ኮኒና ተከታዮቻቸው በሰሜን ዩጋንዳ ፤ በደቡብ ሱዳን ፤ በኮንጎ እና ማዕከላዊ አፍሪካ የሚንቀሳቀሱና የአራቱም መንግስታት የፀጥታ ስጋት ሲሆኑ ጦራቸው በትንንሽ ቡድኖች መከፋፈሉና ምንም አይነት ቴክኖሎጂ የማይጠቀም መሆኑ በቀላሉ ለማጥቃት ወይም ለመያዝ ፈተና እንደሆነ ዩጋንዳ ትናገራለች፡፡በማዕከላዊ አፍሪካ በሎርድስ ሬዚስታንስ አርሚ ላይ ለሚካሄደው ዘመቻ አሜሪካን 35 ሚሊዮን ዶላር የመደበች ሲሆን የአሜሪካን ጦር ልዩ ሀይል እና የአሜሪካን የመረጃ ቡድን ይህን ለማሳካት በተልዕኮ ላይ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ በሴንትራል አፍሪካ - ኦቦ ፤ በደቡብ ሱዳን - ናዝራ፤ በዲሞክራቲክ ሪፖብሊክ ኮንጎ-ዱንጉ፤ በኢንቴቤ እና ካምፓላ - ዩጋንዳ የተሰማሩት እነዚህ ቡድኖች፤ የአራቱን አገሮች የጦር አዛዞች ያማክራሉ፤ የመረጃ ልውውጦችንም ያደርጋሉ፡፡
ኮኒ በማዕከላዊ አፍሪካ ጫካ ውስጥ እንዳሉ ቢነገርም በዩጋንዳ ባለስልጣኖች መረጃ መሰረት ግን ኮኒ ከሌሎች የሎርድስ ሬዚስታንስ አርሚ ተነጥለው በሱዳን ጫካ ውስጥ ተሸሽገዋል፡፡ በ2012 የመጀመሪያ ወራቶች የሎርድስ ሬዚስታንስ አርሚ ጥቃት ጨምሮ የነበረ ቢሆንም በደረሰበት ከፍተኛ ጫና በአሁኑ ወቅት የቡድኑ ህልውና ጥያቄ ውስጥ እንደገባ የአሜሪካን ጦር ልዩ ሀይል ቃል አቀባይ ሜጀር ጀምስ ስኮት ራውሊንሰን ገልፀዋል፡፡