• በ2014 የኢትዮጵያ አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ከ8 በላይ ማራቶኖችን አሸንፈዋል፡፡
  • በዓመቱ ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ የኢትዮጵያ አትሌቶች ብዛት ከኬንያ በእጥፍ ይበልጣል፡፡
  • ቀነኒሳ በፓሪስ፤ ጥሩነሽ በለንደን የመጀመርያ ማራቶናቸውን ይሮጣሉ፡፡
  • የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች የበላይነት ከነገሰ 20 ዓመታት አልፈዋል፡፡
  • በትልልቅ ማራቶኖች  ታዋቂ አትሌት  ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ፤ ሪከርድ በመስበር ካሸነፈ በሽልማት እና በተለያዩ ጥቅማጥቅሞች ከሆነ በአማካይ እስከ 750ሺ ዶላር ሊያገኝ ይችላል፡፡

       በመላው ዓለም ታላላቅ የማራቶን ውድድሮች የሚካሄዱበት ወቅት ከገባ ወር አልፎታል፡፡ በትልልቆቹ የማራቶን ሊግ ውድድሮች እና ሌሎች ማራቶኖች ኢትዮጵያዊያን  ሯጮች በውጤታማነት ነጥብ ለማስመዝገብ፤ በየውድድሩ የሚቀርቡ ማራኪ የገንዘብ ሽልማቶችና ቦነሶችን ለመሰብሰብ ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የማራቶን ሯጮች ዘንድሮ ያሳዩት መልካም አጀማመር ‹‹ማራቶን ልዕልቷ››ን ከእነ ክብረወሰኖቿ ወደ ቤቷ ሊመልሷት እንደሚችሉ ተስፋ ፈጥሯል፡፡ 2014 ከገባ ወዲህ ኢትዮጵያዊ የማራቶን ሯጮች በሁለቱም ፆታዎች የውድድር ዘመኑን ፈጣን ሰዓቶች በማስመዝገብ እና በተለያዩ የዓለም ከተሞች በተደረጉ የማራቶን ውድድሮች በማሸነፍ እና ተከታትለው በመግባት ከፍተኛ የበላይነት አሳይተዋል፡፡ በዓለም የጎዳና ላይ ሩጫዎች ማህበር ኤአርአርኤስ ድረገፅ የውድድር ዘመኑ የፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ላይ እንደተመለከተው ባለፉት ሶስት ወራት በተደረጉ የማራቶን ውድድሮች በወንዶች ከተመዘገቡ 24 ሰዓቶች 25 ፤ በሴቶች ምድብ ደግሞ ከ25 ፈጣን ሰዓቶች 16 በኢትዮጵያን አትሌቶች ተመዝግበዋል፡፡ ባለፉት 3 ወራት   በወንዶች ምድብ ፀጋዬ መኮንን በዱባይ፤ በዙ ወርቁ በሂውስተን እንዲሁም ድሬባ ሮቢ በማራኬሽ በተካሄዱ ማራቶኖች አሸንፈዋል፡፡ በሴቶች ምድብ ደግሞ ማሬ ዲባባ በሻይናሜን፤ ሙሉ ሰቦቃ በዱባይ፤አበበች አፈወርቅ በሂውስተን እንዲሁም ድንቅነሽ መካሻ በሙምባይ የማራቶን ውድድሮች ድሎችን ተጎናፅፈዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት በሮም ማራቶን በሁለቱም ፆታዎች ያሸነፉት  ሹሜ ሃይሉ እና አየሉ ለማ መሆናቸው፤ በሚቀጥሉት ሳምንታት በሚካሄዱት የፓሪስ፤ የለንደንና የቦስተን ማራቶኖች ኢትዮጵያውያን ከኬንያውያን የተሻለ ውጤታማ እንደሚሆኑ ያመለክታል፡፡ በ2013 /14 “የዎርልድ ማራቶን ሜጀር ሲሪዬስ” “ማራቶን ሊግ” በስድስት ትልልቅ ማራቶኖች  በሚመዘገብ ውጤት መሰረት 1ኛ ሆኖ መጨረስ በሁለቱም ፆታዎች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ  ዶላር ይገኝበታል፡፡ ከሳምንት በኋላ በፓሪስ፤ ከ15 ቀናት በኋላ በለንደን እንዲሁም ከሶስት ሳምንታት በኋላ በቦስተን የሚካሄዱት የማራቶን ሊግ ውድድሮች የኢትዮጵያና የኬንያ አትሌቶች ፉክክር የሚጠበቅባቸው ናቸው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በአትሌቲክስ  የረጅም ርቀት ውድድሮች የምንግዜም ከፍተኛ ውጤት  በማስመዝገብ የሚታወቁት ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ  በማራቶን የመጀመርያ ተሳትፏቸውን በሚቀጥሉት  ሳምንታት ማድረጋቸው ሲያነጋግር ሰንብቷል። የ31 ዓመቱ አትሌት  ቀነኒሳ በቀለ የመጀመርያ ማራቶኑን የዛሬ ሳምንት በፓሪስ ሲሮጥ፤  ከአስራ አምስት ቀናት በኋላ ደግሞ በለንደን ማራቶን   ጥሩነሽ ዲባባ ትሳተፋለች፡፡
በ2013 /14 የማራቶን ሊግ በቀጣይ ሳምንታት በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ከሚካሄዱ ማራቶኖች የ2013 /14 ማራቶን ሊግ ነጥብ የሚያዝባቸው ትኩረት ይስባሉ፡፡  ከማራቶን ሊግ ስድስት ትልልቅ  ውድድሮች የመጀመርያው የዛሬ ወር የተካሄደው የቶኪዮ ማራቶን ነበር፡፡ በማራቶን ሊግ በስድስት ከተሞች የሚደረጉት ውድድሮች የቶኪዮ፤ የለንደን፤ የቦስተን፤ የበርሊን የቺካጎና የኒውዮርክ ማራቶኖች ናቸው፡፡  ከወር በፊት በተካሄደው የቶኪዮ ማራቶን በሴቶች ኢትዮጵያዊቷ ትርፊ ፀጋዬ ማሸነፏ ሲታወስ በወንዶች ደግሞ ኬንያዊው ዲክሰን ቹምባ አሸንፈዋል፡፡ የየ2013 /14 ማራቶን ሊግን በወንዶች ምድብ በ50 ነጥብ የሚመራው የኬንያው ዴኒስ ኪሜቶ ነው፡፡ ቶኪዮ እና በቺካጎ ማራቶኖችን የቦታዎቹን ሪከርዶች በማስመዝገብ ያሸነፈው ዴኒስ ኪሜቶ ከሶስት ሳምንታት በኋላ በቦስተን ማራቶን ከአምናው አሸናፊ ሌሊሳ ዴሲሳ መገናኘታቸው ይጠበቃል፡፡ ሌሊሳ በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ በ40 ነጥብ 3ኛ  ላይ ነው፡፡ አምና የመኻራቶን ሊጉን በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር የወሰደው ፀጋዬ ከበደ በ45 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ የያዘ ሲሆን ከሁለት ሳምንት በኋላ አምና ባሸነፈበት የለንደን ማራቶን  በመሳተፍ የሊጉን የመሪነት ደረጃ ለመረከብ ያነጣጥራል፡፡ የማራቶን ሊጉን ደረጃ በሴቶች ምድብ የሚመሩት እኩል 50 ነጥብ ያስመዘገቡት ሁለቱ ኬንያውያን ፕሪሲካ ጂፔቶ እና ሪታ ጄፔቶ ናቸው፡፡ ፕሪስካ በለንደን፤ ሪታ በቦስተን ማራቶኖች ሲወዳደሩ፤ በ40 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ይዛ የምትገኘው ሌላዋ ኬንያዊት ኤድና ኪፕላጋት በለንደን ትሮጣለች፡፡
ቀነኒሣ በፓሪስ የመጀመርያ ማራቶን ውድድሩን የዛሬ ሳምንት በፓሪስ የሚሮጠው ቀነኒሣ  በቀለ አሸንፎ አጀማመሩን ለማሳመር ፍላጎት እንዳለው በተደጋጋሚ ገልጿል፡፡ የማራቶንን 42.195 ኪ.ሜ ርቀት በሩጫ ዘመኑ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሮጥ 2 ከ03፤ ከ2 ከ05 እንዲሁም 2 ከ06 ለመግባት እንደሚያስብ የተናገረ ሲሆን፤ ማናጀሩ ጆስ ሄርማንስ ከ2 ሰዓት ከ05 ደቂቃ በታች መግባት እንደሚችል ምናልባትም የፓሪስ ማራቶንን የቦታ ሪከርድ በመስበር ጥሩ አጀማመር እንደሚኖረው መስክረዋል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በፓሪስ ማራቶን ከተሳካለት በኋላ ዋና ዓላማው እስከ 2016 እኤአ ብቃቱን በመጠበቅ በ30ኛው ኦሎምፒያድ ብራዚል ሪዮዲጄኔሮ ላይ በመሳተፍ የወርቅ ሜዳልያ ማግኘት መሆኑን ጆስ ሄርማንስ በተጨማሪ ተናግረዋል፡፡ ፓሪስ ማራቶን ዘንድሮ ሽናይደር ኤሌክትሪክስ በተባለው ኩባንያ ስፖንሰርነት  ከሳምንት በኋላ የሚደረገው በታሪኩ ለ38ኛ ጊዜ ነው፡፡ በዚህ ውድድር ላይ ለመጀመርያ ጊዜ ማራቶን የሚሮጠው ኢትዮጵያዊ አትሌት ቀነኒሳ ብቻ አይደለም፡፡ ሌላኛው አዲስ ኢትዮጵያዊ አትሌት በሃይሉ ከተማ ይባላል፡፡ በማራቶን ምርጥ ሰዓታቸው ከ2 ሰዓት ከ10 ደቂቃዎች በታች ያስመዘገቡ የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች ተሳታፊ በሚሆኑበት የፓሪስ ማራቶን ላይ በወንዶች ሌሎች አራት አትሌቶች እንዲሁም በሴቶች ሁለት አትሌቶች ኢትዮጵያን በመወከል ተወዳዳሪ ናቸው፡፡ በወንዶች ምድብ ባስመዘገበው ፈጣን ሰዓት በአንደኛ ደረጃ የሚጠቀሰው አብዱላህ ሻሚ ነው 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ42 ሴኮንዶች ፈጣን ሰዓት አለው፡፡ ሌሎቹ 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ12 ሰኮንዶች ያስመዘገበው አዝመራው በቀለ፤ 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ35 ሰኮንዶች ያለው  ነጋሪ ተፈራ፤ 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ35 ሰኮንዶች የሮጠው ልመነህ ጌታቸው እና 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ41 ሰኮንዶች የተመዘገበለት ገዛሐኝ ግርማ ናቸው፡፡ በሴቶች ምድብ  ደግሞ 2 ሰዓት ከ25 ደቂቃዎች ከ17 ሰኮንዶች ያስመዘገበችው መስከረም አሰፋ እና 2 ሰዓት ከ27 ደቂቃዎች ከ12 ሰኮንዶች የተመዘገበላት ዘምዘም አህመድ ናቸው፡፡
የፓሪስ ማራቶን አብይ ስፖንሰር የሆነው ሽናይደር ኤሌክትሪክስ በኦፊሴላዊ መግለጫው የአትሌት ቀነኒሳ በቀለ ተሳታፊነት የውድድሩን ድምቀት እንደጨመረው ገልፆ፤  አትሌቱ የቦታውን ክብረወሰን የማስመዝገብ ብቃት እንዳለው ገምቷል፡፡ ሌሎች የአትሌቲክስ ዘገባዎች በአንፃሩ አትሌት ቀነኒሳ በፓሪስ የዓለም ሪከርድን ለመስበር ብዙ እድል እንደሌለው ቢያመለክቱም ከማራቶን የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች አንዱን ሊያስመዘግብ እንደሚችል ጽፈዋል። አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ከ4 ወራት በፊት የመጀመርያ ግማሽ ማራቶን ውድድሩን በእንግሊዝ ኒውካስትል ባደረገበት ወቅት ያስመዘገበው ውጤት በማራቶን ጠንካራ ተፎካካሪ እንደሚሆን ያረጋገጠበት ነው፡፡ በወቅቱ በግማሽ ማራቶን ውድድሩ ታላላቆቹን አትሌቶች ሞ ፋራህና ኃይሌ ገብረስላሴን አስከትሎ በመግባት  ሲያሸንፍ ያስመዘገበው ሰዓት 1 ሰዓት ከ09 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜ በፓሪስ ማራቶን ማሸነፍ እንደሚችል ያመለክታል በሚል ግምቱን የሰነዘረው ደግሞ ሌትስ ራን የተባለው የአትሌቲክስ ዘጋቢ ድረገፅ ነው። አትሌቲክስ ኢልስትሬትድ የተባለ ድረገፅ በበኩሉ በቀነኒሳ የመጀመርያ የማራቶን ተሳትፎ ላይ በሰራው ትንታኔ አትሌቱ ፓሪስ ላይ ስኬታማ ጅማሮ እንደሚኖረው ሲያስረዳ፤ በመጀመርያው ማራቶኑ ቢፈጥን በ2 ሰዓት ከ01 ደቂቃ ከ05 ሴኮንዶች (አዲስ እና አስደናቂ የዓለም ሪከርድ ሊሆን የሚችል ነው) ከዘገየ ደግሞ ከ2 ሰዓት 06 ደቂቃዎች አካባቢ ሊገባ እንደሚችል ገምቷል፡፡ ከ1500 ሜትር ጀምሮ እስከ ግማሽ ማራቶን ባሉ ውድድሮች የዓለማችን የምንግዜም ምርጥ አትሌት የሆነው ቀነኒሳ በማራቶን የሚኖረው ስኬት በአትሌቲክስ ታሪክ ከፍተኛው ውጤት ያስመዘገበ አንደኛ አትሌት ያደርገዋል፡፡ በ5ሺ እና በ10ሺ ሜትር በያዛቸው ክብረወሰኖች ላለፉት 10 ዓመታት  በበላይነት የቆየው አትሌቱ፤ በሁለቱ ርቀቶች በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ እንዲሁም በአገር አቋራጭ ውድድሮች 19 የወርቅ ሜዳልያዎች ሰብስቧል፡፡ እነዚህን የቀነኒሣ ከፍተኛ ውጤቶች ከዘረዘረ በኋላ በፓሪስ የመጀመርያ ማራቶኑን ሲሮጥ ከዓለም ሪከርድ ይልቅ የቦታውን ክብረወሰን ማሻሻል እንደሚችል የገመተው ደግሞ ራነርስ ዎርልድ የተባለው የአትሌቲክስ ዘጋቢ መፅሄት ነው፡፡ የፓሪስ ማራቶን የቦታ ሪከርድ ከሁለት ዓመት በፊት በኬንያዊው አትሌት ስታንሊ ኪውት በ2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ12 ሰኮንዶች የተመዘገበ ነው፡፡ በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ስኬታማ ዓመታት የነበራቸው አትሌቶች በማራቶን የመጀመርያ ተሳትፏቸው ሪከርድ የማስመዝገብ አቅም እንደሌላቸው በርካታ መረጃዎች ያስገነዝባሉ፡፡ ብዙዎቹ ምርጥ የረጅም ርቀት አትሌቶች በመጀመሪያ ማራቶናቸው  በፈጣን ሰዓቶች ደረጃ እስከ 20ኛው ባለ እርከን ለመግባት የሚያስችል ስኬት ነበራቸው፡፡ የወቅቱን የዓለም ማራቶን ሪከርድ የያዘው ኬንያዊው አትሌት ዊልሰን ኪፕሳንግ በ2003 እኤአ ላይ የመጀመርያ ተሳትፎውን በፓሪስ ማራቶን ሲያደርግ ሶስተኛ በመውጣት ያስመዘገበው ሰዓት 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ13 ሰኮንዶች ነበር፡፡ ሞሮካዊው ካሊድ ካኑቺ በ1997 እኤአ በቺካጎ ማራቶን 2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ10 ሴኮንዶች፤ ፖል ቴርጋት በ2001 እኤአ በለንደን ማራቶን ሁለተኛ ደረጃ ሲያገኝ 2 ሰዓት ከ08 ደቂቃዎች ከ15 ሴኮንዶች፤ እንዲሁም ኃይሌ ገብረስላሴ በ2002 እኤአ በለንደን ማራቶን ሶስተኛ ሲወጣ አዲስ የኢትዮጵያ ሪከርድ በማስመዝገብ  ስኬታማ  ጅማሮ ነበራቸው፡፡
ጥሩነሽና ሞ ፋራህ በለንደን ከ2 ሳምንታት በኋላ የሚካሄደው የለንደን ማራቶን በትልልቅ አትሌቶች ስብስብ የምንግዜም ምርጥ ተብሏል፡፡ እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ እና ኢትዮጵያዊቷ ጥሩነሽ ዲባባ በማራቶን የመጀመርያ ተሳትፏቸውን ለንደን ላይ ማድረጋቸው ልዩ ትኩረት ፈጥሯል፡፡  ከ650ሺ በላይ የለንደን ነዋሪዎች በከተማዋ ጎዳናዎች ተሰብስበው የሚከታተሉት ማራቶኑ የዓለም ምርጥ ማራቶኖችን ደረጃ በአንደኝነት የሚመራ ሲሆን በ150 አገራት የቴሌቭዥን ስርጭት ያገኛል፡፡ ከ2 ሳምንታት በኋላ በሚደረገው የለንደን ማራቶን ላይ ክብረወሰን እንዲሰብር የውድድሩ አዘጋጆች ከፍተኛ ፍላጎት አላቸው፡፡ ለዚህም ይመስላል የዓለም ማራቶን ክብረወሰንን በበርሊን ለሁለት ጊዜያት በመስበር ክብሩን ለ5 ዓመታት ይዞ የነበረው ኃይሌ ገ/ስላሴን ከአሯሯጮቹ አንዱ አድርገውታል፡፡ ታላቁ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በለንደን ማራቶን ለሶስት ጊዜያት ተሳትፎ ብዙም አልተሳካለትም፡፡ ዘንድሮ በ40 ዓመቱ በአሯሯጭነት ሲሳተፍ እስከ 30 ኪሎሜትር ድንቅ ፍጥነት እንዲያሳይ እምነት ተጥሎበታል፡፡
በለንደን ማራቶን ላይ 5 የዓለም ሻምፒዮና እንዲሁም 3 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ያሏት ጥሩነሽ ዲባባ የመጀመርያ ማራቶን ውድድሯን ስትካፈል በከባድ ተፎካካሪዎች ተከብባ ነው፡፡ ዋናዋ ተቀናቃኟ ኬንያዊቷ ፕሬሲካ ጄፕቶ ስትሆን በ2013 የኒውዮርክ ማራቶንን በማሸነፍ እና የማራቶን ሊግን በአንደኛነት በመጨረስ 625ሺ ዶላር ያገኘች ምርጥ አትሌት ናት፡፡ ሌሎቹ ተፎካካሪዎቿ በማራቶን ከፍተኛ ልምድ ያላቸው ናቸው። በ2012 የለንደን ኦሎምፒክ በማራቶን ሻምፒዮን የሆነችውና በ2012 የሮተርዳም ማራቶንን ስታሸንፍ ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ18 ደቂቃ ከ56 ሰኮንዶች በመጨረስ የኢትዮጵያን ማራቶን ሪከርድ ያስመዘገበችው ቲኪ ገላና ግንባር ቀደሟ ተጠቃሽ ናት፡፡ ለሁለት ጊዜያት የበርሊንን ማራቶንን እንዲሁም ባለፈው አመት የቶኪዮ እና የሻንጋይ ማራቶኖችን ያሸነፈችው አበሩ ከበደ ሌላዋ ተሳታፊ ናት። በማራቶን 2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ30 ሰኮንዶች ፈጣን ሰዓት ያስመዘገበችው አበሩ ከበደ ዘንድሮ በለንደን ማራቶን የምትሳተፈው ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን በ2011 እኤአ 9ኛ እንዲሁም በ2012 እኤአ 6ኛ ነበረች፡፡ ሌላዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ደግሞ በ2012 እኤአ የቺካጎ ማራቶንን  አምና ደግሞ የፓሪስ ማራቶንን ያሸነፈችውና 2 ሰዓት ከ21 ደቂቃዎች ከ06 ሰኮንዶች ፈጣን ሰዓት ያላት ፈይሴ ታደሰ ናት፡፡ በዘንድሮው የለንደን ማራቶን ከሚሳተፉ ሴት አትሌቶች ሶስቱ ፈጣን ሰዓታቸው ከ2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች በታች ሲሆን 8 አትሌቶች ደግሞ ከ2 ሰዓት 25 ደቂቃዎች በታች ያስመዘገቡ ናቸው፡፡በለንደን ማራቶን በሴቶች ምድብ እንግሊዛዊቷ አትሌት ፓውላ ራድክሊፍ ላለፉት 10 ዓመታት ይዛ የቆየችው 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ከ25 ሰኮንዶች የሆነው ሪከርድ ሊሰብር እንደሚችል አንዳንድ ባለሙያዎች እየገለፁ ናቸው፡፡ ለዚህ እጩ የሆኑት የመጀመርያው ተሳትፏዋን የምታደርገው ጥሩነሽ ዲባባ፤ የኦሎምፒክ ሻምፒዮኗ ቲኪ ገላና፤ የዓለም ሻምፒዮኗ ኤድና ኪፕላጋት እና አምና አሸናፊ የነበረችው ፕሪስካ ጄፕቶ  ነበሩ።  ይሁንና አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በመጀመርያ የማራቶን ሩጫዋ የዓለም ሪከርድን እንደምታስመዘግብ ብዙም ባይጠበቅም፤ የለንደን ማራቶንን የቦታ ሪከርድ ወይ ደግሞ የኢትዮጵያን አዲስ ሪከርድ ልታስመዘግብ እንደምትችል ግን ግምት ተሰጥቷል።  እንግሊዛዊቷ ፓውላ ራድክሊፍ በ2002 እኤአ ላይ በለንደን ማራቶን የመጀመርያዋን ተሳትፎ አድርጋ ስታሸንፍ ያስመዘገበችው 2 ሰዓት ከ18 ደቂቃዎች ከ55  ሴኮንዶች  ነበር፡፡ የጥሩነሽ ሰዓት በዚሁ አካባቢ እንደሚሆን የተገመተ ነው፡፡  
በለንደን የመጀመርያ ማራቶን ውድድሩን የሚያደርገው ደግሞ ሞፋራህ ብቻ አይደለም፡፡ በሁለት የዓለም ሻምፒዮናዎች በ10ሺ ሜትር የተናነቀው ኢትዮጵያዊው ኢብራሂም ጄይላንም ይሮጣል፡፡ ከእነሱ ባሻገር የዘንድሮ ለንደን ማራቶን በታላላቅ አትሌቶች የተጨናነቀ ነው። አምና የዓለም የማራቶንን ሪከርድን በበርሊን የሰበረው ኬንያዊው ዊልሰን ኪፕሳንግ፤ በማራቶን በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና የወቅቱ ሻምፒዮን የሆነው ኡጋንዳዊው ስቴፈን ኪፕሪቺች፤ የወቅቱ የማራቶን ሊግ አሸናፊ በመሆን ከ500ሺ ብር በላይ የተሸለመውና በ2013 የለንደን ማራቶንን ያሸነፈው ኢትዮጵያዊው ፀጋዬ ከበደ እና የለንደን ማራቶንን ሪከርድ የያዘው ኬንያዊ ኢማኑዌል ማታይ ተሳታፊ ናቸው፡፡ ሞ ፋራህ ወደ ማራቶን ለመግባት ሲወስን ኃይሌ ገብረስላሴ  እድሜው ገና ነው በሚል ድጋፍ ባይሰጠውም እንግሊዛዊቷ ፓውላ ራድክሊፍ ግን ውሳኔው ልክ እንደሆነና በትራኩ እንደተሳካለት ማራቶኑንም ይቆጣጠራል በማለት መስክራለት ነበር፡፡  ሞ ፋራህ ስለመጀመርያው የማራቶን ተሳትፎው ሲናገር‹‹ በትራክ ብዙ ውጤቶች እና ሜዳልያዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ስለዚህ ለምን በማራቶን ራሴን አልፈትንም፡፡ ለንደን ላይ ከተሳካልኝ በሌሎች ሁለት እና ሶስት ትልልቅ ማራቶኖች እሮጣለሁ፡፡›› በማለት  ተናግሯል። ከሳምንት በፊት በኒውዮርክ በተካሄደው የግማሽ ማራቶን የተሳተፈው ሞፋራህ በውድድሩ ዋናው ትኩረቱ ለለንደን ማራቶን አቋሙን መፈተሽ ነበር፡፡ በዚሁ ውድድር ላይ ሞ ፋራህ ሶስተኛ ደረጃ አግኝቶ አጠናቅቋል። ይሁንና የውድድሩን መጨረሻ መስመር አልፎ ሲገባ ተዝለፍሎ በመውደቅ ለሶስት ደቂቃም እራሱን ስቶ ነበር። አንዳንድ የአትሌቲክስ ባለሙያዎች ሁኔታው በለንደን ማራቶን ሲሮጥ የሚጠብቀውን ከባድ ፈተና እንደሚያሳይ በመግለፅ ውጤታማነቱን ተጠራጥረዋል፡፡
የማራቶን ሪከርዶች የኪፕሳንግ 2፡03፡23፤ የራድክሊፍ 2፡15፡25
በዓለም የማራቶን ሪከርድ ታሪክ በወንዶች ምድብ የኢትዮጵያ አትሌቶች በክብረወሰኖቹ መሻሻል ጉልህ አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ ባለፉት 3 ዓመታት ግን ይህ የበላይነት በኬንያውያን እጅ ገብቷል፡፡ በሴቶች ምድብ ግን አንድም ኢትዮጵያዊ አትሌት የዓለም ሪኮርድ አስመዝግባ አታውቅም፡፡ በማራቶን ታሪክ በወንዶች የመጀመርያው የዓለም  ሪከርድ የተመዘገበው እኤአ በ1908 በለንደን ማራቶን በአሜሪካዊው ጆን ሄይስ በ2 ሰዓት ከ35 ደቂቃ ከ18 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ነበር፡፡ ይህ የመጀመርያ ሪከርድ ከተመዘገበ ከ32 ዓመታት በኋላ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ለመጀመርያ ጊዜ በኢትዮጵያዊ አትሌት የተመዘገበው በ1960 እኤአ ላይ በሮም ኦሎምፒክ በባዶ እግሩ ሮጦ ባሸነፈው አበበ ቢቂላ ነበር፡፡ በወቅቱ አበበ ያስመዘገበው የማራቶን ክብረወሰን 2 ሰዓት ከ16 ደቂቃዎች ከ23 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ነበር፡፡ ከ4 ዓመታት በኋላ አበበ ቢቂላ ለሁለተኛ ጊዜ የማራቶን ሪከርድን   በ1964 እኤአ ላይ በቶኪዮ ኦሎምፒክ ያስመዘገበ ሲሆን ጊዜውም 2 ሰዓት ከ12 ደቂቃዎች ከ11 ሰኮንዶች ፡፡ አበበ በቂላ  በኦሎምፒክ መድረክ ባስመዘገበባቸው  ሁለት የዓለም የማራቶን ሪከርዶች  ለአምስት አመታት ነግሶ ቆይቷል፡፡ ከአበበ ቢቂላ ሪከርዶች 24 ዓመታት  በኋላ የዓለም ማራቶን ሪከርድን ሊያዝ የበቃው  ሁለተኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞ ነበር፡፡ በላይነህ እኤአ በ1988 በተካሄደው ሮተርዳም ማራቶን ሲያሸንፍ ርቀቱን የሸፈነበት 2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች ከ50 ሴኮንዶች የሆነ ጊዜ አዲስ የዓለም ሪከርድ ነበር፡፡ በላይነህ ዴንሳሞ በዚህ ሪከርዱ ርቀቱን ከ2 ሰዓት 7 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያው አትሌት ከመሆኑም በላይ ክብረወሰኑን ለ10 ዓመታት ይዞ ቆይቷል። ከበላይነህ ዴንሳሞ በኋላ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ክብረወሰን ወደ ኢትዮጵያ የተመለሰው ከ19 ዓመታት በኋላ ነበር፡፡ በ2007 እኤአ ላይ በበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ26 ሰኮንዶች   በሆነ ጊዜ ባሸነፈው ኃይሌ ገብረስላሴ አማካኝነት ነበር፡፡ በ2008 እኤአ ላይ ኃይሌ ይህን ክብረወሰኑን በድጋሚ ሲያሻሽል 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ59 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ርቀቱን በመሸፈን ነበር። ይሄው ሰዓት የኢትዮጵያ ሪከርድ ነው፡፡ በዚሁ ሁለተኛ የማራቶን  ሪከርዱ ኃይሌ ገብረስላሴ ርቀቱን ከ2 ሰዓት 4 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያ አትሌት ሲሆን በክብረወሰኑ ባለቤትነት ለ5 ዓመታት ቆይቷል። በአጠቃላይ በወንዶች የዓለም ማራቶን  ታሪክ ሶስት የኢትዮጵያ አትሌቶች 5 ጊዜ ሪከርዶችን አሻሽለዋል። 3 ደቂቃዎች 49 ሰኮንዶች ከማራቶን የሪከርድ ሰዓት ላይ በመቀነስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ ኢትዮጵያ በሪከርዱ ባለቤትነት ለ19 ዓመታት የበላይ ሆና እንድትቆይ አድርገዋል፡፡ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ በኬንያ ቁጥጥር ስር የገባው  በ2012 እኤአ ላይ በኬንያዊው አትሌት ፓትሪክ ማካው በበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ38 ሴኮንዶች በሆነ ጊዜ ተሰብሮ ነበር፡፡ ባለፈው አመት ደግሞ ሌላው ኬንያዊ አትሌት ዊልሰን ኪፕሳንግ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ23 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ተይዞ ይገኛል፡፡
በበርሊን ማራቶን ባለፈው ዓመት የተመዘገበው የዊልሰን ኪፕሳንግ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በውድድሩ ታሪክ ለ32ኛ ጊዜ የተመዘገበ ክብረወሰን ነው፡፡ አስቀድሞ በኬንያዊው ፓትሪክ ማኩ ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን በ15 ሰኮንዶች ያሻሻለ ነው፡፡ ዊልሰን ኪፕሳንግ ሪከርዱን ሲያስመዘግብ 31 ዓመቱ የነበረ ሲሆን በማራቶን መወዳደር ከጀመረ ከ4 ዓመታት እና ከ7 ውድድሮች ተሳትፎ በኋላ ሊያሳካው ችሏል፡፡ ባለፉት 10 ዓመታት በትልልቅ ማራቶኖች በምርጥ አትሌቶች የሚመዘገቡ ፈጣን ሰዓቶች የተለየ መሻሻል ቢታይባቸውም አዲስ የዓለም ሪከርድ የሚመዘገብበት እድል የጠበበ እንደሆነ ያመለክታሉ፡፡ በቦስተን 2፡07፤ በለንደን 2፡06 ፤ በቺካጎ 2፡08 እንዲሁም በበርሊን 2፡05 ነው፡፡ እንደስፖርት ሳይንቲስት ድረገፅ ጥናታዊ ትንታኔ የማራቶን ርቀትን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት ከእንግዲህ እስከ 25 ዓመታት ይጠይቃል። አሁን ዊልሰን ኪፕሳንግ የያዘውን ክብረወሰን ለማሻሻል እና ድፍን 2 ከ03 በመግባት ሪከርድ ሰዓት ለማስመዝገብ የሚቻለው በሚቀጥሉት 5 ዓመታት ነው፡፡ ከ2 ሰዓት 02 እና ከዚያም በታች ለመግባት እስከ 10 ዓመት ይፈጃል፡፡
በሴቶች ምድብ እንግሊዛዊቷ አትሌት ፓውላ ራድክሊፍ ላለፉት 10 ዓመታት ይዛ የቆየችው ክብረወሰን በቅርብ ጊዜ እንደሚሻሻል ተገምቶ አያውቅም፡፡ 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ከ25 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ የተመዘገበው የራድክሊፍ ሪከርድ በለንደን ማራቶን የተመዘገበ ነበር፡፡
በሁለቱም ፆታዎች የተመዘገቡ የዓለም የማራቶን ሪከርዶች በየትኛው ውድድር እንደሚሰበር ለመገመት በተሰሩ ጥናቶች ግነባር ቀደም የሆነው የበርሊን ማራቶን ነው፡፡ቺካጎ፤ ሮተርዳም፤ ለንደን  እና ፓስ ማራቶኖች እስከ 5 ያለውን ደረጃ ያገኛሉ፡፡
የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች የበላይነት በማራቶን ውድድሮች የኢትዮጵያ እና የኬንያ አትሌቶች ላለፉት 10 እና 15 ዓመታት ተፎካካሪ አጥተዋል፡፡ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በየትኛውም የዓለም ክፍል በሚደረጉ የማራቶን ውድድሮች እስከ አምስተኛ እና ስድስተኛ ደረጃ ተከታትለው በመግባት ፍፁም የበላይነት እያሳዩ ናቸው። የኤስያ፤ የአውሮፓ እና የአሜሪካ አትሌቶች የበላይነት ካከተመ ከ30 ዓመታት በላይ ተቆጥሯል፡፡ ምዕራባውያን እንደ ምስራቅ አፍሪካውያን ለማራቶን ውድድር ፍቅር ስለሌላቸው ውጤታማ አልሆኑም በሚል ቀሽም ማስረጃ ሁኔታውን ለማብራራት የሚሞክሩ አሉ፡፡ እነዚህ አስተያየት ሰጭዎች አሜሪካውያንና አውሮፓውያን ከማራቶን ይልቅ በቅርጫት ኳስ፤ በእግር ኳስ፤ በቤዝቦል እና ሌሎች ስፖርቶች ስኬታማ መሆንን ቅድሚያ በመስጠታቸው በምስራቅ አፍሪካ የሩጫ ገድል ተበልጠዋል በማለት ይከራከራሉ፡፡ አንዳንድ የጥናት ውጤቶች የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በማራቶን ውድድሮች ስኬታማ የመሆናቸው ምስጥርን ሲያብራሩ ግን ሁኔታው ለየቅል ነው፡፡ በኢትዮጵያ እና ኬንያ ታዳጊ ወጣቶች በየቀኑ ወደትምህርት ቤት ለመጓዝ አምስት እና 10 ኪሎሜትር የእግር ጉዞ በማድረጋቸውና በከፍተኛ አልቲትዩድ በአስቸጋሪ የኑሮ ሁኔታዎች በማደጋቸው  ፅናት በሚጠይቁት የማራቶን ውድድሮች ስኬት ማግኘት አይከብዳቸውም በሚል ጥናታዊ ማስረጃዎች ቀርበዋል፡፡ በሌላ በኩል በአትሌቲክስ ስፖርት በሚኖር ውጤታማነት የሚገኘው የሽልማት ገንዘብ እና ልዩ ልዩ ጥቅማጥቅም ድህነትን ለማሸነፍ አማራጭ ሆኖ በመገኘቱ ለምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ውጤታማነት አብይ ምክንያት ሆኗል በማለት ያስረዳሉ፡፡
የምስራቅ አፍሪካን አትሌቶችን የበላይነት አሃዛዊ መረጃዎችም ያመለክታሉ፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በወንዶች ምድብ የማራቶን ርቀትን ከ2 ሰዓት ከ10 ደቂቃዎች የገቡ 149 አትሌቶች ተመዝግበዋል። ከእነዚህ አትሌቶች መካከል 80 ያህሉ ኬንያውያን ሲሆኑ 47 ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ ስምንት አትሌቶች ደግሞ የኤርትራ እና የኡጋንዳ ዜግነት አላቸው፡፡
በአጠቃላይ በማራቶን ውድድሮች  የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶችን የበላይነት ሌላው ዓለም ክፍል በቅርበት የሚቀናቀነው አይደለም፡፡ በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ የተሰባሰበ አሃዛዊ መረጃ እንደሚያመለከትው ደግሞ በወንዶች ማራቶን ፈጣን ሰዓት ደረጃ እስከ 100ኛ ድረስ ከተመዘገቡት ከምስራቅ አፍሪካ ውጭ የሌሎች አገራት  ውክልና በ9 አትሌቶች ብቻ የተወሰነ ነው፡፡ ከ101 እስከ 200 ባለውም ደረጃ ቢሆን 14 አትሌቶች ብቻ ከጃፓን፤ ከብራዚል፤ ከደቡብ አፍሪካ ፤ ከአሜሪካ እና ከጣሊያን ናቸው፡፡ በአጠቃላይ በዓለም ዙርያ ከሚገኙ 300 ፕሮፌሽናል የማራቶን ወንድ ሯጮች 246 ያህሉ ከምስራቅ አፍሪካ የፈለቁ ናቸው፡፡ ከ50 ዓመት በፊት በተካሄደ የቦስተን ማራቶን ከ1 እስከ 10 ደረጃ ያገኙ አትሌቶች ከአምስት አገራት ቤልጅዬም፤ ፊንላንድ፤ ካናዳ፤ አሜሪካ እና አርጀንቲና የተውጣጡ ነበሩ፡፡ በዚያው ዓመት በተካሄደ ኦሎምፒክ በተመሳሳይ ከ1 እስከ 10 ያለውን ደረጃ ከአምስት አህጉራት የተወከሉ አትሌቶች ያገኙት ነበር፡፡
የማራቶንና ማራኪ ገቢዎች አንድ የማራቶን ሯጭ ለአንድ ውድድር ቢያንስ የ3 ወራት ጥብቅ የልምምድ እና የዝግጅት ጊዜ ያስፈልገዋል፡፡ ምርጥ የሚባሉት የማራቶን ሯጮች በእንደዚህ አይነት የልምምድ ሁኔታዎች በአንድ አመት ሁለት እና ሶስት ማራቶኖችን መሳተፍ ይችላሉ፡፡ ማራቶኖችን ከሌሎች የአትሌቲክስ ውድድሮች የሚለያቸው በሽልማት መልክ፤ በስፖንሰርሺፕ እና በቦነስ ክፍያዎች ከፍተኛ ገቢ ስለሚገኝባቸው ነው፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር የሚካሄዱ የትራክ ውድድሮች በመመናመናቸው  በርካታ አትሌቶች በጎዳና ላይ ሩጫዎች በተለይ በግማሽ ማራቶንና በማራቶን ውድድሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ፡፡ አብዛኛዎቹ የማራቶን ውድድሮች ለአሸናፊ አትሌቶች ከ50ሺ እስከ 100ሺ ዶላር በመሸለም ይታወቃሉ፡፡ ቀነኒሳ የሚሳተፍበት የፓሪስ ማራቶን ሽልማት በግልፅ ባይታወቅም እስከ 150ሺ ዶላር እንደሚደርስ ይገመታል፡፡ የኒውዮርክ ማራቶን 130ሺ ዶላር፤ የበርሊን ማራቶን 150ሺ ዶላር፤ የቦስተን ማራቶን 150ሺ ዶላር፤ የቺካጎ ማራቶን 100ሺ ዶላር፤ የለንደን ማራቶን እስከ 55ሺ ዶላር  በነፍስወከፍ በሁለቱም ፆታዎች ለሚያሸንፉ አትሌቶች ያበረክታሉ፡፡ አንድ የማራቶን ሯጭ በአሸናፊነቱ ከውድድሮቹ አዘጋጅ ከሚያገኛቸው ሽልማት ባሻገር በሚያስመዘግበው ፈጣን ሰዓት እና ሪከርድ  የቦነስ ሽልማች የሚያገኝበትም እድል አለው፡፡ አሁን ለምሳሌ በኒውዮርክ ማራቶን የቦታውን ሪከርድ  ለሚያስመዘግብ 70ሺ ዶላር ቦነስ አለ፡፡   ከ2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ በታች ለሚገባ አትሌት በለንደን ማራቶን 100ሺ ዶላር ፤ በኒውዮርክ ማራቶን 50ሺ ዶላር ቦነስ ይሰጣል፡፡ በብዙዎቹ ማራቶኖች የቦታ ሪከርድ ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች ከ25 እስከ 100ሺ ዶላር ይሰጣል፡፡  ሌላው የገቢ ምንጭ ትልልቅ አትሌቶችን በውድድሮቻቸው ለማሳተፍ የሚፈልጉ አዘጋጆች ከ100ሺ ዶላር ጀምሮ መክፈላቸው ነው፡፡ ለምሳሌ የለንደን ማራቶን ለአንዳንድ አትሌቶች ተሳትፎ እስከ 200ሺ ዶላር እንደሚሰጥ ይገልፃል፡፡
በሌላ በኩል አትሌቶች ትጥቃቸውን ስፖንሰር ከሚያደርግላቸው ኩባንያም በአንድ ማራቶን ውድድር በመሳተፍ ውጤታማ ሲሆኑ ከ50 እስከ 70 ሺ ዶላር ይበረከትላቸዋል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞም አንዳንድ እውቅ አትሌቶች የሚያገኙት የመሮጫ ጫማቸውን በሚያቀርብላቸው ኩባንያ የሚያገኙትም ጥቅም አለ፡፡ በአጠቃላይ በትልልቆቹ የዓለማችን ማራቶኖች አንድ ታዋቂ አትሌት ተሳትፎ ጥሩ ሰዓት በማስመዝገብ የሚያሸንፍ ከሆነ በአማካይ እስከ 750ሺ ዶላር ሊያካብት ይችላል፡፡

        ጠያዊው ወንድ ተጠያዊው ደግሞ የተዋልዶ ጉዳዮችን በተመለከተ በዌብ ሳይቱ  (ኢንተርኔት) ምላሽ የሚሰጥ ባለሞያ ነው፡፡ ጥያቄው “ረዥም ጊዜ በቆየንባቸው የፍቅር ጓደኝነት ጊዜ ጓደኛዬ ድንግል እንደሆነች ነበር የምትነግረኝ ሆኖም ጊዜው ደርሶ አልጋ ላይ ስንወድቅ የፍቅር ጓደኛዬ ድንግል አልነበረችም፡፡ ምንም አይነት የደም ምልክትም አልነበረም ጓደኛዬ በተፈጥሮ ድንግል ላትሆን ትችላለች ወይንስ ዋሸችኝ?” መላሹ በተራው ጥያቄውን በጥያቄ ይጠይቃል ጓደኛህን ታምናታለህ ወይንስ አታምናትም? ከጓደኛህ የምትፈልገው ከእሷ አንድ ነገርን ነው ወይንስ ጠቅላላ ማንነቷን? ብሎ ይጀምራል፡፡  
የሴቶችን የድንግልና ጉዳይ አሁንም በብዙ ወንዶች ዘንድ ትልቅ ጉዳይ እንደሆነ እናስባለን፡፡ “ብር አንባር” አሁንም የክብር፣ የታማኝነት፣ የፍቅር ሰንሰለት ማጥበቂያ፣ መቼም አንደዬ ባህልና ልምዱ የተለያዩ ጉዳዮችን መግለጫ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በአንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ አረብ ሀገራት ሴት ልጅ በሰርጓ ቀን ምሽት ባሏ፣ የቧላ ቤተሰቦችና የራሷም ቤተዘመድ እንደሚጠብቃት ድንግል ሆና ካልተገኘችና የዚህም ማረጋገጫ ካልታዬ ባሏ ሊገድላት፣ ከሱ እጅ ከተረፈች ደግሞ ወንድሞቿ ወይም አባቷ ሁሉ ሊገድላት ይችላል፡፡ የክብር መገለጫ፣ ሌላውንም ማስከበሪያና የትዳሩም መሰረት ተደርጎ ይወሰዳልና፡፡ እንዲህ ያለ ግድያ ወንጀል ቢሆንም ገዳዮች በጎሳዋቻቸው ባህል ውስጥ ይሰወራሉ፡፡
በህንድ ሳንሲ በተሰኘ ጎሳ ማህበረሰብ ውስጥ የሴቶች ድንግልና የሚሰጠው ቦታ በጣም የላቀ ነው። አንዲት ሳንሲ ድንግል አለመሆኗ ከታወቀ ቀጥሎ በዱላ ሁሉ የምትገደደው ድንግልናዋን ማን እንደወሰደ እንድታወጣ ነው፡፡ ይህን የፈፀመው ሰው ደግሞ ለወላጆች ካሳ ይከፍላል፡፡ ይህ የሳንሲ ማህበረሰብ የሴት ድንግልና መግለጫ መኖር አለመኖር የሚመረመሩበት የራሣቸው ልማዳዊ ዘዴ አላቸው፡፡ ግምገማውን ለእናንተ ለአንባቢያን ትቼ የምርመራ ልምዱን እንመልከት፡፡
የመጀመሪያው የውሃ ሙከራ የሚሉት ነው፡፡ የድንግልና ምርመራ የሚደረግባት ሴት ልጅ ራሷን ወይም ጭንቅላቷን ሙሉ በሙሉ ውሃ ውስጥ እንድትደፍቅ ትደረጋለች፡፡ ያለ ምንም አየር (ኦክስጅን) አንድ ሰው መቶ እርምጃ ተራምዶ እስቲደርስ መቆየት ከቻለች ሳንሲዎች ልጅቱ ድንግል መሆኗን አረጋገጡ ማለት ነው። ሁለተኛው መንገድ ደግሞ የእሳት ሙከራ የሚሉት ነው። ሙሽራዋ በሠርጓ እለት ከመጀመሪያው ለሊት በፊት ቅጠልና ሊጥ እጇ ላይ አድረጋ የጋለ (ፍም) የመሰለ ብረት ይዛ እንድትጓዝ ትጠየቃለች ብረቱ ቅጠሉንና አልፎ እጇን ካቃጠላት ድንግል አይደለችም ብለው ይወስዳሉ፡፡ እንዚህ ሁለት ሙከራዎች ከድንግልናው ጋር ምን ያያይዛቸዋል ካላችሁ ለሁላችንም እንቆቅልሽ መሆኑ ነው፡፡ መንግስት የዚህን ማህበረሰብ ወግ ጥሶ መግባት አልቻለም፡፡   
በቱርክ ደግሞ የሴቶች የድንግልና መገለጫ መኖር አለመኖር ማረጋገጫ ሙከራ ድርጊቱ ሴት ልጆችን ማማረር ብቻም ሳይሆን ራሳቸውን ለማጥፋት የሚሞክሩ ሴቶች መኖራቸውን አሶሼትድ ፕሬስ የአንድ ወቅት ሪፖርቱ ነበር፡፡ ቱርኮች በሰርጋቸው ቀን ሴቷ የድንግልናዋ  መገለጫ ይሆን ዘንድ ቀይ መቀነት ወገቧ ላይ ይደረግላታል ድንግል ከሆነች ማለት ነው፡፡ የድንግልና ምርመራን በተመለከተ በቱርክ በተደረገ ጥናት ተገድጄ ተደፍሬአለሁ የሚል ስሞታ ለምታሰማ ሴት ልጅ ምርመራው ያስፈልጋል የሚሉ ቢበዙም በተጨባጭ ግን የሚደረጉት ምርመራዎች ከልምዶቻቸው ጋር በተያየዘ የሚደረጉ ናቸው፡፡ ለምሳሌ አንዲት ሴት ልጅ ከማግባቷ በፊት ለባሏና ለአካባቢዋ ሰርተፊኬት ማቅረብ አለባት። ያለገባ ሠርተፊኬት እንደሚሰጠው ሁሉ ለድንግልናም እንደዚያው ሠርተፊኬት ይሰጣል፡፡
በአጠቃላይ ምርመራውን ግን በሴቶች ላይ የስነልቦና መታወክ (Psychological trauma) መፍጠሩ አልቀረም ይላል ጥናቱ ምክንያቱም አብዛኛዎቹ ምርመራዎች የሚካሄዱት ከሴቶቹ ፈቃድ ውጭ በመሆኑ ነው፡፡
ወደ አቅራቢያ ደቡብ አፍሪካ ደግም በተለይ በዙሉ ማህበረሰብ የወንዶችም የሴቶች የድንግልና ምርመራ ኤች. አይ. ቪን ከመከላከል ጋር አቆራኝተው ያስቡታል፡፡ ሆኖም ከዚህ በተፃራሪ በዚሁ ማህበረሰብ ውስጥ አንድ የተሳሳተ አስተሣሰብ (myth) እንዳለ ይታወቃል፡፡ ይኽውም ኤች. አይ. ቪ ኤድስ ያለበት ሰው ድንግል ከሆነች ሴት ጋር ግንኙነት ካደረገ ይፈወሳል በሚል ሌሎች አደጋዎች በተለያዩ ጊዜያት ተከስተዋል፡፡  
በዙሉ የወንዶች የምርመራ አይነት አሁንም ቀደም ሲል በህንድ እንዳየነው እንቆቅልሽ አይነት ነው። ረዥም ሽቦ በሦስት ስንዝር ከመሬት ከፍ ብሎ ግራና ቀኝ እንጨቶች ላይ ይታሰራል፡፡ ታዲያ የድንግልና ምርመራ የሚደረግበት ወንድ ብልቱን በእጁ ሣይዝ ከሽቦው አሻግሮ እንዲሸና ይጠየቃል፡፡ ሽንቱን በቀጥታ መሬት ላይ ከጨረሰ ድንግል ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ሆኖም ከተፈናጠረና አወራረዱ የተዝረከረከ ከሆነ ሽቦውን ካበላሸው ውጤቱ ተቃራኒ ይሆናል፡፡ ሌላም አለ አሸዋ ላይ በተመሣሣይ ሁኔታ እንዲሸና ይጠየቃል ሽንታቸው አሸዋው አንድ ቦታ ላይ ብቻ ቀዳዳ ከፈጠረ ድንግል ናቸው ብለው ይወሰዳሉ። በአጠቃላይ የድንግልና ምርመራ በዙሉ ማህበረሰብ ፍርሃት እንዲነግስ አድርጓል። በተለይ ተገዶ መደፈር ያውም ህፃናትን በዝቶ የሚታይ ክስተት በመሆኑ። ወደመነሻችን ርዕስ ጉዳይ እንመለስ፣ ድንግልና ምንድን ነው ከተባለ ለሴቶች ብቻ የሚውል ቃል አይደለም፡፡ የሴቶችን የድንግልና መስመር ወይም መረብ (hymen) የሚገልፅም አይደለም፡፡ ምንም አይነት ወሲባዊ ተራክቦ የሌለው ሰው ድንግል ነው፣ ግን ወሲባዊ ግንኙነትስ የግድ የወንድና የሴት ተራክቦን የተለመደውን ብቻ የሚያሳይ ነው?   
የሴቶች የድንግልና መገለጫ (hymen) ስስ የሴቶችን ብልት የውስጥ ክፍል ወይም በር (ሙሉ በሙሉ ባይሆንም) የሚዘጋ መረብ መሰል ሥሥ ሽፋን (tissue) ነው፡፡ ጠንካራ አጥር ወይም ጠንካራ ቆዳ ትግል፣ ኃይል የሚፈልግ አይደለም እንደባለሞያዎቻች ትንተና፡፡ ከግንኙነት ውጭም በተለያዩ ምክንያቶች በቦታው ላይገኝ ይችላል፡፡ በእርግጥም ደግሞ የሴቶች ጥፋት ተደርጎ ሊወሰድ አይገባም፡፡
በእርግጥ የድንግልና መገለጫ መስመር (hymen) በተፈጥሮ ማንኛዋም ሴት ልጅ ይኖራታል፡፡ ይሁንና በመጀመሪያው የግንኙነት ቀን ጊዜ ህመም ሊኖራትም ላይኖራትም፣ ህመሙ ጠንካራ ወይም ቀላል ሊሆን ይችላል፡፡ የደም ፈሣሽ ሊበዛም፣ ሊያንስም በጣም ትንሽ ሊሆንም ይችላል፡፡ ብቻ በማንኛውም መንገድ ከወንድ ጋር በሚደረግ ወሲባዊ ተራክቦም ይሁን በሌላ አጋጣሚና ሁኔታዎች የድንግልና መገለጫ (hymen) ከፈረሰ በኃላ ራሱን የሚተካበት ወይም መልሶ የሚዘጋበት ወይም እንደሌላ የአካል ክፍል የሚያድግበት ሁኔታ የለም፡፡ ይሁንና ህንዶች ከባህሎቻቸው ጫና የተነሳ በቀዶ ጥገና የነበረውን በነበረበት መመለስ አስፈልጓቸዋል፡፡ አንዲት የዚህ ህክምና ባለሞያ ስትገልፅ በቀዶ ጥገናው የድንግልና መገለጫ የሆነውን (hymen) እንደገና መሥራትና መዝጋት ብቻም ሣይሆን ቀጣይ ወሲባዊ ግንኙነት ሲፈፀም የደም ፈሣሽ ክስተት ይኖር ዘንድ የድንግልና መገለጫውን ከሌላው የአካል ክፍል ህዋስ (Cells) ጋር የሚያገናኝ ሰንሰለት (membrane) እንዲፈጠር ይደረጋል፡፡ ይህ ቀዶ ጥገና ሁለት ቀናት የሚወስድ ሥራ ሲሆን ቀደም ሲል የገለፅነውን የባህል ጫና ለማቃለል ህንዶች ይጠቀሙበታል፡፡ ሌላ ወግ ይዘን ለሣምንት እንመለሳለን፡፡ ቸር ሰንብቱ፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

በአምስተረዳም አንድ ሰው ከሞተና የሚቀብረው ወዳጅ ዘመድ ከሌለው አንድ ገጣሚ ግጥም ይፅፍለትና በቀብር ሥነ-ሥርአቱ ላይ ያነብለታል፡፡
ቦሊቪያ ውስጥ የሚገኘው ትልቁ ወህኒ ቤት ምኑም እስር ቤት አይመስልም ነው የሚባለው፡፡ እስር ቤቱ ራሱን የቻለ ህብረተሰብ የፈጠረ ሲሆን ግቢው ውስጥ ጥበቃዎች የሉም፡፡ ወህኒ ቤቱን የሚጠብቁት ራሳቸው እስረኞቹ ሲሆኑ የራሳቸውን መሪዎች ይመርጣሉ፤ የራሳቸውን ህጎችም ያወጣሉ፡፡ እዚያው ተቀጥረው በመስራት ከሚያገኙት ክፍያም ለእስር ክፍላቸው ኪራይ ይከፍላሉ፡፡ ከቤተሰባቸው ጋር መኖርም ይፈቀድላቸዋል፡፡ እስር ቤቱ ውስጥ፡፡
እ.ኤ.አ ከ1939 እስከ 1989 ባሉት ዓመታት ከስፔን የተለያዩ ሆስፒታሎች 300ሺ ገደማ አዲስ የተወለዱ ጨቅላ ህፃናት ተሰርቀዋል፡፡ ህፃናቱ የተሰረቁት ደግሞ በውጭ ሰዎች ሳይሆን ህገወጥ የህፃናት ዝውውር መረብ በዘረጉ የህክምና ተቋማት ሃኪሞች፣ ነርሶች፣ ቄሶችና መነኮሳት እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ወላጆች ልጆቻቸውን ሲጠይቁም እንደ ሞቱ ይነገራቸው ነበር፡፡
የጃፓኗ ኦኪናዋ ደሴት በምድራችን እጅግ ጤናማ ሥፍራ በሚል ትታወቃለች፡፡ በዚህች ደሴት ከ100 ዓመት በላይ ዕድሜ ያላቸው ከ450 በላይ ሰዎች ይኖራሉ፡፡
የአውሮፓ ፓርላማ ዋና ተርጓሚ የሆነው አዮአኒስ አይኮኖም 32 ቋንቋዎችን አቀላጥፎ እንደሚናገር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

Published in ማራኪ አንቀፅ

ሰው በላቡ ካልገራው፣ ውሀ ብቻውን
ሰው አይፈው-ስም፣
ሀገር በእውቀት ሳይጠመቅ፣ ከድንቁርና
ሰው አይካ-ስም፡፡
‹‹የአባይ ፍቅርም›› ተምሳሌት ነው
መንታ ትርጉም፣ መንታ እውቀት፣
አንድም የሰነፍ ፍቅር ሕይወት፣
አንድም የታላቅ ወንዝ እውነት!
ይህን ቅኔ ያጤነ ሰው፣ ‹‹ነቢይ ባገሩ...››ን
ቢያስታው-ስም፣
የቁጭት ግድቡ ተደርምሶ፣ የሀገር ፍቅሩ
ደለል ቢለብ-ስም፣
እርግጥ ነው አይደፈር-ስም!
እውነት ነው አይደጎ-ስም...
ምስርም አቡን ስትልክ፣ ‹‹ከዕምነት››
አታፋር-ስም፡፡
ለእኛ ጳጳስ ስታበጅ፣ የማጥመቂያ እንኳ
ውሀ አትቀን-ስም¡
በደረቁ የላጨችው ካህን፣ በውሀ ማህሌት
ቢቀስ-ስም፣
የተንኮል ድግምቱ ከሽፏል፤ ዛሬ አባይ ላይ
አይቀድ-ስም፡፡
እናም...ዓባይ
አንተ የወንዝ ምት፣ አንተ የግጥም ስም   
ምስር እውነቱ ቢያንቃትም፣ ያለ እውቀት
የትም አትደር-ስም!
እርግጥ ነው፣ እኛ ሕይወት ከፍለን፣ እርሷ
የነፍስ ውሀ ብታፍ-ስም፣
መጋኛ መሐጸኗን እንደመታው፣ እንዳሶረዳት
ሴት፣ ደም ብታፈ-ስም፣
ከእንግዲህ ዓባይ ድረቅ እንጂ፣ የናስር
ግንቧን አታፈር-ስም!
ሀሩር ምድሯን በውሀ ደፍረህ፣ ድንግል
መሬቷን አትገስ-ስም!
ምስር ‹‹ውል አለኝ›› ብላለች፤ ‹‹በውነት...››
ስልህ ጫፏ አትደር-ስም፡፡
አንተ ሰላማዊ ወንዝ ነህ፤ የተፈጥሮ
ውል አትጥ-ስም!
                  የካቲት 11፣ 2006ዓ.ም

Published in የግጥም ጥግ

       ኖህ ዌብስተር የመጀመሪያውን መዝገበ ቃላት ለማዘጋጀት 36 ዓመት ፈጅቶበታል፡
ዳን ብራውን “ዘ ዳ ቪንቺ ኮድ” የተባለውን መፅሃፉን ከመፃፉ በፊት የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝና የዘፈን ግጥም ደራሲ ነበር፡፡ ሁለተኛው የሙዚቃ አልበሙ “ኤንጅልስ ኤንድ ዴሞንስ” በሚል ስያሜ ነበር የወጣውስ፡፡
ሲድኒ ሼልደን 50ዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ እስኪገባ ድረስ ረዥም ልብወለዶችን መፃፍ አልጀመረም ነበር፡፡ ከዚያ በፊት በነበሩት ጊዜያት “I Dream of Jeannie” እና “The Patty Duke Show” የመሳሰሉ ተወዳጅ የቴሌቭዥን ድራማዎችን ነበር የሚፅፈው፡፡ ቬልይን “The Bachelor and the Bobby Soxer” በተባለች የፊልም ጽሑፉ ኦስካር አሸንፏል- “ምርጥ ኦሪጅናል የፊልም ጽሑፍ” በሚል ዘርፍ፡፡
የ “ሃሪ ፖተር” ደራሲ ጄ.ኬ.ሮውሊንግ መጀመሪያ ላይ ሥራዋን የሚያሳትምላት አጥታ መከራዋን በልታለች፡፡ ብዙዎች ውድቅ እያደረጉባት ተስፋ ከቆረጠች በኋላ ብሉምስበሪ ፕሬስ ሊያሳትምላት ተስማማ፡፡ እሱም ቢሆን ግን አይሸጥ ይሆናል በሚል ፍራቻ 500 ቅጂዎችን ብቻ ነበር ያሳተመላት፡፡ ሴት ፀሐፊ መሆኗ እንዳይታወቅ ሙሉ ስሟን እንዳትጠቀም አድርጓታል፡፡ አሁን ደራሲዋ ቢሊዮነር መሆኗ ይታወቃል፡፡
የታዋቂዋ ደራሲ ዳንኤላ ስቲል ህይወት በአንዳንድ መልኩ የፈጠራ ሥራዎቿን ይመስላል ይባላል፡፡ ደራሲዋ አምስት ጊዜ ጋብቻ የመሰረተች ሲሆን ሳን ፍራንሲስኮ ክሮኒክል እንደዘገበው፤ ሁለተኛ ባሏ ከእሷ ጋር እያለ አስገድዶ በመድፈር የተፈረደበት የባንክ ዘራፊ ነበር፡፡ ሦስተኛ ባሏ ደግሞ የአደንዛዥ ዕፅ ሱሰኛና ቤት ሰርሳሪ ነበር ተብሏል፡፡



Published in ማራኪ አንቀፅ

አልአሳድ “የጠፈር ምርምር ማዕከል አቋቁሜያለሁ” እያሉ ነው!
ዮሐንስ ሰ.

       ከሶስት አመት በላይ በዘለቀው የሶሪያ የእርስ በርስ እልቂት፣ እስካሁን ከ150 ሺ በላይ ሰዎች ተገድለዋል። በአመት ሃምሳ ሺ መሆኑ ነው። በየሳምንቱ ወደ አንድ ሺ ገደማ ሰዎች በእርስ በርስ ጦርነት ይሞታሉ ማለት ነው። ከ23 ሚሊዮን የአገሪቱ ዜጎች መካከል፣ በእርስ በርስ ጦርነቱ የተፈናቀሉ ሶስት ሚሊዮን ያህል ሶሪያውያን ድንበር አቋርጠው ተሰደዋል። ግን፤ እነዚህ ብቻ አይደሉም የተፈናቀሉት። ከስድስት ሚሊዮን በላይ ሰዎች፣ ቤት አልባ ሆነዋል። በጦርነቱ ያልተለበለበ አካባቢ፣ ያልፈራረሰ ከተማ፣ ያልተበተነ ቤተሰብ ማግኘት ያስቸግራል። ከ10 ሶርያዊያን መካከል አራቱ፣ ወይ አገር ጥለው ተሰደዋል፤ አልያም ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው መውደቂያ ፍለጋ የሚባዝኑ ሚስኪኖች ሆነዋል።
መጥፎነቱ ደግሞ የሶሪያውያን ሰቆቃ በዚህ ያበቃ ይሆናል የሚል ተስፋ የለም። በእርግጥ የበሽር አልአሳድ መንግስት ተዳክሟል፤ አውሮፕላኖችንና ታንኮችን ቢያዘምትም አንድ ሶስተኛ ያህል የአገሪቱን ክልል ብቻ ነው መቆጣጠር የቻለው። በደርዘን የሚቆጠሩ አማፂ ሃይሎች፣ በአብዛኛውም ከአልቃይዳ ያልተሻሉ አክራሪና አሸባሪ ድርጅቶች ሌላውን የአገሪቱ አካባቢ ተቀራምተውታል።
ሰሜናዊና ምስራቃዊ የአገሪቱን ክፍል፣ የተለያዩ አማፂ ቡድኖች የተቀራመቱት ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ከስማቸውና አይነታቸው ብዛት የተነሳ አንዱን ከሌላው ለይቶ ለማወቅ የሚያስቸግሩ በርካታ ታጣቂ ቡድኖች፤ በዋና ከተማዋ ደማስቆ ዙሪያ ሳይቀር መንደሮችንና ከተሞችን ተቆጣጥረዋል። ለመዲናይቱ በጣም ቅርብ ከመሆናቸው የተነሳ የፕሬዚዳንቱን መኖሪያ ሰፈር ሳይቀር በሞርታር ይደበድባሉ።
ነገር ግን፤ አማፂ ቡድኖች ድል በድል እየሆኑ ነው ማለት አይደለም። በተቃራኒው፣ ካለፈው አመት ወዲህ ግስጋሴያቸው ቆሟል ማለት ይቻላል። በውጊያ ማሸነፍና የሚቆጣጠሩትን አካባቢ ማስፋፋት አቅቷቸዋል። አሁን አሁን ደግሞ፣ ሽንፈትን ማስተናገድ ጀምረዋል። ከደማስቆ በመቶ ኪሎሜትር ዙሪያ እስከ ሊባኖስ ድንበር ድረስ ለሁለት አመታት ያህል የተቆጣጠሯቸው ቁልፍ የመተላለፊያ ከተሞችን ከጥቃት መካላከል አቅቷቸው በውጊያ ተነጥቀዋል።
አማፂ ቡድኖች እንደሚሉትና የተለያዩ የሚዲያ ተቋማት እንደዘገቡት ከሆነ፤ የበሽር አልአሳድ መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከደማስቆ በስተሰሜን ድል የቀናው፤ ከኢራቅ እና ከሊባኖስ በመጡ ተዋጊዎች እርዳታ ነው። መንግስትን ለማገዝ ከጎረቤት አገራት ከመጡት 8ሺ ገደማ ታጣቂዎች መካከል፣ ግማሽ ያህሉ ከሊባኖስ የመጡና ሄዝቦላ የሚመካባቸው ተዋጊዎች ናቸው። ግን፣ እልል የሚያስብል ድል አይደለም። ከደማስቆ በስተደቡብ፣ አማፂ ቡድኖች ከሳምንት በፊት ባካሄዱት ዘመቻ በመንግስት ስር የነበሩ ከተሞችን ወረዋል። እናም፤ ከደማስቆ በ300 ኪሎሜትር ርቀት የሚገኙ አካባቢዎችና ከተሞች የመንግስት ጠንካራ ይዞታ ናቸው ቢባሉም፤ የመንግስት ወታደሮች ከከተማ ከተማ እንደልብ መንቀሳቀስ አይችሉም። በየመሃሉ በአማፂ ቡድኖች ቁጥጥር ስር የወደቁ በርካታ አካባቢዎች አሉ - ለደማስቆ ቅርብ የሆኑ። ከደማስቆ ራቅ ያሉ የሰሜንና የምስራቅ አካባቢማ (ከአገሪቱ ጠቅላላ ስፋት ግማሽ ያህሉ) ሙሉ ለሙሉ በአማፂዎች እጅ ገብቷል ማለት ይቻላል።
እንግዲህ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ነው፤ ፕሬዚዳንት በሽር አልአሳድ፤ ሰሞኑን ታላቅ የምስራች ዜና ይዘው ብቅ ያሉት። ከቅርብ እስከ የሩቁን ሕዋ የሚያጠና የሶሪያ የጠፈር ምርምር ኤጀንሲ እንደተቋቋመ በአገሪቱ የመንግስት ቴሌቪዥን የተዘገበው በታላቅ የፌሽታ ስሜት ነው። የብዙ መቶ ሺ ወይም የሚሊዮን ኪሎሜትሮች ርቀት አቋርጬ ጨረቃንና ፕላኔቶችን ለማጥናት የምርምር ማዕከል አቋቁሜያለሁ የሚለው የአልአሳድ መንግስት፤ ከደማስቆ ጥቂት መቶ ኪሎሜትሮችን ርቆ መጓዝ ያቃተው መሆኑ ነው ነገሩን የቅዥት አለም የሚያስመስለው። በደርዘን የሚቆጠሩት አማፂዎች እርስ በርስ እየተጨፋጨፉለት ቢሆንም፤ መንግስት ይዞታውን ማስመለስ አልቻለም። ምን አለፋችሁ? አገሪቱ ጤና የላትም ቢባል ሳይሻል አይቀርም። ከመንግስት ወታደሮች ጋር የሚዋጉት አማፂ ቡድኖች፤ እርስ በርሳቸውም ይተራረዳሉ።
የአማፂ ቡዱኖቹ ለቁጥር ያስቸግራሉ። አይነታቸውና ስማቸው ብዙ ነው። ከእነዚህ መካከል በደርዘን የሚቆጠሩ አማፂ ቡድኖች፣ በተወሰነ ደረጃ ለመተባበር ግንኙነት ፈጥረዋል - ነፃ የሶርያ ሠራዊት በሚል ስያሜ። ትብብር ውስጥ ሳይገቡ በየፊናቸው የሚዋጉ አማፂ ቡድኖችም ጥቂት አይደሉም። በስተሰሜን ጫፍ የኩርድ ተወላጆች በሚበዙበት አካባቢም በርካታ አማፂ ቡድኖች ተቋቁመዋል። ከእነዚህ በቁጥር የማይተናነሱ ሌሎች ቡድኖች ደግሞ፣ የሃይማኖት አክራሪነት ላይ የተመሰረቱ ናቸው - አንዳንዶቹም በአልቃይዳ የሚታገዙ። በዚያ ላይ፤ ሶሪያንና ኢራቅን በአንድ እስላማዊ ግዛት ለማጠቃለል ታጥቆ የተነሳው አይኤስአይኤስ የተሰኘ እጅግ ነውጠኛ ቡድንም አለ። በቀድሞ የኢራቅ ወታደሮች መሪነት የሚንቀሳቀሰው ይሄው ቡድን፤ በአብዛኛው ከተለያዩ የውጭ አገራት በመጡ አክራሪ ተዋጊዎች የተዋቀረ ነው። እነዚህ ሁሉ፤ ከመንግስት ጋር እና እርስ በርሳቸው ይጨፋጨፋሉ። በዚህም ነው በየሳምንቱ አንድ ሺ ገደማ ሶሪያውያን የሚሞቱት። ይህም ብቻ አይደለም። አማፂ ቡድኖች በየፊናቸው ከጠቅላላ አገሪቱ ስፋት ሁለት ሶስተኛ ያህሉን ቢቆጣጠሩም፤ የምር ሲታይ ግን በመድፍና በቦምብ የተቦዳደሱ ግንቦችን፣ በአውሮፕላን ድብደባ የተቆፋፈሩ ከተሞችን በአጠቃላይ የፍርስራሽ  ክምሮችን ነው የተቆጣጠሩት።
የሶርያ የእርስ በርስ ጦርነት በአለማቀፍ ደረጃ እልባት የሌለው ተስፋ አስቆራጭ እልቂት ለመሆን የበቃው አለምክንያት አይደለም። ከጤናማዎች ተርታ ሊመደብ የሚችል ቡድን ብርቅ በሆነበት አገር፣ ፀበኛ ወገኖችን ለማደራደርና ለማስታረቅ መሞከር ከንቱ ድካም ነው። አንዱን ወገን ከምር አውግዞ ሌላኛውን ወገን ለማገዝ መሞከርም፤ ከእልፍ ሽፍቶችና ነፍሰገዳዮች መሃል ገሚሶቹን እየቀጡ ገሚሶቹን እንደመሸለም ይቆጠራል። ለዚህም ነው፤ አሜሪካና የአውሮፓ አገራት አንዳች ነገር ለመዘየድ ያቃታቸው። መጀመሪያ ላይ እስራኤልንና አሜሪካን፤ ከዚያም የምዕራብ አገራትንና ክርስትያኖችን በጠላትነት በመፈረጅ ራሳቸውን የሙስሊሞች አለቃ አድርገው ለመሾም ሲሞክሩ የነበሩ አፋኝና አምባገነን አልያም አክራሪና አሸባሪ ቡድኖች፤ ዛሬ ዛሬ “ሺአ ሙስሊም” እና “ሱኒ ሙስሊም” በሚል እየተቧደኑ ይገዳደላሉ።
የሃይማኖት አክራሪነት መጨረሻ ይሄው ነው። ከ700 አመታት በፊት “ሙስሊም” እና “ክርስትያን” ብሎ በማቧደን ጦርነቶችን ያስከተለው የክርስትና አክራሪነት፤ የኋላ ኋላ “ካቶሊክ”፣ “ኦርቶዶክስ” እና “ፕሮቴስታንት” ወይም “ሉተራን” ብሎ ወደተቧደነ ግጭትና እልቂት እንዳመራ ይታወቃል። አሁን በዘመናችንም የሃይማኖት አክራሪነት እንደ ድሮው ተመሳሳይ ውጤት ሲያስከትል ይታያል። የሶሪያ አማፂ ቡድኖች፣ ለማመን በሚከብድ ሁኔታ “ሺአ” እና “ሱኒ” የሚለውን ጥላቻ ከማቀጣጠላቸው የተነሳ፤ የሟቾችን አስከሬን እየነከሱ ፎቶ እስከመነሳት ደርሰዋል።
በአልቃይዳ የሚደገፉ አንዳንዶቹ ቡድኖች፤ በውጊያ አንዳች ከተማ ወይም መንደር ሲቆጣጠሩ፤ ለአፍታ ያህል እረፍት ለማድረግ ፈቃደኛ አይደሉም። ነዋሪዎችን ወደ ማሳደድ ይገባሉ። ታዲያ ከሁሉም በፊት ኢላማቸውን የሚያነጣጥሩት በክርስትያኖች ላይ አይደለም - የሺአ ሙስሊሞች ላይ ነው። የሺአ ሙስሊም ብለው በጠላትነት የፈረጇቸውን ሰዎች ከፊሉን ገድለው፣ ከፊሉን አስረው፣ የቀረውን ደግሞ ከመኖሪያው ነቅለው ከአካባቢው ካባረሩ በኋላ ነው፤ ክርስትያኖችን ማሳደድ የሚጀምሩት። ከዚያ በኋላ ደግሞ “ለዘብተኛ የሱኒ ሙስሊሞች” ላይ ይዘምታሉ። ሂዝቦላ ከሊባኖስ የላካቸው ወታደሮችን ጨምሮ፣ ከበሽር አልአሳድ መንግስት ጎን ለመሰለፍ የመጡ ተዋጊዎች ደግሞ፤ በተቃራኒው ኢላማቸውን በቅድሚያ የሚያነጣጥሩት “የሱኒ ሙስሊሞች” ላይ ነው።
እንዲህ ናላው በተቃወሰ አገር ውስጥ ማንን አውግዞ ማንን መደገፍ ይቻላል? ለጤነኛ ሰው አስቸጋሪ ነው። ግን የማይቸገሩ አልጠፉም። በሊቢያና በግብፅ፣ በቱኒዚያና በባህሬን የተካሄዱ አመፆችን በማወደስ ስትደግፍ የነበረችው ኢራን፤ በሶሪያ ዋነኛ የአመፅ ተቃዋሚ በመሆን ለአልአሳድ መንግስት አለኝታነቷን ለመግለፅ ቅንጣት አላመነታችም። ለምን? “የሺአ ሙስሊም” በሚል ስሜት ነው። የሂዝቦላ አሰላለፍም ተመሳሳይ እንደሆነ ይታወቃል። በአረብ አገራት የተካሄዱትን አመፆች በመቃወም የምትታወቀው ሳውዲ አረቢያ ደግሞ፤ በሶሪያ የአማፂዎች ዋና ደጋፊ ሆናለች። ለምን? “የሱኒ ሙስሊም” በሚል ስሜት ነው። የሶሪያ ነገር፣ ከቅዠት አለም ያልተናነሰ እልባት የማይገኝለት ተስፋ ቢስ የእልቂት አለም ነው ቢባል ምን ይገርማል?
ይሄው ቅዠት አልበቃ ብሎ፤ በሽር አልአሳድ ደግሞ ሌላ ቅዠት ጨመሩበት - የጠፈር ምርምር ማዕከል አቋቁሜያለሁ በሚል አዋጅ ፌሽታ ለመፍጠር ሞከሩ። ሌላስ ምን ቀራቸው? አባታቸው ሲሞቱ ተተኪ ሆነው ስልጣን የያዙት በሽር አልአሳድ፤ ፕሬዚዳንት ለመሆን የገጠማቸው ችግር አንድ ነገር ብቻ ነበር - የፕሬዚዳንቱ እድሜ ከ40 በላይ መሆን አለበት የሚለው ህግ። ያንን ችግር ለማስወገድ አፍታ አልወሰደባቸውም። የእድሜ መነሻ ወደ 34 አመት ዝቅ ተደርጓል ተብሎ ታወጀ። ተገጣጠመ። በወቅቱ የአልአሳድ እድሜ 34 ነበር። እናም ፕሬዚዳንት ሆኑ። ለ30 አመት የገዙ አባታቸውን በመተካት፣ ይሄውና አስራ አምስተኛ የስልጣን አመታቸው ላይ ደርሰዋል። ታዲያ በአባትዬው ዘመንም ሆነ በልጅዬው የስልጣን ዘመን፤ ተቀናቃኝ ተቃዋሚ ፓርቲ ኖሮ አያውቅም፤ አሁንም ክልክል ነው። ቢሆንም ግን፤ በሚቀጥለው ሰኔ በሚካሄደው ምርጫ እወዳደራለሁ ብለዋል - ተወዳዳሪ የሌላቸው ፕሬዚዳንት። በሶሪያ፣ አንዳች ውድድር አለ ከተባለ፤ ውድድሩ የመጨፋጨፍ ውድድር ብቻ ነው።

Published in ከአለም ዙሪያ

        በአዲስ ጉዳይ መጽሔትና በድረ-ገፆች ላይ የተለያዩ መጣጥፎችንና ግጥሞችን በመፃፍ የሚታወቀው አሌክስ አብርሃም ፤“ዶ/ር አሸብርና ሌሎችም ታሪኮች” በሚል ያዘጋጀው የአጫጭር ልብወለዶች መድበል ባለፈው ሳምንት ለገበያ ቀረበ፡፡ ሃያ አምስት አጫጭር ልቦለዶችንና ታሪኮችን የያዘው መድበሉ፤237 ገፆች ያሉት ሲሆን በሊትማን መጽሐፍት አከፋፋይነት በ50.65 ብር እየተሸጠ ነው፡፡  
በሌላ በኩል በብርያን ትሬሲ ተፅፎ በእስክንድርያ ስዩም የተተረጎመው “መቶ የቢዝነስና የአመራር ህጎች” የተሰኘ የንግድ ክህሎት መፅሀፍ እየተሸጠ ነው፡፡ በስምንት ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ142 ገፆች የተቀነበበው  መፅሀፉ፤በህይወትና በስኬት ህግጋት፣ በመሪነት፣ በገንዘብና በሽያጭ ህጎች እንዲሁም በንግድ ሥራ ህጎችና መሰል ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥን ሲሆን የተሳካ የንግድ ስራን ለመጀመር፣ ለመምራትና ለማሳደግ የሚረዳ መፅሐፍ ነው ተብሏል፡፡ የእንግሊዝኛው መፅሃፍ በብዙ ሚሊዮን ቅጂዎች እንደተሸጠና የብዙዎችን የቢዝነስና የአመራር ህይወት እንደቀየረ ተጠቁሟል፡፡ ወደ አማርኛ የተተረጎመው መፅሀፉ   በ35.45 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በየሺወርቅ ወልዴ የተፃፈው እና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “የጠፋው ቤተሰብ” የተሰኘ ልብ ወለድ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሀፉ በውስጡ ሌሎች አጫጭር ታሪኮችና ግጥሞች የተካተቱበት ሲሆን ለደራሲዋ ሁለተኛ ስራዋ እንደሆነም ታውቋል፡፡  “የጠፋው ቤተሰብና ሌሎችም” መፅሐፍ 122 ገፆች ያሉት ሲሆን በ35 ብር ለገበያ ቀርቧል። ደራሲዋ ከዚህ ቀደም “አትሮኖስ” የተሰኘ የግጥም መፅሀፍ ለንባብ አብቅታለች፡፡ በሌላ በኩል በገጣሚ ውድነህ ግርማ (የአስቴር ልጅ) የተፃፈው “ሽበቴን ለቅማችሁ” የተሰኘ የግጥም መድበል ሰሞኑን በገበያ ላይ ውሏል፡፡ ከ120 በላይ አጫጭር ግጥሞችን የያዘው መጽሐፉ፤በ65 ገፆች የተቀነበበ  ሲሆን በ30 ብር ይሸጣል፡፡ ግጥሞቹ በፍቅር፣ በማህበራዊ ኑሮ፣ በታሪክና ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ ያጠነጥናሉ፡፡ ወጣቱ ገጣሚ የግጥም መድበሉ የበኩር ስራው እንደሆነ ጠቅሶ ወደፊት ሊያሳትም ያዘጋጃቸው የልብወለድ ስራዎች እንዳሉትም ገልጿል፡፡

አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንትና ፕሬስ ሥራዎች ከኤሎሄ አርት ፕሬስ ጋር በመተባበር የሚያዘጋጁት “ስንቅ” መፅሔት ዛሬ ከቀኑ በ10 ሰዓት በኦካናዳ ሬስቶራንት እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ በኪነጥበብ ላይ አተኩሮ በየአሥራ አምስት ቀኑ እየታተመ የሚወጣው መጽሔቱ፤ባለፈው ቅዳሜ የመጀመሪያ ዕትሙን ለንባብ እንዳበቃ ታውቋል፡፡ “ስንቅ” መፅሔት ከወቅታዊ ጉዳዮች ባሻገር ሙዚቃ፣ ግጥሞች፣ ወጎች እና ሌሎች የኪነጥበብ ስራዎችን ያስተናግዳል፡፡  

    ከለርስ ኦፍ ዘ ናይል ዓለም አቀፍ ፊልም ፌስቲቫል ባለፈው ሰኞ በብሄራዊ ቲያትር ለሁለተኛ ጊዜ የተከፈተ ሲሆን በዘንድሮ ፌስቲቫል ‹‹ሌንሶች ለአፍሪካ ህዳሴ›› በሚል መሪ ቃል ከመጋቢት 15- 22 የፊልም ስክሪኒግ እና ወርክሾፖች እንደሚካሄዱ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ብሉ ናይል የፊልምና ቴሌቭዥን አካዳሚ ከኢትዮጵያ የፊልም ሰሪዎች ማህበር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ፌስቲቫል  የአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት መሪ ቃልን በማስተጋባት ሲኒማ ህብረተሰቡን በማነጽ፣በማዝናናት፣አፍሪካውያንን በማቀራረብ፣አፍሪካዊ ባህልን በማዳበር እንዲሁም ለትውልድ በማስተላለፍና ዴሞክራሲያዊ ባህልን በማጎልበት ለአፍሪካ ህዳሴ አስተዋፅኦ  እንደሚያበረክት ተገልጿል፡፡
በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሲስ፣ በጣሊያን ካልቸር ኢንስቲትዩት እና በብሄራዊ ሙዚየም በሚደረጉ የተለያዩ ዝግጅቶች 48 የውጪና የሀገር ውስጥ ፊልሞች ለውድድር እንደሚቀርቡ የታወቀ ሲሆን ከ22 አገራት  የተውጣጡ ከ28 በላይ የፊልም ባለሞያዎች ይሳተፉበታል፡፡ ፌስቲቫሉ የፊታችን ማክሰኞ በብሄራዊ ቲያትር በሚካሄድ የመዝጊያ ፕሮግራም ይጠናቀቃል፡፡
ባለፈው ዓመት ‹‹የአፍሪካ ሲኒማ ዘመናዊ ስፍራ›› በሚል መሪ ቃል በተካሄደው የመጀመሪያው የፊልም ፌስቲቫል፤ ከ28 አገራት የተውጣጡ ከ40 በላይ ታዋቂ የፊልም ባለሙያዎች መሳተፋቸው የሚታወስ ሲሆን 56 ምርጥ የአፍሪካ ፊልሞች ተስተናግደውበታል፡፡

Page 1 of 17