የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በተከሰተው የኢኮኖሚ ቀውስ ምክንያት ሚኒስትሮቻቸው የአዲስ ዓመት እረፍት እንደማይወስዱ ሰሞኑን አስታወቁ፡፡ በሩሲያ ትልቁ በዓል እንደሆነ በሚነገርለት የፈረንጆች አዲስ ዓመት፤ በመላ አገሪቱ የሚገኙ የሩሲያ ኩባንያ ሰራተኞች ለበዓሉ የ12 ቀናት እረፍት ይወስዳሉ፤ ከጃንዋሪ 1 እስከ 12፡፡
ፑቲን ባለፈው ሐሙስ በቴሌቪዥን በተሰራጨ የመንግስት ኃላፊዎች ስብሰባ ላይ፣ በዚህ ዓመት የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው እረፍት መውሰድ እንደማይገባቸው ተናግረዋል፡፡ “ቢያንስ ለዚህ ዓመት መንግስት ይሄን ረዥም የበዓል ዕረፍት መስጠት አይችልም - መቼም የምለው ይገባችኋል” ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡
የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ በበኩላቸው፤ በበዓሉ ወቅትም ጭምር (ከዓመቱ የመጀመሪያ ቀናት አንስቶ) የኢኮኖሚውን ሁኔታ እንዲከታተሉላቸው እንደሚፈልጉ ለሚኒስትሮቹ ነግረዋቸዋል፡፡
በነዳጅ ዋጋ መቀነስና በምዕራብ አገራት ማዕቀብ ክፉኛ የተጎዳው የሩሲያ ኢኮኖሚ፤ ከስድስት ዓመታት ወዲህ ለመጀመሪ ጊዜ በቀጣዩ ዓመት “ድቀት” ውስጥ የሚገባ ሲሆን፣ የአገሪቱ ገንዘብ ሩብልም በአሁኑ ሰዓት ከዋጋው ግማሽ በታች ወርዷል፡፡ ከያዝነው ወር መጀመሪያ አንስቶ አንድ ዶላር በ80 ሩብል ሲመነዘር የቆየ ሲሆን፣ ባለፈው ሐሙስ የ2 በመቶ መጠነኛ መሻሻል አሳይቶ አንድ ዶላር በ52 ሩብል መመንዘሩ ታውቋል፡፡
የሩሲያ ማዕከላዊ ባንክ የአገሪቱ መጠባበቂያ ገንዘብ ከ2009 ዓ.ም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ400 ቢሊዮን ዶላር በታች መውረዱን አስታውቋል፡፡ ዋጋው እጅግ ያሽቆለቆለውን የአገሪቱን መገበያያ ሩብል ማረጋጋት፣ የሩሲያ የገንዘብ ኃላፊዎች ተቀዳሚ ስራ ይሆናል ተብሏል፡፡ ከዩክሬን ጋር በተያያዘ በአገሪቱ ላይ የተጣለው ማዕቀብ፣ በርካታ የሩሲያ ኩባንያዎችን ከምዕራብ አገራት የፋይናንስ ገበያ እንዳስወጣቸው ተዘግቧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

የትንፋሽ ማጠር ገጥሟቸው ባለፈው ማክሰኞ ሂዩስተን ሜቶዲስት ሆስፒታል የገቡት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት  ጆርጅ  ኤች ደብሊው ቡሽ፤ ከትላንት በስቲያ የተከበረውን የፈረንጆች የገና በዓል በሆስፒታል አሳለፉ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ጂም ማክግራዝ፤ ቡሽ በጥሩ ጤንነት ላይ እንደሚገኙና የገና በዓልን በሆስፒታል ያሳለፉት በሽታው ከፍቶባቸው ሳይሆን ለጥንቃቄ ሲባል እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በተመሳሳይ ጊዜ ብሮንካይትና በሃይለኛ ሳል ይዟቸው ሆስፒታል ከገቡ በኋላ የገና በዓልን ጨምሮ ለሁለት ወራት እዚያው መቆየታቸውን ያስታወሱት ቃል አቀባዩ፤ የአሁኑ ግን ከቀድሞው በጣም ይለያል ብለዋል - የፕሬዚዳንቱን ጤናማነት ሲገልፁ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ሆስፒታል መግባት ላሳሰባቸው በርካታ ወዳጆችና አድናቂዎቻቸው የቡሽ ዋና ኃላፊ በሰጡት መግለጫ፤ “የቡሽ ቤተሰብ፤ ለጭንቀታችሁ፣ ለፍቅራችሁና፣ ለፀሎታችሁ በእጅጉ ያመሰግናል፡፡ ይሄ የዛሬ ሁለት ዓመት እንደሆነው ዓይነት አይደለም፡፡ የትንፋሽ ማጠር ነው፡፡ በጥቂት ቀናት ውስጥ ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ” ብለዋል፡፡ ቡሽ ሆስፒታል መግባታቸውን የሰሙት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸውም ለቀድሞው ፕሬዚዳንትና ለመላው የቡሽ ቤተሰብ የመልካም ጤንነት ምኞታቸውን ልከዋል፡፡
ሪፐብሊካኑ የ90 ዓመቱ ቡሽ፤ 41ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በመሆን አገራቸውን ያገለገሉ ሲሆን የ43ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽም አባት ናቸው፡፡ የዊልቸር እስረኛ ባደረጋቸው ከፍተኛ የነርቭ ህመም ሲሰቃዩ የቆዩት ቡሽ፤ በቅርቡ ግን ነቃ ነቃ ማለት ጀምረው ነበር ተብሏል፡፡ ባለፈው ሰኔ ለ90ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው ከሄሊኮፕተር ላይ በፓራሹት የዘለሉ ሲሆን የዛሬ ወር “41፡ A Portrait of My Father” የተሰኘ አዲስ መፅሃፋቸው የምረቃ ስነስርዓት ላይ ከልጃቸው ጋር ተገኝተው ነበር፡፡
ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡበትን 25ኛ ዓመት በዓል በቅርቡ ያከበሩት ጆርጅ ቡሽ፤ በፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን ዘመን ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው አገልግለዋል፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በባህር ኃይል አብራሪነት የተሳተፉ ሲሆን ወደ ፖለቲካው ዓለም ከመግባታቸው በፊት በቴክሳስ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ውስጥ እንደሰሩ የህይወት ታሪካቸው ያወሳል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

መኪና ሲያሽከረክሩ የተያዙ ሁለት የሳኡዲ ሴቶች ለአንድ ወር ገደማ ከታሰሩ በኋላ ባለፈው ሳምንት ጉዳያቸው ሽብርተኝነትን ለሚመለከት ልዩ ፍ/ቤት እንደተላለፈ ተገለፀ፡፡
የ25 ዓመቷ ሎዩጄይን አል ሃትሎል እና የ33 ዓመቷ ማይላ ይሳ አል - አሙዲ ጉዳይ ወደ ልዩ ፍ/ቤት የተላለፈው በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጡት አስተያየት ነው ብለዋል - የመብት ተሟጋቾች፡፡ ሳኡዲ በዓለም ላይ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የምትከለክል ብቸኛ አገር ናት፡፡
ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ በፅሁፍ የተቀመጠ ህግ ባይኖርም የመንጃ ፈቃድ የሚሰጠው ግን ለወንዶች ብቻ ነው፡፡ ሴቶች በአደባባይ ሲያሽከረክሩ ከተገኙም በፖሊስ ተይዘው ከመታሰርም ባሻገር ይቀጣሉ፡፡
የሳኡዲ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የተጣለባቸው እገዳ እንዲነሳላቸው ማህበራዊ ሚዲያን ጨምሮ የተለያዩ ተከታታይ እንቅስቃሴዎች ሲያካሂዱ ቆይተዋል፡፡
አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል እንደዘገበው፤ ሚስ ሃትሎል የተያዘችው ከጐረቤት አገር፣ ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ እያሽከረከረች ወደ ሳኡዲ ለመግባት ስትሞክር ነው፡፡
ነዋሪነቷን በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ያደረገችው የሳኡዲ ጋዜጠኛ ሚስ አላሙዲም የተያዘችው ሚስ ሃትሎልን ለመርዳት ድንበር ላይ ስትደርስ ነው ብሏል - የዜና ወኪሉ፡፡
ሁለቱም ሴቶች በትዊተር እጅግ በርካታ ተከታይ ያሏቸው ሲሆን ሚስት ሃትሎል ወደ አገሪቱ ለመግባት አንድ ቀን ሙሉ ያችውን ውጣ ውረድ በትዊተር ገጿ ላይ እንዳሰፈረች ተዘግቧል፡፡ ባለፈው ሐሙስ በአገሪቱ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኘው አል - አህሳ ፍ/ቤት፤ የሁለቱ ሴቶች ጉዳይ በሪያድ የሽብርተኝነት ክሶችን ለመከታተል በተቋቋመው ልዩ ፍ/ቤት እንዲዳኙ በይኗል፡፡ የሴቶቹ ጠበቆች ግን ይግባኝ ለመጠየቅ ማሰባቸውን የመብት ተሟጋቾች ለአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ጠቁመዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

     በደራሲ ሐማቱማ “The case of the Socialist witchdoctor” በሚል ርዕስ ተፅፎ በህይወት ታደሰ “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ” በሚል ወደ አማርኛ የተመለሰው መፅሃፍ ለንባብ በቅቷል፡፡ የተለያዩ በርካታ ታሪኮች ስብስብ የሆነው ይሄው መፅሃፍ፤ በአንድ ሶሻሊስት ጠንቋይ ላይ ያተኮረ ታሪክ የያዘ ሲሆን ሌሎችም አስገራሚ ፖለቲካዊ ታሪኮችን አካትቷል፡፡ መፅሃፉ በ307 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ50 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

 “የዘንድሮ ትዳሮች” በሚል ርዕስ በመቅደስ በቀለ (ማክዳ) ተፅፎ በእርከን ቢዝነስ ዲቨሎፕመንት አሳታሚ የታተመው መፅሐፍ በገበያ ላይ ውሏል፡፡ በቅርቡም ይመረቃል ተብሏል፡፡
በመፅሀፉ የዘንድሮ ትዳሮችን ጨምሮ ሌሎች እውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረቱ ከ15 በላይ አጫጭር ልቦለዶች እንደተካተቱበትና በ200 ገፆች ተሰናድቶ በ60 ብር ለገበያ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ መቅደስ በቀለ (ማክዳ) የበርካታ ፊልሞች ደራሲና ዳይሬክተር ስትሆን “የዘንድሮ ትዳሮችና ሌሎች” ሁለተኛ መፅሃፏ መሆኑ ታውቋል፡፡ ደራሲዋ ከዚህ ቀደም “የፍቅር መስዋዕት” የተሰኘ መፅሃፍ አሳትማለች፡፡

የገጣሚ የሺመቤት ካሳ “አመሻሽ” የግጥም መድበል ሰሞኑን በ25 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
የግጥም መድበሉ 62 አጫጭርና ረጃጅም ግጥሞች የተካተቱበት ሲሆን ገጣሚዋ ማስታወሻነቱን ለቀደምት ደራሲያንና ለነገው ደራሲያን ማድረጓን አስታውቃለች፡፡

በጋዜጠኛና ደራሲ አሰግድ ሀምዛ ተፅፎ የታተመው “በህይወት መስኮት” የተሰኘ መፅሃፍ ዛሬ በሀዋሳ ከተማ ይመረቃል፡፡ መፅሃፉ፤ ወጎችና የፍቅር ደብዳቤዎችን ያካተተ ሲሆን ደራሲው በመምህርነት ባገለገለበት ሙርሲ ብሔረሰብ ውስጥ የታዘበውንና የኖረውን እውነታ በሚጥም ቋንቋና ውበት ፅፎታል፡፡
141 ገፆች ያሉት መፅሀፉ ዛሬ ሲመረቅ፣ የዘርፉ ምሁራን አስተያየት የሚሰጡ ሲሆን በስነ ስርዓቱ ላይ የጥበብ አፍቃሪዎችና ቤተሰቦች እንደሚታደሙ ታውቋል፡፡ መፅሃፉ አገር ውስጥ በ40 ብር፣ በውጭ አገር በ8 ዶላር እንደሚሸጥ ተገልጿል፡፡

የደራሲ ስንዱ አካልነህ “ኤል-ማጐት” የተሰኘ የረዥም ልቦለድ መፅሃፍ እየተነበበ ነው፡፡
በጐንደር ማተሚያ ድርጅት ታታሞ ለገበያ የቀረበው መፅሃፉ መቼቱን በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ያደረገ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ መፅሃፉ በ75 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Monday, 29 December 2014 07:56

2014ን ወደኋላ

     በ2014 በዓለም ዙሪያ ታላላቅ የስፖርት ውድድሮች ተካሂደዋል፡፡ ጎን ለጎን በርካታ አወዛጋቢ አጀንዳዎችም ተከስተዋል፡፡ በራሽያዋ ግዛት ሶቺ የተካሄደው የክረምት ኦሎምፒክ ያስወጣው ከፍተኛ በጀት ያስገረመ ነበር፡፡ ብራዚል ያስተናገደችው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ደግሞ የምን ግዜም ምርጥ ቢባልም በውዝግቦች ታጅቧል፡፡ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ተራቅቋል በአነጋጋሪ ክስተቶች የደመቀ ዓለም ዋንጫ ነበር፡፡ በሌላ በኩል ግዙፎቹ የስፖርት አስተዳደር ተቋማት በተለያዩ የውዝግብ አጀንዳዎች የታመሱበትም ዓመት ነበር፡፡ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ‹‹ፊፋ›› ምንም እንኳን ብራዚል ባዘጋጀችው 20ኛው ዓለም ዋንጫ እስከ 4.5 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ ቢያጋብስም 2009 አባል አገራት ያሉት ፊፋ 9 ዓለም ዋንጫዎች አዘጋጆችን ምርጫ ሙስና በተንሰራፋበት አሰራር ማከናወኑ ከፍተኛ ትችት አስከትሎበታል፡፡ ዓለም አቀፉ የኦሎምፒክ ኮሚቴም በታላቁ የስፖርት መድረክ ኦሎምፒክ ዙሪያ አሳሰቢ አጀንዳዎች ተፈጥረውበታል፡፡ የኦሎምፒክ አዘጋጆች የሚጠይቀው ከፍተኛ የበጀት ወጪ የአገራትን የመስተንግዶ ፍላጎት እያሳጣበት ነው፡፡ በኦሎምፒክ ውድድርና መስተንግዶ ተሃድሶ ለማድረግ መነሳቱ አበይት መነጋገርያ ሆኖ ይጠቀሳል፡፡ 2015 እኤአ ዓለም ዋንጫና ኦሎምፒክ ባይኖሩበትም በተለያዩ አህጉሮች የሚደረጉ ትልልቅ የስፖርት ውድድሮች ይስተናገዱበታል፡፡ በ2015 የውድድር ካለንደር በርካታ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን በማስተናገድ እድለኛ የሆነችው አውስትራሊያ ናት፡፡ የኤስያ ካፕ፤ የዓለም የሜዳ ቴኒስ ሻምፒዮና፤ የዓለም የክሪኬት ዋንጫን ታዘጋጃለች፡፡ ቻይና 15ኛውን የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በጉዋጄንግ ቤጂንግ ስታስተናግድ፤ በአፍሪካ አህጉር ደግሞ ኢኳቶርያል ጊኒ የምታዘጋጀው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ይሆናል፡፡ ካናዳ ደግሞ የሴቶች እግር ኳስ ዓለም ዋንጫን ታዘጋጀለች፡፡
ስፖርት አድማስ በ2014 እኤአ በስፖርቱ ዓለም ያጋጠሙ አበይት ክስተቶችና ሁኔታዎችን ከዚህ በታች ከልሷቸዋል፡፡
የጀርመን የዓለም ዋንጫ ድል
የ2014 እኤአ ዋና የስፖርት መድረክ በነበረው የብራዚል 20ኛው ዓለም ዋንጫ የጀርመን የበላይነት የተረጋገጠበት ነበር ቢሆንም በዓመቱ በእግር ኳስ እንደ ጀርመን ስኬታማ የሆነ የለም፡፡ የጀርመን እግር ኳስ በፊፋ ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ በ1725 ነጥብ በመሪነት በክለብ እና በብሄራዊ ቡድን ደረጃ በየውድድሮቹ ቋሚ ተፎካካሪ የሆነበር ዕድገት የዓመቱ ትልቅ ስኬት ሆኖ ይጠቀሳል፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ የፍፃሜው ጨዋታ የጀርመን ብሄራዊ ቡድን አርጀንቲናን 1ለ0 በማሸነፍ ለአራተኛ ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ይሄ  የዓለም ዋንጫ ድል ከ24 ዓመታት በኋላ የተገኘ ነበር፤ አውሮፓዊ ቡድን ደቡብ አሜሪካ አህጉር ላይ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም ዋንጫን ክብር መቀዳጀቱም አዲስ ታሪክ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ የጀርመን እግር ኳስ ስኬት በዓለም ዋንጫ ድል ብቻ የተወሰነ አልነበረም፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት የአገሪቱ ክለቦች በአውሮፓ ትልልቅ ውድድሮች ቋሚ የዋንጫ ተፎካካሪ ሆነዋል፡፡ የቦንደስ ሊጋ ውድድር በስታድዬም ተመልካች ብዛት እና በአስተማማኝ የኢኮኖሚ ጥንካሬው ተምሳሌት ሆኖ ይገኛል፡፡ በፊፋ የ2014 የወርቅ ኳስ ፉክክር ውስጥ ጀርመናዊያን በዋና ዋና የሽልማት ዘርፎች  የመጨረሻ እጩ ናቸው፡፡ የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን ይህን ስኬት በሚቀጥሉት 10 ዓመታት በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ እቅድ በ2024 እኤአ ላይ ደግሞ የአውሮፓ ዋንጫን በታላቅ ድምቀት ለማዘጋጀት ይፈልጋል፡፡ ኦሎምፒክንም ለማስተናገድ ፍላጎት አለ፡፡
የሪያል ማድሪድ ኃያልነት
በአውሮፓ እግር ኳስ  2014ን የነገሰበት የስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ ነው፡፡ 4 ትልልቅ ዋንጫዎችን ሰብስቧል፡፡ አስረኛውን የሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ድል አትሌቲኮ ማድሪድን 4ለ1 በማሸነፍ መቀዳጀቱ የመጀመሪያው ነበር፡፡ በተጨማሪ የአውሮፓ ሱፕር ካፕ ፤ የስፔን ኮፓ ዴላ ሬይ እና የዓለም ክለቦች ሻምፒዮና ሶስት ዋንጫዎችን በሽልማት ያስገባው ገንዘብ ከ65 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ነው፡፡ አሶስዬትድ ፕሬስ በ2014 የእግር ኳስ ገድላቸው ጎልቶ ለወጡ ክለቦች በሰራው ደረጃ በ137 ነጥብ በአንደኛነት የሚመራም ክለቡ በ2015 እኤአ ተጨማሪ 4 ዋንጫዎችን ለመሰብሰብ አቅዶ እየሰራ እንደሚገኝ ጣሊያናዊው አሰልጣኝ ካርሎ አንቸሎቲ ተናግረዋል፡፡
የታላላቅ ተጨዋቾች ጡረታ
በ2014 የቀድሞ ታላላቅ ተጨዋቾች እግር ኳስን  በጡረታ ተሰናብተዋል፡፡ በጡረታ ጫማቸውን ከሰቀሉት መካከል ቲዬሪ ሆንሪ፤ ሃቪዬር ዛኔቲ፤ ካርሎስ ፒዮል፤ ሪያን ጊልስ፤ ክላረንስ ሲዶርፍ፤ ቬሮንና ሪቫልዶ ይጠቀሳሉ፡፡ በተጫዋችነት ባሳለፉባቸው የውድድር ዘመናት በተለያዩ የአውሮፓ ሊጎች እና የውስጥ ውድድሮች 50 ዋንጫዎችን 15 የሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ድሎችንም አግኝተዋል፡፡ ለብሄራዊ ቡድኖቻቸው 857 ጨዋታዎችን ያደረጉም ናቸው፡፡ ሶስት የዓለም ዋንጫን ያሸነፉ ፤ ሁለት የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያ የተጎናጸፉ እንዲሁም የወርቅ ኳስ ተሸላሚ ብራዚላዊው ሪቫልዶ ይገኙበታል፡፡
የኦስካር ፒስቴርዬስ ወንጀል
በ2014 እኤአ በስፖርቱ ዓለም አስደንጋጭ እና አነጋጋሪ ከነበሩ ክስተቶች መጠቀስ ያለበት ደቡብ አፍሪካዊው የፓራኦሎምፒክ ጀግና ኦስካር ፒስተርዬስ የትዳር አጋሩን ራሴን ለመከላከል በሚል ምክንያት በጥይት ተኩሶ ገድሏታል፡፡ ፍርድ ቤት የተመላሰበት የክስ ሂደት ከፍተኛ ትኩረት የሳበ ነበር፡፡ ከሁለት ወራት በፊት 5 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶበት ወህኒ ወርዷል፡፡ የ36 ዓመቱ ኦስካር ፒስቴርዬስ በፓራኦሎምፒክ የአጭር ግዜ ተሳትፎው በጣም ስኬታማ ነበር በ100 ሜትር እና በ200 ሜትር ውድድሮች 6 የወርቅ፤ 1 የብር እና 1 የነሐስ ሜዳልያዎችን በፓራ ኦሎምፒክ ውድድሮች ተጎናፅፏል፡፡ በ100 የፓራኦሎምፒክ ሪከርድም አስመዝግቧል፡፡ ሰሞኑን በተፈረደበት የ5 ዓመት የወህኒ ቆይታ ላይ ይግባኝ ጠይቋል አልተሳካለትም፡፡ በመልካም ተመክሮ ለመፈታት ቢያንስ 10 ወራት ወህኒ እንዲቆይ ይጠበቅበታል፡፡
ዶፒንግና  አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ
ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ‹‹አይኤኤኤፍ›› በ2014 እ.ኤ.አ የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና፣ ኢንተርኮንትኔንታል ካፕ፤ የዱላ ቅብብል የዓለም ሻምፒዮና የዓለም የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና፤ የዳይመንድ ሊግ እና ሌሎች ውድድሮችን በተሳካ ሁኔታ አካሂዷል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከዶፒንግ በተያያዘ የሚነሱት አጀንዳዎች በዓመቱ መጨረሻ የተከሰቱ ነበር፡፡ ከ1999 እኤአ አንስቶ ዓለምን አቀፉን የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር የመሩት ሴኔጋላዊው ለሚን ዲያክ ጫና ውስጥ ገብተዋል፡፡ 2014 የመጨረሻ የግልጋሎት ዘመናቸው እንደሚሆን እየተገለፀ ነው በዶፒንግ ዙርያ የተፈጠሩት አወዛጋቢ አጀንዳ በስልጣን የመቆየታቸውን ተስፋ አጠያያቂ አድርገዋል፡፡ ባለፈው ሰሞን የጀርመን ብሄራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ የሰራው ጥናታዊ ፊልምም በዶፒንግ ዙሪያ ያሉ የተድበሰበሱ ችግሮችን አጋልጧል፡፡ አይኤኤኤኤፍ በዶፒንግ ዙሪያ በከፍተኛ የአሠሪር ችግር መውተብተቡን የረዳ ፊልም ሆኗል፡፡ በውድድር ወቅት አስፈላጊውን የህክምና ምርመራ ባለማድረግ፤ ብቃትን የሚጨምሩ መድሃኒቶችን ለመቆጣጠር ባለመቻል እና በለዘብታ በማለፍ ዓለም አቀፉ ማህበር እና ታላላቅ አትሌቶች መጠየቅ አለባቸው የሚል ዘመቻ ከፍቷል፡፡ በጀርመኑ የቴሌቭዥን ጣቢያ በዶፒንግ ችግር ተጠርጣሪ ናቸው ተብሎ በወጣው የ150 አትሌቶች ዝርዝር የብሪታኒያ፤ የራሽያና የኬንያ አትሌቶች ይገኙበታል፡፡
በተለይ የራሽያ ኦሎምፒያኖች 99 በመቶ ብቃት የሚጨምሩ መድሃኒቶች ይጠቀማሉ በሚል የተሰራው ዘገባ እያነጋገረ ነው፡፡ ከራሽያ ባሻገር በዶፒንግ ችግር የገዘፈ ክብር እና ዝናው አደጋ ውስጥ የወደቀው ደግሞ የኬንያ አትሌቲክስ ነው፡፡ ኬንያዊ እውቅ አትሌቶች ከመደበኛ የዶፒንግ ምርመራ በማፈንገጥና ከምርመራ በኋላ ብቃት የሚያሳድጉ መድሃኒቶች  መጠቀማቸው በአንዳንዶቹ ላይ መረጋገጡ  የአገሪቱ አትሌቲክስ እያቃወሰው ይገኛል፡፡ የኬንያ መንግስት  በኬንያ አትሌቶች የዶፒንግ ችግር ዙርያ ዋና ተጠያቂ ያደረገው አትሌቲክስ ኬንያ ተብሎ የሚጠራው ፌደሬሽን ነው፡፡ አስፈላጊው ትኩረት እና ጥንቃቄ እንዲደረግ አልሰራም የሚል ምክንያት በማቅረብ አመራሮቹ ከስልጣናቸው እንዲለቁ ግፊት እያደረገባቸው ነው፡፡  የኬንያ አትሌቶች ኤጀንቶች እና ማናጀሮችም በኬንያ መንግስት ተወቅሰዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት የቦስተን እና የቺካጎ ማራቶኖችን ያሸነፈችው ሪታ ጄፔቶከወር በፊት  የተከለከለ መድሃኒት መጠቀሟ በዶፒንግ ምርመራ ተደርሶበታል፡፡ ብቃት ያሳድጋል የተባለውና እና እውቁ ብስከሌተኛ ላርንስ አርምስትሮንግ በመጠቀሙ አምኖ የተቀጣበትን “ኢፕኦ” የተባለ መድሃኒት መውሰዷ በመረጋገጡ ነው፡፡ በ2014 ብቻ ከዶፒንግ ምርመራ ጋር በተያያዘ የ32 የኬንያ አትሌቶች የክስ ፋይል መከፈቱ ቢነገርም በይፋ የተገለፀው የ16ቱ ብቻ መሆኑ የኬንያ አትሌቲክስ  ፌደሬሽን አመራሮች ከ25 ዓመታት በላይ በሃላፊነት መቆየታቸው ጥያቄ ውስጥ ገብቷል፡፡ የፌደሬሽን አመራሮቹ በኬንያ ያለው የዶፒንግ ችግር ከራሽያና ከቻይና የባሰ አይደለም በሚል ይሟገታሉ፡፡ ለአትሌቶች ብቃት የሚያሳድጉ መድሃኒቶችን የሚያቀርቡ ህገወጥ ቡድኖች ታድነው  ለፍርድ እንዲቀርቡም አይኤኤኤፍ ይፋ ባደረገው ሪፖርት በ2014 እኤአ በዓለም አትሌቲክስ በ39 አገራት የሚገኙ 225 አትሌቶች በዶፒንግ ዙርያ ክስ ቀርቦባቸው ምርመራ ተደርጐባቸዋል፡፡
ኢቦላ ያመሰው የአፍሪካ እግር ኳስ
2014 የአፍሪካ እግር ኳስ በኢቦላ የታመሰበት ዓመት ነው፡፡ ከ5 ወራት በፊት የኢቦላ ወረረሽኝ በምዕራብ አፍሪካ ሲከሰት የአህጉሪቱ የእግር ኳስ ውድድሮች ተቃውሰዋል፡፡ በአፍሪካ እግር ኮንፌደሬሽን የሚካሄዱ የማጣርያ ውድድሮች ፕሮግራማቸው ተዛብቷል፡፡ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ ተሰርዞ ለምትክ አስተናጋጅ ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡ በአፍሪካውያን ስፖርተኞች ላይ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች የመገለል እና ከልክ ያለፈ ጥርጣሬ ተፈጥሯል፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው የስፖርት ክለቦች እና የውድድር አመራሮች ወረርሽኙን በመፍራት ባወጧቸው የጥንቃቄ መመርያዎች የዘረኝነት አጀንዳዎች አከራክረዋል፡፡ በ2015 እኤአ ላይ 30ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ የምታዘጋጀው ሞሮኮ ነበረች፡፡ ከኢቦላ ወረረሽኝ በተያያዘ በተፈጠረ ስጋት ግን ውድድሩን በ2016 እንዳስተናግድ ይሸጋሸግልኝ ብላ ጥያቄ አቀረበች፡፡ ካፍ አልተቀበለውም፡፡ ስለሆነም ውድድሩ ለምትክ አዘጋጇ ኢኳቶርያል ጊኒ መሰጠቱ ግድ ሆኗል፡፡ ጊኒ፤ ላይቤርያ እና ሴራልዮን ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድሮችን በአገራቸው መሬት እንዳያካሂዱም የኢቦላ ወረርሽኝ ምክንያት ነበር ታግደው ዓመቱን አሳልፈዋል፡፡
የፊፋ ቅሌት
ዓለምአቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋ በ2014 በበርካታ የአስተዳደር ቀውሶች ተበጥብጧል፡፡ በማህበሩ አመራሮች ላይ በተደጋጋሚ የቀረቡ ክሶች የተቋሙን ተዓማኒነት አደጋ ላይ ጥለውታል፡፡ በ2018 እ.ኤ.አ 21ኛውን ዓለም ዋንጫ ራሽያ፤ በ2022 እ.ኤ.አ 22ኛው የዓለም ዋንጫ ኳታር እንዲያዘጋጁ የተመረጡት በከፍተኛ የሙስና መረብ መሆኑ መጋለጡ አሁንም እያነናገርነው፡፡ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በተሰራጩ የምርመራ ሪፖርቶች የውስጥ ገበናው ተጋልጦበታል፡፡ ትልልቅ ባለስልጣናቱ እርስ በራስ እንዲወዛገቡ እና አንዳንዶቹም ከስልጣን እንዲለቁ ምክንያት የሆኑ ውዝግቦች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንትነት  ለ16 ዓመታት ያገለገሉት ሴፕ ብላተር ግን ቅሌቱን ለማስተባበል መሟገታቸውን አልተውም፡፡ በ2014 በከፍተኛ ደረጃ ከተወቀሱና ከተተቹ የስፖርት አመራሮች ግንባር ቀደሙ ተደንቋል፡፡ በ2015 እ.ኤ.አ ሴፕ ብላተር ለፊፋ ፕሬዚዳንትነት ለአምስተኛ ጊዜ ለመመረጥ ፍላጐት እንዳላቸው አስታውቀዋል፡፡
የኦሎምፒክ በጀት መጥፋት
በ2014 በከፍተኛ ድምቀት ለመካሄድ ከቻሉ የስፖርት መድረኮች በራሽያዋ ግዛት ሶቺ ለመካሄድ የበቃው የ2014 የክረምት ኦሎምፒክ ይጠቀሳል፡፡ በከፍተኛ የበጀት ወጭው እና በተሳካ መስተንግዶው ተደንቋል፡፡ የሶቺ የክረምት ኦሎምፒክ ለማዘጋጀት ራሽያ ከ50 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጭ አድርጋለች፡፡ የምንጊዜም ውድ የኦሎምፒክ መስተንግዶ  ሆኖ በታሪክ መዝገብ ሰፍሯል፡፡ ይሁንና ከፍተኛ በጀት የሚጠይቀው የኦሎምፒክ መስተንግዶ ዓመቱን ሙሉ ሲያከራክር ነበር፡፡ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ቶማስ ባች የኦሎምፒክ ውድድር ተሃድሶ እንደሚያስፈልገው በማሳሰብ ከፍተኛ ዘመቻ እያደረጉ ናቸው፡፡ በ2022 እኤአ የክረምት ኦሎምፒክ ለማዘጋጀት አመልክተው በተለያዩ ምክንያቶች እቅዳቸውን የሰረዙት ሶስት ከተሞች ናቸው፡፡ ይህ ያሳሰባቸው ፕሬዝዳንቱ ታላቁ የስፖርት መድረክ ትኩረት እንዳያጣ ይፈልጋሉ፡፡ የስዊድኗ ስቶክሆልምና የዩክሬኗ ኪዬቭ ከተሞች የክረምት ኦሎምፒክ ለማስተናገድ የነበራቸውን ፍላጎት ሰርዘዋል፡፡ በጀቱን አንችልም በሚል ምክንያት ነው፡፡  የክረምት ኦሎምፒኩን ብቻ ሳይሆን ዋናውን የኦሎምፒክ ውድድር ከወጭው ክብደት አንፃር ቢሆኑም ማለት ነው፡፡ ማዘጋጀት የሚፈልጉ አገራት ጠፍተዋል፡፡  ዓለም አቀፉን የኦሎምፒክ ኮሚቴ ሁኔታው አሳስቦታል፡፡ አስቀድሞ ኦሎምፒክን ለማስተናገድ  ለአንድ አዘጋጅ አገር ብቻ የሚሰጠውን እድል በመከለስ አገራት ለጣምራ አዘጋጅነት  እንዲያመለክቱ ግፊት እያደረገ ነው፡፡ በ2016 እኤአ ብራዚል በሪዮ ዴጄኔሮ ከተማ 31ኛውን ኦሎምፒያድ እንዲሁም በ2020 ጃፓን በቶኪዮ ከተማ 32ኛውን ኦሎምፒያድ እንዲያስተናግዱ ተመርጠዋል፡፡ በ2024 እኤአ 33ኛውን ኦሎምፒያድ ማን እንደሚያስተናግድ ግን ከወዲሁ የታወቀ ነገር የለም፡፡ የመስተንግዶ ወጭዉ በየኦሎምፒኩ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መምጣቱ አዘጋጅ አገር የማግኘቱን እድል እያጠበበው መጥቷል፡፡ በ1996 እኤአ አትላንታ ኦሎምፒክ 1.8 ቢሊዮን፤ በ2000 እኤአ ሲድኒ ኦሎምፒክ 3.8 ቢሊዮን፤ በ2004 እኤአ አቴንስ ኦሎምፒክ 15 ቢሊዮን፤ በ2008 እኤአ ቤጂንግ ኦሎምፒክ 40 ቢሊዮን እንዲሁም በ2012 እኤአ ለንደን ኦሎምፒክ 49 ቢሊዮን ዶላር ወጥቷል፡፡
የወርቅ ኳስ ፖለቲካ  
በ2014 እኤአ በከፍተኛ ደረጃ መነጋጋርያ ከሆኑ የእግር ኳሱ ዓለም አጀንዳዎች አንዱ የፊፋ የወርቅ ኳስ ሽልማት ነው፡፡ 3 የመጨረሻ እጩዎች ከታወቁባቸው የ2014 የመጨረሻ ወራት ወዲህ ክርክሩ በመጧጧፉም አሸናፊውን ለመገመት አዳጋች ሆኗል፡፡ የሽልማት ስነስርዓቱ ከ2 ሳምንታት በኋላ በዙሪክ እንደሚከናወን ይጠበቃል፡፡ በዓለም ኮከብ ተጨዋች ምርጫው የሻምፒዮንስ ሊግና የዓለም ዋንጫ ስኬቶች እንዲሁም አዳዲስ የእግር ኳስ ሪከርዶች የሚኖራቸው ተጽእኖ  አከራካሪ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በአንዳንድ የስፖርት ሚዲያዎች የምርጫው ሂደት ፖለቲካዊ አጀንዳ እየተንፀባረቀበት መሆኑም ተገልጿል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንት ሚሸል ፕላቲኒ የወርቅ ኳሱን የዓለም ሻምፒዮን የሆነ ተጨዋች መሸለም አለበት ብሏል፡፡ ከዚህ አስተያየት በኋላ በስፖርቱ ዙርያ ያሉ አሰልጣኞች፤ ተጨዋቾች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የወርቅ ኳሱን ማን ይሸለም በሚለው አጀንዳ ሲሟገቱ ሰንብተዋል፡፡  የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሊውስ ቫን ሃል፤ እውቁ የሆላንድ የእግር ኳስ ሰው ዮሃን ክሮይፍ፤ ለባየር ሙኒክ የሚጫወተው ዣቪ አሎንሶ የሚሸል ፕላቲኒን ሃሳብ ይጋራሉ፡፡ ሽልማቱ ለግብ ጠባቂው ኑዌር ይገባል ይላሉ፡፡ የሪያል ማድሪድ አሰልጣኝ የሆኑት ካርሎ አንቸሎቲ በበኩላቸው ሽልማቱ የሚገባው በግሉ ምርጥ ብቃት ላሳየ ተጨዋች ይገባል በሚል አስተያየት ለሮናልዶ ድጋፍ ሲሰጡ፤ የክለቡ ፕሬዝዳንት ፍሎረንቲኖ ፔሬዝም በዓለም እግር ኳስ ሁሉን ያሟላ ተጨዋች ሮናልዶ በመሆኑ መሸለሙ ተገቢ ነው ብለዋል፡፡  የቼልሲው ጆሴ ሞውሪንሆ በበኩላቸው የወርቅ ኳሱ ፖለቲካ ለእግር ኳስ እንደማይበጅ በመናገር ማንም ቢያሸንፍ ግድ እንደሌላቸው ይገልፃሉ ከሰሞኑ ደግሞ አንጋፋው የባርሴሎና ተጨዋች ዣቪ ኸርናንዴዝ ሮናልዶ ከሶስቱ እጩዎች ተርታ መሰለፍ እንደሌለበት ተናግሯል፡፡ የወርቅ ኳስ ለመሸለም በዓለም ዋንጫ ስኬት ማሳየት ዋና መስፈርት ሊሆን ይገባል በማለትም ሜሲ ካልተሸለመ ማኑዌል ኑዌር ቢሸለም ይገባዋል ብሏል፡፡  ባለፈው ዓመት ከሶስቱ የመጨረሻ እጩዎች አንዱ የነበረው ፈረንሳዊው ፍራንክ ሬበሪ ደግሞ ሽልማቱን አርያን ሮበን ባይወስድ እንኳን ለማኑዌል ኑዌር እንደሚገባ አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል የባርሴሎናው ኔይማር ሆኖ የሰጠው ድምፅ ሰሞኑን ግሎቦ በተባለ የአገሩ ጋዜጣ ወጥቷል፡፡ የብራዚል ብሔራዊ ቡድን አምበል ለቡድን አጋሩ ሊዮኔል ሜሲ ድጋፍ እንደሰጠ ተጋልጧል፡፡
ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር እንዳስታወቀው የፊፋ አባል ከሆኑ 209 አገራት ዋና አሰልጣኞች እና አምበሎች 87.3 በመቶ እንዲሁም ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች  94 በመቶ ድምፅ ሰጥተዋል፡፡ በምርጫው ባለፈው ዓመት ከፊፋ 205 አባል አገራት 505 ድምፅ ተሰብስቧል፡፡ 170 አምበሎች፤ 170 አሰልጣኞች እንዲሁም 165 የዓለም አቀፍ ሚዲያ ባለሙያዎች ነበሩ፡፡
ታዋቂው ጎል ስፖርት የድረገፅ አንባቢዎቹን ድምፅ እንዲሰጡ በማድረግ በሰራው ስሌት የዘንድሮ የወርቅ ኳስ ሽልማትን ማን ሊወስድ እንደሚችል በመቶኛ ተንብዮታል፡፡ ባለፈው ዓመት ሁለተኛውን  የወርቅ ኳስ የወሰደውና ዘንድሮ ሶስተኛውን ለመሸለም  እድል ያለው ክርስትያኖ ሮናልዶ በ57.2 በመቶ ድምፅ ከፍተኛውን ግምት አግኝቷል፡፡ ሮናልዶ በመጨረሻ እጩነት ሲቀርብ በውድድር ዘመኑ ከክለቡ ሪያል ማድሪድ ጋር የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን መውሰዱና  በ17 ጎሎች ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ መጨረሱ ይታወቃል፡፡ሊዮኔል ሜሲ በጎል ድረገፅ አንባቢዎች 22.6 በመቶ ግምት በመውሰድ ለወርቅ ኳሱ ሽልማት ባለው እድል ሁለተኛ ደረጃ ተሰጥቶታል፡፡ ሜሲ በ2014 የውድድር ዘመን ከክለቡ ባርሴሎና ጋር ምንም አይነት የዋንጫ ድል  ባያስመዘግብም በስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋና በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የከፍተኛ ግብ አግቢነት ክብረወሰኖችን መቆጣጠሩ ወደ ፉክክሩ አግብቶታል፡፡ ሁለቱን አጥቂዎች ክርስትያኖ ሮናልዶንና ሊዮኔል ሜሲን በመፎካከር ከሶስቱ የመጨረሻ እጩዎች አንዱ ለመሆን የበቃው ደግሞ የጀርመን ብሄራዊ ቡድንና የባየር ሙኒክ ግብ ጠባቂ የሆነው ማኑዌል ኑዌር ነው፡፡ ማኑዌል ኒዌር በ20ኛው የዓለም ዋንጫ ከጀርመን ብሄራዊ ቡድን ጋር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን መብቃቱ ከፍተኛ ድጋፍ ያስገኝለታል፡፡ ኑዌር ከክለቡ ባየር ሙኒክ ጋር ባለፈው የውድድር ዘመን አራት ትልልቅ የዋንጫ ድሎችን አስመዝግቧል፡፡ በጎል ድረገፅ አንባቢዎች ለወርቅ ኳሱ በ20.2 በመቶ ድምፅ የማሸነፍ እድል ሶስተኛ ደረጃ ወስዷል፡፡ በፊፋ የዓለም የኮከብ ተጨዋቾች ምርጫ ታሪክ ከመጨረሻዎቹ እጩዎች ተርታ ለመግባት የቻለው ብቸኛው ግብ ጠባቂ  ከስምንት ዓመት በፊት የጁቬንትስ እና የጣሊያን ተጨዋች የሆነው ጂያንሉጂ ቡፎን  ነበር፡፡ በሌላ በኩል የወርቅ ኳስ ተሸልሞ የሚያውቅ በረኛ በታሪክ አንድ   ጊዜ ብቻ አጋጥሟል፡፡ በ1963 እኤአ  ‹ጥቁሩ ሸረሪት› በሚል ስም የሚጠራው ራሽያዊው ግብ ጠባቂ ሌቭያሺን የተሸለመበት ነበር፡፡
የማራቶን ሪከርድና ኃይሌ
2014 እኤአ የዓለም የማራቶን ሪከርድ በኬንያዊው አትሌት ዴኒስ ኬሜቶ በበርሊን ማራቶን መሰበሩ አበይት ክስተት ነበር፡፡ ዴኒስ ኬሚቶ ያስመዘገበው አዲስ የዓለም ማራቶን ሪከርድ 2፡02፡57 የተመዘገበ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሳው በ2007 እና በ2008 እኤአ ላይ ለሁለት ጊዜያት የዓለም ማራቶን ክብረወሰኖችን ለማስመዝገብ የበቃው ኢትዮጵያዊ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ራነርስዎርልድ መፅሄት ከወር በፊት ይፋ ባደረገው አንድ ዘገባ በማራቶን ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ያገኙ አትሌቶችን ደረጃ እንደሚመራ ማስታወቁ ኃይሌ ገ/ስላሴን ያስነሣዋል፡፡ በ2015 እኤአ የመጨረሻ የማራቶን ውድድሩን ለመሮጥ እንደወሰነ ያስታወቀው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በሩጫ ዘመናቸው ከፍተኛ ገቢ ከሽልማት ገንዘብ ያገኙ አትሌቶች ደረጃን የሚመራው በሰፊ ልዩነት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ደረጃውን ሳይነጠቅ ለዓመታት እንደሚቆይ ያመለክታል፡፡ ራነርስዎርልድ መፅሄት በዓለም አቀፍ የማራቶን ውድድሮች የምንግዜም ከፍተኛ የገንዘብ ተሻላሚዎች ደረጃን ያገኘው ከዓለም አቀፉ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ስታስቲክስ ማህበር መሆኑን የሚገልፀው መፅሄቱ በወንዶች ምድብ የምንግዜም ከፍተኛ ተሻላሚ ደረጃ ኃይሌ ገብረስላሴ በ3,548, 398 እንዲሁም በሴቶች ፓውላ ራድክሊፍ በ2,236,415 ዶላር ገቢያቸው ይመሩታል፡፡ በሯጭነት ከ23 ዓመታት በላይ ልምድ ያለውና 41ኛ ዓመቱን የያዘው አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ከጡረታ በፊት አንድ የመጨረሻ ማራቶን የመሳተፍ ፍላጎት እንዳለው የተናገረው ሰሞኑን ነው፡፡ በማራቶን ተወዳዳሪነት 9 ውድድሮችን ያሸነፈው ኃይሌ ገብረስላሴ ለአራት ጊዜያት የበርሊን ማራቶንን፤ ለሶስት ጊዜያት የዱባይ ማራቶንን አሸንፏል፡፡ በማራቶን ሁለት የዓለም ክብረወሰኖችን ያስመዘገበው ኃይሌ ከ2 ሰዓት ከሰባት ደቂቃዎች በታች በ10 ማራቶኖች፤ ከ2 ሰዓት ከ06 ደቂቃ በታች በአምስት ማራቶኖች፤ ከ2 ሰዓት 05 ደቂቃ በታች በሶስት ማራቶኖች እንዲሁም ከ2 ሰዓት ከ04 ደቂቃ በታች በአንድ ማራቶን ርቀቱን በመሸፈን ስኬታማ ነበር፡፡

    ስነቃል (Oral literature) የሰው ልጅ ራሱን ከሚገልጥባቸው፣ ስሜቱን ከሚነግርባቸውና ማንነቱን ከሚቀርስባቸው ባህላዊ እሴቶች አንዱ ነው፡፡ በመሆኑም ማህበረሰብና ስነቃል ያላቸው ቁርኝት እጅጉን ጥብቅ ነው፡፡ ለዚህም ነው የአንድን ማህበረሰብ ባህላዊ እሴቶች ማጥናትና መረዳት ማህበረሰቡን ማወቅ ነው የሚባለው፡፡  አይነቱና መጠኑ ከማህበረሰብ ማህበረሰብ ቢለያይም ስነቃል የሌለው ማህበረሰብ የለም፡፡
የጽሑፌ ማጠንጠኛ ስነቃል፣ ከስነቃልም (በቅርጽ ግጥማዊ የሆነው) ቃል ግጥም (Oral poetry) ነው፡፡ ትኩረቴም በደርግ ዘመን በስርዓቱ ላይ በተቃውሞ የተነገሩት (በድጋፍ ከተነገሩት ይበዛሉና) ቃል ግጥሞች ናቸው፡፡ በዚህም በሰፊው የተነገሩ ጥቂት ቃል ግጥሞችን “የዘመኑን እውነት” (ግጥሞቹ የተነገሩባቸው ግፊቶች ዘመኑ ውስጥ አሉና) እማኝ አድርጌ እቃኛለሁ፡፡ ምክንያቴም በአንድ የአገዛዝ ዘመን የተነገሩ ስነቃሎች የአገዛዙን መንፈስ፣ የወቅቱን ማህበረሰብ አስተሳሰብና ስነልቡና እንዲሁም ለአገዛዙ የነበረውን ምላሽ በጉልህ ያሳያሉ ብዬ ማመኔ ነው፡፡ ነገሬን እንዲህ አስረድቼ “ይለፍ” አልነፈገምና ልቀጥል፡፡
ወታደራዊው የደርግ መንግስት የንጉሡን ስርዓት “አስወግዶ” ስልጣን በመያዝ ይህቺን ሀገር ለ17 ዓመታት ማለትም ከ1966 እስከ 1983 ዓ.ም አስተዳድሮአል፡፡ በእነዚህ ዓመታትም በሀገሪቱ የተለያዩ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ለውጦች ተመዝግበዋል፡፡ ከለውጦቹና ክንዋኔዎቹ መካከል ስርዓቱ ቀድሞ ያቀነቀነው የመሬት ለአራሹ አዋጅ፣ የእድገት በህብረት ዘመቻ፣ የሠፈራ ፕሮግራም፣ ቀይ ሽብር፣ ብሔራዊ ውትድርና የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡
በዘመኑ የነበረው ማህበረሰብም እንደቀደሙት ዘመናት አባቶቹ ሁሉ እነዚህና ሌሎች ከስርዓቱ መለወጥ ጋር ተያይዘው የመጡ ክስተቶች ያሳደሩበትን የአዎንታም ይሁን የአሉታ፣ የድጋፍም ይሁን የተቃውሞ ስሜት በስነቃል፣ ከስነቃልም በቃል ግጥም ሲገልጽ ኖሮአል፡፡ በደርግ ዘመን የተነገሩት ቃል ግጥሞች በወቅቱ በመንግስት የተከወኑ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ለውጦችን መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ ትኩረቴ በተቃውሞ የተነገሩት ላይ መሆኑን ቀድሜ አትቻለሁና ወደነሱ ልለፍ፡፡ ከእነሱም በዘመኑ “ጉልህ” ክስተቶች በነበሩት ማለትም “ቀይ ሽብር”፣ “ሠፈራ” እና ጦርነት ላይ የተነገሩትን ላንሳ፡፡
በደርግ ዘመን በነበረው የ“ቀይ ሽብር ዘመቻ” ሳቢያ የበርካታ ዜጎች (በተለይ የወጣቶች) ህይወት አልፎአል፡፡ ይህ “ዘመቻ” በመላው ሀገሪቱ ሊባል በሚችል መልኩ የተካሄደ ሲሆን በዘመቻውም የጠፋው የሰው ሕይወት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ነው፡፡ በዘመኑ የነበረው ማህበረሰብም “ዘመቻው” ያደረሰውን ጉዳትና ጉዳቱም የፈጠረበትን ሀዘንና ስሜት በተለያዩ የስነቃል አይነቶች በተለይም በቃል ግጥም ገልጾአል፡፡ በ“ቀይ ሽብር” ላይ ከተነገሩ ቃል ግጥሞች መካከል በጎንደር ከተማ የተነገሩትን ሁለት ቃል ግጥሞች እንመልከት፡፡
መላኩ ተፈራ የእግዜር ታናሽ ወንድም
የዛሬን ማርልኝ የነገን አልወልድም
(ይህንን ማርልኝ ከእንግዲህ አልወልድም)
ግጥሙ መላኩ ተፈራ ጎንደርን “ያስተዳድር” በነበረበት ዘመን የተነገረ ነው፡፡ መላኩ በጎንደር በርካታ የ“ኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ” (ኢህአፓ) አባላት የሆኑ ወጣቶች “እንዲገደሉ” እንዳደረገና “የፈለገውን የመግደልና የፈለገውን የማዳን” ስልጣን እንደነበረው ይነገራል፡፡ በዚህ ወቅት ነው አንዲት ልጇ ሊገደልባት የነበረች እናት ይህንን ግጥም የተናገረችው ይባላል፡፡ (ይባላል ነው!)
በግጥሙ ሴቲቱ “ማንም ከልካይ የሌለበትንና የፈለገውን የሚያደርገውን” መላኩን “የእግዜር ታናሽ ወንድም” አድርጋዋለች፡፡ ከዚህም ሌላ “ይህንን ማርልኝ” እንጂ “ከእንግዲህ አልወልድም” በማለት ሌላ ልጅ ላለመውለድ ቃሏን እስከመስጠት ደርሳለች፡፡ ይህ ግጥም የዘመኑ ማህበረሰብ በዘመቻው የደረሰበትን ጉዳትና ሰቀቀን በሚገባ ማሳየት የሚችል ነው፡፡ በዚያው በጎንደር (ቀይ ሽብር ከፍተኛ ጉዳት ካደረሰባቸው ከተሞች አንዷ ጎንደር መሆኗን ልብ ይሏል፡፡) የተነገረ አንድ ሌላ እንጨምር፡፡
የማራኪ ጎመን አልበላም እርሜ ነው
ያባሳሜል ጎመን አልበላም እርሜ ነው
 እሱ የበቀለው በወጣቶች ደም ነው፡፡
ሁለቱ (የተሰመረባቸው) በጎንደር በ“ቀይ ሽብር” የተገደሉ ወጣቶች በጅምላ ይቀበሩባቸው የነበሩ ቦታዎች ናቸው፡፡ ይህንን የሚያውቀው ሀገሬው በሁኔታው የተሰማውን የመረረ ሀዘን ፊት ለፊት ሳይሆን አዙሮና አጠይሞ በግጥሙ ገልጾአል፡፡ የሀገሬው ጉዳይ ወይንም ሊያስተላልፍ የፈለገው መልዕክት ስለሚበላው ጎመን አይደለም፡፡ እሱን ያስቆጨውና ያስመረረው በሁለቱ ቦታዎች ላይ የፈሰሰው የወጣቶቹ (የልጆቹ) ደም ነው፡፡ ሆኖም ይህንን ድርጊት በግልጽ ለመቃወምና ለመውቀስ ፍርሀት ስለነበረበት ጎመንን ጠርቶ ቁጭቱን ገልጾአል፡፡
ግጥሞቹ በዘመኑ የነበረው ማህበረሰብ በቀይ ሽብር የደረሰበትን ፍራት፣ ጉዳትና ሰቀቀን እንዲሁም ለክስተቱ የነበረውን ምላሽ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ምንም እንኳን ግጥሞቹ የተነገሩት በጎንደር በነበረው ሁኔታ መነሻነት ነው ቢባልም የዘመቻው ጉዳት በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎችም የነበረ በመሆኑ የምንደርስበት መደምደሚያ የተለየ አይሆንም፡፡
“ሠፈራ” ላይ የተነገሩ ቃል ግጥሞችን እንመልከት፡፡ “የሠፈራ ፕሮግራም” በደርግ ዘመነ መንግስት በተለያዩ ጊዜያት ተካሂዶአል፡፡ በዚህም በሀገሪቱ ልዩ ልዩ ቦታዎች በተፈጠረ “የተፈጥሮ ችግርና ድርቅ” ምክንያት መንግስት የአንዳንድ አካባቢ ነዋሪዎችን ከነበሩበት ቦታ አንስቶ የተሻለ ነው ወደአለው ቦታ እንዲሠፍሩ አድርጎአል፡፡ የሠፈራው ተገቢነት አከራካሪ ቢሆንም ማህበረሰቡ “እትብቴ ተቀብሮበታል!” ከሚለውና ተኩሎና ተድሮ ልጆች ካፈራበት ርስቱ ጋር ያለው ቁርኝት እጅጉን የጠበቀ በመሆኑ፣ ተነስተህ ወደ ሌላ ቦታ ሥፈር ሲባል የደረሰበት የስነልቡና እና “የማንነት ጥያቄ” ቀውስ ቀላል አልነበረም፡፡ ያም ሆኖ ግን በአንድ በኩል በልቶ ህይወቱን ለማቆየት ከነበረው ተስፋና ጉጉት፣ በሌላም በኩል በመንግስት ተፅእኖ የኖረበትን መሬት ለቅቆ ወደተባለው ቦታ ሄዶ ሠፍሮአል፡፡ ሠፈራው ያሳደረበትንም ከቀዬው የመነጠል መሪር ስሜት በቃል ግጥሞች ገልጾአል፡፡ እንዲህ እያለ:-
የኮምሽን ስንዴ ጣዕሙ ጥሩ ነበር
ውለው እያደሩ ስፈሩ ባልነበር!
ግጥሙ ምንም እንኳን በወቅቱ በመንግስት ለማህበረሰቡ ይታደል ስለነበረው “የኮሚሽን ስንዴ” የሚናገር ቢመስልም ጉዳዩ ሠፈራው ነው፡፡ ማህበረሰቡ በየጊዜው ያላችሁበትን ለቅቃችሁ ወደ ሌላ ቦታ “ሥፈሩ” በመባሉ የነበረውን ተቃውሞ ግጥሙ በሚገባ ያሳያል፡፡ ሆኖም በወቅቱ ይህንን ተቃውሞውን በግልጽ ለመናገር የማይችል በመሆኑ (አሁን ይችላል አላልኩም!) ቃላዊ ሀብቱን ተጠቅሞ፣ ስለ ስንዴ ያወራ በመምሰል በሠፈራው ላይ ያለውን ተቃውሞ ገልጾአል፡፡
ምንድን ነው ሠፈራ ዶሮ ይመስል
ላከኝ ከጦር ሜዳ ከወንዶች ሰፈር
ይህ ደግሞ ከቀደመው ቃል ግጥም በከረረ መልኩ ማህበረሰቡ ለሠፈራው የነበረውን ተቃውሞ የገለጸበት ነው፡፡
 በግጥሙ የመጀመሪያ መስመር ላይ “ሠፈራ” ለዶሮ እንጂ ለሰው እንዳልሆነ/እንደማይሆን ያስረግጣል፡፡ ይህም “እኛ ሰዎች ሆነን ሳለ የዶሮ ያህል አሳንሰው እያሠፈሩን ነው” ወደሚል ትርጉም ያደርሰናል፡፡ ይህንን ልብ ብለን ወደ ሁለተኛው የግጥሙ መስመር ስናልፍ ግን የምናገኘው መልዕክት ከዚህም የመረረና የጠነከረ ነው፡፡ ማህበረሰቡ በግጥሙ መንግስትን “ከሰው አሳንሰህ እንደ ዶሮ ከምታሠፍረኝ ወደ ጦር ሜዳ ላከኝ” ብሎአል፡፡ በጦር ሜዳ ሞት አለ፡፡ ሆኖም እንደ ዶሮ ከመኖር ጦር ሜዳ ሄዶ መሞትን መርጦአል፡፡… ይህንን እዚህ ላይ ገተን በዘመኑ በነበረው የማያቋርጥ ጦርነት ላይ ወደተነገረው እንለፍ፡፡
የደርግ ዘመን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጊዜያት ከጦርነት የፀዳ ነበር ማለት ማበል ነው፡፡ በቀዳሚዎቹ የአገዛዙ ዓመታት ከሶማሊያ መንግስት ጋር ከባድና ብዙ ጉዳት ያደረሰ ጦርነትን አድርጎአል፡፡ እንዲሁም ከኤርትራ ነጻ አውጪ ግንባሮችና ከወያኔ ሠራዊት ጋር የስልጣን ዘመኑ እስከሚያበቃበት የመጨረሻዎቹ ወቅቶች ድረስ ተዋግቶአል፡፡
 በእነዚህ ጦርነቶችም በርካታ ዜጎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ጦርነቱ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ በመሆኑም የደርግ መንግስት በተለይ በመጨረሻዎቹ ዓመታት “ብሔራዊ ውትድርና” በሚል ብዙ ወጣቶችን “አፍሶ” ወደ ጦር ግንባሮች ልኳል፡፡
ይህ ሁኔታ ልጁን ለተነጠቀው ማህበረሰብ እጅግ መራር ሀዘንን የፈጠረ በመሆኑ ሌላ ጊዜ እንደሚያደርገው ሁሉ ስሜቱን በቃል ግጥም አውስቷል፡፡ ጦርነቱ ላይ የተነገረን አንድ ቃል ግጥም እንጥራ፡፡እንዴት ያል ዘመን ነው የዘመን ቆረንጮ
ወልዶ ለጦርነት ሰርቶ ለመዋጮ
በግጥሙ የመጀመሪያ መስመር ላይ ማህበረሰቡ ሆኖና ተደርጎ የማያውቅ ነገር በዘመኑ በመፈጸሙ ይህንን ሲወቅስ እንመለከታለን፡፡ በሁለተኛው መስመር ላይ በሚገኙት ሁለት ሐረጎች የምናገኘው መልዕክት ግን ሁለት ነው፡፡
ማህበረሰቡ የወለደውን ልጅ ጦርነቱ እየነጠቀው በመሆኑ ተስፋ ቆርጦአል፡፡ ሰው የሚወልደው ለጦርነት አይደለም፡፡ ለብዙ ሰዋዊ ዓላማዎች ነው፡፡
 ሆኖም ግን በወቅቱ ለነበረው ማህበረሰብ መውለድ ለጦርነት ሆኖ ተሰምቶታአል፡፡ በመሆኑም “ምናባቱ ባልወልድስ” እስከማለት አድርሶታል፡፡
 ሁለተኛው ሐረግ ደግሞ ማህበረሰቡ ለመስራትም ልቡ እንደሰነፈና ተስፋ እንደቆረጠ ያሳያል፡፡ በዘመኑ ማህበረሰቡ “ለእናት ሀገር” በሚል መዋጮ እንዲያዋጣ ይደረግ ነበር፡፡ በመሆኑም “ባልሰራስ፣ ቢቀርስ” በሚል ተስፋ ቆርጦአል፡፡
በሀገራችን በዘመነ ደርግ ስርዓቱ ላይ የተነገሩትን የተቃውሞ ቃል ግጥሞች አነሳሁ እንጂ በየዘመናቱና ስርዓቱ በተለያዩ ቋንቋዎች ሥፍር ቁጥር የሌላቸው ቃል ግጥሞች ተነግረዋል፡፡ አሁንም ይነገራሉ! እነዚህ ቃል ግጥሞች ማህበረሰቡ ለየዘመኑና በዘመኑ ለነበረው ስርዓት የነበረውን ሁሉን አቀፍ ስሜትና ምላሽ የያዙ በመሆናቸው ዘመኑንና የወቅቱን ማህበረሰብ ስነልቡና የሚያሳዩ ህያው ምስክር ናቸው፡፡
ይህንን እየከተብኩ እንዲህ አሰብኩ፡፡ በዘመነ ኢህአዴግ እየተነገሩ ያሉ ቃል ግጥሞችስ ምን ይመስሉ ይሆን? በዘመናችን ቃል ግጥምን ሊያስነግሩ የሚችሉ በርካታ ጉዳዮች አሉ፡፡
 በርካታ! ስራ አጥነት፣ መልሶ ግንባታ፣ ውሃ ማቆር፣ የኑሮ ውድነት፣ ስደት፣ ምርጫና የፖለቲካ ውዝግብ… ሌሎችም ብዙ! ታዲያ ማህበረሰቡ ለእነዚህ ጉዳዮችና በአጠቃላይ ለአገዛዙ ያለውን ምላሽ በቃል ግጥሙ እንዴት ገልጾ ይሆን? ጊዜና አጋጣሚ ቢፈቅድ ሌላ ጊዜ እመለስባቸዋለሁ፡፡
መልካም ሰንበት!!

Published in ህብረተሰብ
Page 1 of 13