Saturday, 24 September 2011 09:49

በ800 ሚ.ብር የተሰራ ሆስፒታል፤ በጎረቤት አገራትም ዝነኛ ለመሆን አቅዷል

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(1 Vote)

ህመማቸው በአገር ውስጥ ሕክምና እንደማይድን የተነገራቸው በርካታ ኢትዮጵያውያን፤ ሌላ አገር ሄደው መታከም እንደሚችሉ ሲገለላቸው ብዙም ተስፋ አይታያቸውም፡፡ በመቶ ሺ ብሮች የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚያስፈልግ ያውቃሉና፡፡ በቲቪ፣ በሬዲዮና በጋዜጣ የእርዳታ ጥሪዎችን በተደጋጋሚ የምንስማውም ያለ ምክንያት አይደለም፡፡  ..ውድ ወገኖቼ የተቻላችሁን ያህል በባንክ የሂሳብ ቁጥር እንድታስገቡልኝ በእግዚአብሔር ስም እማፀናለሁ.. ይላል ከህፃን እስከ አዋቂ በምንሰማው የድረሱልኝ ጥሪ፡፡   

እንደነዚህ አይነት በርካታ ችግሮች የሚቀርፍ፣ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያሟላ ዘመናዊ ሆስፒታል በአዳማ ናዝሬት መከፈቱን ያበስራሉ - የሆስፒታሉ ባለቤት አቶ ከቢር ሁሴን ዋቆ፡፡   
የጤና ኮሌጅን በማካተት በ813ሚ.ብር የተሰራው ዘመናዊ ሆስፒታል ባለፈው ሐምሌ ወር አጋማሽ ነው የተመረቀው፡፡  
በአርሲ፣ ኢተያ ወረዳ ከገበሬ ቤተሰብ የተወለዱት አቶ ከቢር፤ እርሻውን ከቢዝነስ ጋር በማጣመር ሃብት ለማፍራት ጥረት የጀመሩት ገና በታዳጊ እድሜያቸው ነው፡፡ ..ዝናብና ብርዱ አያስወጣም፤ ሙቀትና ቃጠሎው አያንቀሳቅስም፤ ዛሬ የዕረፍት ቀኔ ነው፤...ሳልል፣ ነጋ ጠባ፤ 4ዐ አመት ሙሉ በየእርሻ ስፍራውና በየንግድ ጣቢያው ስሰራ ኖርኩ፡፡ በረዥም ዓመት ጥረት ያፈራሁት ሀብት ዕድሜ ልኬን ያኖረኛል፡፡ አሁንስ ልረፍ፤..... አላሉም፡፡ ..ገና ምኑ ተነካና!..የሚሉ ይመስላሉ፡፡ አቶ ከቢር በአዳማ ናዝሬት የተቋቋመውን ሆስፒታል በደስታ እየተመለከቱ ራሳቸው አያስጎበኙም፡፡ ከሚያስጎበኝ ባለሙያ ጋር ያገናኛሉ እንጂ፡፡ 210 የህክምና አልጋዎችን በማሟላት አገልግሎት እየሰጠ ባለው ሆስፒታል ውስጥ ለሚሰሩ ባለሙያዎች ካላቸው ክብር የተነሳ ነው፡፡ በእርግጥም የስራ ሰው ባለሙያዎችን ያከብራል፡፡ አለበለዚያ ስኬታማ ሊሆን አይችልም፡፡ bkFt¾ የህክምናና የቴክኒክ ባለሙያዎች ነው የሆስፒታሉን ዘመናዊ መሳሪያዎች እንዲሁም አገልግሎት ክፍሎችን የጎበኘነው፡፡ በጉብኝቱ ከመደነቃችን በፊት ግን፤ ትንሽ ስለ ወጣቱ ከቢር እናውራ፡፡ አቶ ከቢር በአንዲት አነስተኛ ቤት ውስጥ የሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ የከፈቱበትን ጊዜ ያስታውሱታል - የዛሬ አርባ አመት በ1964 ዓ.ም፤ ምን ያህል ገንዘብ ይዘው ወደ ንግዱ እንደገቡም አልረሱትም - 366 ብር፡፡     
ከሁለት ዓመት በኋላ፤ በንግድ ያጠራቀሟት ገንዘብ ላይ፣ ከብት ሸጠው ጨመሩበትና ስራቸውን ለማሳደግ ወሰኑ፡፡ በሁሩታ ከተማ በአምስት ሺህ ብር የእህል ንግድና የእርሻ ስራ ጀመሩ፡፡
እንዲያም ሆኖ ወጣቱ ከቢር፤ ከንግዱና ከእርሻው ጎን ለጎን ትምህርቱንም ቸል የሚል አልነበረም፡፡ ከ12ኛ ክፍል ፈተና በኋላ፤ ንግድ ሥራ ኮሌጅ ገብተው እንደነበር የሚያስታውሱት አቶ ከቢር፣ እንደቀድሞው፣ እርሻ፣ ንግድና ትምህርት አጣጥሞ ማስኬድ እንዳልቻሉ ይናገራሉ፡፡ ስራው አርሲ፤ ትምህርቱ አዲስ አበባ ሆነና አንዱን መምረጥ የግድ ሆነ፡፡ ሥራውን በሙሉ ልብ ተያያዙት፡፡ አቶ ከቢር፤ በ1985 ዓ.ም በ170 ሚሊዮን ብር በባሌ ጉበር ባጂ እና በወለጋ አሌሊቱ መካናይዝድ እርሻ ጀመሩ፡፡ ከ8 ዓመት በፊት ደግሞ በሆለታ አካባቢ በ80ሚ.ብር የአበባ ምርት ጀምረው የውጭ ምንዛሪ እያስገኙ ነው፡፡  
አቶ ከቢር በእርሻ ኢንቨስትመንት ሆነ በእህል ንግድ ሃብት ለማፍራትና ስኬታማ ለመሆን የበቁት፤ ለሰዎች የሚጠቅም ምርትና አገልግሎት በብቃት መፍጠር በመቻላቸው ነው፡፡ ነገር ግን በቂ ሆኖ የታያቸው አይመስልም፡፡  
..ለአገርህና ለወገንህ ቋሚና ዘላቂ ነገር ትተህ እለፍ.. የሚል ሀሳብ በአእምሯቸው ለብዙ ጊዜ ሲመላለስ መቆየቱን የሚገልፁት አቶ ከቢር፤ ..በ40 የስራ አመታት ውስጥ አልፌ፤ ዕድሜና ገንዘብ ከሰጠኝ ለምን ለአገርና ለሕዝብ የሚጠቅም ቋሚ ነገር ሠርቼ አላልፍም?.. በማለት ሐሳቡን ወደ ተግባር ለመለወጥ ዘዴ ማፈላለግ ጀመሩ፡፡    
ሥራውን ከመጀመራቸው በፊት ስለሚሠራው ነገር የራሳቸውን መመዘኛ አወጡ፡፡  ..በአገራችን ከፍተኛ የሕክምና አገልግሎት አልተስፋፋም፡፡ የሚሉት አቶ ከቢር፤ ..በርካታ ሕሙማን ወደ ተለያዩ አገራት ለህክምና እየሄዱ፤ ከፍተኛ ገንዘብ ለማውጣት ይገደዳሉ.. ይላሉ - ለትራንስፖርት፣ ለሆቴል፣ ለቀለብ፣...፡፡ ታማሚዎች ብዙ ጊዜ በማያውቁት አገር እንደሚንገላቱና ይህንን ችግር የሚያቃልል ሆስፒታል ለመስራት እንደወሰኑ አቶ ከቢር ጠቅሰው ከዚህም በተጨማሪ ከውጭ አገራት በተለይም ምስራቅ አፍሪካ ታማሚዎችን ተቀብሎ እያከመ የውጭ ምንዛሪ የሚያስገኝ ይሆናል ብለዋል፡፡ ሃሳባቸው እውን እንዲሆን፤ ሆስፒታሉ ምን አይነት መሆን አለበት?
..ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ የያዘ፤ በምርጥ ባለሙያዎች የሚመራና የተደራጀ፤ ዓለም የመጨረሻ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶችንና መሳሪያዎች ያሟላ ዘመናዊ ሆስፒታል መሆን አለበት.. በማለት ወደ ተግባር ተሸጋገሩ - አቶ ከቢር፡፡  
..ይኼው ዛሬ ምኞቴ በመሳካቱ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ መሳሪያዎቹ እጅግ ዘመናዊ በመሆናቸው፣ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የተገዙ ናቸው፡፡ መንግሥት ኢንቨስተሮችን ለማበረታታትና ሕዝቡን ለመጥቀም በፈጠረው ምቹ ሁኔታ መሳሪያዎቹን ከቀረጥ ነፃ በማስገባቴ መንግሥትን አመሰግናለሁ፡፡   
ሆስፒታሉ የወገኖቼን ችግር የሚቀርፍ ብቻ ሳይሆን፤ ለምሥራቅ አፍሪካም የሚያገለግል ነው፤ በዚህም የውጭ ምንዛሪም ያስገኛል፡፡ እዚህ በመድረሴ በጣም ደስ ብሎኛል.. በማለት ተናግረዋል - አቶ ከቢር፡፡  
ከአውሮፓ እስከ አሜሪካ፤ ከአፍሪካ እስከ ጃፓን ለበርካታ አመታት በህክምና ሞያ የሰሩት የአጥንት ስፔሻሊስት ዶ/ር ኤርኒኮ ቦሲ ናቸው የሆስፒታሉ ዳሬክተር፡፡ ወደ ቢሯቸው ስንሄድ፣ መጽሐፍ ዘርግተውና የተለያዩ የሰውነት አጥንቶችን ስለው ለሥራ ባልረባቸው እያስረዱ ነበር፡፡  
..ይህ ሆስፒታል ከሌሎች መደበኛ ሆስፒታሎች ይለያል.. ያሉት ዶ/ር ቦሲ፣ ሦስት መሠረታዊ ዓላማዎች እንደያዘ ይገልፃሉ፡፡  
..ተቀዳሚው ዓላማችን ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ ያለው ሕክምና መስጠት ነው፡፡ ሁለተኛው ስልጠና የመስጠት አላማ ነው፡፡ ሥራ በሚጀምረው የጤና ኮሌጃችን ከፍተኛ ብቃት ያላቸውን ባለሙያዎች እናሰለጥናለን፡፡ ሦስተኛው አላማ፤ ጥናትና ምርምር ማካሄድ ነው - የህክምና አገልግሎታችንን በየጊዜው ለማሳደግ ይጠቅማል.. ይላሉ - ዶ/ር ቦሲ፡፡  
ሆስፒታሉ አላማዎቹን ለማሳካት በዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶችና መሳሪያዎች እንደተደራጀ ዶ/ር ቦሲ ካስረዱን በኋላ ነው፤ ከአቶ አብዲ ደረጀ ጋር የሆስፒታሉን የተለያዩ የህክምና መስጫዎችን የጎበኘነው፡፡  
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በሕክምና ላቦራቶሪ ቴክኖሎጂ ተመርቆ ለ10 ዓመት ሲሰራ የቆየው አቶ አብዲ፤ የላቦራቶሪ ክፍል ኃላፊ ነው፡፡    
..የማኅፀንና ጽንስ ህክምና ክፍላችን በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆኑ መሳሪያዎችን ያሟላ ነው.. የሚለው አቶ አብዲ፣ ብዙ ነገሮችን ለመስራት የሚያስችል ኮሎስኮፒ የተባለ መሳሪያ ስላለው፤ ወደ ኦፕራሲዮን ክፍል መሄድ የማያስፈልጋቸውን አነስተኛ ኦፕሬሽኖች ለማከናወን ያስችላል ብሏል፡፡ በኤሌክትሪክ ኃይል ከፍና ዝቅ የሚለው አልጋ ላይ የተገጠመው ዘመናዊ ማይስክሮስኮፕ ማኅፀን አፍ አካባቢ ያሉ ችግሮችን እንደሚያሳይ አቶ አብዲ ገልፆ፤ ታካሚዋ በስክሪን እያየች ትታከማለች ብሏል፡፡
ዋናው የላቦራቶሪ ክፍል ሦስት ንዑስ ክፍሎች አሉት - የፓቶሎጂ፤ የሞሎኪዩላርÂ የማይክሮ ባዮሎጂ ምርመራዎች የሚሠሩበት፡፡  
ፈረንሳይ ስሪት የሆነና ቪዳስ (Vidas PC) የተባለው መሳሪያ ኤችአይቪን ጨምሮ ሌሎች ቫይረሶችና ባክቴሪያዎችን ከደም ውስጥ እንደሚለይ ሃላፊው ይገልፃል፡፡ የካንሰር፣ የእንቅርት፣ የመካንነት፣ የልብ በሽታ ምልክቶች፣ የሆርሞን መጠን... እንደሚመረምር በመጥቀስ፡፡ መሳሪያው፣ ራሱን የቻለ የኮምፕዩተር ሲስተም እንዳለውና በአንድ ጊዜ የሚቀበለው የናሙና ብዛትም፤ እስካሁን ወደ አገር ውስጥ ከገቡት ተመሳሳይ መሳሪያዎች የተለየ እንደሚያደርገው ኃላፊው ተናግሯል፡፡   
ከዚህኛው የበለጠ ትልቅ ተመሳሳይ መሳሪያም ስላለን፣ በአንድ ጊዜ ከመቶ በላይ ምርመራዎች ማድረግ እንችላለን ይላል ሃላፊው፡፡   
..በአንድ ጊዜ 50 ናሙናዎችን የመቀበል አቅም ያለው ሲስሜክ የተሰኘው መሳሪያ በጃፓን የሚፈበረክ ሲሆን ይኼኛው ዘመነኛው ሞዴል ነው.. ብሏል ኃላፊው፡፡    
ሊካ (Leica) የተባለው የፓቶሎጂ መመርመሪያ መሳሪያ ነው፡፡ የታካሚውን የበሽታ ዓይነት ከደም ናሙና ማግኘት በሚያስቸግርበት ጊዜ፤ አካል ሳይቆረጥ፣ እንደ መርፌ ወደ ሰውነት ገብቶ የፈሳሽ ወይም ቲሹ ናሙና ተቆንጥሮ የፓቶሎጂ ምርመራ ይካሄዳል ለዚህም ሊካ የተሰኘው መሳሪያ ጥቅም ላይ ይውላል፡፡   
ባክትአለርት (3D) እና ቫይቴክ ከተሰኙት ሌሎች መሳሪያዎች በተጨማሪ፤ አውቶማቲክ የሆኑ የማይክሮ ባዮሎጂ፣ የፓቶሎጂና የሞሎኪዩላር ባዮሎጂ መሳሪያዎችም እየተተከሉ እንደሆኑ ሃላፊው ገልፀው፤ እነዚህ መሳሪያዎቹ ለዲኤንኤ ምርመራ እንደ¸ÃglGlù ለጊዜው ለሄፕታይተስ ቢ እና ሲ እንዲሁም ለኤችአይቪ ምርመራ እየተሰራባቸው ነው ብለዋል፡፡  
ሲቲ SµN:- ይህ መሳሪያ የሚሠራው በጨረር ሲሆን፣ እስካሁን ወደ አገር ውስጥ ከገቡት ተመሳሳይ መሳሪያዎች ይለያል፡፡ ቀደም ሲል የገቡት በአንድ ጊዜ አንድ ወይም ሁለት ምስል ብቻ ሲያነሱ፣ ይኼኛው እጅግ ዘመናዊ በመሆኑ፣ በአንድ ጊዜ 16 ምስሎችን በጥራት ማንሳት ይችላል፡፡
እንደ ቀድሞዎቹ በአንድ ጊዜ አንድ ወይም ሁለት ምስል ብቻ ሳይሆን 16 ምስሎችን በጥራት ማንሳት የሚችል የሲቲ ስካን ዘመናዊ መሳሪያ እንዲሁም የኤምአርአይ (MRI) መሳሪያ በሆስፒታሉ አንድ ላይ መሟላታቸው ትልቅ እርምጃ ነው ብሏል - የምስል ራጅ ክፍል ባለሙያ አቶ ቴዎድሮስ ተሰማ፡፡    
ማሞግራፊ የጡት ዕጢ (ካንሰር) ራጅ የሚያነሳ ሲሆን፣ ባዮፕሲም ይወስዳል፡፡ ፍሎሮስኮፒ ደግሞ መድኃኒት እየተሰጠ የመጣው ለውጥ የሚታይበት መሳሪያ ነው፡፡ ..ከሲቲ ስካንና ከኤምአርአይ በተጨማሪ፤ ማሞግራፊ፣ አንጆግራፊ እና ፍሎስኮፒ የተሰኙ የተራቀቁ ዘመናዊ መሳሪያዎች በመያዝ ከአገሪቱ ሆስፒታሎች የመጀመሪያው ነን.. ያለው አቶ ቴዎድሮስ፣ የኤክስሬይ እና ፍሎሮስኮፒ መሳሪያዎቹ ዲጂታል ናቸው ብሏል፡፡
የኩላሊት ስራ ሲሰናከል፤ ደም የሚያጣራ ሔሞ ዲያላይስስ የተባለ መሳሪያ እና ያለ ኦፕራሲዮን የኩላሊት ጠጠር ማፍረሻ መሳሪያዎች እንደተሟሉ የሚገልፀው አቶ አብዲ፤ ከአራት ዓመት በኋላ ኩላሊት የመተካት ቀዶ ህክምና እንደሚጀምሩ ተናግሯል፡፡  
ዶ/ር ሰለሞን ገ/ማርያም የልብ ስፔሻሊስት ናቸዉ፡፡ ለ23 ዓመታት የኖሩት ግሪክ ነው፡፡ የሕክምና ትምህርት ጀምረው ጠቅላላ ሐኪም ከዚያም ካርዲዮlÖ©þSTÂ ኢንተርቨንሽናል የሆኑት እዚያው ግሪክ ነው፡፡ አሁን በአዳማ አጠቃላይ ሆስፒታል የልብ ሕክምና ክፍል ኃላፊ ናቸው፡፡
የልብን አሠራርና ድም መስማት በሚያስችሉ ኤሌክትሮ ካርዲዮ ግራም እና ኢ.ኮ  ካርዲዮ ግራም በተባሉ እጅግ ዘመናዊ መሳሪያዎች ምርመራ እንሚካሄድ ዶ/ር ሰለሞን ጠቅሰው፣ መሳሪያው በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ ካሉ መሳሪያዎች በመጀመሪያ ደረጃ ተመራጭ የሆነ ዘመነኛ ቴክኖሎጂ ነው ብለዋል፡፡ አንጆግራፊ የደም ስሮች (በተለይ የልብ) ብቻ ምስል የሚነሳበት መሳሪያ ነው፡፡
..የመሳሪያው መኖር፣ ብቻውን ዋጋ የለውም፡፡ የመሳሪያውን አቅም አውቆ የሚጠቀምበት ባለሙያ መኖር አለበት፡፡ ሁለቱንም አሟልተን በመገኘታችን ኩራት ይሰማኛል.. ብለዋል ዶ/ር ሰለሞን፡፡    
የሆስፒታሉ የቀዶ ሕክምና ማዕከል፤ የተለያዩ ቀዶ ሕክምና የሚደረግባቸው አምስት ክፍሎች እንዳሉ፣ የማዕከሉ ባለሙያ ሲስተር ማርታ ገልጻለች፡፡  
ከበድ ያለ ቀዶ ሕክምና ሲደረግ ሐኪሙ፣ ከአውሮፓ ወይም ከአሜሪካ ታዋቂ ባለሙያዎች ጋር እየተመካከረ የሚሠራበት የቴሌ መድሲን መሳሪያ በማዕከሉ ተገጥሟል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፣ የኮሌጁ ተማሪዎች፣ ክፍል ውስጥ ሆነው የቀዶ ህክምና በቀጥታ በቪዲዮ እንዲያዩ ያስችላቸዋል፡፡
ዶ/ር አመሐ፣ የዓይን ሕክምና ክፍል ኃላፊ ሲሆኑ፣ የክፍሉ መሳሪያዎችም የዘመኑ ቴክኖሎጂ ጥበባዊ ውጤት እንደሆኑ ገልዋል፡፡ በጃፓንና በጀርመን ስሪት መሳሪያዎች የተደራጀ ስለሆነ፣ የጨረር (ሌዘር) ሕክምናን ጨምሮ ማንኛውንም ዓለም አቀፍ ደረጃ ሕክምና መስጠት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡   
..በጨረር ከሚታከሙ በሽታዎች መካከል አንዱ ከስኳር በሽታ ጋር በተያያዘ የአይን ጉዳት ነው፡፡ አጠቃቀሙ የተለየ ነው እንጂ ሌላ ትልቅ የሌዘር መሳሪያም አለን.. ይላሉ ዶ/ር አመሐ፡፡  
አቶ አብዲ፣ በመሳሪያ ብልሽት አገልግሎት በፍፁም አይቋረጥም ይላል፡፡ ..አንድ የሕክምና ተቋም የፈለገውን ያህል ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ ያላቸው መሳሪያዎች ኖሮት፣ መጠባበቂያ (ባክ አፕ) ከሌለውና በየጊዜው፣ መሳሪያው ..ተበላሽቷል፤ ጥገና ላይ ነው፣ እድሳት ላይ ነው፣..... እየተባለ አገልግሎት የሚቋረጥ ከሆነ ጥራት ያለው አገልግሎት እየሰጠ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ስለዚህ የሆስፒታሉ መሳሪያዎች በሙሉ ጥንድ ጥንድ ናቸው.. ብሏል፡፡  
የሆስፒታሉ አቅም 260 አልጋዎች ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ለሥራ ዝግጁ የሆኑት 210 አልጋዎች ናቸው፡፡ 50ዎቹ አልጋዎች በቅርቡ አገልግሎት እንደሚጀምሩና ከአራት ዓመት በኋላ ሌሎች ሕክምናዎችን ለመጀመር የማሰፋፊያ ሥራ ሲካሄድ የአልጋዎቹን ቁጥር 400 ለማድረስ መታቀዱን አቶ አብዲ አስታውቋል፡፡

Read 4186 times