Saturday, 27 October 2012 09:51

ይድረስ ለታሪክየቀይ መስቀል ማህበር የተደናበረ ጉዞ Featured

Written by  እውነቱ ተሻለ
Rate this item
(4 votes)

ጥሎብኝ ቀይ መስቀልን እወዳለሁ፡፡ ሰብዓዊነትን አንግቦ የተነሳ የሰላም፤ የፍትህ፤ የዕኩልነትና የጋራ መተሳሰብን አየር የሚተነፍስ፤ በዘር፤ በቀለም፤ በፖለቲካ ልዩነት የማያምንና እንዲኖርም የማይፈልግ መሆኑን በዓለምአቀፋዊነት ኮሮጆ አቅፎ መለያውን የቀይ መስቀል ባንዲራ የሚያወለበልብ በመሆኑ ደስ ይለኛል፡፡ ከሁሉም ማሕበራት በላይ አድርጌ እመለከተዋለሁ፡፡
በእርግጥም ከሁሉም በላይ ነው፡፡ የተቋቋመው በመንግሥት ለብቻው በወጣ ቻርተር ነው፡፡ አገራዊ ሆኖ የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ማሕበር አባል ነው፡፡ የአገሪቱ ርዕሰ ብሔር ክቡር አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስም የማሕበሩ የበላይ ጠባቂ ናቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ሰብዓዊነት ተልዕኮ ያለው ብቸኛ ድርጅት ነው ፡፡ ታዲያ ለምን የበላይ አይሆን!

 

በመሆኑም፤ ከቀይ መስቀል ማሕበር ጋር ከሁለት ዓሥርት ዓመታት በላይ በሠራተኝነትና በአባልነት ቆይቻለሁ፡፡ በቆይታዬም ዘምሬለታለሁ፤ ገጥሜለታለሁ፤ በየጊዜው የታዘብኩትን ከጓደኞቼና ከወዳጆቼ እንዲሁም ከቀይ መስቀል ማሕበር ጥቂት ቤተሰቦች ጋር በየጊዜው ተወያይቻለሁ:: እርር ድብን የሚያደርጉ ሁኔታዎችን ታዝቤያለሁ፤ ፍርሀት ቀፍድዶ ስለያዘኝና በሌላም በኩል “ማን ሊሰማ” በሚል አባዜ ተጀቡኜ እውነትን ለማውጣት ሳልሞክር ኖሬያለሁ፡፡ ዛሬም ፈራ ተባ እያልኩ ብዕሬን አሹሌ በነጭ ወረቀት ላይ ስተክል ሳነሳ ሰነባበትኩና፣ ዛሬስ ይውጣልኝ በሚል እንደጀግንነት ብጤ ተሰማኝና ይህችን መጣጥፍ ላቀርብ ወሰንኩ፡፡ ደፍሬም ቢሆን ገና ብዙ ሚስጥሮችን አላወጣሁም፡፡ ግን አይን ገላጭ ትሆናለች ብየ ነው፡፡ ጉዳዩ የአንድ ማሕበር ብቻ ሳይሆን የአገር ነውና፡፡
ለዚህ መጣጥፍ ምክንያት የሆነኝ በአዲስ አበባ ቀይ መስቀል ማሕበር ቅ/{/ቤት ተከሰተ ስለተባለው የቦርድ አባላት አለመግባባትን ተመልክቶ ስለተነሳ ጉዳይና በዚሁ ላይ ስለተደረገ እንቅስቃሴና የስብሰባ አካሄድና ውጤት ነው፡፡ ወዳጅ አይጥፋና በመኖሪያ አካባቢዬ ካለው የቀይ መስቀል ን/ቅ/{/ቤትና ከብሔራዊ {/ቤት ችግሩን በተመለከተ የተÚፉ ደብዳቤዎች በእጄ ገብተዋል፡፡ በተመስጦ ስከታተላቸው ቆይቻለሁ፡፡ ከኃላፊዎችም፤ ከሠራተኞችም ከባለጉዳዮችም አፍ ሰምቻለሁ፡፡ በመጨረሻው ስብሰባም እንደምንም ጥግ ይዤ ስብሰባውን በቅርብ ሩቅ ለመከታተል ችያለሁ፡፡ ያየሁትንና የታዘብኩትን አሁንስ በቃ የሚሰማ ኖረ አልኖረ፣ ጉዱን የሚያወጣ ኖረ አልኖረ ይድረስ ለታሪክ ብዬ ቢያንስ ማሕበራችንን ለማዳን ፍላጎት ያለው ግለሰብ ሆነ የመንግሥት አካል ይስማው፤ አሊያም ታሪክ እንደልማዷ ትመዝግበው ብዬ ይህችን መጣጥፍ ደፈርኩ፡፡
በሌላም መልኩ ቢያንስ ደግሞ ዕውነትን ለመሸፋፈን የሞከሩ፤በጥቅማጥቅምና በጎሳ በዘመኑ አነጋገር በብሔር ብሔርተኝነት፣ ወገንተኝነት አልያም በድርጀት አባልነት በመቆላለፍ ከትልቅነት ወደትንሽነት ቁልቁል የተንደረደሩ፤ የህሊና ወቀሳን ተሸክመው እንደሰው ለብሰው ግን ባያውቁትም ዕርቃናቸውን የሚሄዱና ወደፊትም እንዲሁ ለመሆን ያሰቡ፣ ሁሉ ሁሌ ፋሲካ የለምና የለመደ ዐመል ጉድ እንዳይሠራ በየተሰማሩበት መስክ ምክር እንድትሆናቸው፤ እራሳቸውን እንዲያርቁ፤ ለንስሀ ይበጃቸው ዘንድ እነሆ ይቺ ጽሑፍ በጠቋሚነት ቀርባለች፡፡ መልዕክቷ ለቀይ መስቀል ብቻ ሳይሆን ለሁሉም እንድትሆንም ነው፡፡
ከየት ልጀምር ስል አንድ ሁለት ነገሮች ትዝ አሉኝ፡፡ አንደኛው በጉዳዩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መልኩ የተሳተፍኩበት ጉዳይ ነው፡፡ ባልሳሳት ከአምስት ዓመት በፊት በአ.አ ቀይ መስቀል ቅ/{/ቤት የበላይ አካል መሪ የሆኑ በብሔራዊ ቀይ መስቀል ማሕበር ውስጥ በያዙት የንግድ ሥራ ከፍተኛ ጥፋት ፈጽመው ተግሳጽ መቅረብ ይቅርና ከነአካቴው ለሁለተኛ ዙር ተመራጭ ሊሆኑ ለትንሸ አመለጣቸው፡፡ በብሄራዊ ጽ/ቤቱና በየክልሎች የሚደረገው የአሠራር ድክመት ይህ ነው አይባልም፡፡ ሁሉም ተደፋፍኖ አንተ ትብስ አንቺ ትብሽ ተብሎ ሲጓዝ የቆየ ልምድ ነው፡፡ በሌላ ጊዜ ከጨረታ ጋር በተያያዘ ምክንያት ጉድ የተባለ ዜና በዜና ብዙሀን ተላለፈ፡፡ ሰዎች ታሰሩ፡፡ ከሥራ ተባረሩም፡፡ ይህ የተከሰተው በብሔራዊ ጽ/ቤት ሆነ በቦርዱ ቆራጥ እርምጃ እንዳይመስለን፡፡ ጉዳዩ የተሰማውና ለዚህ ዓይነት ወሬ መሰማት ዕድሉ የተገኘው ተበደልን ባሉ ሰዎች ለሙስና ኮሚሽንና ለቀይ መስቀል ማሕበር የበላይ ጠባቂ ፕሬዚዳንት ለክቡር አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ አቤቱታ በመቅረቡና ክትትል በመደረጉ ነው፡፡ ውጤቱ ግን እንደኔ የበታችን በማሠርና በማስወጣት ብቻ መቆም ያለበት አይመስለኝም፡፡
አሁንም ማጣራቱ ቀጥሎ ይሆን? ወይስ እንደዋዛ እንደተለመደው ተድበስብሶ ቀረ? በክልሎች የግዴታ አባል ለሆነው ገጠሬ ሕዝብና በአዲስ አበባና በከተሞች በውዴታ አባል ለሆነው በአጠቃላይም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ውጤቱ በይፋ የተገለጸ አይመስለኝም፡፡ የቀይ መስቀልን የአባልነት ሳይሆን የገንዘብ አሰባሰብ ሁኔታን አናውቅም ብላችሁ አደራችሁን እንዳታስቁኝ፡፡ ካሳቃችሁኝ በጄ፡፡ ሳቅ ከጠፋች ዘመናት አልፈዋል ብዬ ነው፡፡ ከእንግዲህማ በስብሰባም አትገኝ፡፡ ምን ይውጥሽ አዳሜ!
በቀጣይ የሚገርመው ደግሞ በአሁኑ ጊዜ ብሔራዊ ቦርዱና ብሔራዊ ጽ/ቤቱ ለውጥ አመጣን ያሉበት የመዋቅር ለውጥና የደመወዝ ጭማሪ ነው፡፡ የአሠራር ስትራቴጂ አየር ያልሸተተው ለውጥ ተብሎ የተወራለት የደመወዝ ጭማሪ አስቂኝ ገጽታው ብዙ ነው፡፡ ዋናው ዓላማ በብሔራዊ ጽ/ቤት ሠራተኞች ማሕበሩን ለአንድ ዓመት እንኳ ሳያጤኑት ከቅ/ጽ/ቤቶች ቦርድ አመራር ጋር የሥራ ግንኙነት ሳያደርጉ፤ እራሳቸውን ሳያውቁና ሳይፈትሹ ፍላጎታቸው የራሳቸውን ደመወዝ ማሳበጥ ብቻና ብቻ በመሆኑ ትኩረቱ በዚህ ላይ አርፎ ጥናት ተጠና ተብሎ፣ በብሔራዊ ጽ/ቤት በብር 5000 ደመወዝ ለመሥራት ተስማምተው የተቀጠሩ ባለሙያዎች ከኃላፊዋ ጀምሮ፣ ባለ25000፤ 17000 እና 16000 ደመወዝ እንዲከፈላቸው ያደረገና የሚያደርግ ነው፡፡ በቅ/ጽ/ቤት ደረጃ ደግሞ ባለ2000 ብር ደመወዝተኛ ብር 9000 እና 12000፣ ባለ 3000 ብር ደመወዝተኛ ደግሞ ብር 14000 የሚያደርግ ነው፡፡ እንዲህ እያለ ይወጣል፡፡
በዚህም ከላይ እስከታች ያለ ሠራተኛ በደመወዝ እንዲፍነሸነሸ ተወሰነ፡፡ በብሔራዊ ጽ/ቤትና በተወሰኑ ክልሎችም ተግባራዊ ሆነ አሉ፡፡ የሚገርመውና አስቂኝ የሆነው ደመወዝ ለምን ተጨመረ አይደለም፡፡ አካሄዱና አፈÚጸሙ አስቂኝና ከሌለ ቋትና ለሰብዓዊነት ከሚገኝ የእርዳታ ገንዘብ መሆኑና የሥራ ለውጥ የሚያመጣው ይህ ብቻ እንደሆነ መቆጠሩ ነው፡፡ የሚšል የነበረው ለዓመታት በዝቅተኛ ደመወዝ የሚገኙትን ሠራተኞችን ደመወዝ በማššል መጀመር ነበር፡፡ ሌላም ብዙ የሚሠራ ነበር፡፡ ዘመቻው ሠርቶ ማግኘት ሳይሆን፤ በዕርዳታ ለምኖ ደመወዝን የትየለሌ ማድረስ የመጀመሪያው የለውጥ ትኩረት ሆነ፡፡
ብሔራዊ ቦርድ በቀይ መስቀል ታሪክ ለደመወዝ እጅግ ከፍተኛ የሆነን በጀት ያጸደቀው በራሱ ሥልጣን ነው፡፡ ዕቅድና በጀት መጽደቅ ያለበት በብሔራዊ ጠቅላላ ጉባዔ መሆኑ እየታወቀና የደመወዝ ጭማሪው ተራ ጭማሪ ያለመሆኑና የመዋቅር ለውጡም በበጀት ላይ ያለው አንደምታ እጅግ ከፍተኛ መሆኑ እየታወቀ ሥልጣኑን አሳብጦ፣ ፈላጭ ቆራጭ የሆነበት ምክንያት ግልጽ አይደለም፡፡
ቦርዱ ያጸደቀውንና በብሔራዊ ጽ/ቤት በአፋጣኝ ተግባራዊ የሆነውን ሥር ነቀል ለውጥ የተባለለትን የመዋቅር ለውጥና የደመወዝ ጭማሪ አፈÚጸምን በተመለከተ በተጠራ ስብሰባ፣ ሠራተኞች በአራት ቡድን ተከፋፍለው ሃሳባቸውን እንዲያቀርቡ ተደርጎ፣ በአንድነቱ ስብሰባ ላይ የአራቱ ቡድኖች ተወካዮች ያቀረቡት ሃሳብ አንድ ዓይነት ሆኖ መገኘቱ ብሔራዊ ቦርዱንና ጽ/ቤቱን የሚያሳፍርና የሚያስደነግጥ ነበር፡፡
ደመወዙ ተጋነነ፡፡ አቅሙ የለንም፡፡ የእኛ ደመወዝ ከክልል ፕሬዚዳንቶች በላይ ሆነ፡፡ ሕብረተሰቡም ሆነ መንግሥት የምናደርገውን ድጎማና ዕርዳታ ለራሳቸው ደመወዝ ለማድረግ ከሆነ ምን ድጎማ ማድረግ ያስፈልጋል ማለታቸው አይቀርም፡፡ ትዝበት ላይ ይጥለናል፡፡ መዋቅሩም በርካት ሠራተኞችን ከሥራ ያፈናቅላል፡፡ ገንዘቡም ስለሌለን የግድ ይሁን ከተባለ ብሔራዊ ጽ/ቤቱ የተባለውን ደመወዝ ለ5 ዓመታት የሚችለን ካልሆነ ፈጽሞ አይታሰብም የሚል አርቆ አስተዋይነት የተመላበትና አራቱም ቡድኖች አንድ ላይ ሳይወያዩ አንድ ሆነው መገኘታቸው ድንቅ ነበር፡፡ ይህንን ሃሳባቸውን የሚደግፍ አስተያየት መሰንዘሩ ትዝ ይለኛል፡፡ አመራሩን ግን አስቆጣ፡፡
በብሔራዊ ደረጃ ማፈሱ በመጀመሩ ምክንያት ይሁን አይሁን ወይም የቦርዱ ውሳኔ እንዴት ይšራል በማለት ይሆን ተጠቃሚው በመቆርቆርና በሚዛናዊነት የተቃወመውን ለውጥ ተብየ ስብሰባውን ይመሩት በነበሩት ሁለት የቦርድ አባላትና የለውጡ ተጠቃሚ ሁለት የብሔራዊ ጽ/ቤት ኃላፊዎች ጉንጭ አልፋ ክርክርና ተጽእኖ “ጭማሪውን አትፈልጉም ትፈልጋላችሁ?” በሚል ጥያቄ በጭብጨባ አጠቃለሉት፡፡
ይህችናት ለውጥ ማለት፡፡ ይች ናት አመራር፡፡ በማግሥቱ ደግሞ የብሔራዊ ጽ/ቤት ኃላፊ የቅ/ጽ/ቤት ኃላፊዎችን በመሰብሰብ እናንተ እኮ ከሥራ አትወጡም፡፡
ሌሎችንም በአንዴ አታስወጡም፡፡ ደመወዛችሁን ዲታው ብሔራዊ ጽ/ቤት ለአንድ ዓመት ይችላችኋል ተብለው ከምሳ ግብዣ ጋር ተሰነባበቱ፡፡ ለውጥ ይሏል እንዲህ ነው፡፡ በምክንያት የእናንተም የእኛም ደመወዝ ይጨመር እንጂ መዋቅሩና መስፈርቱ መሟላት አጣዳፊ አይደለም ተባለና አረፈው፡፡ ቦርዱም አሠራሩ ምን ያህል ከሥርዓትና ከተጨባጭ ሁኔታው የራቀና ከሠራተኞች መማር ያልቻለ መሆኑን ያሳያል፡፡
ቀጥሎ ደግሞ የአዲስ አበባ ቀይ መስቀል ቅ/ጽ/ቤት ጉዳይ ብቅ አለ፡፡ ከቅ/ጽ/ቤቱ ቦርድ ሰብሳቢ ለሚመለከታቸው የተላኩ ደብዳቤዎችን ተመልክቻለሁ፡፡ ግልጽነትም ያለው ነው፡፡ ቦርዱና ብሔራዊ ጽ/ቤቱ ግን የተለመደውን ድክመታቸውን ብቻ ሳይሆን ነገር አለ፤ ይህን ነገር ከነካኩ ነገ በእነርሱ እንዳይመጣ የፈሩት ጉዳይ አለ የሚያሰኝ ሃሳብ ተደቅኖብኛል፡፡
ካለምክንያት እይደለም፡፡ ለተስብሳቢዎች የላከውን የስብሰባ ጥሪና ቦርዱን ያፈረሰበትን ደብዳቤዎች ተመልክቻለሁ፡፡ እውነቱን የሚያሳይ አይደለም፡፡ በዚህም እንደኔ ቀይ መስቀልን ደርግመውታል፡፡ ሳይሠሩ ሠራን ያሉበት ሁኔታ እንዳለ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ከሥልጣናቸው ውጭ መሥራታቸውና የአሠራር ድክመትን ሸፋፍነው መሄድን የመረጡበት ምክንያት ነግ በኔ ስለሚሆንና በሌላም በኩል በስመ “የማሕበሩ ዝና እንዳይጠፋ” በሚል ሰበብ በግልጽ የተንጸባረቀውን የቡድን ስሜትንና ወንጀልን የመደፋፈን አካሄድን መምረጥ ተስተውሏል፡፡ ከሁሉም በላይ ንጹህ ህሊናን መጠቀም ሰብዓዊነት ነው፡፡
እውነትን ደብቆ፤ እያወቁ እንዳላወቁና በፖለቲካ ይሁን በጠባብ ቡድን መደጋገፍ ስሜት የሌላውን ስሜት መንካት ህሊናን እንደማቆሸሽ ይቆጠራል፡፡ ማሕበራችን የሚያስፈልገው ለዝና ወይንም ለግል ጥቅም ተብሎ ሙስና ማስተናገድ፤ ርካሸ የሆነ የቡድን ስሜትን፤ ጠባብነትንና ብልሹ አሠራርን ማስተናገድ ወይም ፈጻሚ ሆኖ መገኘት አይደለም፡፡ እንዲህ ከሆነ ደግሞ ቀይ መስቀል ማሕበር ባይባል ይመረጣል፡፡የአ.አ ቀይ መስቀል ጽ/ቤት የበላይ አካል የክልሉ ጠቅላላ ጉባዔ መሆኑ እየታወቀ፤ ብሔራዊ ቦርዱ በቦርድ አባላት መካከል ያለመግባባት ስለተፈጠረ ቦርዱን መበተን መብቱ አይደለም፡፡ ያለመግባባቱ ምንድን ነው? ብሎ መመርመርና የመፍትሄ አቅጣጫ መስጠት ለምን ተሳነው? መጀመሪያ የሚጠበቅበት በእውነት መሥራትና የክልሉ ጠ/ጉባዔ ተጠርቶ፣ እራሱ ችግሩን እንዲፈታ ሁኔታዎችን በማመቻቸት አስተዋጽኦ ማድረግ ሲገባው፣ እራሱን ከሕግና ከሥርዓት በላይ አድርጎ የቆጠረውን የብሄራዊ ጽ/ቤት ጣልቃ ገብነት፣ በተለይማ ከአንደኛው ቡድን ጋር መምከርን፤ በሕግ አስተያየት ስም የሚቀርብን የሳሳና ጭብጥ የሌለ ከቡድንተኝነት ያልተላቀቀ፤ መሬት ያልረገጠና ሙያዊ ብቃትን ያላሳየ አስተያየትን መሠረት ያደረገ ነው ለማለት የማያስደፍርን ይዞ መቅረብና ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ እንዲሉ አባላቱ ባላቸው ዕውቀትና ዕድሜ በዚህ ሁኔታ መቅረባቸው አጀብ ያሰኛል፡፡ በስብሰባው የተሳተፍንና ያልተሳተፍን ሠራተኞችና በጎ ፈቃደኞች የማናውቅ ብንመስልም መኮፈš መጠሪያ ባይኖረንም፣ ቢያንስ የሥራ ልምዳችን እናንተን የመታዘብና የመገምገም አቅም እንደሚሰጠን ብትረዱልን መልካም ነው፡፡ ይህን ሁሉ ስል ከምንም ተነስቼ አይደለም፤ ኮተት ብዬ ከሁሉም ወገኖች ማለትም ከፈራጆች፤ መግባባት አልቻሉም ከተባሉት ቦርድ አባላትና ከሠራተኞች ያገኘሁትን መረጃና በበቂ ሁኔታ የቃረምኩትን አስተ ያየት መሠረት በማድረግ ነው፡፡አካሄዱማ አስቂኝ ነው፡፡
መጀመሪያ ቦርዱን በተነ፡፡ በመቀጠል ስብሰባ ጠራ፡፡ የቦርድ አባላትንም ዕውቅና አልሰጠም፡፡ የቀረበው አጀንዳ ውሳኔ ይዞ ነው የቀረበው፡፡ ምርጫ እንደሚካሄድ፡፡ አጀንዳውም በጉባዔው እንዲጸድቅ አልተደረገም፡፡ ከመገረም አልፎ የሚያስገምተው፣ የብሔራዊ ቦርዱ ሰብሳቢና የብሔራዊ ጽ/ቤት ኃላፊ ባቀረቡት መግለጫና ሪፖርት፣ ስለችግሩ ምንነት አንዲት ነገር ትንፍሸ አላሉም፡፡ ለምን? ማን ማንን ያጋልጣል? የራስን ቡድን ማን ይነካል ይሆን? ቤቱም ለመጠየቅ አልደፈረም፡፡ ቢደፍርርም መልስ አይሰጠውም፡፡
እኔና ብዙዎቻችን ግን ጉዱን እናውቃለን፡፡ በአዲስ ተሳታፊነት የተጋበዙት ግን ምንም ሳያውቁ በደፈናው ዛሬ ይመረጥ በሌላ ቀን ከሚለው ውጭ ሊራመዱ አልቻሉም፡፡
ጥፋተኛ ሳይጣራ በማንአለብኝነት ከኃላፊነታቸው የተነሱትና እንደመሰለኝ ከእናንተ ከመጣ ግልግል ያሉት የመሰለኝ የቅ/ጽ/ቤቱ ቦርድ ሰብሳቢ፣ የችግሩን ምንነት የሕዝብንና የመንግሥትን ሀብትና ንብረት የመጠበቅና ብሎም በመድሎ አሠራር ምክንያት የተደረገ ክፍፍል መሆኑን ሲጠቁሙ፤ የጉባዔው ስብሳቢ በተደጋጋሚ አቁም በማለት አስገደዱ፡፡ ለነገሩማ አጀንዳው የፈቀደው ጥያቄ ማቅረብ እንጂ ውይይት እንዲደረግ አይጋብዝም፡፡
የብሔራዊ ጽ/ቤት ሪፖርት ዋንኛ ግምገማ መሠረት ያደረገው ቃለ ጉባዔ ነው፡፡ የክልሉ ጠቅላላ ጉባዔ ያደቀውን የሁለት ዓመት ሪፖርት ሁሉ ናደው፡፡ በቃለ ጉባዔ የተመሠረተ ግምገማ ! ድንቄም ግምገማ ተደርጎ ተሞቷል፡፡
ቦርዱና ጽ/ቤቱ የማይናበቡ መሆናቸውን የሚያሳየው ቦርዱ ይሄን ያህል ተሰበሰበ የሚለው ዋጋ አለው ሲል፤ እራሱ በዚህ ዓይነት ቢገመገም የተለየ እንደማይሆን ያወቀው የቦርድ አባል፤ አካሄዱ ዋጋ እንደሌለው አሰመረ፡፡
እንደቦርድ አባሉ አመለካከት አንድ የቦርድ አባል በአራት ዓመት 3 ቀን ከተሰበሰበም በቂ ነው፡፡ ጽ/ቤቱ ደግሞ ይህን ያህል ተሰበሰቡ፤ እነእከሌ ይህን ያህል ተሰበሰቡ የሚል የግምገማ መሠረት አደረገ፡፡
የትኛው ይወሰድ! ሌላው የግምገማው ውጤት በዕለት ተዕለት ሥራ ጣልቃ ገብተዋል የሚል ነው፡፡ ሠራተኛውንም ከፋፍለዋል ተብሏል፡፡ ይህን ያህል ሲያጠፉ የት ነበራችሁ? ከመድረክ ልዩነቱ በንብረትና በሀብት ምክንያት ነው የተባለው ምንድን ነው? የሚሉትንና ሌሎች ጥያቄዎችን በተመለከተ አንዳችም መልስ ወይንም አስተያየት አልተሰጠም፡፡
የምርጫ ጊዜው ይተላለፍ፡፡ ይታሰብበት፤ የተšለ መሠረት ይጣል ቢባሉም ሰብሳቢው ባደረጉት ተጽእኖ ምርጫው እንዲካሄድ ተደረገ፡፡ የተšለ አሠራር መዘርጋት እንደልብ መሆንን ስለማያስችልና አደገኛነት እንዳለው ተገምቶ ነው መሰል እንደዚህ ዓይነቱን ቀና አመለካከት ከመቀበል ይልቅ እንደቡድንም እንደግልም ድርጅታዊ አሠራርን በመጠቀም ማፈን መቻልን እንደአቅሚቲ የተካኑ መሆናቸውን ለማየት ችለናል፡፡ ቦርዱ በዕለት ተዕለት ሥራ መግባቱ ጥፋት ከሆነ፣ ፖሊሲን የሚያይ በወር አንዴ ብቻ የሚሰበሰብ መሆኑ ከታወቀና ጽ/ቤቱ በብሔራዊ ጽ/ቤት ሥር መሆኑ ከታወቀ ምርጫው ለምን ተጣደፈ? ፍርሃት? ስጋት? ወይስ ሌላ? አዎ! የቦርዱንና የብሔራዊ ጽ/ቤትን አመራር ራዕይ የሚያስፈጽሙ፣ በድርጅታዊ አሠራር ለአ.አ.ቅ/ጽ/ቤት ቦርድ አባላት የሚሆኑትን ማስመረጥ ዋና ተልዕኳቸው ስለነበር ነው፡፡
እንዳሰቡትና እንዳለሙት ያዘጋጁት አዲሱ ቦርድ ከመግባቱ የመጀመሪያው ተቀዳሚ ተግባር ዕረፍት ተሰጥቶት እንዳለ፣ ውሳኔ እንዲሰጥበት የተባለውን ጸሐፊ በተለመደው የመሞዳሞድ አካሄድ መልሰው አስገቡት፡፡ መረጃዎችን አጥፍቷል የተባለን ግለሰብ የበለጠ መረጃዎችን እንዲያጠፋና እንዲያመቻች ብሎም ለሕዝብና ለመንግሥት ሀብትና ንብረት እንዲሁም ለፍትህ የቆሙትን ሠራተኞች አንገት ለማስደፋት፣ ለማስመታትና በዚህም የብሔራዊ ጽ/ቤት ጸሐፊ በሪፖርታቸው እንዳሰሙት፣ የተከፋፈለው ሠራተኛ በአንድ አቅጣጫ ተሰባስቦ ለዘረፋና ለብልሹ ሥራ እንዲሰለፍ በማስደረግ ያለሙትን ለማሳካት የተወሰደ እርምጃ ነው፡፡
ካልሆነማ ሠራተኛ አቤት ያለበትን በኦዲት የተረጋገጠበትን በጭፍን መልሶ መጫን፣ ሰውየው አብሮ የሠራውን እንዳያወጣ፤ መዘዙም ወደእነሱ እንዳያነጣጥር በማሰብ ሳይሆን አይቀርም፡፡
የአ.አ.ቅ/ጽ/ቤት ተጠሪነቱ ለብሔራዊ ጽ/ቤቱ ነው፡፡ ቦርዱ አቅጣጫ ሰጭ ነው፡፡ ታዲያ በአሃዳዊ አሠራሩና ከተጠሪነቱ አኳያ ለቅ/ጽ/ቤቱ መዳከም በዋንኝነት ተጠያቂዎች ብሔራዊ ቦርዱና ጽ/ቤቱ መሆናቸው ግልጽ ነው፡፡ ለማንኛውም፤ ጥፋተኛ ሳይጣራ፤ ችግሩ ሳይታወቅ፤ ሪፖርት ሳይቀርብ፤ የርክክብ ሥነ ሥርዓት ሳይፈጸም ስብሰባው ባልጸደቀና በተጫነ አጀንዳ ተጀምሮ ሳይጀመር፣ ሥራ ሳይሠራ እንደፍላጎታቸው ተጠናቀቀ፡፡ የቀይ መስቀልን መርሆዎችንና መፈክሮችን በማስተጋባት የ
ቡድን ስሜትንና ጠባብነትን የምታራምዱ፤ ሀብቱንና ንብረቱን እንደልብ የምታደርጉ፤ ከሥራ ይልቅ ሀሜትንና አሉባልታን የምታራምዱ ሁሉ የአሁኑ አመራር እስካለላችሁ ድረስ ይመቻችሁ ይሆናል፡፡ ተጠያቂ አትሆኑምና!! ኋላ ግን አይቀርላችሁም፡፡ ሌላው ቢቀር ዞሮ ዞሮ የህሊና ደወል ማቃጨሉ፤ መደወሉና ማንገጫገጩ አይቀርም፡፡ አይ ጅሎ ትሉኝ ይሆናል፡፡
ይሁንላችሁ፡፡ ግን የመንፈስ እርካታ ውሸት!! መዋሸት፤ ቅጥፈት፤ በሆድ ወይንም በራስ ጥቅም መገዛት፤ በሀቅ ያለመሥራትን የመሰለ መጥፎ ነገር የለም፡፡ ሰው ከመግደል ያላነሰ ወንጀልና ለአገር ዕድገት ጸር ነውና በዚህ ሁሉ የምትዋኙ ይቅር ይበላችሁ፡፡
የእንደዚህ ዓይነቶች ወላጆች ከመባል ያድናችሁ፡፡ ምንም እንኳ አዲሱ ዓመት ከገባ ሁለተኛውን ወር የያዘ ቢሆንም ቀሪ ወራትን የያዘው አዲሱ ዓመት ይታረቃችሁ፡፡ ሌላ ምን ይባላል!!!
እባካችሁ አለቆች፡- የአ.አ.ቅ/ጽ/ቤትን ቦርድ አባላትን ጥፋት ምክንያት ሳታደርጉ ክኒኗን መልሳችሁ ዋጧት፡፡ አጠፋን ማለት ነውር የለውም፡፡ ከሁሉም በላይ ችግሩን በማድበስሰሳችሁ ተጠያቂ መሆን አለባችሁ፡፡ ከቤቱም ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ የዲሞክራሲ፤ የፍትህ፣ የነጻነትና የእኩልነት መለማመጃ ሊሆኑ የሚገቡ ማሕበራትን የብልሹ አሠራር መናኸሪያ አታድርጓቸው፡፡
ሠራተኞችን ከፋፍለዋል የተባሉት የቦርድ አባላትም መጠየቅ አለባቸው፡፡ ሠራተኛን በዘር፤ በፖለቲካ፤ በሃይማኖት ወይስ በምን ይሆን የከፋፈሉት? ይህ ደግሞ ወንጀል በመሆኑና መከፋፈልም የቀይ መስቀል መርህን የሚጻረር ስለሆነ ግልጽ ተደርጐ ተጠያቂ መሆን አለባቸው እላለሁ፡፡
ይህ የተባለው ሀሰት ከሆነ ደግሞ በስም አጥፊነት እናንተው መጠየቅ አለባችሁ፡፡ የቀይ መስቀል ማሕበራችን በጎሳ፤ በጓደኝነት፤ በድርጅት አባልነት ተጠራርቶ ለአመራር የሚበቃበትና ለሆድም ሆነ ለፖለቲካ ፍርፋሪ ደካሞችን ለግል ጥቅም የሚያሰባስብ እስከሆነ ድረስ የትም መድረስ አይቻልም፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ ከታች እሰከ ላይ ያለው ሰንኮፍ ካልተነቀለ ቀይ መስቀል ቀይ መስቀል ነው ማለት ውሸት! በአጭሩ የረጅም ጊዜ ዕድሜ ያለው ቀይ መስቀል ማሕበር ውስጡ ቢፈተሽ ብዙ ጉድ ያለውና እውነት ባለቤት አለው እንዴ! የሚያሰኝ ከሆነ ዓመታትን አስቆጥሯልና በጋራ እናንሳው፡፡
መቼም ጉዳችን ብዙ ነው፡፡ ሀቅን ትቶ በእንደዚህ ዓይነት አቋምና አካሄድ ይችን አገራችንን መታደግ ዘበት ነው፡፡ እስቲ ከህሊናችን ጋር እንኑር፡፡
የአኩሪ ባህላችንንና የሃይማኖታችንን እሴቶች ይዘን ህሊናን ከሚወቅስ ሥራ እንቆጠብ፡፡ ለአገራችን መልካም ማሰብና መሥራት እንጀምር፡፡ ቀሪውን እኔ ነኝ ላለ፤ ጀግና ነኝ ላለና ለታሪክ ትቼዋለሁ፡፡ አሁን ተፈወስን እስክል ድረስ በቴዲ አፍሮ ውብ ዜማ ልደምድም፡፡- አመመኝ! አመመኝ! እኔን አመመኝ!!! ቸር እንሰንብት፡፡

Read 3704 times Last modified on Saturday, 27 October 2012 10:20