Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 03 November 2012 13:22

“ኢህአዴግን እከስሳለሁ”

Written by 
Rate this item
(5 votes)

መግቢያ
በእኔ ላይ ተተርጉሞ አስተውዬዋለሁ ማለት እችላለሁ፡፡ ተወልጄ ያደግኩት ባሻ ወልዴ ችሎት አካባቢ ነው፡፡ ባሻ ወልዴ ችሎት፣ ጉብታ ላይ የተንሰራፋው የምኒሊክ ቤተ - መንግስት ግርጌ ከተኮለኮሉት ጐስቋላ ሠፈሮች አንዷ ነበረች፡፡ ይቺ ሠፈር ነዋሪዎቿን እንደታቀፈች ፖለቲካ ሠራሽ በሆነ በሽታ ወድቃ፣ ቃትታና አጣጥራ የተንከራተተች ውሻ ሞት ስትሞት አብሬአት ነበርኩ፡፡
ወቅታዊው እሳቤዬና ስሜቴ ሁሉ የዚህ ነባራዊ ሁኔታ ውጤት ነው፡፡ ኩሬ ላይ እንደተጣለ ጠጠር የራሷን የማዕበል ሠፌድ ፈጥራ ከሠፈር አካባቢ፣ ከአካባቢ ከተማ፣ ከከተማ አገር አቀፍ ይዘት ትላበስ እንጂ መነሻው አራት ኪሎ ባሻ ወልደ ችሎት ናት፡፡
አገርና ዜግነት…

 

አለቃ ተሰማ “አገር፣ ልብስ ነው፤ ሰው ሁሉ በልብሱ ዕርቃነ አካሉን እንደሚሰውር አገርም ልብስ ከለላ መጋረጃ ነው” ይሉታል፡፡ በእርግጥ ነው? አገር እያለ ዕርቃነ አካል መሰወሪያ አይታጣም? ከውርደት ጋር አይኖርም? ከሰቀቀን ጋር አይታደርም?...
አፄ ቴዎድሮሳዊ ሥልጣኔና….
አለቃ ዘነብም የጌታው ጥላ ነው፡፡ አፄ ቴዎድሮስ ክብራቸው የማይፈቅድበት ቦታ እየተገኘ፣ የአፄው ክብር የማይፈቅድበት ቦታ እና ክብራቸው የማይፈቅደው ባህሪ ውስጥ እየተሰለቸም ቢሆን በእውቀት ቃርሚያ ላይ ተሰማርቶ ወገኖቹን ሳይንስ ለመቀለብ ያደገደገ ታታሪ፡፡
“መጽሐፈ ጨዋታ ስጋዊ ወመንፈሳዊ” የተባለ ድርሰቱ ለእነዚህ እውቀት እንቢ ባይ ወገኖች የቀረበ ማዕድ ነው፡፡
ደጋግሞ እንዲህ በማለት ይመክራል “ድንጋይና ጭቃ ቢቀጣጠሉ ታላቅ ቤት፣ ረጅም ቅጥር ይሆናሉ፤ እናንተም መሬታውያን ሰዎች እንዲህ ብትረዳዱ ጥበባችሁና ኃይላችሁ ከሰማይ በደረሰ፡፡”

ሰለስቱ ክፉ “ጊዜ”ዎች
ተስእለ ፩ እምነገሥት ወይቤ እፎ ሀለወት ዘመን፡፡
ወይቤልዎ እስመ ዘመንሰ ለሊክ ውእቱ፤
እመ አሠነይካ አንተ ትሤኒ
ወለእመ እሕሰምካ አንተ ተሐሥም ዘመን
ትርጉም -
ጊዜ ምንድር ነው? ሲል ከንጉሶች አንዱ ጠየቀ
“ጊዜ አንተ እራስህ ነህ” ሲሉ፣ መለሱለት
መልካም ካደረከው፣ መልካም ይሆናል
ካከፋኸው ይከፋል፡፡”
ለዚህ መንግሥት ኢትዮጵያ የንግድ “ዩኒየን” ናት፡፡
ክልሎች የንግድ ኮንፌዴሬሽኑን ያቋቋሙ የንግድ ቀጠናዎች ናቸው፡፡ የክልሎች መገንጠል ከንግድ ኮንፌዴሬሽኑ እራስን ማግለል ብቻ ነው፡፡ ንግድን ማዕከል ላደረገው መንግስት ሀገር፣ ዜጋ፣ ባንዲራ…ዋጋ የላቸውም፡፡
ጠላት የሚመጣው የንግድ መደብርህን ለመዝረፍ ነው፣ አንተም የምትዋጋው መደብርህን እንዳይዘርፍ ብቻ ነው፡፡ ሀገርና ዜግነት እንዲህ ዝቅ ያሉበት ክፉ “ጊዜ”!!
ኢህአዴግ ኪሎው ስንት ነው?
በዚህ የመንግሥት ባህርይ ሁሌም አንናደድም፣ አንዳንዴ እናዝንለታለን፡፡ ምክንያቱም ከ”ፔስ ሜከሩ” ጋር በጠላትነት ይፎካከራል፣ ከቻለ ጠልፎ ይጥላል፡፡ ማንፀሪያውን በማጥፋት እራሱን ያደበዝዛል፡፡ ትራኩን ቢቆጣጠርም ለብቻ መሮጥ መወዳደር ሳይሆን የእብደት መፈንጨት እንደሆነ አይረዳውም፡፡
ኢምንቱን እንደ ግዙፍ ይገጥማል፡፡ የኢህአዴግ ነገር “ዶሮን ስለፈሯት በመጫኛ ጣሏት” ነው፡፡ ይሄ የሥነ -ልቡና ቀውስ ነው፡፡ የዶሮን አቅም የማያገናዝብ የመጫኛ መጥለፍ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል?
ኢሕአዴግ ብትወድቅበትም ቢወድቅብህም እንደሚጐዳህ የማያውቅ ከሆነ፣ የሥነ-ልቡና ቀውስ ይሉሃል ይሄ ነው! ድርጅት እንደ ድርጅት የሥነ - ልቡና ቀውስ ይኖረዋል? የሚለውን ትተን የቀውሱን ምንጭ እንምዘዝ፡፡
“የባህል ምች”…
መጪውን ጊዜ የምሁሩን ጉዳይ በለዘብታ ይዞ መዝለቅ እንደማይቻል መንግሥት እየገባው የመጣ ይመስላል፡፡ ምክንያቱም በአመት እስከ ሰባ ሺህ የከፍተኛ ትምህርት ተመራቂዎች ቢኖሩም የሥራ ዕድሉ የተመራቂዎችን ያህል አላደገም፡፡ በመሆኑም በቅርብ አመታት ውስጥ የተማሩ ሥራ አጦች አገሪቱን ሊያጥለቀልቁና ህዝባዊ ተቃውሞውን በዕውቀት ሊያቀጣጥሉት ይችላሉ፡፡
በመሆኑም መንግሥት እንደ አጼ ኃይለሥላሴና እንደ መንግሥቱ ኃይለማርያም “የሥርዓቱ አደጋዎች” ያላቸውን እነዚህ ምሁራን የሚኮሩበትን በትረ ምሁር የማራከስ ዘመቻ ይዟል፡፡ ጉዳዩ ኢኮኖሚያዊ ተፈጥሮ ያለው ይምሰል እንጂ ሥነ - ልቦናዊነቱ እንደሚያይል አያጠራጥርም፡፡ በቀኝ እጅ የሰጡትን “ምሁራዊ ኩራት” በግራ እጅ የመንጠቅ ዘመቻን ምን ብለን እንሰይመው? “ዘመቻ ምሁር ግባት?”
“ኢህአዴግን እከሳለሁ” ከተሰኘው
የአለማየሁ ገላጋይ አዲስ መጽሐፍ የተቀነጨቡ



 

Read 5353 times