የግብርና ግብአት አቅርቦትና አገልግሎት ማዕከል ከፍቷል
ሁለት ኮምባይነርና አንድ የጭነት መኪና ገዝቷል
ካፒታሉ 13.2 ሚሊዮን  ደርሷል

የግብርና ግብአት አቅርቦትና አገልግሎት ማዕከል ከፍቷል ሁለት ኮምባይነርና አንድ የጭነት መኪና ገዝቷል ካፒታሉ 13.2 ሚሊዮን ደርሷል በአካባቢው ስንዴ በብዛት ይመረታል፣ ካሁን በፊት በስሩ ካሉ መሠረታዊ የገበሬ ማኅበራት የሚሰበስበውን ስንዴ፣ በጥሬው ነበር የሚሸጠው። አሁን ግን፣ እሴት ጨምሮበት፣ ዱቄቱን ለገበያ ለማቅረብ አቅዷል፡፡ ለዚህም ይረዳው ዘንድ በቀን 800 ኩንታል ስንዴ የሚፈጭ ፋብሪካ ለማቋቋም፣ ከአንድ የቱርክ ኩባንያ ጋር ውል ተፈራርሞ፣ ኤል ሲ (ሌተር ኦፍ ክሬዲት) እየከፈተ ነው፡፡ ለዱቄት ፋብሪካው ፕሮጀክት 33 ሚሊዮን ብር መመደቡንና ለፋብሪካው ተከላ ከዶዶላ ከተማ አስተዳደር 6‚600 ካ.ሜ ቦታ በኢንቨስትመንት ማግኘታቸውን በዶዶላ ወረዳ የተቋቋመው የራያ ዋከና ገበሬዎች ኅብረት ዩኒየን ሥራ አስኪያጅ አቶ መሐመድ ዩሱፍ ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከንጉሡ ዘመን አንስቶ የግብርና ምርት ግብአት አቅርቦት በማሻሻል፣ የገበሬውን ሕይወት ለመለወጥ በመንግስት፣ በማኅበራትና በግል ድርጅቶች ጥረት ቢደረግም እስካሁን ድረስ፣ ገበሬው ዘንድ የግብርና ምርት ግብአት በስፋት ሊደርስ እንዳልቻለ፣ በንግድ እርሻ አገልግሎት ፕሮግራም፣ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ (ኢንቫይሮመንታል ስፔሻሊስት) ዶ/ር ጂሬኛ ግንደባ ተናግረዋል፡፡

መቀመጫውን ዋሽንግተን ያደረገው ሲ ኤን ኤፍ ኤ የተባለ ዓለም አቀፍ ድርጅት ላለፉት 30 ዓመታት በምሥራቅ አውሮፓ አገሮች ለገበሬዎች የምርት ግብአት ለማዳረስ ባደረገው እንቅስቃሴ ስኬታማ በመሆኑ፣ የተከበረ ስም እንዳለው ዶ/ር ጂሬኛ ገልፀዋል፡፡ ይኼው ድርጅት በአፍሪካም በተመሳሳይ የእርሻ ምርት ግብአት ለማቅረብ ዩኤስኤ አይዲን እርዳታ ጠይቆ፣ የ2 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ስላገኘ፣ በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ የሁለት ዓመት የንግድ እርሻ አገልግሎት ፕሮግራም ቀርፆ፣ በኦሮሚያ ስድስት አካባቢዎች፣ በቢሸፍቱ፣ አምቦ፣ ነቀምቴ፣ ፍቼ፣ ዶደላና ሻሸመኔ አካባቢ ነዋሪ ገበሬዎች፣ ከግል ድርጅቶችና ማኅበራት ጋር ለሙከራ የግብርና ምርት ግብአት አቅርቦት ማዕከል እያቋቋመ ነው፡፡ ከ“ራያና ዋከና ዩኒየን” ጋር በመተባበር ያቋቋመው ማዕከል፣ ባለፈው ሳምንት የተመረቀ ሲሆን ቀደም ሲልም የነቀምቴና የቢሸፍቱ ተመርቀው አገልግሎት መጀመራቸውንና የተቀሩትም ሥራቸው በቅርቡ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል፡፡

የራያ ዋከና የገበሬዎች ኅብረት ዩኒየን፣ በመጋቢት 1996 ዓ.ም፣ ከአዳባ ወረዳ ሦስት፣ ከዶዶላ ወረዳ ደግሞ ስድስት መሠረታዊ ማኅበራትና 3‚684 አባወራዎችን በመያዝ በ155ሺ ብር መነሻ ካፒታል መቋቋሙን፣ አሁን ሁለት ወረዳዎች ተጨምረው የአራት ወረዳ 65 መሠረታዊ ማኅበራት ማቀፉንና በ2004 ዓ.ም ኦዲት ሪፖርት መሠረት ካፒታሉ 13.2 ሚሊዮን ብር መድረሱን ሥራ አስኪያጁ አቶ መሐመድ ገልፀዋል፡፡ የዩኒየኑ ዓላማ፣ መሠረታዊ ማኀበራት ከአቅማቸው በላይ የሆኑትን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግር መቅረፍ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት፣ ዩኒየኑ፣ ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘር፣ ፀረ - ተባይና ፀረ - አረም ኬሚካሎችና መርጫ መሳሪያዎች፣ የተለያዩ አትክልት ዘሮች (ጥቅል ጐመን፣ ቲማቲም፣ ካሮት፣ ሽንኩርት…) የእንስሳት መድኃኒት አቅርቦትና ሽያጭ ያከናውናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ዩኒየኑ፣ መሠረታዊ ማኅበራት የሚገለገሉባቸው እያንዳንዳቸው 40 ኩንታል መያዝ የሚችሉ ሁለት ኮምባይነሮች፣ በ3 ሚሊዮን ብር ገዝቶ አቅርቧል፡፡ መሠረታዊ ማኅበራት ምርታቸውን ወደገበያ የሚወስዱበት፣ ከገበያ ደግሞ ማዳበሪያ፣ ኬሚካሎች፣ ምርጥ ዘር፣… በማመላለስ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ አይሱዙ መኪናና የዘር ማበጠሪያ አለው፡፡ እንዲሁም እያንዳንዱ መሠረታዊ ማኅበር በየዓመቱ በዩኒየኑ ወጪ ኦዲት ያስደርጋል፣ የመጋዘን አገልግሎትም ይሰጣል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ ምርጥ ዘር እያባዛ በዩኒየኑ ስም አሽጐ ያሰራጫል፡፡

“በዚህ ዓመት ግብርና መሩን ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ ለማሸጋገር እየሠራን ነው፡፡ የዚህ አካባቢ ምርት ስንዴ ነው፡፡ እስካሁን፣ ስንዴውን በጥሬው ነበር የምንሸጠው፡፡ አሁን ግን አስፈጭተንና እሴት ጨምረን ዱቄት ለማቅረብ ወስነናል፡፡ በዚሁ መሠረት ፋብሪካውን የምንተክልበት 6‚600 ካ.ሜ ቦታ ከዶዶላ ከተማ አስተዳደር በኢንቨስትመንት ተረክበናል፡፡ በቀን 800 ኩንታል የሚፈጭ ወፍጮ ለመትከል፣ ከቱርክ ኩባንያ ጋር ውል ተፈራርመን ኤል ሲ (ሌተር ኦፍ ክሬት) እየከፈትን ነው፡፡ ይህም፤ 33 ሚሊዮን ያህል ብር የሚፈጅ ትልቅ ፕሮጀክት ነው” ብለዋል አቶ መሐመድ፡፡ ቀደም ሲል ዩኒየኑ የአባላትን ምርት የሚሸጠው ለተለያዩ ድርጅቶች ነበር፡፡ ዘንድሮ ግን ለኢትዮጵያ እህል ንግድ ድርጅት 9ሺ ኩንታል ስንዴ ለማቅረብ ተስማምተውና አብዛኛውን ማለትም 8‚500 ኩንታል አቅርቧል። ቀሪውን 500 ኩንታል ሲያስረክቡ አዲስ ውል እንደሚፈራረሙ ተናግረዋል፡፡ ሌላው አቶ መሐመድ ለዩኒየኑ ትልቅ ስኬት ነው ያሉት፣ ከዩኤስኤ አይዲ የግብርና ንግድ አገልግሎት ፕሮግራም ጋር በግብርና ምርት ግብአት አቅርቦት ዙሪያ በጋራ ለመሥራት መዋዋላቸውን ነው፡፡ በስምምነቱ መሠረት፤ ዩኤስኤ አይዲ 40ሺ ዶላር ሲያወጣ፣ እኛ ደግሞ ከዚያ በላይ እናወጣለን። እኛ በ750ሺ ብር ያህል የግብአት መሸጫ ማዕከል ሠርተናል፡፡ እነሱ፣ የላቦራቶሪ ዕቃዎች፣ ኮምፒዩተር፣ ፍሪጅ፣ ጠረጴዛና ወንበር፣ የመድኃኒትና መደርደሪያ ያሟሉ ሲሆን እዚያ ውስጥ ለሚሠሩ አራት ባለሙያዎች የሁለት ዓመት ደሞዝ ይከፍላሉ፡፡

ገበሬው ከዚህ ማዕከል የሚያገኘው ጥቅም ብዙ ነው፡፡ ቀደም ሲል የምርት ግብአቶችን ከተለያዩ አቅራቢዎች ለመግዛት ሲያፈላልግ ብዙ ጊዜ ያባክን ነበር፡፡ እንደዚያም ሆኖ የሚገዛው የእርሻ ግብአት ዋጋው ውድና ጊዜው ያለፈበት ሊሆን ይችላል። አሁን ግን ግብአቶቹን ፍለጋ ሳይንከራተት፣ የሚፈልጋቸውን ግብአቶች፣ በተመጣጣኝ ዋጋ በአንድ ማዕከል ያገኛል፡፡ ምርጥ ዘር፣ ፀረ - አረም፣ ፀረ - ዋግ፣ ፀረ - ተባይ፣ የተለያዩ አትክልት ዘሮች እንዲሁም የእንስሳት መድኃኒቶች ገዝተን እናቀርባለን፡፡ እኛ ቀደም ሲልም የምርት ግብአቶችን እናቀርብ ነበር፡፡ አሁን እነሱ ያቀረቡልን ለየት ያለ ነገር የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር ነው፡፡ አሁን ገበሬው ግብአቶቹን መግዛት ብቻ ሳይሆን እንዴት መጠቀም እንዳለበት እንዲሁም ማድረግ ስላለበት ጥንቃቄ እናሰለጥነዋለን፡፡ በተግባርም እናሳየዋለን፡፡ ዩኤስኤአይዲ እያደረገ ያለው መንግሥት፤ በእርሻ ዘርፍ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያደርገውን ጥረት መደገፍ ነው እንጂ ይህ የግብርና ንግድ አገልግሎት ፕሮግራም ራሱን ችሎ ብቻውን የሚንቀሳቀስ አይደለም ያሉት ዶ/ር ጂሬኛ፤ በፊት የእርሻ ግብአቶች በተለያዩ የግል ድርጅቶች በችርቻሮ ይቀርብ ነበር። በዚያ አሠራር፣ ግብአቱ ገበሬው እጅ እስኪገባ ድረስ ሰንሰለቱ ረዥም በመሆኑና ብዙ አቀባባይ ነጋዴዎች ስላሉ ምርቱ ገበሬው ጋ ሲደርስ ዋጋው በጣም ይወደድ ነበር፡፡ የሲ ኤፍ ኤስ ፒ ጥረት ይህን ሰንሰለት አስቀርቶ፤ ግብአቶቹን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማድረግ ነው ብለዋል፡፡ ፀረ - ተባይ በአጠቃላይ መርዝ ነው፡፡ ገበሬው የእነዚህን ኬሚካሎች አጠቃቀምና የአያያዝ ጥንቃቄ ስለማያውቅ፣ ገዝቶ ቤቱ ከደረሰ በኋላ የተወሰነውን በእጁ በጥብጦ በለበሰው ልብስ ይረጫል፤ የተወሰነውን ቤቱ ላይ አንጠልጥሎ ያስቀምጣል፣ ዛሬ የገዛውን እያስቀመጠ ለዓመታት ይጠቀማል። ይህ ሁኔታ ያስከተለው ችግር በአገር አቀፍ ደረጃ አልተጠናም፡፡

የተፈለገው ምርታማነት ግን ሲቀንስ እንጂ ሲጨምር አይታይም፡፡ ገበሬው በብዙ ቦታ ፀረ ተባይ መያዣዎችን ውሃ ይጠጣበታል፡፡ ዘይት ይገዛበታል፣ ለተለያየ አገልግሎት ይጠቀምበታል፡፡ የጥንቃቄ አያያዝና አጠቃቀሙን አያውቅበትም፡፡ ይህ ፕሮግራም መደረግ ያለበትን አጠቃቀም አያያዝና አወጋገድ ያስተምራል፤ ያሰለጥናል፡፡ ከተለያዩ የመንግሥት አካላት ጋር በመሆን፣ ወደ አገር ውስጥ የሚገቡትን ፀረ - ተባይ ኬሚካሎች፣ በተለያዩ ምድቦች በመክፈል “እነዚህን ገበሬው በቀላሉ ሊጠቀም ይችላል፣ እነዚህን ደግሞ መከላከያ ሳያደርግ ገበሬው እንዳይጠቀም፣ መጠቀም ካለበት ደግሞ ራሱንና አካባቢውን ከጉዳት ለመጠበቅ ቅድመ ዝግጅት ያድርግ፡፡ ያ ካልሆነ በጣም መርዛማ የሆነ ፀረ - ተባይ፣ ገበሬ እጅ እንዳይገባ ሙከራ እያደረግን ነው። ለሙከራ በመረጥናቸው ማዕከላት ለምሳሌ በዶዶላ አካባቢ፣ ማንበብና መረዳት የሚችሉ ሰዎችን መርጠን፣ ሥልጠና እንሰጣለን፡፡ እነዚህ ሰዎች መርዛማነታቸው ከፍተኛ የሆኑ፣ በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ ፀረ - ተባይ እና ፀረ - አረም ኬሚካሎችን እነሱ ብቻ ለገበሬው እንዲረጩ፣ ከረጩም በኋላ መያዣዎቹን ወደ ማዕከሉ መልሰው እንዲያቃጥሉ ማዕከሉ ያስተምራል፣ ያሰለጥናል፡፡ በዶዶላ ማዕከል የሚመረቱ ምርጥ ዘሮችን ወደ አምቦ፣ ከዚያ ደግሞ ወደዚህ እንዲለዋወጡ እናደርጋለን፡፡ በተመጣጣኝ ዋጋ ምርታቸውን የሚሸጡት ማዕከላት፣ በውጭ አገራት በውድ ዋጋ የሚሸጡትን ኬሚካሎች መግዛት አይችሉም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ማዕከላት ተደራጅተውና የራሳቸው ኮኦፕሬቲቭ ፈጥረው የግል አትራፊ ድርጅቶች ሳይገቡበት ፀረ - ተባይ፣ ፀረ - አረም ኬሚካል፣ ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ከውጭ ማስመጣት ሲችሉ ዋጋው ይቀንሳል፡፡

ማዕከላቱን ከከፈትን በኋላ በቀጣይ ራሳቸው አስመጪ እንዲሆኑ እየጣርን ነው፤ የግብርና ንግድ አገልግሎት ፕሮግራምም ለዚህ በጀት የመደበ ስለሆነ እንሠራበታለን በማለት ዶ/ር ጂሬኛ ግንደባ፤ ስለ ግብርና ምርት ግብአት አቅርቦት ዓላማና አሠራር አስረድተዋል፡፡ የዶዶላው የግብርና ምርት ግብአት አቅርቦት ማዕከል ሲመረቅ፣ የዩኤስኤአይዲ ተወካይ አቶ ፋሲካ ጅፋር፤ አርሶ አደሮች ምርት የሚያሳድጉባቸው እንደምርጥ ዘር ማዳበሪያ፣ የፀረ ተባይ መከላከያ፣ የእንስሳት ሕክምና አገልግሎት፣ የዘመናዊ መገልገያ መሳሪያዎች አቅርቦት ያለመሟላት በግብርናው ዘርፍ ላይ ተጽእኖ እንዳላቸው ጠቅሰው፤ በሙከራ ላይ ያሉት የግብአት አቅርቦት ማዕከላት በሙሉ አቅማቸው መሥራት ሲጀምሩ ከፍተኛ ጥራትና ተመጣጣኝ ዋጋ ያላቸው የምርት ግብአቶች እንደሚያቀረቡ፣ ስልጠናና ሙያዊ ምክር በመስጠትና የገበያ ትስስር በመፍጠር 30ሺ ያህል አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል። ይህ የሙከራ ፕሮጀክት ውጤታማ ከሆነ፣ በሌሎች የአገሪቷ ክፍሎች በአማራ፣ በትግራይና በደቡብ ተመሳሳይ ፕሮጀክቶች እንደሚጀመሩ አስታውቀዋል፡፡

           ትግራይ ውስጥ በአክሱም አውራጃ ናአዲር በሚባል ወረዳ በ1950 ዓ.ም ነው የተወለዱት። የገበሬ ቤተሰብ ልጅ ቢሆኑም አባታቸው ንግድ ሥራም ይሞክሩ ነበር፡፡ የ10 ዓመት ልጅ እያሉ ከትግራይ ወደ አዲስ ዓለም መጡ፡፡ በመቀጠል ወደ ጅማ አቀኑ፡፡ ሦስተኛው ማረፊያቸው አዲስ አበባ ሆነ፡፡ በልጅነታቸው ከሥራ ጋር መተዋወቅ ሲጀምሩ ሱቅ እያፀዱ በወር 3 ብር ይከፈላቸው ነበር፡፡ በሥራው እያደጉ ሲመጡ በሳምንት 3 ብር ይከፈላቸው ጀመር። እየቆዩ ሲሄዱ በወርቅና ብር ሥራ ላይ የተሰማሩ ቤተሰቦቻቸውን በመጠጋት፣ ከ6 ዓመት ጥረት በኋላ የራሳቸውን ጠረጴዛ ይዘው መሥራት ጀመሩ፡፡ “በአገራችን ሁሉም ሰው ወርቅ ነጋዴ ነው” የሚሉት አቶ ገብረሥላሴ ኪዳኔ፤ የወርቅና ብር ሥራ ጠባቂ ስላጣ ከሚጠፉ ሙያዎች አንዱ ሆኗልም ይላሉ፡፡ ወጣትነትዎን ባሳለፉባት አዲስ አበባ ምን ልዩ ትዝታ አለዎት? መኖሪያዬ ጣሊያን ሠፈር የነበረ ቢሆንም በጽዳት ሥራ ጀምሬ ወደ ወርቅና ብር ሥራ ያደግሁት መርካቶ ውስጥ ነበር፡፡

በ1970 ዓ.ም ለወርቅ ፈርጥ እንድገዛ ተልኬ በወጣሁበት ተይዤ፤ በኢህአፓነት ተወንጅዬ ለ4 ወር ከታሰርኩ በኋላ የሚመሰክርብኝ ስላልተገኘ ተለቅቄያለሁ፡፡ በሌላ ጊዜ ደግሞ ሠራተኞች እንዲደራጁ ሲፈቀድ፣ አሰሪያችን መደራጀታችንን በመጥላቱ፣ በሐሰት ክስ በፍርድ ቤት አስመስክሮብኝ፣ የ6 ወር እስር ቢወሰንብኝም ከ4 ወር በኋላ ተፈትቻለሁ፡፡ በዚያ ዘመን የፍርድ ቤት እስረኛ ዕድለኛ ነው ተብሎ ይታይ ነበር፡፡ ምክንያቱም ያለ ፍርድ የሚታሰሩና የሚፈቱበትን ጊዜ የማያውቁ ብዙ እስረኞች በተለያዩ ቦታዎች ነበሩ፡፡ በዘመኑ በወርቅና ብር ሥራ ላይ የተሰማሩ ስንት ማህበራት ነበሩ? የአሰሪዎች ማህበር አንዱ ነው፤ ሁለተኛው የሠራተኞች ማህበር ሲሆን ሌላኛው የሕብረት ሥራ ማህበር ነበር፡፡ ሦስተኛው ማህበር የወርቅና ብር ሥራ ሙያ ያላቸው በጋራ በመሰባሰብ የመሰረቱትና አሁን ፒያሳ ጣና ወርቅ ቤት በሆነው ሱቅ ውስጥ ተሰባስበን፤ የየራሳችንን ጠረጴዛ በመያዝ፣ በሙያው የምንተዳደር ሠራተኞች ነበርን፡፡ የዚያ ማህበር አባል የሆንኩት በሐሰት ተፈርዶብኝ፣ የእስር ጊዜዬን አጠናቅቄ ከወጣሁ በኋላ ነበር፡፡ በማህበሩ ውስጥ እስከ 1978 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ ኃላፊነቶችም አገልግያለሁ፡፡

ከዚያ በኋላ የግለሰቦችን ቤት እየተከራየሁ፣ በራሴ ሱቅ በመሥራት እስካሁን በሙያው ዘልቄያለሁ፡፡ የማህበራቱ ዕጣ ፈንታ ምን ሆነ? የሠራተኞች ማህበር ብዙ ክሶች ነበሩት፤ የሕብረት ሥራ ማህበሩም ከባንክ ዕዳ ጋር በተያያዘ ፈርሷል፡፡ የአሰሪዎች ማህበር አሁንም ያለ ይመስለኛል፡፡ በኋላ የተመሠረተው የወርቅና ብር ሠሪዎች ማህበርም አለ፡፡ በአዲስ አበባ ምን ያህል የወርቅና ብር መሸጫ መደብሮች አሉ? “ኢትዮ ዕደ ጥበብ የማዕድናት ንግድ ሥራ አክስዮን ማህበር”ን በ1998 ዓ.ም ስንመሰርት ባገኘነው መረጃ፤ በከተማው ውስጥ 300 የሚደርሱ የወርቅና ብር መስሪያና መሸጫ መደብሮች ሲኖሩ፣ በአንጥረኝነት ሙያ ላይ የተሰማሩት ሰዎች በ10ሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ የእኔ ሱቅ በሚገኝበት ገዳም ሠፈር ብቻ 50 እና 60 የሚሆኑ ባለሙያዎች በየቤታቸው የወርቅና ብር ሥራ አገልግሎት ይሰጣሉ። እንዲህ በየቤቱ የሚሰሩት በአገር አቀፍ ደረጃ ጥናት ቢደረግ፣ በ100ሺዎች የሚቆጠሩ ይሆናሉ የሚል ግምት አለኝ፡፡ ከዚህ ውስጥ ዘጠና ከመቶ የሚሆኑት የትግራይ ተወላጆች ናቸው፡፡ ወርቅና ብር አንጣሪዎች የትግራይ ሰዎች ባይሆኑ እንኳን ሙያውን ከትግራይ ሰዎች ተማርነው ማለታቸው አይቀርም፡፡

የትግራይ ባለሙያዎች የዕውቀት መነሻ ምንድነው? በአፈ ታሪክ እየተነገረ እንደመጣው ከሆነ፣ ከንጉስ ሰለሞንና ንግስት ሳባ የሚወለደው ቀዳማዊ ምኒልክ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣ ሁሉም እስራኤላዊ የበኩር ልጁንና ከየሙያው ዘርፍ አንዳንድ ሰው እንዲሰጠው ሲወሰን፣ አብረው ከመጡት መሐል አንጥረኞችም ስለነበሩበት፣ ያ ታሪክ መነሻ ሆኖ ነው ትግራይ የወርቅና የብር ሥራ ባለሙያዎች መፍለቂያ የሆነችው፡፡ ወርቅ እንዴትና ከየት ተገዝቶ ነው በተለያየ መልኩ ተሰርቶ በየወርቅ መደብሩ የሚሸጠው? እስከ 2001 ዓ.ም ድረስ በአገራችን የከበሩ ማዕድናት ግብይት እንዴት መከናወን እንዳለበት የሚመራ ሕግ ስላልነበረ፣ የወርቅ ዋነኛው ምንጭ ሕብረተሰቡ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በእኛ አገር ነጋዴው፣ የቤት እመቤቶች፣ ሹፌሮች፣ ባለሆቴሎች፣ የቡና ቤት ሴቶች…ሁሉም ሕጋዊ ፈቃድ የሌለው የወርቅ ግብይት እርስ በእርሱ እያከናወነ ለዘመናት ዘልቋል። ብሔራዊ ባንክ ወርቅ መግዛትና መሸጥ የጀመረው በቅርቡ ነው፡፡ የዓለም የወርቅ ዋጋ በመገናኛ ብዙኃን መነገር የጀመረው አሁን ነው፡፡ የ”ኢትዮ ዕደ ጥበብ ማዕድናት ንግድ ሥራ አክስዮን ማህበር” መመሥረት መንግሥት ሕግ እንዲያወጣና በዘርፉ ያለውም ክፍተት እንዲደፈን አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡

ማህበሩ በዚህ ዘርፍ ያደረገው አስተዋጽኦ ምን ነበር? ማህበሩን መሥርተን በ1999 ዓ.ም ተግባራዊ እንቅስቃሴ ስንጀምር ከብሔራዊ ባንክ፣ ከጉምሩክ ባለስልጣን፣ ከንግድና ከማዕድን ሚኒስቴር ጋር ተቀራርበን መነጋገር ጀመርን፡፡ “ወርቅ በሕጋዊ መንገድ ከውጭ ወደ አገር ውስጥ ለምን አይገባም?” የሚለውን ጥያቄ ያቀረብነው በዚያ አጋጣሚ ነው። ብሔራዊ ባንክም ወርቅ እንዲሸጥልን ጥያቄ አቀረብን፡፡ ከዚህም ባሻገር ከፊታችን የሚመጣ የሚሌኒየም በዓል ስለነበር፣ በሕጋዊ መንገድ የምንገዛውን ወርቅ ወደ ዱባይና ጣሊያን ወስደን የተለያዩ ጌጣ ጌጦችን አሰርተን፣ ወደ አገር ውስጥ በማስመጣት ለሚሌኒየም በዓሉ ለሽያጭ እናቅርብ ብለንም ጠየቅን፡፡ “ጥያቄያችሁን በምን ሕግ እናስተናግደው?” የሚለው ምላሽ፤ ችግሩን ለመቅረፍ ተጨማሪ ጥረት ማድረግ እንዳለብን አመለከተን፡፡ ለሚመለከታቸው የባለስልጣንና ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ደብዳቤዎች መፃፋችንን ገፋንበት፡፡ በግንባር እየተገኘንም ለማስረዳትና ለማሳመን ጥረት አደረገን፡፡ እንዲህም ሆኖ አንዱ አካል ከገደብ ጋር የፈቀደልንን ሌላው አካል ሙሉ ለሙሉ እንደከለከለን ስናስተውል፣ ዋናው ችግር የሕግ አለመኖር ስለሆነ፤ በአዲስ አበባ ከተማ የሚኖሩና በአንጥረኝነት ሙያ የተሰማሩትን ስብሰባ ጠርተን፣ ከመንግሥት ጋር የምንወያይበትን መድረክ አመቻቸን፡፡ በውጤቱም “የከበሩ ማዕድናት ግብይት አዋጅ” በ2001 ዓ.ም ለመውጣት ቻለ፡፡ ይህ ሕግ ባለመኖሩ ምክንያት ለሚሌኒየም በዓል ያሰብነውን ታላቅ ስራ ተግባራዊ ሳናደርግ ቀረን፡፡

ለሥራው የማህበራችን አባላት 3 ማሊዮን ብር አዋጥተው ነበር፡፡ ማህበሩ የተቋቋመበት ዓላማዎች ምን ነበሩ? የከበሩ ማዕድናት የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴን ማስቆም፣ ሙያውን ማስፋፋት፣ ሕጋዊ ከለላና ጥበቃ እንዲኖረው ማድረግ፣ ማምረቻ ፋብሪካ መክፈት፣ ለሥራው የሚያገለግሉ ማሽኖችን ማስመጣት፣ ሙያው ትውልዶች እንዲቀባበሉት ትምህርት ቤትና ማሰልጠኛ መክፈት…በሚሉ ዓላማዎች ነው የተቋቋመው፡፡ እስካሁን ከዓላማዎቹ የተወሰኑትን አሳክቷል፡፡ 777 ሜትር ካሬ መሬትና ቤት ፒያሳ ላይ ገዝቷል፡፡ ለሥራው የሚሆኑ ማሽኖች ባለቤትም ሆኗል፡፡ በዱባይ የወርቅ ፋብሪካ የነበራቸው አንድ ኢትዮጵያዊና ሕንዳዊያን በዘርፉ ለመስራት ማሽኖቻቸውን ጭምር ነቅለው ይዘው ቢመጡም እኛን አላሰራ ያለን የሕግ አለመኖር እነሱንም ለፈተና ዳረጋቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ማሽኑን ሸጡልን፡፡ ዝርዝር ታሪኩ ብዙና ሰፊ ቢሆንም በሂደት የእኛ ማህበር አባል ሆኑ፡፡ በዚህም ምክንያት የማህበራችን መጠርያ ሥም “አዲስ የወርቅና ብር ጌጣጌጥ ፋብሪካ ኃ.የተ.የግ.ማህበር” ተባለ፡፡ በኋላ ሕንዳዊያኑ አንዳንድ ችግር ፈጥረው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ስናመራው፣ የማሽናቸውን ዋጋ ጠይቀው፣ ተከፍሏቸው ወደ አገራቸው ሄዱ፡፡ እስከዚህ ጊዜ ድረስ እኔ የማህበሩ ዋና ሥራ አስኪያጅ ነበርኩ፡፡ ሙያውን ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት የማቋቋም እቅዳችሁ ምን ደረሰ? የሕንዶቹን ከመግዛታችን በፊት የወርቅና ብር መስሪያ ማሽኖችን ከውጭ ለማስመጣት ጥናት አሰርተን ነበር፡፡ የምናስመጣውን ማሽን ለማስተከል ያቀድነውም በትግራይ ክልል ነበር።

ይህንን ያሰብነው በሁለት ምክንያት ነው፡፡ አንደኛው ምክንያት የሙያው መነሻ ስፍራ በመሆኑ ነው። ሁለተኛው ምክንያት ፋብሪካውን እዚያ ከፍተን ትምህርትና ስልጠና ለመስጠት መንቀሳቀስ ብንጀምር፣ ለማሰልጠንም ለመሰልጠንም ፍላጐት ያላቸው ብዙ ሰዎችን እናገኛለን በሚል ነበር፡፡ ይህንን ተሞክሮ ያገኘነው ደግሞ ጣሊያንን በጐበኘንበት ጊዜ ነው፡፡ በጣሊያንም ለአንጥረኝነት ሙያ መነሻ የሆነች ከተማ አለች፡፡ በዚህ ምክንያት ከተማዋን ላይ ሙያውን ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት አላቸው፡፡ የጣሊያኗን ከተማና ትግራይን እህትማማች ከተሞች የማድረግ እቅድ ሁሉ ነበረን፡፡ ሃሳባችንን ተግባራዊ ማድረግ ችለን ቢሆን ኖሮ በጥፋት ላይ ያለ አንድ ሙያን እንታደግ ነበር፡፡ ሙያው እየጠፋ ስለመሆኑ ማስረጃችሁ ምንድን ነው? የአክሱም፣ የጐንደር…የሚል መለያ ያላቸው መስቀሎች፣ የአንገትና የጆሮ ጌጦች ነበሩ፡፡ እነዚህ ሥራዎች በአገር ውስጥ ጥበቃ የሚያደርግላቸው ባለመኖሩ፣ ዲዛይናቸው ወደ ውጭ እየሄደ በአርቴፊሻል ጌጣ ጌጥ ጭምር ተሰርተው እየመጡ ገበያውን አጥለቅልቀውታል፡፡ ይህ ደግሞ ሙያው እየጠፋ መሆኑን ያመለክታል፡፡ የሹራብ ሥራም እንዲህ ቀስ በቀስ ነው እየጠፋ ያለው፡፡ ዛሬ በጣት የሚቆጠሩ ሹራብ ሰሪዎች፤ ለትምህርት ቤቶች የሚሆኑ ሹራቦችን እየሰሩ ሲሆን ገበያውን የተቆጣጠረው ግን የቻይና ምርት ሆኗል። ለሹራብ አምራቾች ማህበር በተሰጠው የኮልፌ የንግድ ቦታ ሹራብ አምራቾችን ማግኘት እያስቸገረ ነው፡፡ የወርቅና ብር ሥራም ሕጋዊ ከለላና ጥበቃ ስላልተደረገለት፣ በመጥፋት ሂደት ላይ ነው ያለው፡፡ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ውስጥ እንኳን አልተካተተም። አንጥረኝነት ሙያ በመጥፋት አደጋ ላይ ስለመሆኑ ከዚህ በላይ ምን ማስረጃ ያስፈልጋል?

Published in ህብረተሰብ

እ.ኤ.አ በ2015/ አለም አቀፉ ህብረተሰብ መሻሻል ሊያሳይባቸው ካሰባቸው 8/ ነጥቦች አንዱ የእናቶች ሞት መጠንን ከነበረበት በ3/4ኛ መቀነስ ነው፡፡ ይህንን እቅድ ማሳካት ኢትዮጵያን ጨምሮ ለብዙ ሀገራት የቤትስራ በመሆኑ እረፍት የለሽ እንቅስቃሴ እየተደረገበት ይገኛል፡፡ ለመሆኑ በኢትዮጵያ ያለው አሰራር ምን ይመስላላ በሚል በፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሚመለከታቸውን ባለሙያዎች ለዚህ እትም ጋብዘናል፡፡
ዶ/ር ማርታ ምንውየለት በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር  የእናቶችና ሕጻናት ዳይሬክቶሬት ምክትል ዳይሬክተርና ዶ/ር ኢክራም መሃመድ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር  የእናቶችና ሕጻናት ዳይሬክቶሬት የእናቶች ጤና ኬዝ ቲም ኦፊሰር በአገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የእናቶች ሞት ምክንያት የማወቅ አሰራር እንደሚከተለው ያብራራሉ፡፡
ዶ/ር ኢክራም መሐመድ እንደሚሉት “...ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶችን እና ህጻናትን ጤና ለማሻሻል የተለያዩ የአሰራር ዘዴዎችን ቀርጾ እየተገበረ ይገኛል፡፡ ለዚህም በከፍተኛ ሁኔታ የእናቶችን ሞት ምንነት ለማወቅ ይረዳል ተብሎ የታመነበት አዲስ አሰራር የእናቶች ሞት ቅኝት እና ተገቢው ምላሽ የሚባል አሰራር ነው፡፡ ይህም ማለት አንዲት እናት በአንድ አካባቢ በምትሞትበት ጊዜ በአካባቢው ከሚገኙ ሰዎች አንዳቸው ለጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛዋ ሪፖርት ያደርጋሉ፡፡ የጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛዋ ያለውን ሁኔታ በስፍራው በመገኘት ካጣራች በሁዋላ ወደጤና ጣብያ በመሄድ እሪፖርት ታደርጋለች፡፡ በጤና ጣያ ደረጃ ከደረሰ በሁዋላ በተቋቋመው ኮሚቴ ሁኔታውን በመመልከት የሞተችው እናት ጉዳይ ደረጃ በደረጃ ማለትም ወደዞን ከዚያም ወደፌደራል ይተላለፋል፡፡ የዚህ አሰራር ጥቅም 1/ ምን ያህል እናቶች እንደሞቱ ለማወቅ  2/ የሞት ምክንያቱ ከታወቅ ወደፊትም ሌሎች እንዳይጎዱ እርምጃ ለመውሰድ 3/ በጤና ጣቢያ ደረጃ ሊሰሩ የማይችሉትን በዞን ወይንም በወረዳና በክልል እንዲሰራ ማስቻል ነው፡፡  
ዶ/ር ማርታ ምንውየለት እንደሚሉት “... በእድሜዋ ከ15-49 አመት ያለች ሴት ስትሞት የጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛዋ ለጤና ጣብያ ሪፖርት ታደርጋለች፡፡ በጤና ጣብያ ይህንን ጉዳይ ለመከታተል ብቻ የተቋቋመው ኮሚቴ የሞት ምክንያቱን ለማወቅ ከጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛዋ ያገኘውን መረጃ በመያዝ ወደስፍራው ያመራል፡፡ ይህ ስራ የሚሰራው የአካባቢውን ነባራዊና ባህላዊ ሁኔታ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት እንጂ ከባድ ሀዘን ላይ ሆነው ወይንም በድንገት አይደለም፡፡ የኮሚቴው አባላት ወደስፋራው ከደረሱ በሁዋላ በሚያነሱዋቸው ጥያቄዎች መሰረት የተከሰተው ሞት የእናት ሞት ነው? ወይንስ አይደለም የሚለውን ይለያሉ፡፡ የእናት ሞት ማለት አንዲት ሴት ነፍሰ ጡር ሆና ወይንም በወለደች በስድስት ሳምንት ውስጥ የሚከሰት ሲሆን ከእርግዝናው ጋር በቀጥታ በተያያዘ ወይንም ሌሎች ተያያዥ የሆኑ ሕመሞች ተባብሰው ለሞት ያበቋት ከሆነ ተጣርቶ ይመዘገባል፡፡ በእርግጥ ከአሁን ቀደምም የእናቶች ሞት የሚመዘ ገብበት አሰራር የነበረ ቢሆንም አሁን የተነደፈው ስልት ግን ዛሬ አንዲት እናት የሞተችበት ምክንያት ነገ ለሌላ እናት ሞት ምክንያት እንዳይሆን እርምጃ ለመውሰድ በሚያ ስችልበት መንገድ የሚመዘገብ በመሆኑ አሁን የተዘረጋው አሰራር ይበልጥ ጠቃሚ ነው፡፡”
ዶ/ር ኢክራም መሐመድ በኢትዮጵያ በአገር አቀፍ ደረጃ ለእናቶች ሞት ምክንያት ናቸው ተብለው የተመዘገቡትን እንደሚከተለው ገልጻለች፡፡
“...የእናቶች ሞት ምክንያት ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆነ በሚል በሁለት ይከፈላል፡፡ ቀጥተኛው የእናቶች ሞት ምክንያት ከእርግዝና ጋር የተገናኘ ሲሆን ይህም ከእናቶች ሞት ውስጥ ወደ 85% የሚሆነውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ይህም ሲዘረዘር፡-
የተራዘመ ምጥ 13%
የማህጸን መተርተር ወደ 12%
በእርግዝና ወቅት ከሚከሰቱ የደም ግፊት ጋር በተያያዘ ወደ 11%
ከውርጃ ጋር በተያያዘ ወደ 6%
ከወሊድ በሁዋላ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች ወደ 5%
ከወሊድ በፊት ደም መፍሰስ 5%
ሌሎች ምክንያቶች ወደ 9% ይደርሳሉ፡፡
ቀጥተኛ ያልሆነ የእናቶች ሞት ሲባል አንዲት እናት ቀደም ሲል ሕመም የነበራት ሆኖ ነገር ግን በጽንሱ ምክንያት ከተባባሰ ደረጃ በመድረስ ለህልፈት ሲዳርጋት ነው፡፡ እነዚህ ሕመሞችም በመቶኛ ሲሰሉ፡-
ኤችአይቪ ኤይድስ ወደ 4%
የደም ማነስ 4%
ወባ 9% ናቸው፡፡
እናቶችን ለሞት እንዲበቁ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ተብለው የተመዘገቡ ደግሞ ሶስት መዘግየቶች አሉ፡፡
እናቶች ወይንም የትዳር ጉዋደኞቻቸው እንዲሁም በቅርብ የሚገኙ ቤተሰቦች በጤና ተቋም የመጠቀምን ጥቅም በሚመለከት ግንዛቤ ማጣት፣
አንዲት እናት ወደጤና ተቋም በተገቢው ሰአት አለመድረስ (የትራንስፖርት እጥረት የመንገድ አለመኖር ወይንም የገንዘብ እጥረት) በመሳሰሉት ምንያቶች፣
አንዲት እናት ወደጤና ተቋም ከደረሰች በሁዋላ የሚያጋጥሙዋት መዘግየቶች... በቂ የሆነ የሰው ኃይል እጥረት ...ወዘተ...”
ከላይ የተዘረዘሩትን ነጥቦች ለማስወገድ ወይንም እናቶች ሞት እንዳይገጥማቸው ለማድረግ ያለውን አሰራር ዶ/ር ማርታ ሲገልጹ ...
“...ዋናው በአገር አቀፍ ደረጃ እየተሰራበት ያለው ጉዳይ ህብረተሰቡ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚነትን አስፈላጊነት እንዲያውቅ ማድረግ ነው፡፡ ያ ማለትም ህብረተሰቡ ወይንም እናቶች በጤና ተቋም የመውለድን ጥቅም እና አስፈላጊነት ከተረዱ ሁሉም እናቶች በሰለጠነ የሰው ኃይል ስለሚወልዱ በከፍተኛ ደረጃ ለሚጠበቀው የእናቶች ሞት መቀነስ ያግዛል፡፡ ይህንንም ለማድረግ... የጤና ልማት ሰራዊት የአንድ ለአምስት ትስስር እና የጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኞች አሉ፡፡ እነዚህ አካላት 2500 /ሁለትሺህ አምስት መቶ/ በሚሆኑ የህብረተሰብ አባላት ዙሪያ በመሆን በማስተማርና የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ በሙሉ ተሳትፎ ይሰራሉ፡፡ ህብረተሰቡ መረዳት ወይንም ማወቅ የሚፈልገውን ነገር በየሳምንቱ ወይንም በየአስራ አምስት ቀኑ ከጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኞች ጋር በመገናኘት ግንዛቤያቸውን ያዳብራሉ፡፡ በዚህ የተቀናጀ አሰራር የአካባቢው ሰዎች በመሀከላቸው እርጉዝ ሴት ካለች ወደህክምና ተቋም በመሄድ ክትትል እንድታደርግ ሀሳብ ያቀርባሉ... የተወለዱ ልጆች ካሉ የእናቱን ጡት እንዲጠባ እንዲሁም ክትባት በወቅቱ እንዲያገኙ ያደርጋሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የቤተሰብ እቅድ መጠቀም ያለባት ሴት ካለች እንድትጠቀም እና ሌሎች ከጤና ጋር የተያያዙ ክንዋኔዎችን ከጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኞች ጋር እየተወያዩ ይሰ ራሉ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ሴቶች እራሳቸው ጤናቸውን ለመንከባከብ አስፈላጊውን ድጋፍ ስለሚ ያደርጉ ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው፡፡” ብለዋል፡፡
ዶ/ር ማርታ በጤናው ዘርፍ ያሉትን አገልግሎቶች በማጠናከር ረገድ የሚከተሉትን ዋና ዋና ነጥቦች አብራርተዋል፡፡
በመንግስት ደረጃ ወደ 150 /አንድ መቶ ሀምሳ/ የሚጠጉ ሆስፒታሎች ይገኛሉ፡፡ እንዲሁም ከ3 ሺህ በላይ የሚሆኑ ጤና ጣብያዎች በስራ ላይ ይገኛሉ፡፡
የግል ባለሀብቶችም በዘርፉ እንዲሰማሩ መንግስት የሚያበረታታ ሲሆን አሁን በስራ ላይ ያሉትም የህክምና ተቋማት የእናቶችን ሞት በመቀነስ ረገድ ያላቸው እገዛ ቀላል አይባልም፡፡
የትራንስፖርቱን አገልግሎት ለማሻሻል የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባለፈው አመት ወደ 811 /ስምንት መቶ አስራ አንድ/ አምቡላንሶችን ገዝቶ ለክልሎች አሰራጭቶአል፡፡
ሆስፒሎችንና ጤና ጣብያዎችን በማስተሳሰር የሕመምተኞችን ቅብብል ወይንም ሪፈራል የተሳካ ለማድረግና ታካሚዎች ተገቢውን ሕክምና በወቅቱ እንዲያገኙ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶ ትግበራው ተጀምሮአል፡፡
የድንገተኛ የቀዶ ጥገና ሐኪሞችን እያሰለጠኑ ብዛታቸውን በመጨመር እንዲሁም የሐኪሞችንና የአዋላጅ ነርሶችን ቁጥር በማሳደግ በጥራት እና በፍጥነት ህብረተሰቡ ጋ የመድረስ ስራ በስፋት እየተሰራ ነው፡፡
ባጠቃላይም ከላይ የተገለጹት የአሰራር ሂደቶችና ሌሎችንም ተግባራት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በቀዳሚነት እያስተባበረ እና እራሱም እየፈጸመ የሚገኝበት ሁኔታ ያለ ሲሆን የእና ቶችን ሞት በመቀነሱ ረገድ ግን መንግስት ብቻውን የሚወጣው ሳይሆን መላው ህብረተሰብ እና የሚመለከታቸው አካላት እጅ ለእጅ ተያይዘው ከተፈለገበት ደረጃ ለማድረስ ኃላፊነቱን እንደሚ ጋሩ እሙን ነው፡፡” ብለዋል ዶ/ር ማርታ ምንውየለት፡፡






Published in ላንተና ላንቺ

የግጥም፣ የወግና የአጭር ልቦለድ ስብስቦች የተካተቱበት  ‹‹ታሽጓል››  መጽሐፍ፣ ባለፈው ሳምንት አርብ በጎንደር ከተማ ‹‹ሲኒማ አዳራሽ›› የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ ገዛኸኝ ፀጋው፣ በክብር እንግድነት በተገኙበት በይፋ መመረቁን በስፍራው የነበረው ሪፖርተራችን ዘግቧል፡፡  
 የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር የጎንደር ቅርንጫፍ ሰብሳቢ በሆኑት በአቶ ግርማይ ከበደ የተደረሰው ‹‹ታሽጓል›› መጽሐፍ፣ 123 ገጾች ሲኖሩት፣ በ30 ብር ለገበያ መቅረቡ ታውቋል፡፡


በሮማን ተወልደብርሃን ገ/እግዚአብሄር የተጻፈው “ሪፍሌክሽንስ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ግጥሞችና የፎቶግራፎች ስብስብ መጽሃፍ ባለፈው አርብ በኢትዮጵያ ሆቴል ተመርቆ ለንባብ በቃ፡፡ ነዋሪነቷ በለንደን የሆነው ሮማን፤“የውስጣዊ ስሜቴ ነጸብራቆች ስብስብ ነው” ብላለች- መፅሃፉን።  በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ 60 ግጥሞችና በመምህር ቶማስ ለማ የተነሱ 26 ፎቶግራፎችን ያካተተው “ሪፍሌክሽንስ”፤ በተለያዩ የመፃህፍት መደብሮችና አዟሪዎች እጅ የሚገኝ ሲሆን በ40 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
ገጣሚዋ በቀጣይ የታዋቂ ኢትዮጵያውያን ገጣሚዎችን የተመረጡ ግጥሞች ወደ እንግሊዝኛ በመተርጎም በውጥ አገር ውጭ ተነባቢ ለማድረግና የአገሪቱን ስነጽሁፍ ለተቀረው አለም የማስተዋወቅ ዕቅድ እንዳላት በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ ተናግራለች፡፡

በጋዜጠኛ ሸዋዬ ገላው ተጽፎ፣ በራሱ በሸዋዬና በደመወዝ ጎሽሜ የተዘጋጀው “ባቢሎን” የተሰኘ ኮሜዲ ፊልም በሳምንቱ መጀመሪያ በተለያዩ ሲኒማ ቤቶች ለእይታ በቃ፡፡
የአንድ ሰዓት ከአርባ ደቂቃ ርዝማኔ ያለው ፊልሙ፤ በብድር ባገኙት ገንዘብ የኤሌክትሪክ ምጣድ በማደስ ራሳቸውን ለመለወጥ የሚተጉ ጓደኛሞች የሚገጥሟቸውን ፈተናዎች የሚያሳይ ሲሆን  ሰርቶ ለመጨረስ አንድ አመት ከመንፈቅ ፈጅቷል፡፡ በፊልሙ ላይ አሰፋ በየነ፣ ሰላም ይሁን አስራት፣ በረከት በላይነህ (አመዶ)፣ ትዕግስት በጋሻው፣ እንግዳ ጌታቸው እና ሌሎች ተዋንያን ተሳትፈውበታል። ጋዜጠኛ ሸዋዬ ገላው በ“ገመና 2” ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ ላይ በደራሲነት ተሳትፏል፡፡

በገጣሚ ሰሎሞን ሞገስ /ፋሲል/ የተጻፈው “ጽሞና እና ጩኸት” የተሰኘ የግጥም መድበል ዛሬ ከጠዋቱ 2 ሰዓት ከ30 ጀምሮ በጣይቱ ሆቴል የጃዝ አምባ ማዕከል ይመረቃል። የገጣሚው ሶስተኛ ስራ የሆነው መጽሃፉ፤76 ገጾች ያሉት ሲሆን በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 59 ግጥሞችን አካቷል፡፡ የመሸጫ ዋጋውም 20 ብር ነው፡፡
ገጣሚው ከዚህ በፊት ‘እውነትን ስቀሏት’ እና ‘ከጸሃይ በታች’ የተሰኙ የግጥም መፃህፍትን ለንባብ ያበቃ ሲሆን በተለያዩ የስነጽሁፍ መድረኮች ላይ ግጥሞቹን በማቅረብም ይታወቃል፡፡ በሌላ በኩል በህግ ባለሙያዋ ሂሩት ምህረት የተጻፈው “ማርሲላስ” የተሰኘ የረጅም ልቦለድ መጽሐፍ ነገ ማለዳ በሐገር ፍቅር ቲያትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡ ለፀሃፊዋ የመጀመሪያ ስራዋ የሆነውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው ልቦለዱ፤270 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ በ75 ብር በተለያዩ የመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች እየተሸጠ ይገኛል፡፡

           ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ከጐንደር ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ጋር በመተባበር ያዘጋጃቸው “ጐንደርን ለአገር ቤት” እና “ጐንደርን ለህፃናት” የተሰኙ የቱሪዝም ዳይሬክተሪዎች ታትመው  ባለፈው ሳምንት ጐንደር ከተማ በሚገኘው ቋራ ሆቴል ተመረቁ፡፡ የምረቃ ስነስርዓቱን የኢፌዲሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሙሉጌታ ሰይድ ከፍተውታል፡፡
ከዚህ በፊት “ጐንደርን ለአገር ቤት” የተሰኘ የጐንደር ቱሪዝም ማውጫ በእንግሊዝኛ መውጣቱ የሚታወስ ሲሆን የአገር ውስጥ ጐብኚዎችና የጐንደር ከተማ ነዋሪዎች ስለጐንደር ቅርሶች ጥሩ ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ቅርሶቹን እንዲንከባከቡ በማሰብ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ  መቅረቡን የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ወ/ት ህይወት ሀብታይ ተናግራለች፡፡ ማውጫው በዋናነት የጐንደርን ዋና ዋና መስህቦች ያካተተ ሲሆን በተለይም የአፄ ፋሲለደስ ግንቦችን፣ ደብረ ብርሃን ስላሴን፣ የአፄ ፋሲለደስ መዋኛን እንዲሁም  ጐንደር ያሏትን ፓርኮችና ሙዚየሞች የሚያስቃኝ ነው፡፡
በዚሁ እለት “ጐንደርን ለህፃናት” የተሰኘ መጽሐፍም የተመረቀ ሲሆን ህፃናት የጐንደርን መስህቦች እንዲያውቁና በቂ ግንዛቤ እንዲያገኙ በሚያስችላቸው መንገድ መዘጋጀቱ ተገልጿል፡፡ ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን በዚህ አመት ብቻ የቱሪዝም ማውጫ ሲያስመርቅ ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን ቀደም ሲል “የሰሜን ሸዋ የቱሪዝም ዳይሬክተሪ” እና “የኢትዮጵያ የተፈጥሮ ፓርኮች ዳይሬክተሪ”ን አስመርቋል፡፡ ድርጅቱ በየሁለት ወሩ የሚወጣና ቱሪዝም ላይ አተኩሮ የሚሰራ “ቱባ” የተሰኘ መጽሔት እንደሚያዘጋጅም ይታወቃል፡፡

ካለፈው አመት ጀምሮ መቅረብ የጀመረው “ግጥምን በማሲንቆ” ባለፈው ሳምንት በጎንደር ተካሄደ፡፡ ለሁለተኛ ጊዜ ጐንደር ከተማ በሚገኘው አፄ በካፋ ሆቴል አዳራሽ የተካሄደው ፕሮግራሙ፣  በየአመቱ በወርሃ ጥር በጥምቀት መዳረሻ ላይ እንደሚካሄድ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ገጣሚ ትዕግስት ሲሳይ ተናግራለች፡፡ በዝግጅቱ ላይ ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ጌትነት እንየው፣ ገጣሚና ጋዜጠኛ ባንቻየሁ አለሙና በርካታ ወጣት  ገጣሚያን ስራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ ግጥምና ማሲንቆ አንዳቸው ያለ አንዳቸው መኖር አይችሉም ያለችው አዘጋጇ፣ፕሮግራሙን የማስፋፋት አላማ እንዳላት ተናግራለች፡፡

1 በመቶ ያህሉ ባለፀጎች 95 በመቶውን ሃብት ተቆጣጥረዋል

ባለፈው ሳምንት ከተለያዩ  አገራት የተውጣጡ  ከአንድ ሺ በላይ የቢዝነስ ሰዎች፣ ፖለቲከኞች፣ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እና ፖሊሲ አውጭዎች “አለምን እንለውጥ” በሚል መሪ ቃል በስዊዘርላንድ በተካሄደው የዓለም ኢኮኖሚክ ፎረም ላይ ተሳትፈዋል፡፡ በፎረሙ ከተነሱት አጀንዳዎች መካከልም የኢኮኖሚ እድገት ዝግመት፣ ስራ አጥነት እና የዋጋ ግሽበት በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ ከፎረሙ ስብሰባ ቀደም ብሎ ኦክስፋም “ዎርኪንግ ፎር ዘ ፊው” በሚል ርእስ  ይፋ ባደረገው ጥናት፤ ሰማኒያ አምስት የሚሆኑ የአለማችን ሀብታሞች ከግማሽ በላይ የሚሆነውን የአለም ሀብት እንደተቆጣጠሩ ያመለከተ ሲሆን እነዚህ ባለፀጎች  1.7 ትሪሊዮን ዶላር የሚገመት ሀብት እንዳካበቱ ተገልጿል፡፡ ከሰማንያ አምስቱ ቱጃሮች ውስጥ 31ዱ አሜሪካውያን ሲሆኑ በሃብት መጠን በአንደኝነት የሚመራው በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ የተሰማራው  ሜክሲካዊው ቢሊዬነር ካርሎስ ስሊም ሄሉ ነው - በ73ቢ. ዶላር የሃብት መጠን፡፡ የሁለተኛነት ደረጃ የያዘው አሜሪካዊው የማይክሮሶፍት መስራች ቢል ጌትስ ሲሆን የሀብቱ መጠን 67 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ተጠቅሷል፡፡ ሌላው አሜሪካዊ  ባለፀጋ ዋረን በፌ፤ በ53.5 ቢሊዮን ዶላር የሦስተኝነት ደረጃ ይዟል። የአለማችን ሀብታም ሴት በመሆን ቀዳሚነቱን የያዘችው ሊሊያን ቤተን ኮርት ስትሆን፤ ሎሪያል በሚል በሚታወቀውና ከቤተሰቧ በወረሰችው የመዋቢያ ምርቶች ኩባንያዋ የ30 ቢሊዮን ዶላር ሃብት ማካበት ችላለች ተብሏል፡፡
ከግማሽ በላይ የአለማችን ሀብት አንድ በመቶ በሚሆኑ ጥቂት ባለፀጎች ተይዟል የሚለው የኦክስፋም ጥናት፤ በሀብታሞች እና በድሆች መካከል ያለው ልዩነት ካለፉት ሰላሳ አመታት ወዲህ በእጅጉ እየሰፋ መምጣቱን ጠቅሶ፤ የአለም ሀብት በተወሰኑ ግለሰቦች እጅ ተጠቅልሎ መያዙ ሁሉን አቀፍ የሆነ የፖለቲካ እና ኢኮኖሚያዊ ስርአት ለመዘርጋት እንቅፋት እንደሆነ አመልክቷል፡፡ የኦክስፋም ዋና ዳይሬክተር ዊኒ ባይናይማ፤በዓለም ህዝቦች መካከል ያለው ኢኮኖሚያዊ ልዩነት እየሰፋ መምጣት ለማህበራዊ ውጥረቶችና  ግጭቶች መባባስ ምክንያት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ “በአለም ላይ እየሰፋ የመጣውን የሀብት ክፍፍል ልዩነት ማጥበብ ካልተቻለ፣ ድህነትን ለመዋጋት የሚደረገው ጥረት ውጤት ያመጣል ብለን ተስፋ አናደርግም” ብለዋል - ዳሬክተሩ፡፡
ካለፉት ሰላሳ አመታት ወዲህ ከአስር ሰዎች ሰባቱ የኢኮኖሚ ልዩነቱ እጅግ እየሰፋ በመጣባቸው አገራት እንደሚኖሩ “ዩኤስ ቱዴይ” ለተባለው ጋዜጣ የተናገሩት ከአጥኚዎቹ አንዱ ኒክ ጋላሶ፤ እስካሁን ለችግሩ እልባት ለመስጠት የተደረገ ፖለቲካዊ ሙከራ እንደሌለ ገልፀዋል፡፡  በኢኮኖሚ ፎረሙ ላይ የተሳተፉት የኢኮኖሚ ባለሙያው ጄኒፈር ብላንክ በበኩላቸው፤ ስራ አጥ የሆኑና በቂ የሙያ ክህሎት የሌላቸው ወጣቶች ቁጥር መብዛት በዓለም ላይ አለመረጋጋትና ቀውስ ሊፈጥር እንደሚችል ጠቅሰው፤ ብዙዎች ኢ-ፍትሀዊውን የሀብት ክፍፍልና ሙስናን በመቃወም ቁጣቸውን ለመግለፅ ወደ አደባባይ መውጣታቸውን  እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል፡፡ “እርካታን ማጣት መጠነ ሰፊ ማህበራዊ ቀውስ ያስከትላል፤ በተለይ ወጣቶች ለነገ የሚያዩት ተስፋ ከሌላቸው ሁሉንም ወገን የሚጎዳ ችግር መፈጠሩ አይቀሬ ነው” ሲሉ አሳስበዋል - ባለሙያው፡፡ እጅግ የተራራቀ የሀብት ልዩነት የዘመናችን መገለጫ ነው፤ ሲሉ በቅርቡ የተናገሩት የአሜሪካው ፕሬዚደንት ባራክ ኦባማም፤ “ይሄ የሃብት ልዩነት እንደ ሰው ያለንን ዋጋ እያጠፋው ነው” ብለዋል፡፡
ኦክስፋም በጥናቱ ላይ እንዳስቀመጠው፤ ከመቶ አንድ እጅ የሚሆኑት የአሜሪካ ሀብታሞች፣ ከኢኮኖሚ ቀውሱ በኋላ  95 በመቶ እድገት ያስመዘገቡ ሲሆን 90 በመቶ የሚሆነው ዝቅተኛው የህብረተሰብ ክፍል የድህነት መጠንም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ሃብታሞቹ ይበልጥ እየበለፀጉ ድሆቹም ይበልጥ እየደኸዩ ነው፡፡  በአሁኑ ወቅት በሀብት ክፍፍል ላይ ያለው ልዩነት ከ1920ዎቹ ወዲህ የታየ የመጀመሪያው ሰፊ ክፍተት እንደሆነ የሚናገሩት መቀመጫውን ጄኔቭ ያደረገው የአለምአቀፉ የሰራተኞች ማህበራት ፌዴሬሽን ዋና ፀሀፊ ፊሊፕ ጂኒንግስ፤ የኦክስፋም ጥናት የአለም ኢኮኖሚ መልክ በእጅጉ እየተለወጠ መምጣቱን ያሳያል ይላሉ። “ጥቂት ሀብታሞች ከግማሽ በላይ የምድሪቱን ሀብት ተቆጣጥረው ሲጠቀሙ ሚሊዮኖች ግን እህል ሳይቀምሱ ወደ መኝታቸው ይሄዳሉ፤ በሺዎች የሚቆጠሩትም በረሀብ ይሞታሉ” ብለዋል - የዓለምን አስከፊ እውነታ ጂኒንግስ ሲገልፁ፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ
Page 1 of 14