አስራ አራት አንጋፋና አማተር ሰዓሊያን የሚሳተፉበት “ጅማሬ” የተሰኘ የስዕል አውደርዕይ ዛሬ በ11 ሰዓት 30 ሽሮሜዳ ኪዳነምህረት ቤ/ክርስቲያን መንገድ ላይ ታቦት ማደሪያው ፊትለፊት በሚገኘው ሚራጅ ኮፊ ሮስተር ይከፈታል፡፡
የአውደርዕዩ አዘጋጅ አቶ ዮሐንስ አክሊሉ እንደገለፁት፤ አውደርዕዩ እስከ ሐምሌ 5 ቀን 2006 ዓ.ም ለ15 ቀናት ለተመልካች ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን  በየሦስት ወሩ የሚዘጋጅ ፕሮግራም እንደሆነም ታውቋል፡፡

በደርግ ዘመን ጠ/ሚኒስትር የነበሩት ፍቅረሥላሴ ወግደረስ “እኛ እና አብዮቱ” በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ፅሑፍ ባለሙያ የሆኑት አቶ ሰለሞን ተሰማ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ እንደሚያቀርቡ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጠቁሞ፤ የሥነ-ፅሁፍ ቤተሰቦች በውይይቱ ላይ እንዲገኙ ጋብዟል፡፡

በመርሲ ዲኮር ዲዛይንና ሞዴሊንግ ማሰልጠኛ ተቋም ለሁለተኛ ጊዜ የተዘጋጀ “Visual Art Meets Fashion” የተሰኘ የስዕልና ቅርፃ ቅርፅ አውደ ርዕይ ትላንት ከምሽቱ 11 ሰዓት ላይ ቦሌ መድኃኒዓለም አካባቢ በሚገኘው ካሌብ ሆቴል የተከፈተ ሲሆን መታሰቢያነቱ ለአርቲስት አለ ፈለገሰላም እና እጅግ ለተከበሩ ለዓለም ሎሬት ዶ/ር ሜድ ጥበቡ የማነብርሃን እንደሆነ ታውቋል፡፡ ትላንት በመክፈቻው ዕለት በዲዛይነር ምህረት ምትኩ የተሰናዳ የፋሽን ትርኢት የቀረበ ሲሆን የ57 ሰዓሊያንና የ6 ቀራፂያን ሥራዎች አውደርዕይ ተከፍቷል፡፡ አውደርዕዩ እስከፊታችን ሰኞ ምሽት ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡ ማሰልጠኛ ተቋሙ ባለፈው ዓመት ለተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ መታሰቢያነት ተመሳሳይ አውደርዕይ አዘጋጅቶ እንደነበር በላከው መግለጫ አስታውሷል፡፡

የዚምባቡዌ ህዝብ ከሙጋቤ በቀር ሌላ መሪ አይተው አያውቁም

የሆነ ሆኖ በድፍን ዚምባብዌ አሁን አየሩን የሞላው ትኩስ የመጋገሪያ ወሬ፣ የሽማግሌው ፕሬዚዳንት ሮበርት ገብርኤል ሙጋቤ በሽታ ካንሰር ነው አይደለም የሚለው ሳይሆን እርሳቸውን የሚተካው መሪ ማን ይሆን የሚለው ብቻ ነው፡፡

ከአመታት በአንዱ አፍሪካ ሙአመር ጋዳፊና ሆስኒ ሙባረክ የተባሉ መሪዎች ነበሯት፡፡ እነዚህ መሪዎች ሀገራቸውን ለረጅም ጊዜ በፕሬዚዳንትነት በመምራት የአፍሪካን ሬከርድ የያዙ ነበሩ፡፡ ፕሬዚዳንት ሙአመር ጋዳፊ ሊቢያን ለአርባ አራት አመት፤ ሆስኒ ሙባረክ ደግሞ ግብጽን ለሰላሳ ሁለት አመት በፕሬዚዳንትነት መርተዋል፡፡
ከሶስት ዓመት በፊት በሊቢያና በግብጽ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ አብዮት፣ ፕሬዚዳንት ጋዳፊን ስልጣናቸውን ብቻ ሳይሆን ህይወታቸውንም ሲያሳጣቸው፤ ፕሬዚዳንት ሙባረክን ደግሞ ከስልጣናቸው ተፈንግለው ወህኒ ለመጣል አብቅቷቸዋል፡፡
አሁን ሬከርዱ የተያዘው በሮበርት ሙጋቤ ነው፡፡ እንደ አውሮፓ ዘመን አቆጣጠር በ1980 ዓ.ም ነፃነታቸውን የተቀዳጁት ዚምባቡዌአውያን ከሮበርት ሙጋቤ በቀር ሌላ መሪ አይተው አያውቁም፡፡ የመጀመሪያዎቹን ሰባት አመታት (1980-1987) በጠቅላይ ሚኒስትርነት፣ ከ1988 ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በፕሬዚዳንትነት የሚመሯቸው ሮበርት ሙጋቤ ናቸው፡፡
በደቡባዊ ዚምባብዌ በምትገኘው የኩታማ ከተማ፣ ጥቅምት 21 ቀን 1924 ዓ.ም ከአናፂ ቤተሰብ የተወለዱት ሮበርት ገብርኤል ሙጋቤ፤ የከፍተኛ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በደቡብ አፍሪካና በጋና ነው፡፡ በ1963 ዓ.ም ከቄስ ንዳባንጊ ሲቶሌ ጋር በመሆን ጆሽዋ ንኮሞ ይመሩት ከነበረው የዚምባብዌ የአፍሪካ ህዝቦች ህብረት (ዛፑ) ተገንጥለው፣ የዚምባብዌ የአፍሪካ ብሔራዊ ህብረት (ዛኑ) በማቋቋም፣ ለነፃነት ትግል ነፍጥ አንስተው፣ ውጊያ እስከጀመሩበት ጊዜ ድረስ በሮማ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ቤት መምህር ነበሩ፡፡
ሮበርት ሙጋቤ፤ ዛኑን አቋቁመው ጫካ እንደገቡ መላ ዚምባብዌአውያን ነፃነታቸውን ለመጎናፀፍ በቁርጠኝነት እንዲታገሉና ከድርጅታቸው ከዛኑ ጎን እንዲሰለፉ ዛሬም ድረስ እጅግ ቀስቃሽ ነው የሚባልላትን ንግግር አደረጉ፡፡ ይህን ንግግር ባደረጉ ልክ በሰባተኛው ወር 1964 ዓ.ም በአያን ስሚዝ በሚመራው የነጮች መንግስት የደህንነት ሀይሎች እጅ ወደቁ፡፡ አፍታም ሳይቆይ የእኛ ሀገር መንግስት “ህገ መንግስታዊውን ስርአት ህጋዊ ባልሆነ መንገድ በኃይል ለመናድ” እንደሚለው አይነት ክስ ተመስርቶባቸው፣ ወንጀለኛ ሆነው በመገኘታቸው፣ የአስር አመት ጽኑ እስራት ተፈርዶባቸው ወህኒ ወረዱ፡፡
ሮበርት ሙጋቤ የእስር ጊዜአቸውን እንዲሁ አላሳለፉትም፡፡ የከፍተኛ ትምህርታቸውን በተልዕኮ በመከታተል በህግ ትምህርት ሁለት ዲግሪያቸውን ለማግኘት ችለዋል፡፡ በፖለቲካ እንቅስቃሴአቸውም ቢሆን እስር ቤት የታሰበውን ያህል ከጨዋታ ውጪ ሊያደርጋቸው አልቻለም፡፡ እዚያው ወህኒ ቤት ውስጥ እያሉ በ1974 ዓ.ም የዛኑ መስራችና መሪ የነበሩትን ቄስ ንዳባኒንጊ ሲቶሌን በመፈንቅለ ስልጣን በማስወገድ ቀጥተኛ አመራር ይሰጡ ነበር፡፡  
በ1974 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ከእስር ቤት የተለቀቁት ሮበርት ሙጋቤ፤ እስከ 1979 ዓ.ም ድረስ ለነፃነት የተካሄደውን የትጥቅ ትግል በዋናነት መርተዋል፡፡ በየካቲት ወር 1980 ዓ.ም በተካሄደው የመጀመሪያው ድህረ ነፃነት ምርጫ፣ ከጆሽዋ ንኮሞ ጋር በጥምር ይመሩት የነበረው የዚምባብዌ አፍሪካ ብሔራዊ ህብረት አርበኞች ግንባር (ዛኑ ፒኤፍ) በከፍተኛ ድምጽ በማሸነፉ፣ ሮበርት ሙጋቤ የነፃይቱ ዚምባብዌ የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን በሃምሳ ስድስት አመት የጐልማሳነት እድሜአቸው የመሪነት ስልጣኑን ተቆናጠጡ፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮም ከመሪነት መንበሩ አልወረዱም፡፡
አምና ለ89 አመቱ አዛውንት ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ጥሩ ጊዜ አልነበረም፡፡ እድሜና ስልጣን አመጣሽ በሽታዎች እየተፈራረቁ የጤናቸውን ሁኔታ በከባዱ ወሰድ መለስ እያደረጉት በጣም ተቸግረው ነበር፡፡ በወቅቱ በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይወዳደሩ ይችላሉ ተብሎ በሠፊው ተገምቶም ነበር፡፡
ላለፉት 33 አመታት የተቀመጠቡትን የፕሬዚዳንትነት የስልጣን ወንበር መልቀቅ ሞት መስሎ ይታያቸው የነበሩት ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ  “ዚምባብዌ እኮ የእኔ ናት፤ ለሌላ ሰው እንዴት አድርጌ አሳልፌ እሠጣታለሁ?” በማለት በምርጫው እንደሚሳተፉ አሳወቁ፡፡ የተካሄደውን ምርጫም ዋነኛ ተቀናቃኛቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር መርጋን ቻንጋራይን በከፍተኛ ድምጽ በማሸነፍ አዳሜን ሁሉ ኩም አደረጉት፡፡
ከሰሞኑ ግን ብዙዎች ከፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ አፍ ይወጣል ብለው በቀላሉ የማይገምቱት ንግግር ተሰምቷል፡፡ የ90 አመቱ አዛውንት ላለፉት 34 አመታት በብቸኝነት የተቀመጡበት የፕሬዚዳንትነት ወንበር እንደሰለቻቸውና በዚህ አመት መጨረሻ ላይ ከስልጣን ወርደው ጡረታ መውጣት እንደሚፈልጉ ተናግረዋል ተብሏል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ፕሬዚዳንት ሙጋቤ አብዛኛውን ያለፉትን ስድስት ወራት ያሳለፉት ካንሰር ነው እየተባለ የሚወራባቸውን በሽታቸውን ለመታከም ወደ ሲንጋፖር በመመላለስ ነው፡፡ መንግስታቸውም ስለ ጤንነታቸው ግልጽ መረጃ ከማቅረብ ይልቅ ስለጉዳዩ የሚያወራና የሚጽፍን ሰው ሁሉ እንደሚቀጣ ማስፈራራትን መርጧል፡፡
የሆነ ሆኖ በድፍን ዚምባብዌ አሁን አየሩን የሞላው ትኩስ የመጋገሪያ ወሬ፣ የሽማግሌው ፕሬዚዳንት ሮበርት ገብርኤል ሙጋቤ በሽታ ካንሰር ነው አይደለም የሚለው ሳይሆን እርሳቸውን የሚተካው መሪ ማን ይሆን የሚለው ብቻ ነው፡፡
እንደኔ እንደኔ፣ የሳቸው ተተኪ ከምክትል ፕሬዚዳንቷ ጆይብ ሙጁሩ፤ ወይም “አዞው” በሚል ቅጽል ስም ከሚታወቁትና የፍትህ ሚኒስትር ከሆኑት ኤመርሰን ምናንጋዋ አሊያም የዚምባብዌ ማዕከላዊ ባንክ ገዢ ከነበሩት ጌዲዮን ጐኖ አያልፍም፡፡ ከዚህ ውጭ ከሆነ ግን እኔ ልቀጣ፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ታጋዮች የህዝብ ጫማ ናቸው፤ ታጋዮች የግል ጥቅምና ምቾታቸውን በሰፊው ህዝብ ጥቅምና ምቾት የቀየሩ የህዝብ መድህኖች ናቸው፤ ታጋዮች ለህዝባቸው ምቾትና ድሎት ሲሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚከፍሉ የህዝብ ቤዛዎች ናቸው፡፡…
እነዚህን የመሳሰሉ የአብዮታውያን የፕሮፓጋንዳ ርግረጋዎች የኢትዮጵያ አብዮት በግብታዊነት ፈነዳ ከተባለበት ከየካቲት 1966 ዓ.ም ጀምሮ አብዮታዊና ተራማጅ ነን ከሚሉ ሃይሎች ዘንድ ስንሰማው የኖርነውና ዛሬም እየሰማነው ያለነው ጉዳይ ስለሆነ ምንም አስደናቂ ነገር የለውም፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ይህ የአብዮታውያኑ መሀላ፣ የታጋዮቹን ሰውነትና የሰውን ልጅ ባህርይ በወጉ ከግምት ውስጥ ያስገባ አይደለም፡፡ እናም ነገሩ አብዛኛውን ጊዜ የሚባለውን ያህል ትክክል ወይም እውነት ሆኖ አይገኝም፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ደግሞ ማስረጃ ፍለጋ የአለም አብዮተኞችን የታሪክ መዝገብ ማገላበጥ ጨርሶ አያስፈልገንም፡፡ የሀገራችን አብዮተኞች ታሪክ ከበቂ በላይ ነው፡፡
የጊዜያዊ ወታደራዊ መንግስት መሪዎች በስልጣን ላይ በቆዩበት አስራ ሰባት አመታት ሰፊውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከአስከፊ ድህነት ለማላቀቅ ሲሉ አንድም ቀን እንኳ ሳይደላቸውና ሳይስቁ ከፍተኛ መስዋዕትነት ይከፍሉ እንደነበር በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር፡፡ እነዚህ አብዮታውያን ወታደራዊ መሪዎች በተግባር ያደረጉት ግን ካለፈው እጅግ የከፋ ድህነትን ለሰፊው ህዝብ እኩል በማካፈል፣ ራሳቸውንና የራሳቸውን ወገን ከድህነት ማላቀቅ ነው፡፡
“አብዮታዊውን” ወታደራዊ መንግስት ለአስራ ሰባት አመታት በዘለቀ የትጥቅ ትግል የዛሬ 23 አመት አሸንፎ ስልጣን የተቆጣጠረው ኢህአዴግ፣ ተራራ ያንቀጠቀጡት ታጋዮቹ በግል ጥቅምና ምቾት የማይንበረከኩ፣ የህዝብ ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና የመጀመሪያም የመጨረሻም የትግል ግባቸው እንደሆነና ለዚህም ግብ መሳካት የህይወት መስዋዕትነት እንደከፈሉ በተደጋጋሚ ሊያስረዳን ሞክሯል፡፡
ጥረቱ ያላቋረጠና ከባድ መሆኑ ሲታይ ደግሞ ኢህአዴግም እንደሌሎቹ አብዮታዊ ድርጅቶች ሁሉ የታጋዮቹን ሰውነት ጨርሶ የረሳ አስመስሎት ነበር፡፡ የማታ ማታ በተግባር የታየው ግን በቃል ከተወራው በእጅጉ የተለየ ነበር፡፡ የራሳቸውን ጥቅምና ብልጽግና ከምንም ሳይቆጥሩ ለህዝባቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና እውን መሆን የህይወት መስዋዕትነት ለመክፈል ለአፍታም እንኳ አያመነቱም ተብለው ብዙ እጅግ ብዙ የተነገረላቸው “አብዮታውያን” ታጋዮች “የከተማ ስኳር ፈታቸው፤ የድል ማግስት ህይወት ጽኑ የትግል መንፈስና ስሜታቸውን ሰልቦ ከማይወጣው የትግል አላማቸው አሳታቸው” ተብሎ በራሳቸው ድርጅት አንደበት ተነገረባቸው፡፡
ይህንን በይፋ የተናገረው ድርጅታቸው ኢህአዴግ፤ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ በማግስቱ እንደ ከፍተኛ የድርጀቱና የሀገር መሪነታቸው ለሌሎች አርአያ መሆን ሲገባቸው፣ በከተማው ስኳር ተታለው ከህዝብ ጥቅምና ብልጽግና ይልቅ ለራሳቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና ሌት ተቀን ሲጥሩና ህገወጥ ድርጊቶችን ሲፈጽሙ አግኝቻቸዋለሁ ያላቸውን ከፍተኛ የኢህአዴግና የመንግስት ባለስልጣናት እንደ እጅ ስራቸው መጠን ህግ ያውጣቸው ብሎ ዘብጥያ አወረዳቸው፡፡
የአብዮታዊቷ ኩባ ታሪክም ከኢትዮጵያም ሆነ ከሌሎቹ አብዮተኛ ሀገራት የተለየ አይደለም፡፡ እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር በ1959 ዓ.ም የባቲስታን መንግስት በትጥቅ ትግል አስወግደው ስልጣን ስለተቆጣጠሩት የኩባ አብዮታዊ ታጋዮች ያልተባለና፣ ያልተነገረ ገድል አለ ለማለት ያስቸግራል፡፡ በተለይ ደግሞ የኩባ አብዮት ግንባር ቀደም መሪና የኩባ ጭቁን ህዝብ አባት ስለሚባሉት ስለ ጓድ ፊደል ካስትሮ በቃል ያልተነገረ፣ በጽሑፍ ያልተፃፈ፣ በፊልምም ያልቀረበ… እራስን ለህዝብ ጥቅም አሳልፎ ስለመስጠት ገድል.. ለሞት መድሃኒት እንኳ ፈልጐ ማግኘት አይቻልም፡፡
ራሳቸውን ለሰፊው ጭቁን የኩባ ህዝብ ፍፁም አሳልፈው የሰጡና ከወታደር ካኪ ሌላ የረባ ልብስ እንኳ የላቸውም እየተባለ ነጋ ጠባ የሚወደሱት ጓድ ፊደል ካስትሮ ግን እንደሚወራላቸው አይነት ሰው ሳይሆኑ ይልቁንም ልክ እንደ አንድ ታላቅ ንጉስ እጅግ በተንደላቀቀ ሁኔታ በምቾት የኖሩ ሰው እንደሆኑ ከተለያዩ ወገኖች በሹክሹክታ ሲወራ ቢከርምም ማረጋገጥ ሳይቻል ቆይቶአል፡፡
ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ የተባለ የ65 አመት ጐልማሳ ኩባዊ ግን ይህንን የሚያረጋግጥ ማስረጃ በቅርቡ ይፋ አድርጓል፡፡ ከ1977 እስከ 1994 ዓ.ም የፕሬዚዳንት ካስትሮ የቅርብ አማካሪና ከታናሽ ወንድማቸው ከራውል ካስትሮ ቀጥሎ እጅግ ጥብቅ ሚስጥረኛቸው የነበረው ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ፣ በቅርቡ ባሳተመው መጽሐፍ፤ ፕሬዚዳንት ጓድ ፊደል ካስትሮ 20ትላልቅ የቅንጦት መኖሪያ ቤቶች፣ የግል ደሴትና የመዝናኛ ጀልባ አሏቸው፡፡
የኩባው አብዮተኛ ጀግና ጓድ ፊደል ካስትሮ፤ በተጠቀሰው አመት ውስጥ በከፍተኛ ሚስጥር ይካሄድ በነበረ የእፅ ዝውውር ንግድ ውስጥ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ሀቫና ከተማ አቅራቢያ ባቋቋሙት የወታደራዊ ማሰልጠኛ ካምፕ ውስጥም እንደ አይ አር ኤ የመሳሰሉ ታጣቂ የሽብር ቡድኖችን ያሰለጥኑ ነበር፡፡     

Published in ከአለም ዙሪያ

     ሾጎሎማንጎጭ በምድር በመካከለኛው ክፍል የሚገኝ በባህር የተከበበ ለም ሀገር ነው፡፡ እዚህ ሀገር ውስጥ ሰው ሁሉ ሀገሩን የሚወድድ፣ ወገኑን የሚያፈቅርና መልካም ባህል ያለው ህዝብ ይኖርበታል፡፡ ሾጎሎማንጎጫውያን ሁለት ዓበይት የጎሣ ክፍሎች አሏቸው፡፡ አንደኛው አዝሮድ ሲባል ሌላው ምርሻድ ይባላል፡፡ ጥቂት አዝሮዶች በምዕራቡ የሀገሪቱ ክፍል በእርሻ ሥራ ሲተዳደሩ፣ ሌሎቹ ደግሞ በምሥራቁ ክፍል የባህር ዳርቻ ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሰማርተው ኑሯቸውን ይገፋሉ፡፡ የተቀሩት በመላው የሀገሪቱ ክፍል እየኖሩ በግል ሥራ ላይ ሆነው የሚተዳደሩ ናቸው፡፡ ምርሻዶች ደግሞ በሁሉም ቦታ እየተዘዋወሩ ከፊሉ በንግድ ሥራ፣ የተቀሩት ደግሞ በእጅ ሥራ ሙያ ላይና በሌላውም ጥበባዊ ዕውቀት ላይ ሁሉ ተሰማርተዋል፡፡
ምርሻዶችና አዝሮዶች ሥርወ የዘር ግንዳቸው ከሁለት ወገን ቢሆንም፣ ይህንን የሚያስብ በመካከላቸው አንድም ሰው አይገኝም፡፡ የሀገሩ ሰው ሁሉ የሚያምነው በቃ ሾጎሎማንጎጫዊ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ተፋቅረው ሲጋቡ፣ ተጋብተው ሲዋለዱ፣ በአገራቸው ላይ የሚመጣውን ጥቃት ሁሉ ባንድነት ሆነው ሲመክቱ፣ በሀዘንም በደስታም ጊዜ በህብረትና በስምምነት ሆነው ይኖራሉ፡፡ የሾጎሎማንጎጫውያን ብቻ የሆነውን የተቆጣ ነብር ምልክት ደረቱ ላይ ያልተነቀሰ ሰው በሾጎሎማንጎጭ ምድር አይገኝም፡፡ ይህ ከአንገቱ በላይ የሚታየው የቁጡ ነብር ምስል ለሀገራቸው ቀናዒ አንድ ህዝብ ለመሆናቸው ማረጋገጫ ምልክታቸው ነው፡፡ ይህን ምስል ከፈጣሪያቸው በታች ከልባቸው ያፈቅሩታል። ማንም ፍቆ ሊያጠፋው የማይችል የልብ ውስጥ ማህተማቸው ነው። አገራቸው ሾጎሎማንጎጭ፣ እነሱም ሾጎሎማንጎጫውያን ናቸው፤ በቃ ይኸው ነው፡፡ ከዚህ ውጪ የሚያስቡት ነገር የለም - ቁጡ ነብር!
ሾጎሎማንጎጫውያን ሎማዲን የምትባል ንግሥት አለቻቸው፡፡ ይህች ሴት በአስተዋይነቷና በብልህነቷ ወደር የማይገኝላት ነች፡፡ መልካም የሆነው ቅን ሥራዋ በህዝቧ ዘንድ የተከበረችና የተወደደች እንድትሆን አድርጓታል፡፡ ለህዝቧና ለሀገሯ እጅግ ቀናዒ በመሆኗ በግዛቷና በመንግሥቷ ብዙ ዘመን ቆይታለች፡፡
በሾጎሎማንጎጫውያን የዘመን አቆጣጠር በአንደኛው ቀን እንዲህ ሆነ፡፡ የሀገሪቱ ህዝብ በመላ ባንድ ላይ ተሰበሰቡና ከመካከላቸውም ቅን የነበሩትን ሁሉ ጥቂት ሰዎች መረጡ፡፡ የተቀሩትን በተኑ፡፡ እኒያ የተመረጡትም ለብቻቸው ሆነው ምክር ያዙ፡፡ እጅግ በጣም የሚወዷትና የሚያከብሯት ንግሥታቸው ድንገት በጠና ስለታመመች፣ ሁላቸውም በማዘናቸው ልባቸው ተሰብሯል፡፡ በምክራቸውም ዘልቀው ንግሥታቸው ድንገት በጠና ስለታመመች ሁላቸውም በማዘናቸው ልባቸው ተሰብሯል፡፡ በምክራቸውም ዘልቀው ንግሥታቸውን በፍቱን መድኃኒት የሚያድንላቸውን ሰው ማፈላለግ ያዙ፡፡ በመጨረሻም ካዚሪዚ የተባለ የገነነ ስም ያለው የታወቀ መድኃኒት አዋቂ ሰውን አገኙ፡፡ ካዚሪዚን ንግሥቲቷን በመድኃኒቱ ይፈውሳት ዘንድ ወደ ቤተ መንግሥት አመጡት፡፡
ይህ ካዚሪዚ የተባለው መድኃኒት አዋቂ ሰው ከሀገር ውጪ እየተዘዋወረ በልዩ ልዩ ሀገራት መድኃኒት ይሰጥ ነበርና፣ በሀገሩ የሌሉ ብዙ ሁኔታዎችን በየጊዜው ሊመለከት ችሏል፡፡ በሥራው ምክንያት የተነሳ የየሀገሩን አንዳንድ ባለስልጣናትን መተዋወቅ ችሎ ስለነበረ ስለ ሀገሩ ልበ ጎዶሎ ሰው ሆኗል፡፡ ዛሬ ግን ንግሥቲትን ሊፈውስ ታዝዞ ቤተ መንግሥት ገብቷል፡፡ የህመሟን ዓይነት እየጠያየቃት ካጠገቧ ባለው ወንበር ላይ ተቀምጧል፡፡
“ንግሥት ሆይ!... ህመሙ እንዴት ነው የሚሰማሽ?” ብሎ ካዚሪዚ ሎማዲንን ጠየቃት፡፡
“ራሴን ይነድለኛል፡፡ ሰውነቴን ብዙ ቦታ ላይ ይቆረጣጥመኛል፡፡ ትኩሳቱ እንቅልፍ ነስቶኛል፣ ህመሙም ምግብ ከልክሎኛል…” አለችው፡፡
“ይኸው ነው?...ሌላስ የሚሰማሽ ነገር አለ?”
“ልቤን ይወጋኛል፡፡ ህመሙ ከፍቶ ነው መሰል የሠራ አካሌ ዝሏል”
“ጥሩ ነው፡፡ ህመምሽን ደርሼበታለሁ፡፡ ኒማክዶራቫ የሚባል ክፉ ደዌ አድሮብሻል፡፡ ፈዋሽ መድኃኒቱን በጥንቃቄ ቀምሜ ለማዘጋጀት አንድ ሳምንት ስለሚፈጅብኝ ትጠብቂኛለሽ፡፡ አይዞሽ አትፍሪ.. ትድኚያለሽ” በማለት ካፅናናት በኋላ፣ ከክፍሏ ወጥቶ ሄደ።
በሩ ላይ የንግሥቲቷ እልፍኝ አስከልካይ ይጠብቀው ኖሮ ህመሟ ምን እንደሆነ ጠየቀው፡፡ ካዚሪዚም ህመሟ ትንሽ ከበድ ያለ እንደሆነና ሊያድናት እንደሚሞክር ገለፀለት፡፡ አክሎም ከአንድ ሳምንት በኋላ መድኃኒቱን ይዞ እንደሚመለስ ነገረው፡፡
ከሾጎሎማንጎጭ ደሴት ከባህሩ ማዶ በቅርብ ርቀት የሚታይ አርኪሞጥ የሚባል ሀገር አለ፡፡ ይህ ሃገር ከሾጎሎማንጎጫውያን ምድር በብዙ ነገር ስለሚለይ የሚመሳሰሉበት የጋራ የሆነ ምንም ነገር አይታይባቸውም። አርኪሞጣውያን እኛ ከሌሎች ልቀን እጅግ ሰልጥነናል ብለው ራሳቸውን ስለሚገምቱ፣ የሌላው ሀገር ህዝብ ከእነሱ በታች ዝቅ ያለ እንደሆነ አድርገው ይገምታሉ፡፡ በዚህም ትዕቢት ከልባቸው ነው፡፡ ሀሰትና ተንኮል የተፈጠሩበት ድርና ማጋቸው ነው፡፡ ስስትና ፍቅረ ንዋይ ከደምና ሥጋቸው ተዋህዷል፡፡ አንዱ ሰው ከሌላው እንዲመስልና ተዋህዶ እንዲኖር አይወዱምና የረጋውን ማማሰል፣ ጅላጅሉን መደለል… የተጣበቀውን መላጥ፣ ውሃ ቅቤ እንዲያወጣ መናጥ… የዘወትር ሥራቸው ነው፡፡ በአንድ አጋጣሚ በህዝብ መካከል ከብዙ ዓመታት በፊት የተደረገን የስህተት አጋጣሚ፣ ዛሬ ላይ አምጥተው አዲስ ትኩስ ቁስል እንዲፈጠር ቀንና ሌት ይደክማሉ፡፡ ዓይናቸውም ከጥቅማቸው ውጪ ሊመለከት አይችልምና፣ የሌላውን ጉስቅልና እይ ቢባል ወዲያው ይታወርባቸዋል፡፡ አርኪሞጣውያን እንዲህና ከዚህም የባሱ ናቸው፡፡
መድኃኒተኛው ካዚሪዚ ስለ ሀገሩ ልበ ጎዶሎ የሆነበት ምክንያትም ከእነዚህ አርኪሞጣውያን ጋር የልብ ወዳጅነት ይዞ ስለነበር ነው፡፡ በገንዘብ ይደልሉታል፣ በቆነጃጅት ያማልሉታል፡፡ በህመም ፈዋሽነቱ ምክንያት ባገኘው ህዝባዊ ክብር ተጠቅሞ ተንኮላቸውን በራሱ ሀገር ህዝብ ውስጥ እንዲዘራ ይመክሩታል፡፡ ካዚሪዚም ቢሆን ልቡን ሰጥቶ ከገበረላቸው እነሆ ጊዜው ቆየ፡፡ ይኸው ዛሬ ደግሞ የራሱ ንግሥት የሆነችው ሎማዲን በመታመሟ ሊፈውሳት መድኃኒት ፍለጋ ብሎ አርኮሞጥ መጥቷል፡፡
የንግሥት ሎማዲን ህመም እያደር እየጠና መጣ። ህመሟን እንዲህ ነው የሚል በሾጎሎማንጎጭ ምድረ ማንም አዋቂ ነኝ ባይ ሰው አልተገኘም፡፡ በየዕለቱ እየደከመች መጣች፡፡ በዚህ መካከል መድኃኒተኛው ካዚሪዚ ከሄደበት ሀገር መድኃኒቱን ይዞ በድንገት ከተፍ አለ፡፡ የእሱን መምጣት የሰማው ሰው ሁሉ እጅጉን ተደሰተ፡፡ ወሬውም ባገሩ ሁሉ ናኘ፡፡
ህዝቡ ስለ ንግሥቲቷ በቶሎ መዳን ከመጓጓቱ ተነሳ ጆሮውን አቁሞ ለንፋሱ ሰጠ፡፡ ህዝቡ እንዲህ መሆኑ ሲያንሰው ነው፡፡ ህዝብን በአንድ ዓይን ተመልክቶ አድልዖ የማያደርግ መሪ እንደ ንግሥት ሎማዲን ዓይነት የት ማግኘት ይቻላል? ከራሱ ቤተሰብ ውላጆችና በዙሪያው ሸብ ረብ ከሚሉት አሽቃባጮቹ ባሻገር፣ ወደ ታች ወርዶ የህዝብን ረሃብና ጥማት ተረድቶ በቶሎ የሚያስወግድ ከሎማዲን በስተቀር ሀገር በጫጩት ቢታሰስ የት ይገኛል? ለሀገሩ ባህልና ታሪክ ክብር ያለው፣ ለሰንደቁና ለዳር ድንበሩ ሁሌም ዘብ የቆመ፣ በጥቅም ታውሮ ለባዕዳን የማይንበረከክ መሪ ሎማዲን ብቻ እንጂ፣ በዚያ አካባቢ ሌላ ወየት አለ? ዕቡያን ብቻ እንጂ ሎማዲንን በሴትነቷ ዝቅ አድርጎ የሚያያት ሰውስ ማነውሳ? እንጥስ! ሲል፣ ‘ይቀንጥስህ!’ በሚባሉ ብዙ የሀገር መሪዎች መካከል፣ ሾጎሎማንጎጫውያን ሎማዲንን የመሰለ ጥሩ መሪ በማግኘታቸው በእርግጥም ዕድለኞች ናቸው፡፡ ታዲያ ክፉዋን ማን ይመኛል? እንዲህ ያለውን ነገር ሾጎሎማንጎጫውያን መካከል ሆኖ ማሰብ ይቻላል ወይ? ለዚህም ነው ህዝቡ በመላ እንደ አንድ ሰው ሆኖ በህመሟ ሲጨነቅ የከረመ፡፡ የመልካም ሥራ ውጤቱ ደግሞ ይህ ነው፡፡
ንግሥት ሎማዲን በቀናው ሥራዋ ከፍ ከፍ አለች። በቅንነቷና በመልካምነቷ የህዝቧን ልብ ማረከች፡፡ እንደ ጧት ጤዛ ፈጥኖ በሚያልፈው ህይወቷ ለማያልፍ ስምና ክብር በቃች፡፡ አቤቱ ፈጣሪ!.. ሾጎሎማንጎጫውያን እንዴት ታድለዋል!? በአልኮል ብዥታና በምርቃና ሞቅታ ምናምኑን እየጫረ አስደንግጎ ከሚገዛ መሪ አምላካቸው ለወደፊቱ ይሰውራቸው እንጂ፣ ዛሬስ እንደ ሎማዲን ያለ ደግ መሪ አላቸው፡፡
*   *   *
ካዚሪዚ ቀምሞ ያመጣውን መድኃኒት ንግሥት ሎማዲንን አጠጣት፡፡ እንደምትድን ተስፋ ሞልቶባት በበነጋው ወደ አርኮሞጥ ምድር ተሻገረ፡፡ የአርኪሞጥ ንጉሥ የሆነው ሳንቶርቢ፣ ካዚሪዚን ከቤተ መንግሥቱ ተቀብሎ አስተናገደው፡፡ በምስጢር ሁለቱ ብቻ የዶለቱት ክፉ ነገር በመካከላቸው ስላለ በልቦቻቸው ተግባቡ፡፡ የአርኮሞጡ ንጉሥ ካዚሪዚን እንዲህ አለው፡፡
“ወዳጄ ሆይ!... የወሰድከውን መድኃኒት ንግሥት ሎማዲንን ይፈውሳት ዘንድ አጠጣሃትን?”
“አዎ!... በትክክል እንዲያ ነው ያደረግሁ” ብሎ፤ ለንጉሡ መልስ ሰጠ፡፡ ንጉሡም መልሶ፤
“ከዛሬ ጀምሮ የእኔና የአርኪሞጣውያን ወዳጅ ሆነሃል፡፡ በል ንሣና የታዘዘልህን ስጦታ ከግምጃ ቤቱ ዘንድ ሄደህ ውሰድ!” አለው፡፡
ካዚሪዚም እንደተባለው አደረገ፡፡ የሾጎሎማንጎጯ ንግሥት ሎማዲንም በማግሥቱ አረፈች፡፡
በሾጎላማንጎጭ ምድር ከባድ ሀዘን ደረሰ፡፡ ዋይታ ሆነ፡፡ ህዝቡ በመላ ማቅ ለበሰ፡፡ እሪታና ጩኸት ምድሪቱን ሞላት፡፡ እያንዳንዱ ሰው በማስመሰል ካንገቱ በላይ ሳይሆን ፍቅሯን አስቦና ልቡ ፈንቅሎት ተንሰቅስቆ እንባዎቹን አፈሰሰላት፡፡ የደጓ ንግሥት ሎማዲን ሞት መሪር ሀዘን ሆነ፡፡ ዜና እረፍቷ እንደተሰማም የየሀገሩ ሰው ሁሉ ወደ ሾማሎማንጎጭ ምድር ጎረፈ፡፡ ከቦታው ለመምጣት ንጉሥ ሳንቶርቢን የቀደመው አልነበረም። በጣም ብዙ ተከታዮቹን አስከትሎ ከሎማዲን ቤተ መንግሥት ገብቶ ሀዘን ተቀምጧል፡፡ ካዚሪዚም በድንጋጤ ክው ያለ በመምሰል ኩርምት ብሎ አንገቱን ደፍቷል፡፡
ካዚሪዚ ከተቀመጠበት ድንገት ብድግ አለና ልቅሶ ለተቀመጠው ሰው ሁሉ እንዲህ አለ፡-
“ያገሬ ሰዎች ሆይ! ዛሬ በደረሰብን ከፍተኛ ሀዘን በጣሙን አዝኛለሁ፡፡ ንግሥትን ለማዳን ሁነኛ መድኃኒት እስካገኝ ድረስ በየሀገሩ እየዋተትሁ ቆየሁ፡፡ በመካከሉ የንግሥት ደዌ ክፉ ነበርና፣ እኔ እስክመለስ ድረስ ደክማ ጠበቀችኝ፡፡ እየሰጋሁ ቢሆንም ሌላ ምርጫ ባለመኖሩ መድኃኒቱን ሰጠኋት፡፡ ተጎድታ ቆየችኝና ያመጣሁት መድኃኒት ሊሠራላት አልተቻለውም፡፡ እናም…” ብሎ፣ የሚናገረውን ሳይገታ ይነፈርቅ ገባ፡፡
ሎማዲንን በመርዝ እንደገደላት ሆዱ እያወቀ የአዞ እንባውን አፈሰሰ፡፡ ኃጢአቱን በሆዱ ቋጥሮ ይዞ ከህዝቡ ሊመሳሰል ቀበጣጠረ፡፡ “የመገበሪያ ስንዴ የበላ ያስፈልገዋል”… እንዲሉ ሆነበት፡፡
በዚያ ግርግርና የህዝቡ ልብ በሀዘን በተሰበረበት ወቅት፣ እነዚያ ንጉሥ ሳንቶርቢን ተከትለው የመጡት ሰዎች ማንም ሰው ልብ ባላለው መንገድ በሀገሪቱ ሁሉ ተበተኑ፡፡ ቀደም ብለው በሃገራቸው ሳሉ የሾጎሎማንጎጫውያን ምልክት የሆነውን     ቁጡ የነብር ምስል ሁላቸውም ከደረታቸው ላይ ተነቅሰው ኖሮ፣ ከሌላው የሀገሪቱ ዜጋ በጭራሽ መለየት አይቻልም ነበር፡፡ በፍጥነት ተመሳስለዋል፡፡ ውለው ሳያድሩ ንጉሣቸው ሳንቶርቢ ያዘዛቸውን ተግባር ሁሉ መከወን ተያያዙ፡፡
በጥንቃቄና በዘዴ መርዛቸውን መርጨት ጀመሩ። በየሰዉ ልብ ከጠፋ የቆየውን አዝሮድና ምርሻድ ይባል የነበረውን የሾላማንጎጫውያን ሥርወ የዘር ግንድ እያነሱ ልዩነታቸውን ማራገብ ጀመሩ፡፡ በዚህ ጉዳይ ያለ እረፍት ለሚያላዝኑ ቡችሎቻቸው ውስጥ ለውስጥ ብዙ ገንዘብ ይረጫሉ፡፡ “አንገተ ረጅም ማሽላ አንድም ለወፍ፣ አንድም ለወንጭፍ” እንዲሉ፣ ለምን? እንዴት? በማለት የሚሞግታቸውን ሰው በስውር ያጠፉታል፡፡ የእነሱን አስተሳሰብ የማይደግፍ ሰው ጠላታቸው ነው፡፡ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ስለ ሀገራቸው አርኪሞጥ ታላቅነት ይሰብካሉ፡፡ የሸቀጥ ዕቃዎቻቸውን በጀልባ እያጓጓዙ ሸጎሎማንጎጭ ምድር ያራግፋሉ፡፡ ዝሙት እንዲሰራጭ፣ ተንኮል እንዲስፋፋ፣ ባህልና ወግ እንዲጠፋ በብዙ ደከሙ፡፡ በዚህ ተግባራቸውም ሆድ አደሩን ሁላ አማልለው ብዙ ሰው ወደ እነሱ አመጡ፡፡ እንዲህ እየሆነ አያሌ ወራትና ዓመታት አለፉ፡፡ ህዝቡም እያደር ቀስ በቀስ በሃሳቡ እንዲለያይ ሆነ፡፡ ሾጎሎማንጎጭ የበፊቱ ዝናዋ እየወረደ ደበዘዘች፡፡ አርኪሞጣውያንም በውስጧ ሥር እየሰደዱ ሄዱ፡፡
እንዲህና ሌላም እየሆነ ጊዜው ሲደርስ፣ የአርኪሞጡ ንጉሥ ሳንቶርቢ ወታደሮቹን አዝዞ በብዙ ጀልባ ሆነው በመንፈስ ደክሞ ጫንቃው የጎበጠውን የሾጎሎማንጎጭን ህዝብ ወረሩ፡፡ ከህዝቡ መካከል አሻፈረኝ ያለው ባለ ወኔው ወራሪዎቹን ወጋ፡፡ ብዙ ነፍስም ጠፋ፡፡ በመጨረሻ ግን ንጉሥ ሳንቶርቢ ሀገሪቱን በሙሉ ያዘ፡፡ መድኃኒተኛው ካዚሪዚንም ኃላፊ አድርጎ በቤተ መንግሥቱ ላይ ሾመው።
በምዝበራው፣ በጭቆናውና በመከፋፈሉ ተንኮል ሁሉ የንጉሡ ሰዎች እጅግ አድርገው ሰለጠኑ። የሾጎሎማንጎጭ የሆነውን ውድ ዕቃዎች ሁሉ እየዘረፉ ወደ እናት ምድራቸው ወደ አርኪሞጥ አሻገሩ፡፡ አርኪሞጣውያን ስለ ሾጎሎማንጎጫውያን ከአባቶቻቸው የወረሱትን ጥላቻና ክፉ ነገር ሁሉ በምድሪቱ ላይ ዘሩ፡፡
የሾጎሎማንጎጭ ብዙ ወንዶች ያለ ባህላቸው የጉትቻ ጌጥ በጆሯቸው ላይ ማንጠልጠል ጀመሩ። ሴቶቹ ጨርቃቸውን አሳጥረው አካሎቻቸውን ገላለጡ፡፡ ወጣት ሾጎሎማንጎጫውያን የሀገር ፍቅር አድሮባቸው ወራሪዎቹ ላይ እንዳይነሱ በጥቅማ ጥቅምና በርካሽ ብልጭልጭ ነገሮች ማርከው መንፈሰ አልባ አደረጓቸው፡፡ ዕፀ ፋርስ በየሰዉ አፍና አፍንጫ ይጉተለተል ገባ፡፡ ህዝቡ ያለ ልማዱ የጎሪጥ መተያየት ጀመረ፡፡ ለምለሚቷ ምድር ጠወለገች። የምላስ አርበኛ እንጂ የተግባር ሰው ጠፋ። ሾጎሎማንጎጭ አንዳች ጉድ ወረደባት፡፡ ህዝቧም በባህር ላይ እየሆነ ወደ ሌላ ምድር ተሰደደ፡፡
በመንግሥታቸው ሞት ሾጎሎማንጎጫውያን በብዙ ተጎዱ፡፡ ይህን ሁሉ ጉድ ያመጣባቸው ከሃዲው ካዚሪዚ በምቾት ቢሆንም፣ የወገኖቹ ጉዳት እያደር ልቡን እያቆሰለው መጥቷል፡፡ ሰላምና እንቅልፍ አጣ፡፡ ወትሮስ ቢሆን ነፍስን ያስገዙለት ምቾትና የህዝብ ገንዘብ እያደር እንደ እሳት ለብልቦ በስተመጨረሻ አይሆኑ ነገር ያደርግ የለ!? አዎ!...
ካዚሪዚ የሆነው ከዚህብ በላይ ነው፡፡ የህዝቡ ጩኸት ጆሮውን ነደለው፡፡ እናም ከዚህ በላይ ከቶም መሸከም አልተቻለውም፡፡ ኑዛዜውን ጻፈና ከደረት ኪሱ ቆልፎበት ወደ አንድ ትልቅ ገደል ሄዶ ራሱን ወደታች ወረወረ፡፡
የኃጢአት ምንዳው ክፉ አሟሟት ነውና፣ ካዚሪዚ በዚህ መንገድ ከሲዖል የማያድነውን ንስሃውን ከፈለ፡፡ አንዲት ክፉ ነፍስ ብዙ ደጋግ ሰዎችን ይዛ ትጠፋለች፡፡ የሾጎሎማንጎጭ ምድርም በዙሪያዋ ወደ ከበባት የባህር ጠለል ዝቅ ዝቅ እያለች ነው፡፡ የምትመካበት የፈጣሪዋ ኃያል ክንድ ቶሎ ይታደጋት ዘንድ ግን እምነቷ ፅኑ ነው። ይህ ሊሆን ደግሞ ሾጎሎማንጎጫውያን ብርቱ ተስፋ አላቸው፡፡


Published in ልብ-ወለድ

የታዋቂው ድምጻዊ ቦብ ዳይላን አንድ የዘፈን ግጥም፣ ሰሞኑን ሱዝቤይ በተባለው አለማቀፍ አጫራች ኩባንያ አማካይነት ለጨረታ ቀርቦ 2 ሚሊዮን ዶላር በመሸጥ ክብረወሰን ማስመዝገቡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከቦብ ዳይላን ታዋቂ ስራዎች አንዱ የሆነው ‘ላይክ ኤ ሮሊንግ ስቶን’ የተባለው ዘፈን ግጥም፣ በራሱ በድምጻዊው የተጻፈ ሲሆን፣ በአራት ነጠላ ወረቀቶች ላይ በእርሳስ የተጻፈው የግጥሙ ኦሪጅናል ኮፒ ነው በጨረታው የተሸጠው፡፡
ቦብ ዳይላን የከፍተኛ መደብ አባላት በሚኖሩበት ማህበረሰብ ውስጥ የብቸኝነት ኑሮን በምትገፋ አንዲት ባይተዋር ሴት ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ይህን የዘፈን ግጥም፣ የ24 ዓመት ወጣት ሳለ ነበር እ.ኤ.አ በ1965ዓ.ም የጻፈው፡፡
የአጫራቹ ኩባንያ ባልደረባ የሆኑት ሪቻርድ ኦስቲን እንዳሉት፣ የቦብ ዳይላን ሥራዎች በዘመናዊው ሙዚቃ ጉዞ ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ያበረከቱና አቅጣጫ የቀየሩ ናቸው፡፡
ግጥሙን ለአጫራቹ ኩባንያ ያቀረበው ግለሰብ ማንነት ባይገለጽም፣ የድምጻዊው የረጅም ጊዜ አድናቂ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከዚህ በፊት ለጨረታ ቀርቦ በከፍተኛ ዋጋ በመሸጥ ክብረወሰኑን ይዞ የነበረው፣ እ.ኤ.አ በ1967 በታተመው ‘ሎንሊ ሃርትስ’ የተሰኘ አልበም ውስጥ የተካተተው የታዋቂው ድምጻዊ ጆን ሌነን ሙዚቃ፣ ‘ፎር ኤ ዴይ ኢን ዘ ላይፍ’ የተሰኘ ግጥም ነበር፡፡ ግጥሙ ከሶስት አመታት በፊት ለጨረታ ቀርቦ በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር መሸጡን ቢቢሲ አስታውሷል፡፡  

Published in ጥበብ
Saturday, 28 June 2014 11:49

የጸሐፍት ጥግ

(ስለ ሂስና ሃያስያን)
ሃያሲ ማለት መንገዱን የሚያውቅ ነገር ግን መኪና ማሽከርከር የማይችል ሰው ነው፡፡
ኬኔዝ ቲናን
(እንግሊዛዊ የትያትር ሃያሲ)
ፊልሞቼን የምሰራው ለህዝቡ እንጂ ለሃያስያን አይደለም፡፡
ሴሲል ቢ.ዲ.ሚሌ
(አሜሪካዊ የፊልም ፕሮዲዩሰርና ዳይሬክተር)
ነፍሳት የሚነክሱን ለመኖር ብለው እንጂ ሊጎዱን አስበው አይደለም፡፡ ሃያስያንም እንደዚያው ናቸው፤ ደማችንን እንጂ ስቃያችንን አይሹም፡፡
ፍሬድሪክ ዊልሄልም ኒቼ
(ጀርመናዊ ፈላስፋና ገጣሚ)
ሃያስያን ለሚሉት ነገር ትኩረት አትስጡ፡፡ ለሃያሲ ሃውልት ቆሞለት አያውቅም፡፡
ዣን ሲቤሊዩስ
(ፊንላንዳዊ የሙዚቃ ቀማሪ)
ሰዎች ሂስ እንድትሰጣቸው ይጠይቁሃል፤ የሚፈልጉት ግን ሙገሳ ብቻ ነው፡፡
ሶመርሴት ሟም
(እንግሊዛዊ ደራሲ)
ሃያሲ ህግ ሳይሆን አስተላላፊ፣ ድልድይ መሆን አለበት፡፡
ቶኒ ሞሪሶን
(አሜሪካዊ ደራሲ)
ጌታዬ፤ ዝንብ ትልቁን ፈረስ ልትነክሰውና ዓይኑን ልታርገበግበው ትችላለች፡፡ ይሄ ግን አንደኛቸው ነፍሳት፣ ሌላኛቸው ፈረስ መሆናቸውን አይለውጠውም፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
(ስለሃያስያን የተናገረው)
ሃያስያን እነማን እንደሆኑ ታውቃላችሁ? በሥነጽሑፍና በሥነጥበብ ዘርፍ ያልተሳካላቸው ሰዎች ናቸው፡፡
ቤንጃሚን ዲስራሊ
(የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትርና ፀሐፊ የነበሩ)
ሃያስያን የሚሉትን ብሰማቸው ኖሮ፣ በስካር ናውዤ የውሃ አሸንዳ ስር እሞት ነበር፡፡
አንቶን ቼኾቭ
(ሩሲያዊ ደራሲ)
ሽልማት የሚያሸንፉ ትያትሮች የሚፃፉት ለሃያስያን ብቻ ነው፡፡
ሊው ግሬድ
(ዩክሬን ተወላጅ እንግሊዛዊ
የፊልምና ቴሌቪዥን ፕሮዲዩሰር)

Published in ጥበብ
Saturday, 28 June 2014 11:41

ማራኪ አንቀፅ

…የኢትዮጵያ መንግሥት ጠቅላይ ሚኒስትር በትግራይ ክልል ርእሰ መስተዳድር ጽሕፈት ቤት፣ መቀሌ፣ ከረፋዱ 3፡30 ላይ፡፡
አሥራ አንዱም የትግራይ ሕዝብ ሐርነት ግንባር የፖሊት ቢሮ አባላት በርእሰ መስተዳድሩ ቢሮ ለአስቸኳይ ስብሰባ ተቀምጠዋል፡፡ የድርጅቱ ሊቀመንበርና የኢትዮጵያ መንግስት ጠቅላይ ሚኒስትር በሰብሳቢ ቦታቸው ተሰይመዋል፡፡ የፓርቲ ስብሰባዎች ላይ ሁልጊዜ እንደሚያደርጉት ቀለል ያሉ አልባሳትን ተጠቅመዋል፡፡ ነጣ ያለ ጉርድ ሸሚዝ፣ ቀለል ካለ ባለ ዚፕ ውሃ ሰማያዊ ጃኬት ጋር፡፡ አጠገባቸው ማንም አልነበረም፡፡
በትጥቅ ትግሉ ወቅት የተጐሳቆለ የፊታቸው ገጽታ ፍጹም መልኩን ቀይሮ ሞላ ብሎ ይታያል፣ ወትሮ ወደ ቢጫነት የሚያዘነብለው የፊት ቆዳቸው ጽድት ከማለቱ የተነሳ ራሰ - በረሃቸውን መስሏል። ከግንባራቸው አንስቶ በአገጫቸው ዙሪያ ክብ ሰርቶ የሚያልፈው ጠየም ያለ የፊት መስመር ፊታቸውን ፍሬም ውስጥ የተቀመጠ ውድ ፎቶ አስመስሎታል፡፡ ጠርዝ አልባ መነጽራቸውን ሰክተውም ቢሆን ቅልብልብ የሚሉት ዓይኖቻቸው አያርፉም፡፡ በአንድ ጊዜ ሺ ነፍስን የመቆጣጠር ተፈጥሮን የተቸሩ ናቸው፡፡ በሲጋራ ጢስ ጠይመው የነበሩ ትንንሽና ግጥምጥም ያሉ ጥርሶቻቸው እንደነገሩ ጸድተው እጭ መስለዋል፡፡ የዛሬው ስብሰባ የሲጋራ ፍጆታቸውን በሁለት አሀዝ የሚያስጨምር እንደሚሆን አላጡትም፡፡
የተወሰኑት የፖሊት ቢሮ አባላት የቢሮውን ግርግዳ ተከትለው መደዳውን በተደረደሩ ጥቁር የፕላስቲክ ሶፋ ወንበሮች ላይ ዘርዘር ብለው ተቀምጠዋል፡፡ ከፊሎቹ በተዘረጉ ማስታወሻ ደብተሮቻቸው ላይ አንዳች ነገር ይቸከችካሉ፡፡ የተቀሩት ፊታቸውን ወደ መድረኩ መልሰው ሊቀመንበሩ በትግርኛ ቋንቋ የሚናገሩትን በአንክሮ ይከታተላሉ፡፡ ሰብሳቢያቸው ተናግሮ ማሳመን ጥርሳቸውን የነቀሉበት ጥበብ ስለመሆኑ አይጠራጠሩም፡፡ በርሃ ሳሉ ጀምሮ ድንጋዩን ዳቦ ነው እያሉ ያሳምኗቸዋል፡፡ ዛሬ ያ እንዳይደገም የሰጉ ይመስል ጠቃሚ የሚሉት ነጥብ የተነገረ በመሰላቸው ቁጥር በማስታወሻቸው ያሰፍራሉ፡፡  የዕለቱ የመነጋገሪያ አጀንዳ “ኤርትራና የወረራ አደጋ” የሚል ነበር፡፡ ሊቀመንበሩ ባለሁለት ቀለም ገጽታ ካለው የፊታቸው ገጽ ላይ የሚታየውን ብርቱ መሰላቸት መደበቅ እንዳልቻሉ ሁኔታቸው በግልጽ ይናገራል…
“እኔ እስኪገባኝ ድረስ ማንኛውም ዓለም አቀፍ ጦርነት በአንድም ይሁን በሌላ መልኩ ፖለቲካዊ ምክንያት አለው…” ብለው ረገጥ አድርገው መናገር ቀጠሉ፤ እንደዚህ ረገጥ አድርገው መናገር ከጀመሩ ሰውየውን መርታት ዳገት እንደመግፋት ከባድ እንደሚሆን የሚያውቁት የትግል አጋሮቻቸው ማስታወሻ ደብተሮቻቸው ላይ ተደፍተው ይጫጭራሉ። “…ኤርትራ ኢትዮጵያን የምትወር ከሆነ የሕዝባዊ ግንባር መሪዎች ይህ ምክንያት ለእነሱም ያስፈልጋል፡፡ በኔ እምነት እነዚህ መሪዎች በሦስት አሳማኝ ምክንያቶች ኢትዮጵያን ለመውረር የሚያደፋፍር ግፊት ሊኖራቸው አይችልም፡፡ የመጀመሪያው ነጥብ ለሠላሳ ዓመታት ደም ያፋሰሳቸው የነፃነት ጥያቄ ለሁለተኛ ጦርነት መንስኤ የሚሆን አንድም ሽርፍራፊ ሰበብ ሳይተው መልስ አግኝቷል… እደግመዋለሁ፡፡ ቅንጣት ሽርፍራፊ ሰበብ ሳይተው መልስ አግኝቷል ይህ ለአሁኑ መሪዎች በመንግሥት ደረጃ ነፃና እኩል ሆነው የመደራደር ሉዓላዊ መብት አስገኝቶላቸዋል፡፡
አሁን ምናልባት የቀሩ ጥቃቅን ችግሮች ቢኖሩ ወይም ወደፊት ቢከሰቱ ይህንን ሉአላዊ ስልጣን ሊጠቀሙ ይችላሉ ብቻ ሳይሆን የተለየ ሌላ አማራጭም የላቸውም፡፡ ይህ አሁን መሬት ላይ ያለው እውነታ ነው። ይህን ግንዛቤ ከወሰድን ዘንዳ በዚህ መሐል ጦርነት ሊፈጠር የሚችለው አንድም በእብደት አልያም ደግሞ አዲስ ጦር መሣሪያ በጀብደኝነት ለመሞከር ከተፈለገ ብቻ ነው…”
ሊቀመንበሩ ዓይኖቻቸውን ተራ በተራ ከሚያይዋቸው ጓደኞቻቸው አንስተው ወደ ማስታወሻ ደብተራቸው የተከፈተ ገጽ መለሱ… ጠርዝ… አልባ መነጽራቸውን ሽቅብ ወደ አፍንጨቸው ገፋ አደረጉት፡፡
(“አውሮራ” ከተሰኘው የሀብታሙ አለባቸው ልቦለድ መፅሃፍ የተቀነጨበ)

Published in ማራኪ አንቀፅ
Page 1 of 18