮች ናቸው ይላል። በተጨማሪም በበርካታ መረጃዎች የተደገፈው የህዝባዊ ታሪክ  ፀሀፊው አቻሜለህ ታምሩ “የወልቃት ጉዳይ” በተሰኘ መፅሐፉ የንጉስ ነአኩቶ ለአብ ገድለ-ታሪክን (Hagiography) ዋቢ አድርጎ እንዳቀረበው፤ የአይሁድ እምነት ተከታይ የሆኑት ፈላሻዎች ለንጉሱ ግብር አንገብርም በማለት በተደጋጋሚ እንደ አመፁ ያስረዳል። ስለዚህ ንጉሱ ግብር ለመሰብሰብ ዘመቻ በሚያደርግበት ጊዜ የአማራውንና የትግሬውን አሰፋፈርና የአስተዳደር ወሰን የሚለየው የተከዜ ወንዝ እንደሆነ ተጠቅሷል።
2.1.2 በዛግዌና በመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ
ኢትዮጵያ ረጅም የሀገረ-መንግስት ታሪክ ያላት ሀገር ብትሆንም፣ የስርዓት ለውጥ ግን ሁሌም በአመፅ የተደገፈ ነበር። ታሪካችን እንደሚያስረዳው፤ የስልጣን ሽኩቻና ግጭት እንደ አሁኑ ዘመን ብሔርን መሰረት ያደረገ አልነበረም። የስልጣን ሽኩቻ (Power Struggle) በዛግዌ ዘመንም ሆነ በመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በጎንደርና በዘመነ መሳፍንት በንጉሳዊያን ቤተሰቦች መካከል ሳይቀር እንደነበር የሚካድ አይደለም። ነገር ግን የስልጣን ሽኩቻ ብሔርንና ቋንቋን መሰረት ያላደረገ በመሆኑ የአስተዳደር ወሰኑ ላይ ለውጥ የለም።
የዛግዌ ዘመን በ1270 ላይ ሲያከትም ስርወ-መንግስቱ (በትረ መንግስቱ)ወደ ሰለሞናውያን እጅ ገባ። የሰለሞናውያን ስርወ-መንግስቱ በ1270 ዳግም ካንሰራራ በኋላ ስማቸው እጅግ በጣም ጎልተው ከሚታወቁት ነገስታት መካከል አምደ ፅዮን አንዱ ናቸው። አፄ አምደ ፅዮን ከሚታወቁበት ባህሪ ውስጥ አንዱ ጠንካራ የግዛት አስተዳደር ነው። ንጉሱ የግዛት ማስፋፋት በሚያደርጉበት ጊዜ የበጌምድርና የሰሜን የትግሬው የግዛት አስተዳደር ወሰን አልቀየሩትም። በቅርቡ ከግዕዝ ወደ አማርኛ በተተረጎመው የአፄ አምደ ፅዮን “ዜና መዋዕል” ላይ የወልቃይት፣ ጠገዴና የጠለምት የአስተዳደር ወሰን (ግዛት) ከእሳቸው በፊት ይገዙ የነበሩትን ነገስታት ይመስል እንደነበር ያስረዳል። ዜና መዋዕሉ የንጉሰ ነገስቱን  ግዛቶች በተከዜ፣ በበሽሎ፣ በአዋሽና፣ በአባይ ወንዞች የተከለሉ መሆኑን ያስገነዝባል። የትግሬና የአማራውን የአስተዳደር ወሰን የሚለየውም የተከዜ ወንዝ እንደሆነ በግልፅ ያስቀምጣል።
የኢትዮጵያን የውስጥ አስተዳደር የግዛት ወሰን በተመለከተ የውጭ ሀገር ጎብኝዎችና የሀይማኖት ሰባክያን የተመለከቱትንና የተገነዘቡትን ከትበው አልፈዋል። ከነገስታት በተሰጣቸው የስጦታ  መፅሐፍ ውስጥ (ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ ሀገር በውጭ ሀገር ጎብኝዎችና በሀይማኖት ሰባክያን በተወሰደው) የአስተዳደር ወሰንን ታሪክ እናገኘዋለን። ለዚሁ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው የትግሬው ገዥ ራስ ልስሁል ሚካኤል፣ ለጀምስ ብሩክ ያበረከቱት “መፅሐፈ አክሱም” የተሰኘው ታሪካዊ ሰነድ ነው። ይህ መፅሐፍ ወልቃይት ጠገዴና ጠለምትና ሁመራ በትግሬው ግዛት ውስጥ ያልነበሩ መሆኑን ያስገነዝባል።
በ15ኛው እና በ16ኛው ክፍለ ዘመን እነዚህ የትግሬው የግዛት አስተዳደር ክፍል እንዳልነበሩ ያስገነዝባል። በየትኛውም የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ወልቃይት ጠገዴና ጠለምት የትግሬ ግዛት እንደነበሩ የሚያሳይ መረጃ የለም። ከእሳቸው በፊት እንደነበሩት ነገስታት ሁሉ በአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመንም እነዚህ አካባቢዎች የሰሜን በጌምድር የአስተዳደር ግዛት ክፍል ነበሩ። በአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን በአክሱም ንቡረ-ዕድ የተፃፈው “መፅሐፈ አክሱም” የተሰኘው (በጀምስ ብሩስና በፈረንሳይ አርኖል ዲአባዲ አማካኝነት ወደ አውሮፓ በተወሰደው ዶክመንት እንደሚገለፀው፤ ወልቃይት፣ ጠገዴና፣ ጠለምት የትግሬው የአስተዳደር ክፍል አልነበሩም።
በተመሳሳይ መልኩ ዮሐንስ መኮነን “Ethiopia The Land and Its People, History and Culture”   እና John R.S “The World Through Maps: A History of Cartography” ላይ ከተዘረዘሩት የትግራይ የግዛት አስተዳደር ውስጥ ወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት የሉም። እነዚህ ሁለቱ የጥናት ውጤቶች እንደሚያሳዩት፤ በ15ኛው ክፍለ ዘመን የትግሬ ግዛቶች ተምቤን፣ ሽሬ፣ ስራየ፣ሀማሴን፣ ቡር፣ ሳማ፣ አጋሜ፣ አምባ ሰናይት፣ ገርአልታ፣ እንደርታና ሰሐራት ናቸው።
ፍራንሲስኮ አልባሬዝ የተባለ ፖርቱጋላዊ የካቶሊክ እምነት ተከታይ፣ በኢትዮጵያ በተለይ በኤርትራ ትግሬና በጌምድር ለ7 ዓመት ከ1520-1527 እንደቆየ ይታወቃል። አልባሬዝ የመጣበት ዋናው ተልኮ የካቶሊክ እምነትን በድብቅ ለመስበክ ቢሆንም፣ የአካባቢውን መልክዓ ምድር ሁኔታ፣ የግዛት አስተዳደርና የህዝብ አሰፋፈርን በማስታወሻው ከትቧል። በጊዜው የነበረውን የግዛት አስተዳደር ሲገልፅ፤ በጌምድር በኢትዮጵያ ከሚገኙት የአስተዳደር ግዛቶች ውስጥ በጣም ትልቁ ነው ይላል። የበጌምድር ግዛት በኤርትራና በጎጃም መካከል ይገኛል በማለት ገልፆታል። በሌላ አገላለፅ የበጌምድር ግዛት ከጎጃም ቀጥሎ የሚገኝ ሲሆን እስከ ባህር ነጋሽ (ኤርትራ) ድረስ 3.2 ማይል ርቀት ይዘልቃል ሲል አስቀምጦታል። ይህም የሚያሳየው የተከዜን ወንዝ ተከትሎ ወደ ምዕራቡ አቅጣጫ የወንዙ ተፈጥሮአዊ ተፋሰስ የኤርትራ ግዛት የሆነውን “አም ሀጀር” የሚያዋስን መሆኑን ነው።--
("የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት የታፈኑ እውነታዎች" ከተሰኘው መጽሐፍ የተቀነጨበ፤ታህሳስ 2014 ዓ.ም)



Read 2226 times