ኢትዮጵያ የዓለም     የፕሬስ ነጻነት ቀንን ቅዳሜ ታከብራለች
 
         በተመሳሳይ ሰዓት ከተለያዩ ቦታዎች በፖሊስ ተይዘው ባለፈው አርብ አመሻሽ ላይ የታሰሩት 6 ፀሐፊዎችና 3     ጋዜጠኞች ጉዳይ በአወዛጋቢነቱ በአገር ውስጥና በውጭ የብዙዎችን ትኩረት  የሳበ ሲሆን ፖሊስ የምርመራ ጊዜ  እንደሚፈልግ ለፍ/  ቤት በመግለጹ ለሁለት ሳምንት በእስር  እንዲቆዩ ተወስኗል፡፡ ፖሊስ በምን ጉዳይ ዘጠኙን  ፀሃፊዎችና ጋዜጠኞች እንዳሰራቸው ለፍ/ ቤቱ ሲገልፅ፣   በመብት ተሟጋችነት ከሚታወቅ የውጭ ድርጅት ጋር በሃሳብና  በገንዘብ ተባብረው፣  በኢንተርኔትና ማህበራዊ ድረገፆች አገሪቱን ለማሸበር በመንቀሳቀስ ተጠርጥረዋል ብሏል፡፡

    በመብት ተሟጋችነት የሚጠቀሰው የውጭ ድርጅት ማን እንደሆነ ፖሊስ ባቀረበው መዝገብ  በስም አልሰፈረም፡፡ አገር ለማሸበር ተንቀሳቅሰዋል በሚል እንዲጠረጠሩ ያደረጋቸው   ድርጊት ምን እንደሆነ የሚጠቁም ነገርም  
አልተጠቀሰም ተብሏል፡፡  በተመሳሳይ ጉዳይ ተጠርጥረዋል ተብለው የታሰሩት፣   ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ  ፣  ጋዜጠኛ አስማማው ኃ/ጊዮርጊስ  ፣   ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ፣  እንዲሁም  ዞን ዘጠኝ  በሚል ስያሜ የሚታወቁት  ፀሃፊዎች-  አቤል ዋበላ፣  ዘላለም ክብረት፣  በፍቃዱ ኃይሉ፣  ማህሌት ፋንታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ እና አጥናፉ  ብርሃነ ናቸው፡፡   
     ጋዜጠኞችን በማሰር በተለያዩ ጊዜያት በዓለም አቀፍ የመብት ተከራካሪ ተቋማት   በምትወቀሰው  ኢትዮጵያ ውስጥ ከ 1994 ዓ. ም በኋላ የተወሰነ ያህል መሻሻል ታይቶ የነበረ ቢሆንም የ 1997  የምርጫ  ቀውስን ተከትሎ በርካታ ጋዜጠኞች ታስረው፣  በርካታ ጋዜጦች   መዘጋታቸው ይታወሳል፡፡ ሰሞኑን ጋዜጠኞችና  ፀሃፊዎች አንድ ላይ በብዛት መታሰራቸው    ግን ካለፉት ዓመታት የተለየ ያደርገዋል፡፡   ይህ በእንዲህ እንዳለ  የዓለም የፕሬስ ቀን በአገራችን በኢትዮጵያ የፊታችን ቅዳሜ ይከበራል፡፡

Published in ዜና

             ዶሮ በተፃፈ ሕግ፣ ፈረንጅ በልማድ በከተማ አውቶብስ አይሳፈሩም፡፡ በዘንድሮው የሁዳዴ ፆም መጠናቀቂያ ስምንተኛው ሳምንት (በሰሞነ ህማማት ማለት ነው) ላይ ግን በከተማ አውቶብስ  ውስጥ  ዶሮም ፈረንጅም ተሳፍረው ተመለከትኩ፡፡ በተለይ ፈረንጅ በአውቶብስ ላይ መሳፈሩና ተሳፋሪውን ለሁለት በከፈለ ክርክር ውስጥ መዶሉ አስገርሞኛል፡፡
ለአዲስ አበባ ከተማ አውቶብስ ድርጅት መቋቋም ሰበቡ ፈረንጆች ናቸው፡፡ በ1933 ዓ.ም ጣሊያኖች ትተዋቸው በሄዱት 10 ያህል አውቶብሶች አገልግሎት መስጠት የጀመረው ድርጅቱ፤ ባለፈው ዓመት 70ኛ የምሥረታ ዓመቱን አክብሯል፡፡ ድርጅቱ በሚሰጠው አገልግሎት ግን ፈረንጆች እምብዛም ሲጠቀሙበት አይታይም፡፡ ፈረንጆች አውቶብስ የመጠቀም ልማድ የላቸው ይሆናል እንዳንል ደግሞ በአገራቸው ከዋናዎቹ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ተጠቃሾቹ አውቶብሶች ናቸው፡፡ በእርግጥ እዚያ እንደኛ አገር መጠቅጠቅ የለም፡፡  
አብዛኞቹ የአማርኛ መዛግብተ ቃላት “ፈረንጅ” ለሚለው ቃል “የቆዳ ቀለሙ ነጭ የሆነ፣ የውጭ አገር ሰው” ብለው ነው የሚተረጉሙት፡፡ መዛግብተ ቃላቱ እንዲህ ይተርጉሙት እንጂ ህብረተሰቡ ደግሞ የተለያዩ አመለካከቶችና አተያዮች አሉት - በፈረንጅ ዙሪያ፡፡
ጣሊያንን ከአንድም ሁለት ጊዜ ከማሸነፋችን ጋር በተያያዘ “ነጭና ጥቁር የቆዳ ቀለም ባላቸው ሰዎች መሐል ምንም ልዩነት የለም፤ ሁለቱም በአዳም አምሳያ የተፈጠሩ ናቸው” የሚል አስተሳሰብ ሰፍኗል፡፡ የአፄ ምኒልክ አነጋገር ለዚህ ሁነኛ ማሳያ ሊሆን ይችላል፡፡ “ፈረንጅ እንደኛው ሰው ነው፡፡ ለገበያ ያቀረበው ዕውቀትም ይሁን ጉልበት ካለው ከፍለነው መጠቀም እንችላለን” ብለው ያምኑ ነበር - ምኒልክ፡፡
“አጤ ምኒልክ” በሚል ርዕስ በጳውሎስ ኞኞ ተዘጋጅቶ፣ በ1984 ዓ.ም ለንባብ በበቃው መጽሐፍ ውስጥ በየስ የተባሉ ታሪክ ፀሐፊ፤ በአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በአዲስ አበባ ከተማ ያጋጠማቸውን እንግዳ ሁኔታ በአንደበታቸው አስቀምጦታል - “…. በምሥራቅ አፍሪካ ባሉ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛቶች ተዘዋውሬ አዲስ አበባ ስመጣ አዲስ ነገር አጋጠመኝ፡፡ ይህም አንድ አፍሪካዊ፣ ነጮችን እያዘዘ፣ ቤት ሲያሰራ ማየቴ ነው…. ኢትዮጵያዊያኖቹ ፈረንጆቹን የሚጠሯቸው ባሪያዎች እያሉ ነበር፡፡”
ታሪክ ፀሐፊው በየስ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት የአፍሪካ አገራት ያዩትን ነገር በኢትዮጵያ መጠበቃቸው ይመስለኛል ነገሩን እንግዳ ያደረገባቸው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ቅኝ አለመገዛታቸውን ካሰቡት ግን ብዙም የሚገርም ነገር የለውም፡፡ እንዴት አንድ ጥቁር ፈረንጅን “ባሪያ” ይለዋል ካልተባለ በቀር፡፡
ሰው የቆዳ ቀለሙ ቢነጣም፣ ቢጠቁርም በሰውነቱ ሁሉም እኩል ነው ብለው ከሚያምኑት በተቃራኒ፤ እንደ ታሪክ ፀሀፊው በየስ፤ ትልቅ ነገር በማሰብ፣ በመስራትና ስኬታማ በመሆን ነጮች ከጥቁር ሕዝቦች የተሻለ አፈጣጠር አላቸው ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያዊያንም አሉ፡፡ እነዚህ ለፈረንጆች ልዩ አመለካከት አላቸው፡፡ ፈረንጆች ገዢ እንጂ ተገዢ አይደሉም፤ ሀብታም እንጂ ደሀ የለባቸውም …. ብለው ያምናሉ፡፡ ለዚህ እምነታቸውም፣ ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ፡
ባለፈው ሳምንት ከለገሀር ወደ ሽሮሜዳ በሚሄደው 31 ቁጥር አንበሳ አውቶብስ ውስጥ አንድ ፈረንጅ ተሳፍሮ በመታየቱ ምክንያት፣ ተሳፋሪዎችን ለሁለት የከፈለ ክርክር የተነሳውም ለፈረንጆች ሁለት የተለያየ አመለካከት ያላቸው ኢትዮጵያዊያን በአውቶብሱ ውስጥ ስለነበሩ ነው፡፡ ለክርክሩ መነሻ የሆነውን ሀሳብ የሰነዘረው ወጣት፤ “እንዴት ከእኛ ጋር ተሳፍሮ እራሱን ያንገላታል?” የሚል ተንኳሽ ጥያቄ ነበር ያቀረበው፡፡
ለምን? እንዴትና በምን ምክንያት እራስህንና ኢትዮጵያዊያንን ዝቅ አድርገህ፤ ፈረንጅን ከፍ ታደርጋለህ? የሚል ሞጋች ጥያቄ እየቀረበ፤ ከግራና ከቀኝ ምላሽ እየተሰጠ ክርክሩ ቀጠለ፡፡ በሙግቱ የረታ ግን አልነበረም፡፡ በድጋፍና በተቃውሞ ከየአቅጣጫው ሃሳቦች ተንሸራሽረዋል፡፡ ክርክሩን ለማርገብ የሞከሩ አልጠፉም “ኧረ ለእንግዳና ሰው አክባሪው መልካም ባህላችን ስትሉ ዝም በሉ” በሚል ግሳፄ፡፡ “ፈረንጁ አማርኛ ብቻ ሳይሆን ግዕዝን ጭምር አቀላጥፎ ያውቅ ይሆናል፤ እንጠንቀቅ እባካችሁ” የሚል ማሳሰቢያም በሹክሹክታ ተሰምቷል፡፡ ማሳሰቢያው ባልከፋ፡፡ ክፋቱ ግን ስንት ነገር ከተባለ በኋላ ሆነ እንጂ፡፡ አንድ ወጣት ተሳፋሪ ደግሞ ለራሱ ለፈረንጁ ስለጉዳዩ በእንግሊዝኛ ማብራሪያ ለመስጠት እየሞከረ ነበር፡፡   
የአውቶብስ ውስጥ ክርክሩ ከአዕምሮ ጅምናስቲክነቱ ባሻገር የሚያስተላልፈው መልዕክትም አለ፡፡ ቀደምት አባቶች ለአገራቸውና ለሕዝባቸው ነፃነት የከፈሉት መስዋዕትነት ፋይዳው የሚገባው ትውልድ እንዳለ በአንድ በኩል ሲያመለክት፣ በሌላ በኩል ደግሞ ፈረንጅ አምላኪዎች መኖራቸውንም ይጠቁማል፡፡
ለመሆኑ ፈረንጆች በከተማ አውቶብስ አይሳፈሩም የሚለው ልማድስ እንዴትና በምን ምክንያት ዳበረ? ያለ ልዩነት ለሁሉም ሰዎች አገልግሎት የሚሰጠው የከተማ አውቶብስ ድርጅት፤ ዶሮ ላይ የጫነው እግድ ግን ለሐበሻ ብቻ ሳይሆን የፈረንጅ ዶሮንም ይመለከታል፡፡ ድርጅቱ ተገልጋዮቼ ማክበር አለባቸው ብሎ በየአውቶብሶቹ በለጠፋቸውና ለቅጣት ይዳርጋሉ ከተባሉ ድርጊቶች አንዱ የቤት እንስሳትን መጫን  ነው፡፡
የቤት እንስሳት በመሆኗ በከተማ አውቶብስ እንዳትሳፈር እግድ የተጣለባት ዶሮ፤ ፋሲካና ሌሎች በዓላትን ከማድመቅ በላይ ባለ ብዙ ታሪክ ናት፡፡ በዶሮ ዙሪያ አስተማሪና አዝናኝ ተረቶች ይነገራሉ፡፡  ዶሮ የቤት እንስሳ ከመሆኗ በፊት ምድቧ ከሰማይ አእዋፋት ነበር አሉ፡፡ በአንዱ ጎዶሎ ቀን አንድ ክንፏ ተገንጥሎ መሬት ላይ ወደቀ፡፡ ከንስር አሞራ መርፌ ተውሳ፣ ክንፏን ሰፍታ ስትጨርስ መሬት ላይ የወደቀው መርፌ ድራሹ ጠፋ፡፡
“የተዋስሽኝን መርፌ እስክትመልሽልኝ ድረስ የእኔና የአንቺ ወዳጅነት በታሪካዊ ጠላትነት ተቀይሯል” ብሎ ንስር አሞራ አቋሙን አሳወቃት፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ንስር አሞራ የዶሮ አሳዳጅ ዋነኛ ጠላቷ ሆነ፡፡ ዶሮም የጠፋባትን መርፌ ፍለጋ መሬት መጫሯን ቀጥላለች፡፡ የሐበሻ ዶሮ የዚህ ታላቅ ታሪክ ባለቤት ናት- አፈ ታሪክ እንደሚለው፡
የሐበሻ ዶሮ እንደ ሕዝቡ ለፍቶ አዳሪ ናት፡፡ ሆነ ብሎ ቀለበት የሚሰፍርላት የለም፡፡ መሽቶ እስኪነጋ መሬት ትጭራለች፡፡ የምትንቀውና የምትጠየፈው ነገር የለም፡፡ ጥራ ግራ ነው አካሏን የምትገነባው፡፡ የሐበሻ ዶሮ እንቁላልም ሆነ ሥጋው ከፈረንጁ ዶሮ የበለጠ ተፈላጊ ነው፡፡ እንቁላልና ሥጋው መድሀኒትነት አለው ብሎ ሐበሻ ያምናል፡፡ ምክንያቱም መሬት ጭራ ብዙ ነገር ስለምትበላ ነው፡፡ የሐበሻ ዶሮ ስትበለትም ወርቅ የሚገኝበት አጋጣሚ አይጠፋም፡፡ ብዙ ሴቶች የዶሮ መቋደሻ ላይ ጥብቅ ፍተሻ የሚያደርጉት ያለምክንያት አይደለም፡፡
አሁንማ ዕድሜ ለኑሮ ውድነቱ! የሐበሻ ዶሮንና የፈረንጅ ዶሮን እኩል ተፎካካሪ አደረጋቸው እንጂ ሀበሻ ለበዓላት ማረድ የሚመርጠው የሃበሻ ዶሮን ነበር፡፡ በተለይ ዶሮ ወጥ ላይ ጣዕማቸው የሰማይና የምድር ያህል ነው ይባላል፡፡
የፈረንጅ ዶሮ፤ ቦታው ሆቴልና ሱፐር ማርኬት ነበር - እንደዛሬው በየቤቱ ሳይገባ፡፡ ፈረንጆቹንም የከተማ አውቶብስ ተገልጋይ ያደረጋቸው የኑሮ ውድነቱ ይሆን እንዴ? በሰሞነ ህማማት ዶሮ የተጣለባትን ሕግ ጥሳ በከተማ አውቶብስ እንደምትሳፈረው፤ ፈረንጆቹም ግርግሩን ተጠቅመው ይሆን እንዴ የቆየውን ልማድ ሰብረው በከተማ አውቶብስ ውስጥ የታዩት?
የሆነ ሆኖ “ፈረንጅ እንዴት ከእኛ ጋር ተሳፍሮ እራሱን ያንገላታል?” የሚለው የአውቶብሱ የክርክር መነሻ ሀሳብ ለተጨማሪ ውይይት የሚጋብዝ ከሆነ አሊያም ሌሎች ሃሳቦችን ከጫረባችሁ ልታካፍሉን ትችላላችሁ፡፡ ሃሳብ አዕምሮን ከአዕምሮ የሚያገናኝ ድልድይ ነው፡፡ መልካም የዳግማይ ትንሳኤ በዓል!!!

Published in ጥበብ
Saturday, 26 April 2014 13:16

የሰሎሞን ዐይኖች

ደራሲ - ሰሎሞን ሞገስ (ፋሲል)
ርዕስ - ጽሞና እና ጩኸት
የገፅ ብዛት - 70
የህትመት ዘመን - ጥር 2006 ዓ.ም
የሽፋን ዋጋ - 20 ብር
ዘውግ - ግጥም
መቅድመ ኩሉ
እውነተኛ የግጥም ደራሲ በጣር ላይ ያለች ነፍስ ይመስላል፤ ዓለም ምኑም አይደለችም፡፡ ሃብትና ንብረትም ቁቡ አይደሉም፡፡ እውነተኛ ገጣሚ ስሜቱ የሸረሪት ድር ያህል ስስ ነው፤ ሃብት ማጋበስ፣ ዝና፣ ርካሽ ተወዳጅነት፣ ስልጣን ምኑም አይደሉም፡፡ እሱ የሚኖረው የብህትውና ኑሮ ነው፤ ከሰው ጋር ቁጭ ብሎ ብቻውን ያወራል፤ ሰዎች ሲገፉ እሱ ይታሰራል፡፡ የምንዱባን ፊት ሲጠቁር እሱ እንባውን ይዘረግፋል፤ ምንዝሩ ህዝብ ሆዱን ሲቆርጠው እሱን ይሞረሙረዋል፤ ፍትህ ሲጓደል የህዝብን ዋይታ ይጮኻል፡፡ በአጠቃላይ የእውነተኛ ገጣሚ ህይወት ምስኪን ናት፤ የእሳት ራት፡፡
ለመሆኑ “እውነተኛና ሃሰተኛ ገጣሚ አለወይ” የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፤ መልሴ “አዎ!” የሚል ይሆናል፡፡ ያገሬ አርሶ አደር ጀግኖችን ሲያደንቅ:-
“ሁሉም ወንድ ነወይ ሱሪ ቢያገለድም?
አባ ስበር…ታጠቅ የእኔ ወንድም!” ይላል፡፡ እውነት ነው፤ ወንዱ ሁሉ በጾታው ወንድ ቢሆንም በግብሩ ወንድ ያልሆነ ወንድ ግን ሞልቷል፡፡ የጊዜያችን አብዛኛው ግጥምም  ወንድ እንዳልሆነው ወንድ የሚመሰል ነው፡፡ ምክንያቱም ቤት መምታት ብቻ ግጥም መግጠም አይደለማ! እዚህ ግባ የማይባል የቃላት ድሪቶ በመከመር ግጥም መጻፍ አይቻልም፡፡ ማሳተም ስለተቻለ ብቻ ገበያውን በአሰስ ገሰስ ከማጣበብ ውጭ የሚፈይደው የለም፤ አያስተምርም፤ አያዝናናም፣ አያስደምም፡፡ ይህ እርግማን ነው፤ ግጥም ትልቅ ተሰጥኦን የሚጠይቅ ረቂቅና ምጡቅ የጥበብ ዘርፍ ነው፡፡ ማንም ተነስቶ ሊጓዝበት የሚችል አውራ ጐዳና አይደለም፤ ተሰጥኦና በንባብ እንዲሁም በህይወት ልምድ መደበርን ይጠይቃል፡፡ “ከመጠምጠም መማር ይቅደም” እንዲሉ ግጥም ለመጻፍ ከመድፈራችን በፊት ተሰጥኦው አለኝ ወይ? ብሎ ራስን መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ ተሰጥኦ ከተፈጥሮ የሚታደሉት እንጂ በግብዝነት የሚታገሉት አይደለም፡፡
በአንፃሩ ተፈጥሮ ለግጥም ያዘጋጀቻቸው፣ ራሳቸውን በንባብ እንደገና የፈጠሩና ይህንን ድንቅ ተሰጥኦቸውን በገቢር የገለጡ (ጥቂት ቢሆኑም) ብርቱ ገጣሚዎች ስላሉን ተስፋ እንዳንቆርጥ ሆነናል፡፡ ከእነዚህ ብርቱ ገጣሚዎች አንዱም ሰሎሞን ሞገስ (ፋሰል) ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ የሰሎሞን ዐይኖች እንደ ንስር ጥልቅ ናቸው፤ እመቀ ዕመቃት ጠልቀው፣ ሰማየሰማያት መጥቀው የማየት ልዩ ኃይል አላቸውና!
ሰሎሞን በገጣሚነት ብቅ ያለው “እውነትን ስቀሏት” በሚል ርዕስ በ2001 ዓ.ም ባሳተመው የግጥም ስብስቡ ነው፡፡ በ2004 ዓ.ም “ከፀሐይ በታች” በሚል ርዕስ ሁለተኛ ስብስቡን ያሳተመ ሲሆን “ጽሞናና ጩኸት” የተሰኘው የግጥም ስብስቡ ሶስተኛ ስራው ነው፡፡ ሰሎሞን “እውነትን ስቀሏት” ላይ አስደምሞን “ይበል” ብንልለትም “ከፀሐይ በታች” በተባለው ስብስቡ ላይ የተወሰኑ ግጥሞቹ ልል ነበሩ፡፡ ግን ያንን ላላ ያለበትን ጐን በአያሌው አጠንክሮና ራሱን አርሞ በ “ጽሞና እና ጩኸት” ግጥሙ ብቅ ብሏል፡፡
የጽሞና እና ጩኸት ይዘት
“በጽሞና እና ጩኸት” ስብስብ ውስጥ የተካተቱት 59 ግጥሞች ሲሆኑ በአስራ አንድ የገለጣ ዘይቤዎች የተቀመሩ ናቸው፤ ወይም ከላይ በተጠቀሰው አሃዝ የሚፈረጁ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ እነሱም  -
ትዝብት (ምፀት) 18    - ንፅፅር 3
ተፈጥሮ 7         - ፍቅር 7
ዝምዝም ወርቅ 5     - ሃገር 2
ትንቢት 3        - ምርምር 2
ፍልስፍና 9        - ተስፋ 1
ህብር 2 ናቸው፡፡
የጠቀስኋቸው ርዕሰ ጉዳዮች የቀረቡበትን ዘዴ (ቴክኒክ) ለማሳየት እንጂ የሁሉም ይዘት ያው የሃገርና የወገን ጣጣ ነው፡፡ ለማሳያነት ያህል የተወሰኑትን ልጥቀስ፤
ሰሎሞን ህሊናውን ረፍት የነሳው የአይረቤ ነገሮች መብዛት ይመስላል፤ በግጥሙ ውስጥ በብዛት የምናገኘውም ፖለቲከኞችን፣ ምሁራንን፣ መንደርተኞችንና ትውልዱንም ጭምር የታዘበበትን መንገድ ነው፡፡ ሰሎሞን ምሁራንን እንዲህ ታዝቧል፡፡
“…ወይ ፀሐይ አያስጥል፣
ወይ ዝናብ አይከልል፣
የፎቶ ላንቲካ ጌጥ ከመሆን በቀር፣
ምንድን ነው ትርጉሙ የዲግሪ ቁም ነገር?
እርጥብ ነው፤ ጭንጫ ነው መሬቱስ የአገሬ፣
ምንድን ነው እሴቱ የምሁሩ ፍሬ?” (ገፅ 33)
ገጣሚው ቅኔ የተማረ አይመስለኝም፤ ግን “ዝምዝም ወርቅ፣ ምርምር እና ህብር” በሚባሉት የቅኔ መንገዶችም ጽፎ እናገኘዋለን፤ “ኢትዮጵያዊነት“ በሚል ርዕስ ያስነበበን ግጥም “ዝምዝም ወርቅ” በምንለው የቅኔ መንገድ የጻፈ ነው፤ እንዲህ ቀርቧል፡፡
“ኢትዮጵያዊነት ዕዳዬ ኢትዮጵያዊነት ፀጋዬ፣
ኢትዮጵያዊነት ስቃዬ ኢትዮጵያዊነት ደስታዬ
ኢትዮጵያዊነት ጉድለቴ ኢትዮጵያዊነት ሙላቴ
ኢትዮጵያዊነት ሹመቴ ኢትዮጵያዊነት ቅጣቴ
ኢትዮጵያዊነት ጭነቴ ኢትዮጵያዊነት እረፍቴ
ኢትዮጵያዊነት ሕይወቴ ኢትዮጵያዊነት ስቅለቴ
ኢትዮጵያዊነት ለቅሶዬ ኢትዮጵያዊነት ተስፋዬ” (ገፅ 16)፡፡
“ህብር” በሚባለው መንገድ የተጻፉ ግጥሞችንም ከሰሎሞን ሥራዎች ውስጥ እናገኛለን፤ ህብር ሁለት ትርጉም መስጠት እንዲችል ሆኖ በአንድ ወይም በሁለት ቃላት የሚገለጥ የቅኔ መንገድ ነው፤ የሚከተሉትን ለአስረጅነት ላቅርብ
“ሙያችን ነው አሉ ልብስ አጣቢዎቹ
እኔስ የሚገርሙኝ አለቅላቂዎቹ፡፡
ለጉዞ ቢነሳ ጓዝ ጉዝጓዙን ቋጥሮ
ይዘልቀው ይሆን ወይ አሁን ስንቱን አስሮ” (ገፅ 72)  
ህብራዊ ቃላቱ ያሉት “አለቅላቂዎቹ” እና “አስሮ” ከሚሉት ላይ ነው፤ ሰሙ ልብስን የሚያለቀልቁ ሲሆን ወርቁ “አለቅላቂዎቹ” አቃጣሪዎች፣ አሳባቂዎች፣ አቶክቷኪዎች፣ ነገረ ሰሪዎች፣ ሸውከኞች ወዘተ ማለት ነው፡፡ “ስንቱን አስሮ” የሚለውም ሰሙ ስንቱን ዕቃውን ሸክፎ፣ ቋጥሮ፣ ቀርቅቦ ማለት ነው ብለን ልንተረጉመው ስንችል ወርቁ ደግሞ ስንቱን ህዝብ ወይም ሰው አስሮ፣ ከርቸሌ አስገብቶ፣ ህሊናውን ቀፍድዶ ይገፋዋል? ማለት ነው፡፡ ይህን አይነቱን የቅኔ መንገድ በተለምዶ “ሰምና ወርቅ” እያሉ በርካታ ሰዎች ሲጠሩት እንሰማለን፤ ግን ስህተት ነው፡፡ የሰምና ወርቅ መንገድ እንደዚህ አይደለም፤ ይህ “ህብር” የሚባለው መንገድ ነው፡፡
ሰሎሞን ሰባት ግጥሞችን የጻፋቸው እንደ ሩሲያ ደራስያን ከተፈጥሮ ጋር እያዛመደ ነው፤ እዚህ ቁጭ ብለን በሩሲያ የሚገኙትን የቮልጋን ወንዝና የካውካሰስን ተራራዎች አብረናቸው የኖርነውን ያህል እናውቃቸዋለን፡፡ ይህን ኃይል የሰጡን ደግሞ እነፑሽኪንና፣ ጎጎል፣ ዶስተዬብስኪ፣ ማክሲም ጎርኪና ራዲሽዮቭን የመሰሉ አንጋፋ ደራሲያን ባበረከቱልን የብዕር ትሩፋት ነው፡፡ ሰለሞን እንደዚያ ነው፤ ተፈጥሮን ያደንቃል፤ ተፈጥሮን በጥልቅ የሚመለከቱ ዐይኖች አሉት፡፡
“በፕላኔቶች ላይ እረማመዳለሁ፣
በጥልቁ ባህር ላይ ቆሜ እደንሳለሁ፣
ከአበባ፣ ከነፋስ፣ ከወፍ አወራለሁ፤
ሲያሻኝ በህዋው ላይ ቤቴን እሰራለሁ፤
ጨረቃዋ ላይ ነው ተኝቼ እምዝናና፣
ምንድነህ ብትሉኝ ገጣሚ ነኝና!” (ገፅ 37) ይለናል ሰለሞን የገጣሚን ምጥቀት፣ የገጣሚን ልዩ ኃይልና ምሉዕ ሰብዕና ሲነግረን፡፡ ለእውነተኛ ገጣሚ የሚሳነው ነገር የለም፤ በጥልቅ ባህር ላይ ደንሳል፡፡ ግን ጥልቁ ባህር እውነተኛ ባለው ነው? ባህር ላይስ ቤት መስራት ይቻላል? በጨረቃ ላይ እሚተኛ ምን አይነት አስማተኛ ቢሆን ነው? መጠየቅ መመራመር አለብን፡፡ አለዚያ ግልብ አንባቢዎች እንሆናለን፡፡  
ገጣሚው ነቢይ ነው፤ ካለፈ፣ ከሄደ በኋላም ታሪክ እንደሚሠራ፣ በመቃብሩ፣ በደሙ፣ በአጥንቱ ላይ ሁሉ ገና እንደሚጽፍ በእርግጠኝነት ነግሮናል፤ እንዲህ እያለ፡-
“… ብዕር ቢጠፋብን
ቀለም ቢደርቅብን
ብራና ቢቸግር ቢያልቅ ወረቀታችን፣
እንጽፋለን ገና በየግንባራችን፡፡
የጋፍነውን ምሬት፣ ያማጥነውን ሲቃ፣
ወረቀት ቢቸግር፣ ብራና ባይበቃ፤
የሆንነውን መሆን፣ ያየነውን ስቃይ፣
እንጽፋለን ገና በየመንገዱ ላይ፡፡
የጅቦቹን ዝርፊ፣ የመድሎውን አቅም፣
የዘር ማጥራቱንም፣ የኑሮውን ሸክም፣
በአጥንታችን ብዕር ከትበነው ለዓለም፣
እንጽፋለን ገና በደማችን ቀለም፡፡
ታሪክ እንዳይስተው የኖርነውን ስቃይ፣
እንጽፋለን ገና መቃብራችን ላይ፡፡” (ገጽ 13) ድንቅ ግጥም ነው፡፡ ህዝባዊ ደራሲያን ከሞቱ በኋላም በሞቱለት ህዝብ ህሊና ውስጥ መቼም ህያዋን ናቸው፡፡ አሌክሳንደር ፑሽኪን “ሀውልት” በሚል ርዕስ እንደ ጻፈው ማለት ነው፡፡
“ለሚመጣው ትውልድ ከበስተኋላዬ
ሃውልት አቁሜያለሁ ለመታሰቢያዬ” እንዳለው፡፡ የደራሲ ሐውልት ስራው ነው፤ መቸም የማይፈርስ፤ በውሃ ሙላት የማይበሰብስ፡፡ የሰለሞን “እንጽፋለን ገና” እንደዚያ ዓይነት ኃይለ ቃል አለው፤ መልእክቱ ግዙፍ ነው፤ ህሊናን ይረብሻል፤ ራስ ምታት ሆኖ አምባገነኖችን ያተራምሳል፤ ይህ የሚሆነው ግን ህሊና ያላቸው ከሆኑ ብቻ ነው፡፡
ያም ሆኖ ሰሎሞን ሰሞኑን የፈራበት አንድ ጉዳይ ገጥሞታል፤ ሰዎችን ለማስደሰት ሲል አህያ፣ ውሻ፣ ፈረስ፣ ወዘተ ሆኖ በማገልገሉ “በግ ሁን” ብለውታል፤ ይህንን ከሁሉም በላይ ፈርቷል፡፡
ለምን? ግጥሙን እንመልት
“አህያ ሁን አለኝ አህያ ሆንሁለት፣
አሰሱን ገሰሱን እንድሸከምለት
ውሻዬም ሁን ብሎኝ ሆንሁኝ ላስደስትው፣
ጭራ እየቆላሁኝ እንዳጨዋውተው፤
ፈረሴም ሁን ብሎ ፈረሱ አደረገኝ፤
በየዳገቱ ነው ወስዶ እሚጋልበኝ፡፡
እንጃ ግን ሰሞኑን “በግ ነህ” ተብያለሁ፣
ሊያርዳኝ ነው መሰለኝ አሁን ፈርቻለሁ” (ገፅ 35)
ሰሎሞንን ያሰጋው ፈረስ፣ አህያ ወይም ውሻ መሆን አይደለም፤ በግ መሆን ነው፡፡ በግ መሆን አንገትን ለቢላዋ ይዳርጋል፤ በመሆኑም እምብዛም የዋህነት እንደማይጠቅም ነግሮናል፡፡
አርሶ አደሩ ሲያቅራራ “እምብዛ ዝምታ ለበግም አልበጃት፣
አምሳ ሆና ቆማ አንድ ነብር ፈጃት” እንደሚለው መሆኑ ነው፡፡
በአጠቃላይ የሰለሞን ሞገስ ግጥሞች እንዴ ተነብበው የሚጣሉ አይደሉም፤ ልክ እንደ ቅኔ ሊመረመሩ፤ ለመሰጠሩ ይገባል፤ በመረመርናቸው በመሰጠርናቸው ቁጥር “አጀብ!” የሚሰኙ ፍሬ ሃሳቦችን፣ ምርምሮችንና አዳዲስ ሃሳቦችን እናገኛለን፡፡ እኛ የምናየው ፊትለፊታችን ያለውን ነው፤ የሰሎሞን ዓይኖች ግን ከግድግዳው ጀርባ ያለውን ሁሉ አጥርተው ያስተውላሉ፤ ሰሎሞን ድንቅ ገጣሚ ነው፡፡ ለመሆኑ ቅኔ ቢማር ኖሮ በዚህ ተሰጥኦው ላይ ምን ዓይነት ገጣሚ ይወጣው ነበር ይሆን? ብየም አስቤያለሁ፡፡  በመጨረሻም ከሰሎሞን “ጽሞና እና ጩኸት” ላይ ያየኋቸውን ድክመቶች ጠቅሼ ጽሑፌን ልቋጭ፤ ጽሞና እና ጩኸት የተጻፈው በአማርኛ ነው፡፡ ማንኛውም የጽሁፍ ቋንቋ የራሱ ህግና ሥርዓት አሉት፡፡ ከህግና ስርዓቱ መሃል የቃላት አጠቃቀምና ስርአተ ነጥቦች ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ የመጽሀፉ ታላቁ ድክመት የሥርአተ ነጥብ አለመኖር ነው፡፡ አብዛኞቹ ግጥሞ የሥርአተ ነጥቦች ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ የመጽሐፉ ታላቁ ድክመት የሥርዓተ ነጥብ አለመኖር ነው፡፡ አብዛኞቹ ግጥሞች የስርዓተ ነጥብ ድህነት አለባቸው፡፡ በጣም አልፎ አልፎም ቢሆን ፀያፍ ብዜቶችን ለምሳሌ “መልዓክቶች” አይነት አይቻለሁ፤ ይህ ለመጽሐፉ ተነባቢነት መሰናክል ሊሆን ይችላልና ጥንቃቄ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ገፅ 48 ላይ የቀረበውና ቤት ሰበር ግጥምን የተመለከተው ጉዳዩም ስህተት ነው፤ ቤት ሰበር ግጥም የተጀመረው በግዕዙ ቅኔ “ፍልስ” ተብሎ የሚታወቅ እንጂ ሰሎሞን የጀመረው አዲስ ነገር አይደለም፡፡ በርካታ ግጥሞችን ርዕስ አልቦ ማድረግም ጥቅሙ አልታየኝም፡፡ በተረፈ ባለ ንስር አይኑ ሰሎሞንን በርታ አለማለት ንፍገት ይመስለኛል፡፡      

Published in ጥበብ

የስነ ጥበብ ስራዎችን ለህብረተሰቡ በማቅረብ አማራጭ መድረክ የመፍጠርና ለጥበብ አፍቃሪያን በተለያዩ አጋጣሚዎችና ስፍራዎች የስነ ጥበብ ስራዎችን የመመልከት፣ የማድነቅና ቁምነገር የመቅሰም ዕድል የመፍጠር አላማ ይዞ የተቋቋመው ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ትናንት ምሽት ተመርቆ ተከፈተ፡፡
የማዕከሉ መስራችና ዳይሬክተር አቶ ሚፍታ ዘለቀ እንደተናገሩት፤ ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ስነጥበባዊ ዋጋው ከፍ ያለ ማህበረሰብ የመፍጠር፣ የስነ ጥበቡን ማህበረሰብ ከሰፊው ህብረተሰብ ጋር የማቀራረብ፣ ስነ ጥበብን መሰረት ያደረገ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም መንፈሳዊ ብልጽግናን የመፍጠር ግብ ይዞ ነው የተቋቋመው፡፡
ትናንት ምሽት በተከናወነው የማዕከሉ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፤ ታደሰ መስፍን፣ ደረጀ ደምሴ፣ ዘላለም ግዛው፣ ዳዊት አድነውና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ሰኣሊያን የተሳተፉበት “ጉራማይሌ - አንድ” የተሰኘ የስዕል ትርዒት ለእይታ በቅቷል፡፡

በርካታ የሀገሪቱን ተዋንያን መፍለቂያ የሆነው እና ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ የሚገኘው “ሚያዚያ 23” አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት እያከበረ ነው፡፡  በ1956 ዓ.ም “አስፋወሰን ካሳ” በሚል መጠሪያ ሥራ የጀመረው “ሚያዚያ 23” በመጪው ሐሙስ ከጧቱ ሦስት ሰዓት በሚከናወን ደማቅ ሥነ-ሥርአት የቀድሞ ተማሪዎቹ እና ያሁኖቹ የሀገሪቱ አንጋፋና ታዋቂ ከያንያንና ጋዜጠኞች በትምህርት ቤቱ እንደሚገኙ የተናገሩት የትምህርት ቤቱ ርእሰ መምህር አቶ ጌታቸው አዋሽ፤ እነዚሁ ከያንያን ልምድና ተሞክሮአቸውን እንዲሁም ትዝታቸውን ለአሁን ተማሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚያቀርቡ ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች የሚቀርቤ ሲሆን 50ኛ ዓመቱን አስመልክቶ እየተካሄደ ያለው የእግር ኳስ ውድድርም ይጠናቀቃል፡፡ ሥራ ሲጀምር ከ120 በታች ተማሪዎች የነበሩት ትምህርት ቤቱ፤ አሁን 1560 ያሕል ተማሪዎች ያሉት ሲሆን ከቀድሞ ተማሪዎቹ መካከል አርቲስት ጥላሁን ዘውገ፣ ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ፣ የቶክሾው አቅራቢው ሰለሞን ሹምዬ፣ አርቲስት ግርማ ተፈራ፣ አርቲስት አለልኝ መኳንንት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የኤፍኤም ጣቢያዎች ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሳሙዔል እንዳለ ይገኙበታል፡፡

     በሽመልስ ይፍሩ (ጤርጢዮስ ከቫቲካን) የተዘጋጀው “የተመለሱና ያልተመለሱ ጥያቄዎቼ” የተሰኘው መፅሃፍ ታትሞ እየተሸጠ ነው፡፡
መጽሃፉ፤ አንዱን ቅዱስ መጽሐፍ እያነበቡ በተለያየ ስም የተጠሩበትንና የተለያየ አቋም የያዙበትን ዐብይ ምክንያት እንደሚፈትሽ የገለፀው አዘጋጁ፤ ርዕሰ ጉዳዩም ስለ እግዚአብሔር፣ ስለ ሰውና ስለ ክርስቶስ ባላቸው የእምነት ግንዛቤ ላይ ብቻ የሚያተኩር ነው ብሏል፡፡
በመፅሃፉ ውስጥ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ፣ የፕሮቴስታንት፣ የሐዋርያዊት (በተለምዶ Only Jesus የሚባሉቱ) ቤተክርስቲያናት እና የይሖዋ ምስክሮች አገልጋዮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ መጽሐፉ በ50 ብር እየተሸጠ ሲሆን በጃፋር የመጽሀፍት መደብር እየተከፋፈለ ይገኛል፡፡

  በቴዎድሮስ ኃይሉ ተፅፎ በሰለሞን ሙሄ የተዘጋጀው “አንላቀቅም” የተሰኘ ሮማንስ ኮሜዲ ፊልም፤ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ በ11 ሰዓት በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በቴዎድሮስ ፊልም ፕሮዳክሽን በቀረበው በዚህ ፊልም ላይ ማህደር አሰፋ፣ ሰለሞን ሙሄ፣ ሙሉዓለም ጌታቸው፣ ነብዩ ኤርሚያስ፣ ሄኖክ አለማየሁና ሌሎች አንጋፋ ባለሙያዎች እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡

    የተለያዩ የቢዝነስ፣ የሞቲቬሽን እና መሰል መፅሀፍት በማዘጋጀት የሚታወቁት ዶ/ር አቡሽ አያሌው፤ ያዘጋጁት “ካይዘን” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በግራንድ ዮርዳኖስ ሆቴል ተመርቋል፡፡ ሩቅ ምስራቃዊያን ሳይንሳዊ እውነታውን ቀድመው በመረዳት ካይዘንን ተለውጠውበታል የሚሉት ዶ/ር አቡሽ፤ ሀገራችንም ካይዘንን ተግባራዊ ካላደረገች ያሰበችው ለውጥ ላይ እንደማትደርስ በማሰብ፣ የካይዘንን ግንዛቤ በህብረተሰቡ ውስጥ ለማስረፅ እንደተዘጋጀ ተናግረዋል በመፅሀፉ ምረቃ ላይ የተለያዩ እንግዶች የተገኙ ሲሆን በመፅሀፉ ዙሪያም ውይይት ተካሂዷል፡፡

    ነዋሪነታቸውን በለንደን ባደረጉት ኢ/ር ወንድሙ ነጋሽ ተፅፈው የተዘጋጁት “የአዕምሮ አስተዳደር ሞዴል” እና “ፍቅር ምንድን ነው” መፃህፍት ዛሬ ረፋድ ላይ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃሉ፡፡
መፃህፍቶቹ ስሜትን ስለመቆጣጠር፣ በራስ ስለመተማመን፣ በአላማ ስለመፅናት፣ ስለ ደስታና የፍቅር ያለንን ግንዛቤ የሚያሰፉ ሲሆን “ፍቅር ምንድነው?” በሚለው መፅሀፍ ውስጥ ፍቅር ምንነትና መሰል ጉዳዮች ተዳስሰውበታል፡፡ መፃህፍቱ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ዛሬ ሲመረቁ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ፀሐፊው ኢንጂነር ወንድሙ ነጋሽ ላለፉት 15 ዓመታት በእንግሊዝ የጦር መርከቦችን ከአደን የመከላከል ሲስተም መሀንዲስ በመሆን ከመስራታቸውም በተጨማሪ በስነ-ልቦና ላይ የተመሰረቱ ተከታታይነት ያላቸው ጥናታዊ መፃህፍት በመፃፍ ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

የተለያዩ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ቅርሶችና የብሔር ብሄረሰቦችን ባህልና ትውፊት በአንድ ላይ በማሰባሰብ ለማስጎብኘት የሚያስችል ነው የተባለ የባህል ማዕከል የፊታችን ሐሙስ ሊከፈት ነው፡፡
“ብርሃን ኢትዮጵያ የባህል ማዕከል” የሚል ስያሜ የተሰጠው የባህል ማዕከል፤ ኢትዮጵያን ቀደምት ታሪኮች የሚያወሱ ቅርሶች፣ ለአገሪቱ ታሪካዊ ቦታዎች ምሳሌ የሚሆኑ ስራዎች፣ ከአፄ ቴዎድሮስ እስከ አሁን ድረስ ያሉ የአገሪቱ መሪዎች ምስሎችና አጫጭር ታሪኮችና ብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ ቤቶችን አካቶ የያዙ መሆኑ ታውቋል፡፡
የማዕከሉ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሳቤላ በላይነሽ አባይ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ማዕከሉ ህብረተሰቡ ባህሉን በአግባቡ ለማወቅና ጎጂውን ለማስቀረት፣ ጠቃሚውን ደግሞ ለመያዝ እንዲችል የሚያግዝ መሆኑን ጠቅሰው፣ ቱሪስቶች በአንድ ጊዜ ሁሉንም አካባቢዎች ለመጎብኘት እንዲችሉ እድሉን ያመቻቸ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ ቄራ ቡልጋሪያ ማዞሪያ አካባቢ የተሰራው የባህል ማዕከል፣ የፊታችን ሐሙስ በይፋ ተመርቆ እንደሚከፈትም ታውቋል፡፡  

Page 1 of 13