Saturday, 15 December 2012 13:29

“ኮንግራ” ኢህአዴግ! ዎርልድ ባንክ ባለ ሁለት ዲጂቱን እድገት አመነ

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(2 votes)

እንኳን ለብሄር ብሄረሰቦች ቀን በሰላም አደረሳችሁ ብዬ ነው ወደ ፖለቲካዊ ወጌ የምገባው፡፡ እኔ የምለው ግን… ወደ ባህር ዳር የመሄድ እድል አግኝታችሁ ነበር እንዴ? ለሌላ እኮ አይደለም - የብሄር ብሄረሰቦችን በዓል ለማክበር ነው፡፡ ለምን መሰላችሁ የጠየቅሁት… አንዳንድ መንግሥት መ/ቤት የሚሰሩ ወዳጆቼ ቅሬታ ስላላቸው ነው፡፡ እንደሌላው ጉዳይ ሁሉ በዚህም መጠቃቀም የሚሉት ነገር ሳይኖር አይቀርም መሰለኝ… አንዳቸውም ወዳጆቼ አልሄዱም፡፡ ምነው ስላቸው… ምን እንዳሉኝ ታውቃላችሁ?

“ሜምበሮቹ ናቸው ተመራርጠው የሄዱት!” አሉኝና ቁጭ! (የፓርቲው አባላት ለማለት እኮ ነው!) እኔ ግን ፈፅሞ ላምናቸው አልቻልኩም፡፡ እንዴ… የብሄር ብሄረሰብ መብትና እኩልነት በሚከበርበት እለት አድልዎና መድልዎ ይፈፀማል? ይሄን ለማጥፋት ደግሞ ሌላ የመብት ትግል ሊያስፈለገን እኮ ነው (ኧረ እኛ ትግል ሰልችቶናል!) 
እኔ የምለው… በዓሉን አስመልክቶ ኢቴቪ ያቀረበውን ፕሮግራም ተከታትላችኋል፡፡ ከወደ ምስራቁ የአገራችን ክፍል የብሄር ብሄረሰቦችን ቀን አስመልክቶ አስተያየት የሰጡ ሁለት ሰዎች የተናገሩት ነገር አስደምሞኛል፡፡ ሁለቱም ስለቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ነበር ያወሱት (ነፍሳቸውን ይማረውና!) አንደኛው ተናጋሪ መለስ የብሄር ብሄረሰቦች ነፃ አውጭና ወዳጅ መሆናቸውን ከገለፀ በኋላ “ሁሉም ብሄረሰብ መለስ የእኔ ብሄረሰብ ናቸው ነው የሚለው…” አለ፡፡
ሌላው የሶማሊያ ተወላጅ ደግሞ እንዲህ አለ “መለስ ብሄር ብሄረሰቦች ናቸው” አያችሁልኝ… ሁለቱም እኮ በተለያየ መንገድ ተመሳሳይ ነገር ነው የተናገሩት፡፡ ሁለቱ ሰዎች የተናገሩትን ጠቅለል አድርገህ ግለፀው ብባል ምን እንደምል ታውቃላችሁ? (ሽልማት ቢኖረውም ባይኖረውም) “መለስ ኢትዮጵያዊ ናቸው!” (Period!) ለምን መሰላችሁ? ብሄር ብሄረሰቦች የጋራ ስማቸው ኢትዮጵያውያን ነዋ! የጋራ ቤታቸውም ኢትዮጵያ ናት፡፡ በእርግጥ እንዳለፉት መንግሥታት ተገደን አይደለም ኢትዮጵያዊ የምንሆነው - ወደንና ፈቅደን እንጂ! እኔ የምለው ግን… ኢትዮጵያ እናታችን አይደለችም እንዴ? እኔ እኮ አንዳንዴ እንጀራ እናታችን ትሆን እንዴ? ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡ ለምን መሰላችሁ? እውነት እናታችን ከሆነች ኢትዮጵያዊነት በውዴታ ወይስ በግዴታ የሚለው ነገር አይመጣም ነበር ብዬ እኮ ነው፡፡ እንዴ… እናት በቃ እናት ናታ! ወልዳን፣ አሳድጋን፣ መኩሪያ መመኪያ ሆናን ስታበቃ “ከፈለግን ብቻ ነው እናታችን የምትሆኚው” ይባላል? (ፌር አይደለም!)
እስቲ አስቡት… እሷ እኮ አንድም ጊዜ ወድጄ እንጂ በግዳጅ እናታችሁ አልሆንም ብላን አታውቅም፡፡ ህዝቦችን የጨቆነ መንግሥትን ወይም አገዛዝን አሊያም ስርዓትን መጥላት፣ ማማረር፣ መርገም…በደንብ ይገባኛል፡፡ እኔ የማይገባኝ “ያኛው መንግሥት ኢትዮጵያዊነትን በግድ ጭኖብን” ምናምን የሚሉት ነገር ነው፡፡ እኔ በበኩሌ በግድ ተጫነብኝም ፈቅጄ ተቀበልኩትም ከኢትዮጵያ ሌላ እናት የለኝም፤ ከኢትዮጵያ ሌላ አገር የለኝም፤ ከኢትዮጵያዊነት ሌላም ዜግነት የለኝም፡፡ እንዴ… ብፈልግስ ማን ይሰጠኛል? በጉዲፈቻ የሚያሳድጉ እንደማይጠፉ አውቃለሁ፡፡ በክፍያ ዜግነት የሚሰጡኝም አላጣም፡፡ ወላጅ እናቱ በህይወት እያለች እነዚህን አማራጮች የሚፈልግ ያለ ግን አይመስለኝም፡፡ (ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!)
እኔ የምላችሁ ግን… ኢትዮጵያ የብሄር ብሄረሰቦች አገር ብቻ ሳትሆን የህብረ ፓርቲዎችም አገር መሆኗን አስባችሁት ታውቃላችሁ? እኔን ካላመናችሁኝ ምርጫ ቦርድ ቢሮ ጐራ ብላችሁ፣ በአገሪቱ ውስጥ ስንት የፖለቲካ ፓርቲዎች ፈቃድ አውጥተው እንደሚንቀሳቀሱ መጠየቅ ትችላላችሁ፡፡ በሽ እኮ ናቸው፡፡ ችግሩ ግን ምን መሰላችሁ? Unity in diversity ለብሄር ብሄረሰቦች እንጂ ለአገራችን ፓርቲዎች አይሰራም፡፡
በልዩነታቸው ውስጥ አንድነት ቢኖራቸውማ መብዛታቸው አያሳስበንም ነበር፡፡
የፓርቲዎች መፈክር ግን ምን እንደሚመስለኝ ታውቃላችሁ? “በልዩነት ውስጥ ልዩነት!” ለዚህ እኮ ነው አንዱ ፓርቲ ከሌላው ጋር ሆድና ጀርባ የሚሆነው፡፡ በልዩነት ውስጥ አንድነት የሚፈጥር ታብሌት (ክኒና) ባገኝ ስፖንሰርም ቢሆን አፈላልጌ እገዛላቸው ነበር፡፡
ሰሞኑን አንድ የረዥም ጊዜ የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊ ወዳጄን አግኝቼው ነበር፡፡ አያችሁ… የእኔን ነገር አምልጦኝ እኮ ነው የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊ የሆነ ወዳጅ እንዳለኝ የተናገርኩት፡፡ በቃ በዓለም ላይ ከነበሩኝ ጥቂት አሪፍ ወዳጆች ሁለቱን አጣኋቸው ማለት ነው፡፡ ለምን መሰላችሁ? እነሱ ደግሞ ከ97 ወዲህ ተቀይሰው የኢህአዴግ ደጋፊዎች ሆነዋላ! እናም የተቃዋሚ ደጋፊ ወዳጅ እንዳለኝ ሲሰሙ ተንጨርጭረው ይጣሉኛል፡፡ (እህል ውሃችን ካለቀ ምን ይደረጋል!) እነሱንስ ግዴለም በሌላ ወዳጆች እተካቸዋለሁ፡፡ ጉዴ የሚፈላው መቼ መሰላችሁ? ከኢህአዴግ ጋር እህል ውሃዬ ያለቀ ቀን ነው፡፡ እናንተም ብትሆኑ አስቡበት! ከኢህአዴግ ጋር እህል ውሃችሁ ሲያልቅ ምን እንደሚውጣችሁ! አንዳንዱ ሞኝ ምን እንደሚል ታውቃላችሁ? “ምን ጣጣ አለው ፓርቲ ቢሄድ ፓርቲ ይመጣል!” (አልሰሜን ግባ በሉት አሉ!) ፓርቲ ሁሉ ፓርቲ መስሎታል! እግሩ እስኪነቃ ሲኳትን ቢውል ኢህአዴግን የሚያህል ጽኑ “የህዝብ ፓርቲ” የትም አያገኝም፡፡ ባይገርማችሁ ከሁለት ሳምንት በፊት እኔም እራሴ ፓርቲ ቢሄድ ፓርቲ ይመጣል ባይ ጉረኛ ነበርኩ፡፡ ይሄን አቋሜን መቼ እንደለወጥኩ ታውቃላችሁ? በቅርቡ የኢህአዴግ ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ሬድዋን ሁሴን እዚሁ ጋዜጣ ላይ የሰጡትን ቃለምልልስ ካነበብኩ በኋላ ነው፡፡ “ለኢትዮጵያ ህዝብ ከኢህአዴግ የተሻለ አማራጭ የለም” በማለት ያብራሩት ሃሳብ ከእንቅልፌ አነቃኝ፡፡ የእሳቸውን ኢንተርቪው አንብቤ ስጨርስ ከልቤ አመሰገንኳቸው (በልቤ!) ከዚያ ምን እንዳልኩ ታውቃላችሁ… (አሁንም በልቤ ነው!) ፓርቲው አገሪቷን መካከለኛ ገቢ ያላቸው አገራት ላይ ለማድረስ የ40 ዓመት ሥልጣን ያስፈልገኛል ያለው ትክክል አይደለም፡፡ በጣም ተሳስቷል፡፡ ኢህአዴግ የሚያስፈልገው የ40 ዓመት ሳይሆን የ100 ዓመት ሥልጣን ነው (የአንድ ክ/ዘመን ማለት ነው!) ለምን…አላችሁኝ እንዴ? የዛሬ ሁለት ሳምንት የወጣውን አዲስ አድማስ ጋዜጣ ፈልጋችሁ አቶ ሬድዋን የተናገሩትን አንብቡ፡፡ ያኔ ነው የሚገባችሁ! እርግጠኛ ነኝ ተቃዋሚዎች ራሳቸው እሳቸው ያሉትን ካነበቡ በኋላ በምርጫ እንኳን ኢህአዴግን መፎካከር ያቆማሉ፡፡ ለምን መሰላችሁ? ኢህአዴግ በ100 ፐርሰንት ድምጽ ምርጫውን በዝረራ አሸንፎ 100 ዓመት እንዲገዛን! እኔ የምለው ግን… ይሄን ያህል ጊዜ ከኢህአዴግ የተሻለ አማራጭ እንደሌለ እንዴት መገንዘብ አቃተኝ? (ለአቶ ሬድዋን ዕድሜ ከጤና ጨምሮ ይስጥልኝ!)
እኔ የምላችሁ…እስቲ አንዲት ጥያቄ ልጠይቃችሁ፡፡ ስለ ኢህአዴግ የስልጣን መተካካት የምታውቁት ነገር አለ እንዴ? የመተካካቱን ሥርዓት መስፈርቶች ለማወቅ ፈልጌ እኮ ነው፡፡ (ይሄንንም እሳቸው ይንገሩን እንዳትሉ!)
እንግዲህ አዲሱ ትውልድ ነው ተተኪው (New blood) ሲባል የሰማሁ መሰለኝ፡፡ ግን ተሸውጃለሁ፡፡ ይሄን ደግሞ መቼ ባውቅ ጥሩ ነው፡፡ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር ሁለት ምክትል ጠ/ሚኒስትሮችን (ክላስተር ሚኒስትሮች ነው ያሏቸው?) የሾሙ ጊዜ! በቃ የዛን ጊዜ አዲሱና “አሮጌው” ትውልድ ተደበላለቀብኝ፡፡ በነገራችን ላይ በአሁኑ ጊዜ በስልጣን ላይ ያሉ የአዲሱ ትውልድ አባላት ዝርዝር ቢነገረን ከአላስፈላጊ ብዥታ ያድነናል ብዬ አስባለሁ፡፡
የዚያ ትውልድ አባላትም ዝርዝር ቢነገረን እኮ የመተካካት ሥርዓቱን በዓይነት ቁራኛ ለመከታተልና ምንም ባናደርግ እንኳ ቂም ለመያዝ ይመቸን ነበር፡፡ (የተቃዋሚዎች አያስፈልገንም!)
እናንተ …ከትላንት በስቲያ ምሽት በኢቴቪ የቀረበውን ሰበር ዜና (Breaking news) ሰምታችኋል? የመርዶ ነጋሪዎች ዜና እንዳይመስላችሁ፡፡ የስኬት ዜና ነው - የድል! ኢህአዴግ ለስንት ዓመት ከዓለም ባንክ ጋር “እመን፤ አላምንም” እየተባባሉ የቆዩበትን ጉዳይ ነው በአሸናፊነት የቋጨው፡፡ እኔ መቼም እንዴት ጮቤ እንደረገጥኩ አልነግራችሁም (ለኢህአዴግ እኮ ነው!)
እናላችሁ …ዓለም ባንክ የማታ ማታ ኢህአዴግ የሚለውን ባለሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገት እንዳለች ተቀበላታ (ኮንግራ ኢህአዴግ!) አያችሁ …እነ ዎርልድ ባንክና IMF ዕድገቱን ይቀበሉት እንጂ ሌላው ዕዳው ገብስ ነው (የእኛን ነገር ማለቴ እኮ ነው!) በድጋሚ ኮንግራ ብዬአለሁ - ለኢህአዴግ!!

Read 3868 times