Saturday, 31 December 2022 13:18

ኢትዮጵያ፡ አላቻ ጋብቻ

Written by  ዶ/ር ዘላለም እሸቴ
Rate this item
(2 votes)

ሁሉም ስለ ኢትዮጵያዊነትና ስለ ብዝሃነት ያወራል። ግን እነዚህ ቃላቶች የሚሰጡት ትርጉም  ጭራሽ የሚቃረኑና የሚጋጩ ናቸው። ለዚህ እንቅፋት የሆነው እነዚህን ቃላቶች ለመተርጎም አህዳዊ/ፌደራላዊ በሚሉት ቃላት በመተርጎማቸው ነው።  ይህ ደግሞ ፖለቲካዊ ማምታታት ነው እንጂ ለመግባባት እንድንችል ቃላቶቹን በራሳቸው ለመተርጎም ሳይቻል ቀርቶ አይደለም። አህዳዊና ፌደራላዊ የሚሉት ቃላቶች የምንተዳደርበት የመንግስት አወቃቀር ይገልጣል። ኢትዮጵያዊነት እና ብዝሃነት ግን በራሳቸው የሚቆሙ እውነቶች ናቸው። ግን ፖለቲካዊ ማምታት መሠረታዊ የሆኑ መግባባቶች እንዲኖሩ አይፈልግም።  የግል ፖለቲካ አጀንዳ ሲኖር አህዳዊ/ፌደራላዊ የሚል ታፔላ ለጥፎ በተጣመመ ትርጉም የሚያምታታና የሚያደናግር ሁኔታ ለመፍጠር በመጀመሪያ ቋንቋ በማደባለቅ ለመግባባት እንዳይቻል ያደርጋል።
ስለዚህ ይህን ፅሁፍ በኢትዮጵያዊነት ፌደራላዊ አስተዳደር አውድ ውስጥ ለመፃፍ ተነሣሣሁ። ዓላማውም ሆን ብሎ ቋንቋችንን ከሚያደባልቀው የፖለቲካ አካሄድ ወጥተን አገራዊ መግባባት እንዲኖረን ኢትዮጵያዊነትን እና ብዝሃነትን በራሳቸው እንተርጉም። ይህንን ለማድረግ ቋንቋችን ሲደባለቅ የሚፈጠሩትን ሦስት አላቻ ጋብቻዎች በምሳሌነት እንጠቀም።
ኢትዮጵያውነት ከዘረኝነት
ስንወለድ በምርጫችን ሳይሆን ፈጣሪ በወሰነልን በየጎሣችን ውስጥ ተሰይመን ነው።  ስንኖር ግን በምርጫ በመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ነን ስንል፣ ያኔ ኢትዮጵያዊነት ገብቶናል ማለት ነው።  በመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ነን ስንል፥ አብሮነትን ማስቀደማችን ነው።  ከጎሣችን እና ከሰፈራችን ወጥተን በአብሮነት ኢትዮጵያን ለአፍሪካ ፋና ወጊ እና ለዓለም ተስፋ እንድትሆን መስራት የምንችለው ያኔ ነው።  አለበለዚያ ኢትዮጵያዊነትን ከዘረኝነት ጋር አጋብተን በመጀመሪያ ጎሣችንን አስቀድመን  ስለ ኢትዮጵያዊነት ብናወራ የምናወራው ከተግባራችን ጋር እየተጋጨብን ተደናግረን እናደናግራለን። ምክንያቱም ጎሣችንን አስቀድመን የምንይዘው ኢትዮጵያዊነት፣ እግራችንን ጠፍረን ጠፍንገን አስረን ስናበቃ፣ እንሩጥ እንደ ማለት ነው።
ጥያቄው ጎሣችንን እንፍቃለን ሳይሆን ማንን እናስቀድማለን ነው? የምናስቀድመው ኢትዮጵያዊነትን ከሆነ አብሮነትን የመጀመሪያውን ቦታ ሰጥተነዋል ማለት ነው።  ያኔ ከሁሉም ጎሣዎች ጋር ለመያያዝና በአብሮነት ሃይል እንዲኖረን ምርጫችን አቅም ሰጠን ማለት ነው። ከዚያ ውጭ ኢትዮጵያዊነትን ከዘረኝነት ጋር አጋብተን ከተጠቀምን ወደሚቀጥለው አላቻ ጋብቻ ይወስደናል።
ብዝሃነት ከተረኝነት
ኢትዮጵያዊነትን ከዘረኝነት ጋር ካጋባን፥ ትንሽ ሳንቆይ ብዝሃነትን ከተረኝነት ጋር እናጋባለን።  ያ ማለት በብዝሃነት ስም ጎሣችንን በሌላው ላይ ለመጫን እንዲያስችለን ኢትዮጵያዊነትን አጣመን እንጠቀምበታለን። ያኔ ኢትዮጵያዊነትን ብቻ ሳይሆን ራሳችንን እና ሌሎችን ይዘን ወደ ጥፋት መንገድ እንገሰግሳለን።  ከዘረኝነት የተፋታ ኢትዮጵያዊነት ግን ብዝሃነትን ከተረኝነት አፋትቶ በትክክለኛው መንገድ ይተረጉምልናል። በመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ነን ማለት አብሮነታችንን ማስቀደማችን እንደሆነና ብዝሃነት ለዚህ ምስጢር እውነተኛነት ምክንያት ነው። ለኢትዮጵያዊነት (አብሮነት) የሚረዳን ብዝሃነት ነው። ምክንያቱም በኢትዮጵያዊነት አውድ ውስጥ ብዝሃነት በእኩልነት እንድንስተናገድ ያደርገናል። አለበለዚያ ኢትዮጵያዊነትን ከዘረኝነት ጋር አጋብተን የጀመርነው ጉዞ፥ ብዝሃነትን ከተረኝነት ጋር ማጋባት ብቻ ሳይሆን ወደ ሦስተኛው አደገኛ አላቻ ጋብቻ ይወስደናል።
አስተዳደር ከሌብነት
ሌብነት በአንዳንድ ሰዎች እጅ ሲሆን ለማጥፋት ቀላል ነው።  ግን ሌብነት ከአስተዳደር ጋር ከተጋባ፤ እኛ ሌብነትን ሳይሆን የምናጠፋው ሌብነት ነው ሁላችንንም የሚያጠፋው። ምክንያቱም ማሰርና መጠየቅ የሚችለው ባለስልጣን ሁሉ ሌባ ከሆነና ሌብነት ባህል እስኪሆን ታግሰን ስር ከሰደደ፣ በየት በኩል ነው መፍትኤ የሚመጣው? በተለይ አስተዳደሩ ኢትዮጵያዊነትን (ኢትዮጵያን ማለትም አብሮነትን የማያስቀድም) እና ብዝሃነት (ሁሉም በእኩልነት የሚስተናገዱበት) ባልሆነበት አውድ ውስጥ ከሆነ ሌብነት ፍፁም ወደማይድን በሽታነት ይቀየራል።
ለዚህ ሁሉ መውጫው መንገድ ከኢትዮጵያዊነት እና ከብዝሃነት ቃሎች ጀርባ ለቃላቶቹ ያለን ትርጉምና ግንዛቤ በእውነት ላይ የተመሠረተ ስናደርግ ነው።  ያኔ የምንናገረውና የምንተገብረው ይጣጣማል፥ ደግሞም ከመደናገር አውጥቶን ግልጽ አቅጣጫ ይሰጠናል፥ አንድ ልብም ይፈጥርልናል።

Read 2625 times