Saturday, 20 October 2012 12:32

ESOG - በ-FIGO ለሁለት የስራ ኃላፊነት ታጨ

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(2 votes)

“...በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ያለው የእናቶች ሞት መጠን ቁጥር ከፍ ያለ ነው ማለት ይቻላል፡፡ መሰረታዊው ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ዜሮ ከሚባለው ደረጃ ማድረስ ባይቻልም እንኩዋን ለውጥ በማምጣት የሞት መጠኑን መቀነስ ስላለብን ጠንክረን መስራራት ይጠበቅብናል ...”
ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የኢሶግ ፕሬዝዳንት አለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር FIGO በኢጣሊያ ሮም ከተማ ለ20ኛ ጊዜ አለምአቀፋዊ ስብሰባውን አካሂዶአል፡፡ ፊጎ በየሶስት አመቱ የሚያካሂደውን ኮንፍረንስ ለ20ኛ ጊዜ ሲያካሂድ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አመራራር አካላትና የቦርድአባላት ተሳትፈው ነበር፡፡

ከኦክቶቨር 7-12/20012 በተሄካደው ስብሰባ የ FIGO አባላት በሆኑ /125/አንድ መቶ ሀያ አምስት በሚደርሱ ሐገራት ባሉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበራት መካከል በተደረገ ውድድር አሸናፊ በመሆን የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ለአፍሪካ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር የቦርድ ፕሬዝዳንትና ለአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር የቦርድ አባል እንዲሆን ተወስኖአል፡፡
የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሰላማዊት ክፍሌ እንደገለጹት በአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ድጋፍ የሚንቀሳቀሱ ማህበራት በላቲን አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ ሰሜን አሜሪን...ወዘተ በአህጉር ደረጃ የተወከሉ ቢሮዎች የነበሩአቸው ሲሆነ በአፍሪካ ግን ማህበራቱን የሚወክል ቢሮ አልተቋቋመም ነበር፡፡ በ20ኛው አለም አቀፍ ስብሰባ አንዱ አጀንዳ የነበረው የአፍሪካን የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ማቋቋም ስለነበር የውድድሩ ውጤት ይህ ቢሮ መቀመጫውን በሱዳን እንዲያደርግና በቦርድ ፕሬዝዳንትነትም ከኢትዮጵያ ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት እንዲመሩት አስችሎአል፡፡
አለም አቀፉን የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በቦርድ አባልነት የሚመሩ ማህበራትን በ125/ አገራት ከሚገኙ የጽንስና ማህጸን ማህበራት ውስጥ በማወዳደር ለስድስት አመት ያህል የቦርድ አባል በመሆን የማገልገል ኃላፊነትን በሚመለከትም በተደረገው ውድድር ከተመረጡት አስር ማህበራት መካከል የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አንዱ ሲሆን በቦርድ አባልነቱም የኢሶግ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት እንደሚሰሩ ስራ አስኪያጅዋ ገልጸዋል፡፡
አቶ ብሩክ ተ/ስላሴ በኢሶግ የፊጎ ሎጂክ ኢንሼቲቭ የእናቶችና ጨቅላ ሕጻናት ጤና ፕሮጀክት አስተባባሪ እንደሚገልጹት ..የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር (ESOG) ከአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር (FIGO) Òር በመተባበር የእናቶችና ሕጻናት ጤንነትን በመጠበቅ ረገድ ፕሮጀክት ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ኢሶግ በተለያዩ መስተዳድሮች አስፈላጊውን ነገር ለማስረጽና ለውጥ ለማምጣት በመስራት ላይ ነው፡፡ በኢትዮጵያ የእናቶችን ሞት በመቀነስ ረገድ ከሚሰራው ስራ አንዱ በአራት ክልሎች ማለትም በአዲስ አበባ ሁለት ሆስፒታሎች በየካቲትና ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታሎች በአማራ ክልል ደብረማርቆስና ደብረብርሀን ፣በደቡብ ደግሞ ቡታጅራ ዱራሜና ሐዋሳ ሆስፒታሎች እንዲሁም በኦሮሚያ በቢሾፍቱ እና አሰላ ሆስፒታሎች ላይ ዳሰሳው በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ በእነዚህ ክልሎች ቅድሚያ ትግበራው ሲካሄድ ቀጣይ ስራውን ደግሞ ሌሎች በዚህ ፕሮጀክት ያልታቀፉት እንደ አንድ ምርጥ ስራ አምነው እንዲሳተፉበት እና ስራው በአገር አቀፍ ደረጃ ውጤታማ እንዲሆን ጥረት እየተደረገ ነው፡፡ ..
የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በሚደረግለት ድጋፍ ከሚያከናውናቸው ተግባራት በተለይም የእናቶችን ሞት ከመቀነስ አኩዋያ እናቶች በምን ምክንያት ይሞታሉ የሚለውን ለማወቅ አብሮአቸው ከሚሰራባቸው የጤና ማእከላት መካከል ቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ አንዱ ሲሆን ከሆስፒታሉ የጽንስና ማህጸን ሐኪም የሆኑት ዶ/ር ማለደ ቢራራ እንደገለጹት ለእናቶች ሞት በምክንያትት የሚጠቀሱ ሶስት መዘግየቶች አሉ፡፡ እነርሱም...እናቶች...
ወደ ጤና ተቋም መሄድ እንደሚገባቸው አለማወቃቸው
ወደ ጤና ተቋም መሄድ እንዳለባቸው ቢያውቁም ለመሄድ አለመቻላቸው እና
ወደ ጤና ተቋም ቢሄዱም ተገቢውን ሕክምና ማግኘት አለመቻላቸው... ናቸው፡፡
ስለዚህ በእነዚህ ምክንያቶች ጤናቸው የሚጎዳ ብሎም ለህልፈት የሚዳረጉ እናቶች መኖራቸው እሙን ነው፡፡ እናቶች ለምን ከጉዳት ላይ እንደሚ ወድቁ የሚታወቅ ነገር ያለ ሲሆን ከዚህም በብዛት በወሊድ ጊዜ ከፍተኛ የሆነ የደም መፍሰስ እንዲ ሁም በእርግዝና ጊዜ የሚከሰት የደም ግፊት ፣ የኢንፌክሽን እና ሌሎች ሁኔታዎች እንደነበሩ ይታመናል፡፡በእርግጥ አሁን በአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር FIGO እና በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ትብብር የተጀመረው የእናቶችን ሞት ምክንያትን የማወቅ ስራ ለእናቶች ሞት ምክንያት ምንድናቸው የሚለውን ከመለየት አንጻር በሚሰራው ስራ ስንት እናቶች በምን ምክንያት እንደሚሞቱ ግልጽ የሆነ መረጃ እየተገኘ ሲሆን የህክምና ባለሙያው እናቶችን ለማዳን የሚያስችለው እር ምጃ ምን እንደሆነ መገመት የሚያስችለው አካሄድ ነው፡፡ ..ብለዋል፡፡
ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር የእናቶች ጤና አማካሪ በአንድ ወቅት ለጋዜጣው ሪፖርተር እንደገለጹት በኢትዮጵያ እንደውጭው አቆጣጠር በ2000 ዓ/ም የእናቶች ሞት ቁጥር ከ100000 አንድ መቶ ሺህ 871 ስምንት መቶ ሰባ አንድ ያህል ሲሆን በ2005 በተደረገው ጥናት ደግሞ ከአንድ መቶ ሺህ እናቶች ወደ 673 ስድስት መቶ ሰባ ሶስት ያህሉ በአንድ አመት ጊዜ እንደሚሞቱ ተረጋግጦአል፡፡ ይህም ቁጥር በታዳጊ አገሮች ከተመዘገበው ከፍተኛው መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በሚሊኒየሙ የልማት ግብ እቅድ መሰረት የእናቶች ሞት እንደውጭው አቆጣጠር ከ1990-2015 ድረስ ከነበረበት በ75 ኀ እንዲቀንስ ይጠበቃል፡፡ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ደግሞ እናቶች ከእርግዝና በፊት፣ በእርግዝና ጊዜ እንዲሁም በወሊድ ወቅትና ከወሊድ በሁዋላ የተሟላ ህክምና እንዲያገኙ ማድረግ ተገቢው እርምጃ ነው፡፡ዶ/ር ታደሰ ከተማ እንደገለጹት ከሆነ የእናቶች ጤና መጠበቅ ሲባል የቅድመ ወሊድ የህክምና ክትትል፣ ከአረገዙ በሁዋላ የህክምና ክትትል፣ የማዋለድ አገልግሎት እና ከወለዱ በሁዋላ የሚሰጥ አገልግሎት ፣ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚሰጠውን አገልግሎት (PMTCT) ይጨምራል፡፡ የኢትዮጵያ ጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበርና ሌሎች የሚመለከታቸው ሁሉ የእናቶችን ሞት ከመቀነስ አኩዋያ ተገቢውን ማድረግ ጠበቅባቸዋል ብለዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ፡፡
የአፍሪካ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ፕሬዝዳንት፣ የአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ቦርድ አባልና የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ፕሬዝዳንት ረዳት ፕሮፌሰር ዶ/ር ርጉ ገ/ሕይወት እንደገለጹት...
.... ከ FIGO ጋር በመተባበር በአገራችን ከዘጠኝ ሆስፒታሎችና ከ45 ጤና ጣቢያዎች ጋር የተዘረጋው ፕሮጀክት የሚያተኩረው በእናቶችና ሕጻናት ጤና ላይ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ዋና አላማ በኢትዮጵያ ውስጥ የእናቶች ጤንነት የሚሻሻልበትን... የእናቶች ሞት የሚቀንስበትን አሰራር መከተል ነው፡፡ ይህንን በሚመለከት ስራው ከሚመለከታቸው እና አግባብ ካላቸው አካላት ጋር አብሮ በመስራት እናቶች የሚያገኙትን አገልግሎት የተሻለ ማድረግ እና ድምር ውጤቱም አመርቂ እንዲሆን ማድረግ ይቻላል፡፡..
ወ/ሮ ሰላማዊት ክፍሌ የኢሶግ ዋና ስራ አስኪያጅ እንዳከሉት ዘንድሮ በኢጣልያ ሮም ከተማ የተካሄደው ስብሰባ ሁለት መልክ ያለው ሲሆን አንዱ አመታዊ ግምገማ ሁለተኛው ደግሞ አለም አቀፉ ማህበር በየሶስት አመቱ የሚያደርገው ስብሰባ ነበር፡፡ በየአመቱ የሚደረገው ስብሰባ ስድስት የአፍሪካ አገራትንናኢትዮጵያን ጨምሮ ሁለት የእስያ አገራትን የሚመለከት ነበር፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይ በአመቱ የተሰሩ ስራዎችን እና ያጋጠሙ ችግሮችን እንዲሁም ለወደፊት ምን ታቅዶአል የሚለው በመድረክ ላይ የተንጸባረቀ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በተንቀሳቀሰባቸው የስራ መስኮች የነበሩ እውነታዎችን በጥናታዊ ስራና በስእላዊ መግለጫ ለመድረኩ አቅርቦአል፡፡
በአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ስብሰባ ላይ ከቀረበው የተጠናከረ መረጃ በመነሳት በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አማካኝነት የእናቶችና ጨቅላ ሕጻናትን ጤና በማረጋገጡ ረገድ የተሰሩ ስራዎችን ጥንካሬ በጉልህ ያሳየ በመሆኑ ማህበሩ በሌሎች የ FIGO አባላት ከፍ ያለ ግምት እንዲሰጠውና ለውድድር እንዲበቃና ከፍ ላሉ ስራዎች በኃላፊነት እንዲታጭ አስችሎታል እንደ ወ/ሮ ሰላማዊት ክፍሌ ማብራሪያ፡፡
ኢትዮጵያ የአፍሪካ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ፕሬዝዳንትና የአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ቦርድ አባል ሆና መመረጧ እስከአሁን ድረስ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በመሰራት ላይ ያለውን የእናቶችንና የጨቅላ ሕጻናትን ጤና መጠበቅ ይበልጥ አጠናክሮ ለመጉዋዝ እንደሚረዳ አያጠራጥርም ብለዋል የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሰላማዊት ክፍሌ፡፡

Read 3042 times Last modified on Saturday, 20 October 2012 12:39