“እንሾሽላ”፣ “ኬር ይሁን”፣ “የአሜሪካ ዲቪ”  በሚሉትና በሌሎች ተወዳጅ የጉራጊኛ ዘፈኖቹ የሚታወቀው ድምፃዊ ፈለቀ ማሩ፤ ላለፉት 10 ዓመታት በሙዚቃ ሙያ ቆይቷል፡፡ የሶዶ ጉራጌ ተወላጅ የሆነው ታዋቂው ድምፃዊ፤ ከሁለት ሳምንት በፊት ቤቱ ውስጥ በደረሰ ድንገተኛ የእሳት ቃጠሎ ሶስት ክፍል ቤቱን ጨምሮ ንብረቱ በሙሉ በእሳት የጋየ ሲሆን ሁለት ልጆቹንና ባለቤቱን ተዓምር በሚመስል ሁኔታ ለማትረፍ ችሏል፡፡ ወደ ግማሽ ሚሊዮን ብር የሚገመት ንብረቱን በቃጠሎው እንዳጣ የሚናገረው ድምፃዊ ፈለቀ፤ “እንደ አዲስ ጎጆ ወጪ ሆኛለሁ” ብሏል፡፡ ስለ እሳት አደጋው ፣  የቤተሰቡን ህይወት እንዴት እንዳተረፈና በሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከድምፃዊው ጋር አውግታለች፡፡

መቼና እንዴት ነበር የእሳት አደጋው የተከሰተው?
አደጋው የተከሰተው ከሁለት ሳምንት በፊት ነው፡፡ መንስኤው ኤሌክትሪክ ነው፡፡  ፍሪጁ ተሰክቶ ሳለ ማከፋፈያው ቀለጠ፡፡ እንዴት እንደሆነ አልገባኝም፡፡
ሌሊት ነው ወይስ ቀን?
ከሌሊቱ 9፡00 ሰዓት ነው ቃጠሎው የተነሳው። ከፍሪጁ አካባቢ ያለው መጋረጃ በእሳት ተያይዞ እሳቱ ወደ ሶፋው ደርሶ ነበር፡፡ በእንቅልፍ ልቤ የሆነ ነገር ይሸተኛል፤ ግን ሙሉ ለሙሉ አልነቃሁም ነበር። ሙሉ ለሙሉ የነቃሁት ሳሎኑ ከግማሽ በላይ ተያይዞ፣ ሶፋው ተቃጥሎ ካለቀ በኋላ ነው፡፡
ግን እንዴት ልትነቃ ቻልክ?
የሚገርምሽ ጭሱ አፍኖን አድክሞናል፤ በተለይ የሶፋው ስፖንጅ ሽታ እስካሁን በውስጤ አለ። በጣም የሚያስጠላ ሽታ ነበረው፡፡ ቤት ውስጥ ሁለት ልጆቼ፣ ባለቤቴና እኔ ነበርን፡፡ ባለቤቴ “ኧረ ፈሌ፤ የሆነ ነገር ይሸተኛል” ስትለኝ የእኔም ስሜት ስለነበር በደንብ ነቃሁ፡፡ ከመኝታ ቤት ወጥቼ ወደ ሳሎን ስሄድ፣ ሙሉ በሙሉ እየነደደ ነው፡፡ በጣም ደነገጥኩ፤ ባለሁበት ቆሜ ቀረሁ፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ አዕምሮዬን ማሰራት ጀመርኩኝ። ንብረቱ አንዴ ወድሟል ግን ልጆቼን እንዴት ላትርፍ የሚለውን ማሰብ ነበረብኝ፡፡ የለበስኩት ቱታ ነው፡፡ ደግነቱ ሻማ ቱታ አልነበረም እንጂ እላዬ ላይ ቀልጦ እኔም ሟች ነበርኩኝ፡፡ ከዚያ በእሳቱ መሃል አቋርጬ በመሄድ፣ ዋናውን በር ከፍቼ ወደ መኝታ ቤት መስኮት ሮጥኩኝ፡፡ ልጆቼን በመስኮት ለማውጣት፡፡
ወደ ውጭ ከምትወጣ ከመኝታ ቤት ወደ ውጭ ብታስወጣቸው አይቀልም ነበር?  ወይስ ድንጋጤው ይህን እንድታስብ እድል አልሰጠህም?
እንደሱ አስቤያለሁ ግን ግድግዳው ከመስኮቱ ሩቅ ስለሆነ፣ ውስጥ ሆኜ ወደ ውጭ ከወረወርኳቸው ሌላ አደጋ ይፈጠራል በሚል፣ ውጭ ሆኜ ባለቤቴ ቶሎ ቶሎ እንድታቀብለኝ ነው ያደረግሁት፡፡ እነሱን ካቀበለችኝ በኋላ እሷም እንደምንም በመስኮት ወጣች፡፡ ለንብረቱ አላሰብኩም፡፡ ዋናው ነገር ልጆቼና ባለቤቴን ማትረፍ ነበር፡፡
እግዚያብሔር ረድቶኛል፤ እነሱ ተርፈውልኛል። ሳሎኑ እየነደደ በር ለመክፈት ስወጣ፣ ግንባሬ ሁሉ ተለብልቦ ነበር (ግንባሩ ላይ እስካሁን ጠቁሮ የሚታይ የእሳት ግርፋት አለ)
የምትጠቀምባቸው ማከፋፈያዎች ይሆኑ እንዴ ለአደጋው መንስኤ የሆኑት?
የማከፋፈያው ችግር አይመስለኝም፡፡ ከዚህ በፊት ቲቪው እንደተሰካ መብራት ጠፋና ሲመጣ ኃይል ጨምሮ ስለነበር ቴሌቪዥኑ ተቃጠለ፡፡ ሌላ ጊዜ እንዲሁ ተንቀሳቃሽ ስልኬ ቻርጅ እየተደረገ ሳለ፣ መብራት ጠፍቶ ሲመጣ ተቃጠለ፡፡ ይሄኔ ቆይ ስታብላይዘር እገዛለሁ እያልኩ ሳስብ ነው ፍሪጁ በተሰካበት ይሄ አደጋ የተከሰተው፡፡
ምን ያህል ንብረት ወደመ?
ቤቱን ሳይጨምር የእኔ ንብረት ብቻ ወደ 500 ሺህ ብር የሚያወጣ ነው፡፡ የቤተሰቤ ልብስ ከለበስነው ፒጃማ ውጭ የባለቤቴ የወርቅ ጌጣ ጌጦች፣ ለመጠባበቂያ ብዬ ቤት ውስጥ ያስቀመጥኩት ገንዘብ፣ የቤት ቁሳቁስ፣ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች፣ ስልኮቻችን፣ ብቻ ከነፍሳችን በስተቀር የተረፈ የለም፡፡ ቤቱ ራሱ ሶስት ክፍል ቤት ነው፡፡ ምንም የቀረ የለም። መኪናዬና የባንዱ የሙዚቃ መሳሪያም የተረፉት ቤት ውስጥ ስላልነበሩ ነው፡፡ እግዚአብሔር በኪነ-ጥበቡ ቤተሰቤን አትርፎልኛል፡፡ የሚገርምሽ የልብስ ማጠቢያ ማሽንና ሌሎች ማሽኖች በረንዳ ላይ ነበሩ፤ እነሱን እንኳን ማዳን ይቻል ነበር። ድንጋጤ ስለነበር ያስታወሰ የለም፤ አብረው ወድመዋል፡፡
ቤቱ የራስህ ነው ወይስ ተከራይተህ?
ተከራይቼ ነው፡፡ ቤት አልሰራሁም፡፡ ቤቱ ከእነንብረቱ ሙሉ በሙሉ ነው የወደመው፡፡  ብዙ ጊዜ በርና መስኮቶች ከውስጥ መስታወት ሆነው ከውጭ በብረት ይበየዳሉ፡፡ የእኔም መስኮት በብረት የተበየደ ቢሆን ኖሮ ልጆቼና ሚስቴ ቤት ውስጥ ከንብረቱ ጋር አልቀው ነበር፡፡ አሁን ሳስበው ይዘገንነኛል፡፡ ምክንያቱም በዚያን ሰዓት ብረቱን ለመፈልቀቅ መሳሪያ ያስፈልጋል፡፡ እሳቱ ደግሞ ሳሎኑን ጨርሶ ወደ መኝታ ቤት እየተጠጋ ነበር፡፡ ብቻ ፈጣሪ ትረፉ ብሎን ነው እንጂ መጥፎ ሁኔታ ውስጥ ነበርን፡፡
ለእሳት አደጋ መከላከያ አልደወላችሁም ነበር?
ተደውሎላቸው መጥተዋል፤ ግን ዘግይተው ነው የመጡት፡፡ የእኔ ቤት ሙሉ ለሙሉ ወድሞ ወደ አከራዮቻችን ቤት ሊዛመት ሲል መጡ። የእኔን ማዳን ባይችሉም ወደ ሌላው ቤት እንዳይዛመት ለማድረግ ችለዋል፡፡
የራስህን ቤት አልሰራህም?
ምንም እንኳን 10 ዓመት በሙዚቃው ብቆይም ወደ ሙዚቃው በደንብ ዘልቄ የምገባበትን ሁኔታ ሳመቻች ነው የቆየሁት፡፡ ከአሁን በኋላ ነው ቤት ብሰራም፡፡ እስካሁን የሰራሁበት ለቤት መስሪያ የሚበቃ አይደለም፡፡ መኪና የገዛሁትም ከቤተሰብም ከምንም ብዬ ነው እንጂ ዘፍኜ አይደለም፡፡
አሁን እንደ አዲስ ጎጆ እየወጣሁ ነው ብለሃል። እንዴት ነው ወዳጅ ዘመድ ረዳህ?
“ሀ” ብዬ እቃ እየገዛሁ ነው፡፡ እንዳልኩሽ ከለበስነው ቢጃማ በስተቀር ምንም አልተረፈም። እስካሁን በውጭ የሚኖሩ የባለቤቴ እህቶችና ቤተሰቦች ድጋፍ እያደረጉልን ነው፡፡ አሁን ሌላ ቤት ተከራይቼ ኑሮን እንደ አዲስ እየጀመርኩኝ ነው፡፡
አከራዮችህ ቤታቸው በመውደሙ ምን አሉ?
አከራዮቼ በጣም የተባረኩ እንደቤተሰቤ የማያቸው መልካም ሰዎች ናቸው፡፡ እነሱ ጭራሽ ቤቱን አላሰቡትም፡፡ ያስደነገጣቸው የእኛ ጉዳይ ነው፡፡ እኛ በመትረፋችን ተፅናንተዋል፡፡ የቤቱ ጉዳይ ጭራሽ አልታሰባቸውም፡፡
በአሁኑ ሰዓት ምን እየሰራህ ነው?
ለጊዜው ነጠላ ዜማዎችን እየሰራሁ ነው፤ የሰራኋቸውም አሉ፡፡
ሙሉ አልበም ለመስራት አላሰብክም?
አላሰብኩም! ምክንቱም አዋጪ አይደለም። የቅጂ መብት ጉዳይ አሳሳቢ ነው፡፡ አንቺ ለፍተሸ ደክመሽ የሙዚቃ ቪዲዮ ሰርተሽ፣ ለግጥምና ዜማ ከፍለሽ፣ ለስቱዲዮ፣ ለተወዛዋዥ፣ ለካሜራና ኤዲቲንግ … ወጪ አውጥተሽ፣ ሰው በኢንተርኔት በብሉቱዝ ተቀባብሎት ቁጭ ይልና ድካምሽ መና ይቀራል፡፡ ይህ ሁኔታ ሳይስተካከል ሙሉ አልበም ለመስራት ፍላጎት የለኝም፡፡
ባይሆን ነጠላ ዜማው ላይ አተኩሬ እሰራለሁ። እስካሁን ሶስት አልበሞችን ሰርቻለሁ፤ በእነሱም ጥሩ ተቀባይነትና እውቅናን አትርፌያለሁ፡፡ በገንዘብ ብዙ ተጠቃሚ ባልሆንም፡፡
በመጨረሻ ምን ትላለህ?
 በዚህ አጋጣሚ በአደጋው ጊዜ ከጎኔ ሆነው ላበረታቱኝ፣ አሁንም ድረስ መልሼ እንድቋቋም ድጋፍ እያደረጉልኝ ላሉት የባለቤቴ እህቶችና ቤተሰቦች፣ እንዲሁም ለእኔም ቤተሰቦችና መልካም ባህሪ ላላቸው አከራዮቼ በሙሉ ከፍ ያለ ምስጋና አቀርባለሁ፡፡

Published in ጥበብ
Wednesday, 30 July 2014 07:56

ዲያብሎስ

       መርካቶ - ሲዳሞ ተራ፡፡ የቀለጠው ሠፈር። የማይታይ ዘረ - ሰብ የለም፡፡ እዚህ ሌላ ቋንቋ፣ ዘወር ሲሉ ሌላ፡፡ የማይሰማ የቋንቋ አይነት የለም። የተደበላለቀ ቋንቋ - የባቢሎን ግንብ፡፡ ሁሉም ጥድፊያ ላይ ነው፡፡ ደላላው ተካልቦ እያካለበኝ ወደ ቴፒ ለመሄድ ሸቀጥ የጫነች አይሱዙ ላይ አሳፈረኝ። ወደ 10 ሰዓት ገደማ ጉዞ ጀመርን - ወደ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ቴፒ፡፡
…12 ሰዓት ወሊሶ ደረስን፡፡ በስንብት ላይ ያለችው ጀንበር ወርቃማ ጨረሮቿን ፈንጥቃ -  የአድማሳቱን ከንፈር ስማ ጠለቀች፡፡
ወልቂጤን አልፈን…ወደ ጊቤ በረሃ እየተቃረብን ነው፡፡ ሹፌሩ የጊቤ በረሐ ዘራፊዎችን ከሰብአዊ ፍጡራን አውጥቶ ደም የጠማቸው አውሬ አድርጐ ይስላቸው ገባ፡፡ … “የመዘዙት ሰይፍ በቀላሉ ወደ አፎቱ አይመለስም - መቀንጠስ አለበት! ያው የሰው አንገት መሆኑ ነው…ደም መፍሰስ አለበት - ለበረሐው ዛር!”
ጥግ የተቀመጠው ረዳት ስለ ዛር ሲሰማ፣ እንደመንዘፍዘፍ አደረገው፡፡ ሹፌሩ ረዳቱን ሰረቅ አድርጐ እያየ “አሁንም ከዚያ መሠረተ ቢስ ፍርሐትህ አልወጣህም…በፍፁም ያየኸው ነገር የለም - አእምሮህ የፈጠረው ነው…”
“በዐይኔ በብረቱ ያየሁትንማ አልክድም” ረዳቱ ቅዝዝ ብሎ መለሰለት፡፡
ስለምን እንደሚያወሩ እንቆቅልሽ ሆነብኝ፡፡ ሹፌሩ ወደ እኔ ዘወር እያለ “ምን መሰለህ ከሦስት ቀን በፊት ከጅማ ወደ አዲስ አበባ ስንመጣ… አጅሬ ጊቤ በረሃ መሐል ሰይጣንን አየሁኝ ነው የሚለው…ለማመን የሚከብድ እኮ ነው”
ረዳቱ ቀበል አድርጐ “አዎን አይቼዋለሁ! ዲያብሎስን…በረዣዥም ጥፍሮቹ ጨበሬውን እያከከ…አይኖቹን እያሽከረከረ … ቀንዶቹን ዚግዛግ እየመታ…”
ከፊት ስትሄድ የነበረችው ጃጓር ሚኒባስ በድንገት ቀጥ ብላ ቆመች፡፡ ሁለት ጊዜ ክላክስ አሰማች፡፡ የእኛው ሹፌር “ሠላም ነው - እኛም ለሽንት” ብሎ ወረደ፡፡ እኔም ተከተልኩት፡፡ ከምሽቱ 5 ሰዓት። ከዋክብት በጥቁሩ ሰማይ እንደአሸዋ ፈሰዋል፡፡ አቤት ጨረቃዋ… ድምቀቷ፤ ምትሀቷ። ንጽህት፡፡ ፅርህት፡፡ አስፓልቱ ጠርዝ ላይ ቆሜ፣ አይኖቼን ወደ ገደሉ ላኩኝ፡፡ ጭው ያለ ድቅድቅ ጨለማ፡፡ ረዳቱ ሰይጣንን እዚህ መቀመቅ ይሆን ያየው? ቶሎ አይኔን ነቀልኩ፡፡ በዚህ ሰዓት ሰይጣንን ለማየት አንዳችም ፍላጐት የለኝም፡፡ የራሴ ጅል ሐሳብ እያሳቀኝ ወደ አይሱዚዋ ገባሁ፡፡ ጉዞአችንን ቀጠልን…ሹፌሩና ረዳቱ እየተቀባበሉ የሚናገሩትን መስማቱ ጆሮን ያግላል፡፡ …ስለ ጥልቁ የመናፍስት ዓለም፡፡ ስለበረሐው የዛር ውላጅ፡፡ ጊቢ ወንዝ ስለሚተፋቸው ሬሳዎች፡፡ ሴቷ ሰይጣን፡፡ የሰይጣን የጡት ልጅ፡፡…
የሚያወሩት ነገር ከእውነታው የራቀ ቢሆንም በዚያ ፅልመት መስማቱ ያንቀጠቅጣል፡፡
የተፈጠረ አንዳችም ነገር አልነበረም፡፡ ጊቤን ለቀን ወጣን፡፡ ጅማ በውድቀት ሌሊት ገባን፡፡ ከቦንጋ ስንወጣ ሌሊቱ እያከተመ፣ ከዋክብቱ ደብዘዝ እያሉ ወርቃማ የብርሐን አምዶች ተሰትረው - ጐህ ቀደደ፡፡
በሰፊው የተንጣለለው ደን ምትሐታዊ ውበት ተጐናጽፏል፡፡ የመላው ኢትዮጵያ እንጥፍጣፊ ድንግል ደን እዚች ምድር ግብአተ መሬቱን ሊፈጽም የተሰበሰበ ይመስላል፡፡
በሐይል ይዘንብ ጀመር፡፡ ዶፍ ወረደ፡፡ አስፈሪ ቁጡ! የመብረቅ ብልጭታዎች እንደ ሰይፍ ብልጭ ብለው ድርግም!! ግም!! ሹፌሩ አይሱዙዋን ጥግ አስይዞ አቆማት፡፡ የዝናቡ ውርጅብኝ፣ የነጐድጓዱ ብርቅርቅታ፣ እንደ ምጽአት ቀን ሰማይ ምድር ተደበላለቀ፡፡
ዝናቡ በመጠኑ ጋብ አለ፡፡ አይሱዙዋ በቆመችበት ጭቃው እንደማስቲሽ አጣብቆ አለቅ አላት፡፡ ሹፌሩ ማርሽ እየለዋወጠ ቢላት ቢሠራት አንድ ጋት ፈቅ ማለት አልቻለችም፡፡
ወጠምሻው ረዳት መኪናዋን ሊገፋ ወረደ፡፡ አንድ! ሁለት! ሦስት! ፎርሳ!...አይሱዚዋ ከገባችበት የጭቃ አረንቋ ወጣች፡፡ ወደፊት 100 ሜትር የሚሆን ሄዳ ቆመች፡፡ ረዳቱን ብንጠብቀው አልመጣም። ከመኪናዋ ወረድን፡፡ ዝናብ አርግዘው የነበሩ ደመናዎች ሰማዩን እርቃኑን ትተው ብን ብለዋል፡፡ እላይ ታች ሽቅብ ቁልቁል ባተልን፤ ረዳቱን ማግኘት አልቻልንም፡፡ ሹፌሩ የረዳቱን ስም እያምባረቀ ቢጠራም ምላሽ አልተገኘም፡፡ ከጥቅጥቅ ደኑ የሚሰማው የገደል ማሚቴ ልብን በፍርሃት ያርዳል። አንድ ሁለት መኪናዎች ምንም ሳይጠይቁን አልፈውን ሄዱ፡፡ ረዳቱ መኪናዋን የገፋባት ቦታ ላይ ቆምን፡፡ የከስክስ ጫማ አሻራው ጭቃው ላይ ታትሟል፡፡ የተሰነጣጠቀው መሬት ላይ አፈጠጥኩ። ምን አልባት በዚያ ስንጥቅ፣ ምድር ውጣው ይሆን? በሚል፡፡ እምጥ ይግባ ስምጥ አልታወቀም፡፡ እንደ እንፋሎት አየር ላይ በነነ? ወይስ ተነነ? “እንደ ኤልያስ በእሳት ሠረገላ ወደ ሰማይ አርጐ ይሆን?” በሚል ወደ ሰማይ ቀና አልኩኝ፡፡ አይኖቼ ብዙም ሳያማትሩ ከአንድ ረጅም ዛፍ ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ ምንድን ነው የማየው?! ህልም ነው ወይንስ ቅዠት?ደንዝዤ ቀረሁ፡፡ በግዙፍ ዛፍ ግንድ ላይ የተጠመጠመ ዘንዶ!! አፉ ላይ ጥንድ ከስክስ ጫማዎች፡፡
ሹፌሩ ያየው ነገር ምትሀት ሆኖበት ጭቃው ላይ እንደታረደ ዶሮ እየተንደፋደፈ “እሪ!” ብሎ እየጮኸ ነበር፡፡ ከሰመመን እንደነቃ ሰው ፍዝዝ…ድንግዝ ብዬ ዳግም አይኖቼን ወደ ዛፉ…ዘንዶው የለም! በደመነፍስ በርግጌ ሹፌሩን ከጭቃው ላይ ጐትቼ እየተፍገመገምን…የህልም በሚመስል ሩጫ አይሱዙዋ ውስጥ ገባን፡፡
ሹፌሩ እንባው ኮለል ብሎ እየወረደ “ከሦስት ቀን በፊት መልአከ ሞትን አይቶት ነበር” አለ፡፡ “ማንን?”
“ዘንዶውን…”
“ማንን እያልከኝ ነው?” ከድንዛዜዬ ሳልወጣ፡፡
“ራሱን - ሰይጣንን!!” ሹፌሩ አንባረቀብኝ፡፡  

Published in ልብ-ወለድ
Wednesday, 30 July 2014 07:56

ሌላው ጦርነት

“ሃሎ?! ኮሎኔል ሙሳ ነኝ! ማን ልበል?”
“ሃሎ! ጓድ ኮሎኔል…ይቅርታ! ከሆቴሉ እንግዳ መቀበያ ክፍል ነው!”
“ለምንድነው ከእንቅልፌ የምትቀሰቅሱኝ?! ለራሴ የበላሁት ምሳ አልፈጭ ብሎኝ መከራዬን ያሳየኛል! ከጓድ ሊቀመንበሩ ቢሮ በስተቀር ከየትም ቢደወል እንዳትቀሰቅሱኝ አላልኩም?!”
“ይቅርታ ጓድ ኮሎኔል! አንዲት ባልቴት እዚህ ሆቴሉ በር ላይ ቆመዋል…እናቱ ነኝ ይላሉ!”
“የማን እናት?”
“የእርስዎ መሰለኝ…በጦርነቱ ተፈናቅዬ ከምስራቅ ጦር ግንባር ነው የመጣሁት ይላሉ ጓድ ጌታዬ!”
“ለመሆኑ ማን እባላለሁ አለች?”
“በላይነሽ እባላለሁ ይላሉ ጓድ ኮሎኔል! የእርስዎ ወላጅ እናት ነኝ ይላሉ…”
“ልትሆን ትችላለች…ማነው ያለሁበትን ያሳያት ግን? እኔ እናት አገርና አብዮት እንጂ ሌላ እናት አላውቅም!”
“ምን ልበላቸው ታዲያ ጓድ ኮሎኔል?”
“በቃ አላውቃትም አልኳችሁኮ! እናቴ ብትሆን ባትሆንም ግድ የለኝም! ማነው ግን ያለሁበትን ቦታ ያሳያት? ይሄ የአናርኪስቶች ሴራ መሆን አለበት!”
“ማን እንዳሳያቸው አይታወቅም ጓድ ኮሎኔል!”
“አስር ብር ስጧትና እንደዚህ የሚባል ሰው እዚህ የለም ብላችሁ ሸኟት! ይልቁኑ ያቺን የማታዋን ቆንጅዬ ልጅ የሆቴል ታክሲ ልካችሁ አሁኑኑ አስመጡልኝ! እዚህ ሌላ ጦርነት ውስጥ ነው ያለሁት! ይገባችኋል?”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! በደንብ ይገባናል!”
“አልገባ ካላችሁ ደግሞ መጥቼ በሚገባችሁ ቋንቋ አነጋግራችኋለሁ!! አናርኪስት ሁላ! ልክ ነው የማስገባሽ!”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! ልጅቷን አሁኑኑ እናስመጣታለን!”
“በጓድ ሊቀመንበርና በአብዮቱ ቀልድ የለም! ይገባችኋል?”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! በደንብ ይገባናል!”
(ከደራሲ ሙሉጌታ ጉደታ “ያልተሸነፈው”
የአጭር ልብወለድ መድበል የተወሰደ፡፡
ሰኔ 2006 ዓ.ም)

Published in ልብ-ወለድ
Wednesday, 30 July 2014 07:54

ብረር ብረር አለኝ

       ናፍቆት ደጋግማ ስትመጣ ደጋግሜ የለም አስባልኩ፡፡ ጋሎይስን ለሦስተኛ ጊዜ ማንበቤ ነው። አንዳንዴ መንገዱ መንገዴ ይመስለኛል፡፡ ሌላ ጊዜ በእልሁ ከእኔ ይልቅ አሰፋ ጢሪሪን ወይም ንዳዴን መስሎ ይታየኛል፡፡
መኝታ ክፍሌ ተዘግቶ ማንበብ ስለሰለቸኝ ወጥቼ ካክስቴ ቤት ሥር የቱሪማንቱሪ ቅጠል አንጥፌ ተቀመጥኩ፡፡ መጽሐፉ የተዘጋጀው ለመኝታ ቤት ውስጥ ይመስላል፡፡ ሌላ ቦታ ለማንበብ አይመችም። በደረት አልጋ ላይ ተንበልብሎ በግራ በኩል መጽሐፉን፣ በቀኝ በኩል መዝገበ ቃላቱን አድርጐ በብዙ ማስታወሻ ወረቀቶች ተከብቦ ሲነበብ የበለጠ ይገባል፡፡ ግን ሰለቸኝ፡፡
ልዑል መውደቂያ ዘወትር ጭር እንዳለች ነው። አሁን ግን አንድ ናዝሬት ሚሽን የሚማር ልጅ ለክረምት ዕረፍት ወላጆቹ ጋ መጥቶ ይረብሻታል። ግራር ላይ ወይም የቱሪማንቱሪ ጫፍ ላይ ወጥቶ የተለያዩ ዘፈኖችን በረጅሙ ይለቅቃል፡፡ አሁንም አለ። የት እንደሆነ ግን ላየው አልቻልኩም፡፡ ዘፈኑ ብቻ እየመጣ ከጆሮዬ ጋር ይላጋል፡፡
“ልቤ ቢቀርበት ምነው
ልቤ ቢቀርበት ምነው
ምኞት እኮ ህልም ነው፡፡”
አባቴ በልጅነቱ ይኼን ልጅ ሳይሆን አይቀርም ስል አሰብኩ፡፡ ዘፈኑን ማስታወስ ከማልፈልገው አባቴ መንጭቄ የምጥልበት ስፈልግ ጋሽ በረደድ ትዝ አሉኝ። አክስቴ ላይ ያላቸው ምኞት ህልም እንደሆነ ከዚህ ዘፈን ሊማሩ ይገባቸዋል፡፡ መኖሪያቸው ከአክስቴ ቤት መደዳ ጫፍ ላይ ነው፡፡ ቤታቸው በእኛ ቤት ላይ ምኞት ያለው ይመስል ከሰልፉ አፈንግጦ በመቆልመም በአንድ ዓይኑ ወደዚህ ይመለከታል፡፡ የጋሽ በረደድ ሚስት አጐንብሰው ወጥተው አጐንብሰው ይገባሉ፡፡ ኅይለኛ ናቸው፡፡ የባላቸው ማጋጣነት ወሬ ሲደርሳቸው፣ ወይም ደስ የማይል አዝማሚያ ባላቸው ላይ ሲመለከቱ ቱግ ይላሉ፡፡ ቱግታቸው ፈር የለቀቀ አይደለም፡፡ የባላቸውን አንቱታን አይዘነጉም፤ ግን ይሳደባሉ፡፡
“አንቱ ሸርሙጣ” ይላሉ በእጃቸው ጭብጥ ጀርባቸውን እየደቁ፡፡ “አንቱ ሸርሙጣ፣ አንቱ ሸርሙጣ፣ አንቱ ሸርሙጣ….”
እኔ ጋሽ በረደድ ላይ እስቃለሁ፡፡ ጋሽ በረደድ አይናደዱም፡፡ ለኔ ምላሽ የሰጡ ሳያስመስሉ፤
“አጤ ቴዎድሮስም የተቸነፉ በሚስታቸው ነው፡፡ ለሚስት መቸነፍ የጀግና ወጉ ነው…ምናምን” ይላሉ፡፡
የልዑል መውደቂያ አባወራዎች ጥቂት ናቸው። ግማሽ ክብ ቅርጽ ላይ በድጋሚ የሚጠመጠምባት ሌላ የቤት መቀነት አለ፡፡ እያንዳንዱ ቤት ፀሐይ እንዳይገባበት ደጃፉ ላይ ቱሪማንቱሪ ዛፍ ተተክሏል፡፡ የጋሽ ጥበቡ ቤት እነዚህ መደዳ ጫፍ ላይ ከጋሽ በረደድ ቤት አጠገብ ይገኛል፡፡ የጋሽ ጥበቡ ሚስት ሲበዛ ተፀያፊ ናቸው፡፡ ጋሽ ጥበቡ ከዓይጥ አደን ሲመለሱ፤
“እዛው፣ እዛው….” እያሉ ያንቋሽሿቸዋል፡፡ የአይጥ ማስገሪያቸውን ማዶ አስጥለው ሳሙናና ውኃ ያመጡላቸዋል፡፡ እየተነጫነጩ ዕቃ ሳያስነኩ እራሳቸው ያስታጥቧቸዋል፡፡ ይህን ስመለከት ምናልባትም ባልና ሚስቱ አብረው ማዕድ ከቆረሱ ብዙ ዓመታቸው ሳይሆን አይቀርም እላለሁ፡፡
“በኑሮ ላይ ተቸግሮ ሰው ሲጐዳ፣
መልኩን ጥሎት ገሸሽ ይላል እንደባዳ”
ልጁን እንደ ጥንብ አንሳ ከተንሿጠጠ እራሱ ጋር ግራሩ ላይ አየሁት፡፡ ሹል አፉን እየከፈተ ሲታይ የሚዘፍን ሳይሆን የሚያንቋርር ይመስላል፡፡
በዚህ መካከል ከየት እንደመጣች ያላየኋት ናፍቆት ፊቴ ተገተረች፡፡ ያለወትሮው እግሯ ንፁህ ሆኖ አየሁት፡፡ በስሱ ቅባት የተባበሰሰ ቢሆንም የሞዶ እንኩሮአማ አቧራ አላንዣበበበትም፡፡ በአየር ላይ ተንሳፋ ካልመጣች በቀር እንዲህ ንፁህ ሊሆን እንደማይችል የታመነ ነው፡፡ የእግሯ ጣቶች በሽብር ዓይንን እንዲያፈገፍግ ያስገድዳሉ፡፡  
(ከደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ
“የብርሃን ፈለጐች” የተቀነጨበ

Published in ማራኪ አንቀፅ

          ባለፈው ሳምንት ለንባብ የበቃው የደራሲ ሙሉጌታ ጉደታ “ያልተሸነፈው” የተሰኘ የአጭር ልብ ወለድ መድበል እየተሸጠ ነው፡፡ መድበሉ 15 ታሪኮችን የያዘ ሲሆን ከባለ አንድ ገጿ የአጭር አጭር ወግ (ሌላው ጦርነት) በስተቀር ሁሉም ዘለግ ያሉ እንደሆኑ ታውቋል።
ብዙ የሚፅፍ (ፕሮሊፊክ) ደራሲ እየተባለ የሚደነቀው ሙሉጌታ ጉደታ፤ እስካሁን 13 ያህል መፃህፍትን ለንባብ አብቅቷል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንድ የአጭር ልብወለድ መድበልና አንድ ረዥም ልብወለድ በእንግሊዝኛ የፃፈ ሲሆን የተቀሩት የአማርኛ አጭር ልብወለዶች መድበሎች ናቸው። የደራሲው አጫጭር ልብወለዶች በጣሊያንኛ፣ በሂብሩና በእንግሊዝኛ መተርጎማቸውን ከአዲሱ መፅሃፉ ጀርባ ላይ ከሰፈሩት መረጃዎች ለማወቅ ተችሏል፡፡
“ያልተሸነፈነው” የአጭር ልብወለድ መድበል በ132 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በገጣሚ ትዕግስት ማሞ የተሰናዳው “የእምነት ወጎች” የተሰኘ የግጥም ስብስብ በሲዲ ተዘጋጅቶ ለገበያ የቀረበ ሲሆን ባለፈው ረቡዕ ምሽት በዋቢ ሸበሌ ሆቴል በድምቀት ተመርቋል፡፡
16 ግጥሞችን ያካተተው የግጥም ሲዲ በተመረቀበት ወቅት የቀድሞ መምህሯ ረዳት ፕ/ር ሙሉጌታ ጀዋሬ፣ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራና ሌሎች ገጣሚያንም ስራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በእለቱ ገጣሚ ትዕግስት ስራዎቿን ያቀረበች ሲሆን የታዳሚያን መግቢያ አንድ ሲዲ ነበር፡፡
በሲዲው ውስጥ ከተካተቱት 16 ግጥሞች መካከል “ትዝታና ፍቅር”፣ “ጋዜጠኛው”፣ “ይድረስ ለወንድሜ”፣ “ይማርሽ”፣ “አድዋ”፣ “ክፈለኝ” እና የሲዲው መጠሪያ የሆነው “የእምነት ወጎች” የሚገኙበት ሲሆን በግጥሞቹ ውስጥ ማህበራዊ ጉዳዮች በምፀትና በትዝብት ተዳስሰዋል፡፡ በ50 ብር እየተሸጠ ያለው የግጥም ሲዲው በአሁኑ ሰዓት ከጎጃም በረንዳ ወደ ዮሃንስ በሚወስደው መንገድ ላይ በሚገኘው “ግሬስ” ህንፃ ላይ እየተከፋፈለ ይገኛል፡፡

   “…ሕይወት የበጋውን ወራት ለማሳለፍ እምድር ውስጥ እንደተቀበረ ህያው እንቁራሪት በረጅሙ አንቀላፍታ ትገኛለች፡፡ በሌላው አገር የምትፍለቀለቀው የምትንቦለቦለው ህይወት እዚህ እፎይ ብላለች… ሁሉ ወግ ነው፡፡ ወግ በልማድ ታስሯል፡፡ ልማድ የሚጥስ የለም፡፡ ለመጣስ የሚያስብ እንኳን የለም፡፡ ወግና ልማድ በሜዳዎቹና በተራሮቹ ላይ እንደረጋው አቧራ… ረግተዋል፡፡ ተጋግረው… ጠጥረዋል፡፡…” (ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ፤ “አደፍርስ”)
የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት በየሣምንቱ ረቡዕ ምሽት ለ3 ዓመት ገደማ ለተመልካች ሲያቀርብ የቆየው “ሰው ለሰው” ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ መጠናቀቅ ነው ለዛሬው ጽሑፌ ምክንያት ሆነኝ፡፡ እንዳልኳችሁ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማው ባለፈው ረቡዕ በግድና በሐይል እንዲቋጭ ተደርጓል፡፡ ይህን ስል ግን ለድራማው ከፍተኛ ፍቅር ስለነበረኝና እንዲሁ እየተንዛዛ እንዲቀጥል ፈልጌ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ።
መላው የኢትዮጵያ ህዝብ “የሰው ለሰው” ተዋንያንን እንደ ቤተሰቡ አካል ቆጥሮ፣ ጊዜውን ሰውቶ፣ በከፍተኛ ፍቅር፣ አክብሮትና ትህትና ድራማውን ሲከታተል ቆይቷል፡፡ ይህም ህዝቡ ለጥበቡና ለሙያተኛው ያለውን ትልቅ ዋጋና ክብር የሚያሳይ ነው፡፡ ነገር ግን ድራማው በህዝቡ ቁመትና ፍላጐት ልክ በጭራሽ ሊቆም አልቻለም፡፡ በዚህ ጽሑፌ የማተኩረው በድራማው፣ በደራሲውና ድራማውን ባስተላለፈው የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ነው፡፡
ከ“ሰው ለሰው” ድራማ ህዝብ ምን አገኘ? የድራማው ፀሐፊና አዘጋጆች ፍላጐት፣ ህልም ምንድነው? የቴሌቪዥን ጣቢያው ኃላፊነቱ ለህዝቡ ነው ወይስ ለድራማው አዘጋጆች? እነዚህን ጥያቄዎችን በማንሳት ከድራማው ፍፃሜ ጋር እያነፃፀርን እንመልከት፡፡
የ“ሰው ለሰው” ተከታታይ ድራማ በቴሌቪዥን መታየት በጀመረበት ወቅት የአብዛኛውን ኢትዮጵያዊ ቀልብ መሳቡ የሚዘነጋ አይደለም፡፡ በዚያው ግን አልቀጠለም፤ እያደር መሔጃው  እንደጠፋበት ፈረስ መደናበር ጀመረ፡፡
የቴሌቪዥን ድራማ በባህሪው የህዝቦችን ማህበራዊ ንቃተ ህሊና ከፍ በማድረግ ትልቅ ሚና የሚጫወተውን ያህል የሰዎችን አእምሮ በማደንዘዝም አሉታዊ ተፅእኖ ያሳድራል፡፡ የአገራችን የቴሌቪዥን ተመልካች ከ “ሰው ለሰው” ምን አገኘ ብለን ብንጠይቅ፣ መልሱ ምንም ነው፡፡ በየሣምንቱ ወሬ ብቻ! በመግቢያዬ ላይ እንዳሰፈርኩት የዳኛቸው ወርቁ “አደፍርስ” ዛሬም ሁሉ ነገር እንደትላንቱ ነው፡፡
ሃቁን ለመናገር ከዚህ ድራማ ምንም አዲስ ነገር አላገኘንም፡፡ ደራሲው ከተደራሲያኑ ልቆ መታየት ይገባዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን በህዝቡና በከያኒው መካከል እምብዛም ልዩነት እንደሌለ የ“ሰው ለሰው” ድራማ ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል፡፡
በተለይ በሐገራችን በጐ ምግባርን፣ ሚዛናዊነትን፣ ግብረገብነትን፣ ችግሮችን በውይይት የመፍታት ባህልንና የስልጣኔ አስተሳሰብን በህብረተሰቡ ውስጥ ማስረፅና አመለካከቱን መቀየር ያለበት ከያኒው ነው - በጠንካራ የጥበብ ሥራዎቹ፡፡ ግን አልተሳካም፡፡ “ሰው ለሰው” ድራማ እንኳንስ እያዝናና ሊያስተምር ይቅርና በቅጡ የሚያዝናና የቴሌቪዥን ድራማ እንኳ ሊሆን አልቻለም፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ከዚህ ሣምንታዊ ድራማ ያገኘው፣ ያው እስከዛሬ በሀገራችን ውስጥ ጐልቶ የሚታየውን አሪስቶክራሲያዊ (በጉልበት፣ በአፈሙዝ) የሚገኝ የበላይነትን ወይም አሸናፊነትን ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ የዘመናት ባህላችን ሆኖ የቆየው የፊውዳል ሥርዓትና የጦርነት ታሪካችን ነው፡፡  
የኢትዮጵያ ህዝብ በጉጉት ሲከታተለው የቆየው የቴሌቪዥን ድራማ፤ የሰው ልጅን የሞራል ውድቀት እንጂ የሞራል ጥንካሬውን የሚያሳይ አይደለም፡፡ አንድ ሰው መራራና ፈታኝ ሁኔታዎች ሲገጥሙት ለሐቅ ሲል የሚወስደውን ትክክለኛ ምርጫ ሊያሳየን አልቻለም፡፡ ከዚህ ይልቅ ሰዎች እውነትን በሃይል ለማሸነፍ ሲሞክሩ ያሳየናል፡፡ ህብረተሰቡ ጥበብና ብልሃት ያልታደለ፣ በፍትህና በሚዛናዊነት የማያምን፣ ለሐቅና መርህ ደንታ የሌለው፣ ለግላዊም ሆነ ለብሔራዊ ክብር ዋጋ የማይሰጥ ሆኖ ነው የተቀረፀው፡፡ ከድራማው የተማርነው ነገር ቢኖር፣ ከኋላቀርና ያረጀ አስተሳሰብ መውጣት እንደማይቻልና ዛሬም በትላንቱ ዓይነት ህይወት ውስጥ መዳከር ዕጣፈንታችን መሆኑን ብቻ ነው፡፡
ለመሆኑ የዚህ ድራማ ፀሐፊና አዘጋጆች ፍላጐት ምንድን ነው? በድራማቸው ውስጥ ለሚኖሩበት ማህበረሰብ ምን ራዕይ ሊያሳዩ ፈልገዋል?
አንዳንድ ችግኝ ተተክሎ ይፀድቃል፡፡ አብቦ ያፈራል፡፡ ሌላ ዘር ይተካል፡፡ ዘሩን ያበዛል፡፡ አንዳንድ ችግኝ ደግሞ ቢፀድቅም አብቦ አያፈራም፡፡ ሌላ ዘር አይተካም፡፡ ዘሩን አያበዛም፡፡ ለብቻው ደርቆ ይቀራል፡፡ “ሰው ለሰው” ድራማም አብቦ የማያፈራ፣ ዘሩን የማይተካ መሆኑን ደራሲውና አዘጋጆቹ በሚገባ አሳይተውናል፡፡
ከሁሉም ያልገባኝ የድራማው ቁንጮ የሆነውን በሁለት ቤተሰቦች ላይ የሚያተኩር ታሪክ እንዲህ በተሽመደመደ መልኩ መቋጨት ለምን እንደተፈለገ ነው፡፡ ፖለቲካዊም ሆነ ማህበራዊ ጠቀሜታው አልታየኝም፡፡
የ“ሰው ለሰው” ድራማ ፀሐፊና አዘጋጆች ዋና ዓላማቸው የነበረው በተቻለ መጠን የአብዛኛውን የቴሌቪዥን ተመልካች ስሜት በሚገዙ ድርጊቶች ላይ በማነጣጠር (ሳቅ፣ ፍርሃት፣ ውጥረት፣ ሽብር…) ጊዜያዊ ብጥስጣሽ ሃሳቦችን ማቀበል ነው። (በነገራችሁ ላይ በቴሌቪዥን ድራማው ላይ ለተሳተፉት ተዋንያን ትልቅ አክብሮት አለኝ፡፡ ሁሉም ጥሩ የትወና ብቃታቸውን አሳይተዋልና፡፡)
የደራሲው ፍላጐት ዛሬም ህይወት ለውጥ እንደሌላት፣ እንደትላንቱ መሆኗን ማሳየት ይመስላል። ለዚህም ነው ለችግሮቻችን መፍትሔው ጉልበት፣ ጠመንጃና ሌላውን መስዋዕት ማድረግ እንደሆነ በድራማው ላይ የተመለከትነው፡፡
በአጠቃላይ “ሰው ለሰው” ለኔ ትላንትን የሙጥኝ ያለ (ትናንትን ናፋቂ እንዲሉ)፣ አዲስ ህይወት፣ አዲስ ተስፋ፣ በጐ የአስተሳሰብ ባህልና የህግ የበላይነት የከሸፉበት እንዲሁም የሃይል ሥርዓት የሰፈነበት ማህበረሰብን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ድራማ ነው። ብዙ ተመልካቾች እንዳሉትም ኢቴቪና “ሰው ለሰው” በኢትዮጵያ ፍትህ እንደሌለ አሳይተውናል፡፡   
የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዛሬም በህዝብ ላይ እየቀለደ እንደሆነ “ሰው ለሰው” ድራማ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ ነገም እንዲሁ “ዝም ብላችሁ መርጬ የሰጠኋችሁን ድራማ ተመልከቱ” ማለቱን ይቀጥላል። የቴሌቪዥን ፕሮግራም ያለተፎካካሪ በሞኖፖል ይዞ ከሚመራ ጣቢያ ከዚህ በላይ መጠበቅ ተገቢ አይመስለኝም፡፡

Published in ጥበብ
Wednesday, 30 July 2014 07:47

የፍቅር ጥግ

የዳቦ ረሃብለ ከማጥፋት ይልቅ የፍቅር ረሃብ  ለማጥፋት የበለጠ ያስቸግራል፡፡
ማዘር ቴሬዛ
(ትውልደ አልባንያ ሮማኒያዊ ካቶሊክ መነኩሲት)
ፍቅርን እንደማጣት አስፈሪ ነገር የለም፡፡ ሞት ከዚህም ይከፋል የሚሉ ዋሽተዋል፡፡
ካውንቲ ኩሌን
(አሜሪካዊ ገጣሚ፣ ደራሲና ፀሃፌ ተውኔት)
ለማፍቀር ፅናት ያላቸው ሰዎች ለስቃይም ፅናት ሊኖራቸው ይገባል፡፡
አንቶኒ ትሮሎፔ
(እንግሊዛዊ ደራሲ)
ፍቅሬ፣ እውነቴን ነው ብላ ስትምልልኝ
እየዋሸችኝ እንደሆነ ባውቅም አምናታለሁ፡፡
ዊሊያም ሼክስፒር
(እንግሊዛዊ ባለቅኔና ፀሃፌ ተውኔት)
ሴት አታፈቅርም፤ አፍቃሪው ወንድ ነው፤ ሴቷ እሷ ተፈቃሪ ናት፡፡
ኦገስት ስትሪንድበርግ
(ስውዲናዊ ድራማ ፀሃፊ)
መድረክ ላይ ከ25ሺ የተለያዩ ሰዎች ፍቅራቸውን ይገልፁልኛል፡፡ የማታማታ ግን ለብቻ ወደ ቤቴ አዘግማለሁ፡፡
ጃስ ጆንሊን
(አሜሪካዊ የሮክ ሙዚቃ አቀንቃኝ)
ብቸኝነት ያለመፈለግ ስሜት በእጅጉ የከፋ ድህነት ነው፡፡
ማዘር ትሬዛ
(ትውልደ - አልባንያ ሮማኒያዊ ካቶሊክ መነኩሴ)
የሴት ምናብ በጣም ፈጣን ነው፡፡ በቅፅበት ከአድናቆት ወደ ፍቅር፣ ከፍቅር ወደ ጋብቻ ይዘላል፡፡
ጄን  አውስተን
(እንግሊዛዊት ደራሲ)
ጋብቻ ድንቅ ተቋም ነው፤ እኔ ግን ወደ ተቋሙ ለመግባት ዝግጁ አይደለሁም፡፡
ማ ዌስት
(አሜሪካዊ ተዋናይና ኮሜዲያን)
ባሎችና ሚስቶች እርስ በርስ የማይግባቡበት ምክንያት ፆታቸው የተለያየ በመሆኑ ነው፡፡
ዶሮቲ ዲክስ
(አሜሪካዊት ጋዜጠኛና ደራሲ)

Published in ጥበብ

የ“ሰው ለሰው” አጨራረስ ይህችን ምድር ገነት አስመሰላት”
የሰው ለሰው አጨራረስ የምንኖርባትን አለም “ገነት” አስመሰላት፡፡ የአስናቀ መሞት ወይም ከፎቅ ላይ መወርወር ሲያንሰው ነው፡፡ ግን የሌሎቹ ገፀባህሪያት ጅምር ታሪክ በደስታ መጠናቀቁ አስገርሞኛል፡፡
እናቶች በወሊድ በሚሞቱባት አገር መዲ ብትወልድ ልትሞት እንደምትችል እየተነገራት፣ የፍሬዘር ሚስት የጤና ችግር እያለባት፣ አዱኛ ያ ሁሉ መጭበርበር ደርሶበት… ሁሉም ድንገት መልክ መልክ ይዞ ሳይ፣ ሌላ ፕላኔት ላይ እንጂ  በምኖርበት ማህበረሰብ ውስጥ ያለ የገሃዱ ዓለም ነፀብራቅ አልመስልህ ብሎኛል፡፡ ወይ መዲ አሊያም የፍሬ ሚስት መሞት ነበረባቸው ባይ ነኝ፡፡
“አብነት” በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ
የቴአትሪካል አርት ተማሪ

የ“ሰው ለሰው” አጨራረስ የፍትህ ስርዓታችን የደከመ መሆኑን አሳይቶኛል”
አስናቀ ለሰራው ግፍና በደል ተይዞ ፍርድ ቤት ተገትሮ የሞት ፍርድ ቢፈረድበትና ያ ተፈፃሚ ሲሆን ብንመለከት ብዙ ትምህርት እናገኝ ነበር፡፡ አሁን ግን አጨራረሱ በዚህች አገር ላይ ያለው የፍትህ ስርዓት ደካማ መሆኑን ነው ከአጨራረሱ የተረዳሁት። ምክንያቱም የገደለችው በአስናቀ ግፍና በደል ስትለበለብ የነበረችው ወ/ሮ ማህሌት ናት፡፡ ሰዎች በአገራቸው የፍትህ ስርዓት ሳይተማመኑ ሲቀሩ ፍትህን በራሳቸው ለማግኘት ሲማስኑ ይታያል፡፡ የአስናቀና የማህሌት ገዳይና ሟችነትም የሚያሳየው ይህንኑ ነው፡፡ እኔ ደስ ይለኝ የነበረው አንድ ሌላ ሰው ሞቶ፣ አስናቀ በህይወት ቢያዝና በፍ/ቤት የእጁን ቢያገኝ ነበር፡፡
(አምባው) ጋዜጠኛ
“ያስደሰተኝ አስናቀ ከፎቅ የተወረወረበት ሲን አኒሜሽንና የመስፍን ከዊልቼር ላይ መነሳት ነው”
 “ሰው ለሰው”ን በጥሩ ሁኔታ ተከታትየዋለሁ። ቀደም ብሎ ማለቅ ነበረበት፤ በኋላ እየተንዛዛ መጥቷል፡፡ የአስናቀ አሟሟት ልጁ ባለበት መሆኑ አሳዝኖኛል፡፡ በዚህ መልኩ ይሆናል ብዬ አላሰብኩም ነበር፡፡  ከሰራው ግፍና በደል አንፃር ጥፍሩ እየተነቀለ፣ እንደ ዶሮ ብልት 12 አይደለም መቶ ቦታ ቢገነጣጠል አይበቃውም፡፡ ግን ፍትህ ባለበት አገር ፖሊስ ሊይዘው አጠገቡ እያለ በሌላ ሰው መገደሉ አላሳመነኝም፡፡ ከድራማው “ሰርፕራይዝ” ያደረገኝና ያልታሰበ የሆነብኝ የመስፍን ከዊልቸር ላይ ተስፈንጥሮ መነሳትና ሙሉ ጤነኛ ሆኖ ማየት ሲሆን፤ ከትዕይንቱ ደስ ያለኝ ደግሞ አስናቀ በሽጉጥ ተመትቶ ከፎቅ ወደ ምድር የተወረወረበት አኒሜሽን ነው፡፡ ይሄ ጥሩ ሙከራ ነው፤ ቀረፃው የተሳካ ነበር፡፡ በተረፈ ያን ያህል የሚያስደንቅ አጨራረስ አልነበረውም፡፡
ቅዱስ ከካዛንቺስ

“አጨራረሱ ብቻ ሳይሆን ድራማው ራሱ ደስ አይለኝም ነበር”
ድራማውን የተጀመረ ሰሞን እመለከተው ነበር በኋላ እየደበረኝ መጣ ለምን ብትይ ብዙ የማያሳምኑኝ ነገሮች ተበራከቱ፡፡ አንደኛ አሳማኝነት አጣሁበት ሁለተኛው እኔ ቀድሜ ያሰብኩት ነው የሚሆነው ድራማው በአጠቃላይ የዚህ አገር ፊልሞች አይነት ባህሪ አለው፡፡ ገና ሲጀመር መጨረሻውን የምታውቂው አይነት፡፡
አንድ መጽሔት ላይ ኢቴቪ ድራማውን በቶሎ ማጠናቀቅ ስላለባችሁ ሲኖብሲስ አስገቡ ተብለው አዘጋጆቹ አስናቀን በሽጉጥ እንገድለዋለን ብለው እንደነበርና የአስናቀን በሽጉጥ መሞት ኢቴቪ አልቀበልም ማለቱን ሰምቼ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁንም በሽጉጥ ነው የገደሉት፡፡ በጭራሽ መሆን አልነበረበትም፤ ለፍርድ መቅረብ ነበረበት። ድራማው ባልሆነ መልኩ እንደሚጠናቀቅ ስሜቴ ይነግረኝ ነበር፡፡
ነቢያት ምትኩ (ተዋናይት)
“የአስናቀ አሟሟት በፍፁም ተገቢ አይደለም”
ሞት ለክፉም ለደጉም አይቀርም፡፡ በደግነታቸው፣ በአገር አመራር ብቃታቸው በተለያዩ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጭነታቸው የተመሰገኑና ብቁ የሆኑ ሰዎች፣ በአልባሌ ሰዎች በሽጉጥ ተገድለዋል፡፡ እንደ ሃየሎም አርአያ አይነት ጀግኖች ባልሆኑ ሰዎች ተገድለዋል፡፡ አስናቀም ከእነዚህ እኩል እንደተገደለ ነው የማምነው፡፡ ያንን ሁሉ በደልና ግፍ ሰርቶ፣ ቤተሰብ በትኖ ለፍርድ መቅረብ ነበረበት፡፡ የሞት ፍርድ ተበይግበት ሲሞት አሊያም እድሜ ልክ እስራት ተበይኖበት እንደማንኛውም ወንጀለኛ ወህኒ ቢወርድ፣ እንደሱ ያሉ ክፉ ሰዎች ይማሩበት ነበር፡፡ ህዝቡም ፍትህ መኖሩን አምኖ ይቀበል ነበር በአጠቃላይ አጨራረሱ ችግር አለበት፡፡ ብዙ ነገሮች አልተቋጩም፡፡
ሐይማኖት ግርማ ነርስ እና
የሶሲዎሎጂ ተማሪ

“ድራማው ከሁለት ዓመት በፊት መጠናቀቅ ነበረበት”
አጨራረሱ አብዛኞቻችን አላረካንም፡፡ የአስናቀ አሟሟትም በዚህ መልኩ ይሆናል ብለን አላሰብንም። ድራማው በአብዛኛው የተጓዘው የስነ-ጥበብንና የስነ-ፅሁፍን መህ ተከትሎ አይደለም። ገቢ መሰብሰብ ላይ ስላተኮሩ እንኳን በባለሙያ ሙያውን በማያውቁትም  ሁሉ ተተችተዋል፡፡
አስናቀ በዚህ ክፋቱ ቀደም ብሎ መሞት ነበረበት። በአስናቀ ግፍ ስንት መከራና በደል የደረሰባትን ማህሌትን ወንጀለኛ አድርገው፣ ህይወቷን ሌላ ዝብርቅርቅ ውስጥ ከሚከትቱት አስናቀ በህይወት ተይዞ ለፍርድ ማቅረብ ተገቢ ነበር፡፡ አስናቀ አልሸነፍ ባይ ስለሆነ፣ ሌላ አደጋ ሳያደርስ ይገደል ቢባል እንኳን በፖሊሱ ቢገደል መልካም ነበር፡፡
በአጠቃላይ አጨራረሱ የይድረስ ይድረስ ሆነ እንጂ ከህግና ከፍትህ አንፃር ቢቋጭ ኖሮ አስተማሪነቱን የጎላ ያደርገው ነበር፡፡ የኢቴቪ ኃላፊዎችም ከፍትህና ከህግ አንፃር መቃኘትና  አስተማሪነቱ ማመዘን አለበት ብለዋቸው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡
ነገር ግን አዘጋጆቹ፤ “በእኛ ስራ ማንም ጣልቃ አይገባም፤ ነፃነት አለን” ብለው ያንን ነፃነታቸውን ለማሳየት ሲሉ በዚህ መልኩ መቋጨታቸውን ሁላችንም አልወደድነውም፡፡ እኛ በአጨራረሱና በአስናቀ ላይ አተኮርን እንጂ ድራማው ብዙ ችግሮች የነበሩበት ነው፡፡
ማለቅ የነበረበት ከሁለት ዓመት በፊት ነው ያልኩበት ምክንያት አላስፈላጊ ታሪኮች ተካትተዋል፣ ተደጋጋሚና አሰልቺ ታሪኮች ነበሩት። መቀጠል የነበረባቸው ታሪኮች በተጠበቀው መልኩ አልቀጠሉም፡፡ ጥሩ ታሪክ ይዘው ተነስተው በምን ምክንያት እንደሆነ ሳይታወቅ ውሃ የበላቸው ገፀባህሪያት አሉ፡፡ አሁን  ረስተናቸዋል፡፡ ይህን ሁሉ ስትመለከቺ ብዙ ችግሮች ያስተናገደ፣ እስካሁን መቀጠል ያልነበረበትና ገቢ መሰብሰብን ማዕከል አድርጎ፣ የስነ-ፅሁፍ ስነ-ምግባርን ያልተከተለ ነው ብዬ በድፍረት ለመናገር እችላለሁ፡፡ ለዚህ ነው ባለሙያዎች ብቻ ሳንሆን በሙያው ውስጥ እንኳን ያልሆኑ ተመልካቾች ትችት የሰነዘሩት፡፡
ታጠቅ ነጋሽ (የቴአትር ባለሙያ)

“የሞተ የሚነሳበት ድራማ መሆኑ አናዶኛል”
“ሰው ለሰው” ድራማ ህዝብ እንደማያውቅ፣ ምንም ማገናዘብ እንደማይችል ተደርጐ የተቆጠረበትና የተናቀበት ከመሆኑም በላይ የሞተ የሚነሳበት ድራማ መሆኑ አናዶኛል፡፡
መዲ፤ እናቷ እንድታስወርድ የሰጠቻት መድሃኒት፣ ደሟን አንጠፍጥፎ ዶክተሩም ሞተች ብሎ ጥሏት ከሄደ በኋላ ነፍስ ዘራች፡፡ ደራሲዎቹ እንደ ፈጣሪም ያደርጋቸዋል እንዴ? ድራማውን ለማራዘምና ገቢ ለመሰብሰብ ሲባል የማያሳምን ነገር መዘብዘብ፣ ህዝብን መናቅና አላዋቂ ማድረግ ነው፡፡ አጨራረሱም ቢሆን ዝብርቅርቁ የወጣና ብዙ ታሪኮች ያልተቋጩበት ነው፡፡ ለምሳሌ ወ/ሮ ማህሌት፣ የመዲን ወንድም አስከሬን በመኪና ወስዳ የጣለችበት ታሪክ ተድበስብሷል፡፡ ኧረ ምኑ ቅጡ! ተጫውተውብናል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ የስነ ጽሑፍና የቴአትር ባለሙያዎች እንዲሁም የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ አስተያየት ሰጥተውበት ወደፊት ለሚቀርቡ ድራማዎችም መማርያ መሆን አለበት፡፡ ታሪኩ በየጊዜው እየፃፈ የሚቀጥልና በደራሲዎቹ በጐ ፈቃድ የሚራዘም ሳይሆን ተሰርተው ተጠናቀው፣ ተገምግመውና ለህዝብ አዕምሮ የሚመጥኑ ሆነው መቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ የአስናቀ አሟሟት መንግስት በዚህች አገር ላይ እንደሌለ የሚያመላክት በመሆኑ አዝኛለሁ፡፡
መሰረት - ከካዛንቺስ

Published in ህብረተሰብ

አቶ ሀይለማርያም ወልዱ በቅርቡ “ህልፈተ አንጃ ወ ክሊክ ዘ ኢህአፓ” የሚል መፅሀፍ ለንባብ አብቅተዋል፡፡ ከመፅሀፉ ጋር በተያያዘ  የኢሕአሠ ቤዝ የነበረውን የኢሮብ ህዝብ አስመልክቶ ከአዲስ አድማስ ጋር ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡



ኢህአፓ አለሁ ነው የሚለው፤ አንተ በመጽሐፍህ “ህልፈት አንጃ ወ ክሊክ ዘ ኢሕአፓ” በማለት ሞቷል ትላለህ፡፡
ይህ የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡ አለሁ የሚለው ወገን መኖሩን ማሳየት መቻል አለበት፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ (ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ያለሁት) ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአፓ እንደ ድርጅት የለም ፣አመለካከቱ ራዕዩ አለ፡፡ የኢህአፓ ልጆች የታገሉለት ነገሮች በህገመንግስቱ ተረጋግጧል። አተገባበር ላይ “እንዴት ነው” ብትይኝ ሌላ ነገር ነው፡፡ በዚህ አይን ከታየ ኢህአፓ አለ፡፡ ከዚያ ውጪ ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአፓ እንደ ድርጅት የለም። ሜዳው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፤ ዳያስፖራ አለሁ ማለት የትም አያስኬድም፡፡
የበረሃ ስም እስኪለምዱት አይከብድም?
ምንም አይከብድም ግዴታ ነው፡፡ እኔን፤ ብርሃነመስቀል በዛብህ ነህ አለኝ፡፡ ተቀበልኩት። እሱን ክርስቲያን አካባቢ ሰለሞን፤ ሙስሊሞች አካባቢ ሱሌይማን እንለው ነበር፡፡
ከኢህአፓ ሠራዊት ከኢህአሠ የምታደንቀው የጦር መሪ ማን ነበር?
እኔ ጦርነት ላይ የመሳተፍ ዕድል አልነበረኝም፡፡ ሮባ ጥሩ ተዋጊ ነው ሲሉ ግን እሠማለሁ፡፡ ሠራዊቱ የምሁር ሠራዊት ነበር፡፡ ምሁር ሁለት ልብ ነው፤ ለጦርነት ምቹ አይደለም፡፡ እኔም ያው ነበርኩ፡፡
እስቲ ወልዱ ስለ ራስህ ንገረኝ
ትውልዴ ኢሮብ ነው፡፡ የተወለድኩት አሊቴና ነው፡፡  እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል የተማርኩት አዲግራት ነው፡፡ አዲስ አበባ በቀዳማዊ ሀይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ ለሁለት አመት ተምሬያለሁ፡፡ በደርግ ዘመን ወደ ትግል ገባሁ፡፡ የመጀመሪያዎቹ የትግል አመታት ጥሩ አልነበሩም፡፡
ለምን የመጀመሪያዎቹ የትግል አመቶች ጥሩ አልነበሩም?
በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው ደርግ እጅ ላይ የወደቅሁት፡፡ የድርጅቴን ስም አጋልጦ ላለመስጠት ራሴን ጀብሀ ነኝ አልኩ፡፡  የታሠርኩት አስመራ ውስጥ ስንበል የሚባል ቦታ ነበር፡፡ የተለመደው የደርግ ምርመራ ከተደረገብኝ በኋላ፣ ጉዳዬ ወደ ጦር ፍርድ ቤት ተላለፈ፡፡ በጦር  ፍርድ ቤት በመታየት ላይ እያለ  ወህኒ ቤት ሆኜ ጥሩ ነገሮችን አግኝቻለሁ።
ምን ጥሩ ነገር አገኙ?
በአጋጣሚ ከአዲስ አበባ የወህኒ ቤት አስተዳዳሪዎች ወደዚያ ሲመጡ የጠየቅሁት የመብት ጥያቄ (ት/ቤትና ላይብረሪ እንዲከፈት) ምላሽ በማግኘቱ፣ በእስረኞቹ ዘንድ ተቀባይነት እንዳገኝ አደረገኝ፡፡ ለእኔ የመጀመሪያ ሹመት ማለት ይቻላል። የእስረኞቹ ፀሐፊ ሆንኩ፡፡ ቋንቋ ተማርኩ፣ ብዙ መፃሕፍት አነበብኩ፡፡
ከመታሰሬ በፊት የነበረኝ የማርክሲዝም ዕውቀት ውሱን ነበር፡፡ ከታሠርኩ በኋላ ማርክሲዝም ሌኒኒዝም፣ ማኦይዝም ከዚያም አልፎ ስለ ፎኮይዝም፤ በደንብ በማንበቤ የቲዮሪ ትጥቅ አገኘሁ፡፡  ስለ ህቡዕ የፖለቲካ ድርጅት አሠራር በተግባር የተማርኩትም ወህኒ ቤት ነው፡፡ ከሁሉም ጋር በነበረኝ ግንኙነት የህዝባዊ ግንባር አይን ውስጥ ገባሁ፡፡ በተማርኩት መሠረትም የቤት ስራ ተሰጥቶኝ በብቃት ተወጥቻለሁ፡፡
የቤት ስራው ምን ነበር?
እስረኞችን ማስፈታት ነበር፡፡ ይሄን ያደረግሁት ከተራ ወታደር እስከ ሃላፊዎች ድረስ በድርጅት እንዲታቀፉ በማድረግ ነው፡፡ ኤርትራዊያኑን በኤርትራ ድርጅት ኢትዮጵያውያኑን በኢትዮጵያ ድርጅት፣ እንዲደራጁ በህዋስ ማዋቀር ነበር፡፡
ማን ነበር የመለመለህ?
አንዲት አዜብ የምትባል ልጅ ናት፡፡ አዲስ አበባ እንደምታውቀኝ ነግራኝ የመለመለችኝ፡፡ በኋላ ላይ ግን እሷን ያሠማራት ሰው አስመራ ውስጥ የታወቀ (ከ1966 እስከ 1983 ድረስ የፌዳይን መሪ የነበረ) ልጅ መሆኑን አወቅሁኝ፡፡ የበረሃ ስሙ ቫይናክ ይባላል፡፡
ቫይናክ በቅርብ በመኪና አደጋ ከሞቱት የኤርትራ ጀነራሎች አንዱ ነው አይደል?  ቫይናክ የተባለው ለምንድን ነው?
አዎ በቅርቡ ነው የሞተው፡፡ ቫይናክ ማለት የመድሃኒት ስም ነው፡፡ የራስ ምታት መድሃኒቶች ካፌኖል፣ ቫይናክ፣ አስፕሪን ናቸው፡፡ ቫይናክ እንግዲህ “አስቸጋሪውን የሚያስታግስ” ለማለት የወጣ ይመስለኛል፡፡
ኢሮብ የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሠራዊት (የኢህአፓ ወታደራዊ ክንፍ) ይንቀሳቀስበት የነበረ ቦታ ነው፡፡ እስቲ ስለአካባቢውና ስለህዝቡ ንገረኝ…
ስለ ህዝቡ ማንነት የተለያዩ አፈታሪኮች አሉ። በአብዛኛው ተቀባይነት ያገኘው፣ አሁን ያለው የኢሮብ ህዝብ ከደጋ አካባቢ  ከውቅሮ በስደት መጥቶ ነው የሚለው ነው፡፡  በኔ እይታ ግን  እዚያ የቆየ ነው የሚሉትን እጋራለሁ፡፡ ምክንያቱም ቋንቋው ከኩሽ ቋንቋዎች የሚመደበው ሳሆ ነው፡፡ ይህ ቋንቋ ከአፋርኛ ጋር ከቀበሌኛ ልዩነት በስተቀር ይግባባል። በምስራቋ አፍሪካ የህዝቦች እንቅስቃሴ ነበር፡፡ በዚህ ውስጥ ግን የሚንቀሳቀሰው ወገን እምነቱንም ሆነ ቋንቋውን አይለቅም፡፡ እኔ ራሴን እንደሳሆ ነው የምቆጥረው፡፡ በሀይማኖት እስከ አስራ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ሶስት ቤተክርስትያኖች ነበሩ፣ ህዝቡም ክርስትናን ተቀብሎ ነበር ይባላል፡፡ ነገር ግን የባህላዊ እምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ በየቦታው መስዋዕት የሚያደርጉባቸው ቦታዎች ነበሩ፡፡ ዝናብ ከጠፋ ላም ወይም  በሬ ስጋውን ትልቅ አምራ መጥቶ ሲወስደው መንፈስ ወሰደው ይህን የሚያሳይ እስከአሁን አሁንም ድረስ ህብረተሰቡ በዘፈኑ ላይ የሚያስገባው ሀረግ አለ፡፡ “አኸዬ ጉማይቶ” (“አሞራው ናና ውሰደው” ማለት ነው፡፡) ከዚያ ዝናብ ይመጣልናል ብለውም ያምናሉ፡፡
ቤተክርስቲያኖች አሉ ይባል እንጂ ቄሶች የሚመጡት ከጉንደጉንደ ነበር፡፡ ጉንዳጉንዲ ደቀ እስጢፋኖስ በመባል በሚታወቅ በ13ኛውና 14ኛው ክፍለዘመን አካባቢ በስራዬ የተጀመረ እንቅስቃሴ ውስጥ የነበሩ መነኮሳቶች የነበሩበት ነው፡፡ እንቅስቃሴው በመሪዎች ተወገዘና ተከታዮቹ ተገደሉ፡፡ ከሠራዬ ታቦታቸውን ይዘው ወደ ሽሬ መጡ፣ ወደ ጐንደር ሄዱ፤ ከዚያ ወደ ጐጃም፣ ወደ ሰሜን ሸዋ መጡ፡፡ ሰሜን ሸዋ ደብረብርሃን ላይ እንዲቃጠሉ ተደረጉ፡፡
ከዚያ ያመለጡት በወሎ አድርገው ትግራይ ገብተው ያረፉት ጉንደጉንደ ላይ ነው፡፡ ከደጋ ወደ ኢሮብ ተሰደደ የሚባለው ህዝብ ከዚህ ታቦት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ኢሮብ የሚለው ቃልም ከዚያ ጋር ይያዛል፡፡
እንዴት?
ቆላ ላይ አንድ እንግዳ ሲመጣ “እንደምን ዋላችሁ” ወይ “አመሻችሁ” ካለ፣ አባወራው አይወጣም። እዛው ሆኖ ግቡ ነው የሚለው፡፡ በሳሆ ኦሮባ ይባላል፡፡ ግቡ ማለት ነው፡፡ እኔ ያገኘሁት መረጃ እንደሚያሳየው፤ ታቦት ይዘው የመጡት ጉንዳጉንዳ እንደደረሱ ሰዎች ያገኙና “እዚህ ቤት” ሲሉ ኢሮባ አሏቸው፡፡ ለቀሩት ተከታዮቻቸው በፃፉት ደብዳቤ፤ “እኛን የተቀበሉን ህዝቦች አግኝተናል፤ ህዝቡም ኢሮብ ይባላል” ብለው ፃፉ የሚል ነው፡፡
ኢሕአሠን  እንዴት ነው የኢሮብ ህዝብ  ኦሮባ ያለው?
አንደኛው ከኢህአፓ መስራቾች አንዱ የሆነው ተስፋዬ ደበሳይ የአካባቢው ተወላጅ ነው፡፡ ተስፋዬን    ጨምሮ ብዙ የአካባቢው ተወላጆች አውሮፓ በተለይ ቫቲካን ነበሩ፡፡ ምክንያቱም ከኢሮብ ጐሳዎች አንዱ የሆነው ቡክናይተአረ የሚባለው  የካቶሊክ እምነት ተከታይ ስለሆነ የትምህርት እድል ይሰጣቸው ነበር።
የኢሕአሠን ትግል  ጐጃም  ለማድረግ ታስቦ ነበር፡፡ ነገር ግን ሱዳን በዚያን ወቅት አስተማማኝ ሀይል አልነበረም፡፡ ባሌም ታስቦ ነበር፡፡ ሶማሌያም አስተማማኝ አልነበረም፡፡ ሌላው ደግሞ አወሮፓ የነበሩ የኢሮብ ተወላጆች የተወሰኑት የኢህአፓ አባል ስለነበሩ ከህዝቡ ተቀባይነት ማግኘት ከባድ አይሆንም በሚል ይመስላል፡፡ ቦታው ለቀይ ባህርም ቅርብ ነው፡፡ አዱሊስ ቅርብ ነው፡፡ አሲምባ ተራራ ጫፍ ላይ የየመን ዋና ከተማ ትታያለች፡፡ ስንቅ ለማጓጓዝም አመቺነቱን በማየት፣ ጂኦግራፊውም ስትራቴጂካዊ ቦታ ላይ ስለሆነ ነው፡፡  
ህዝቡስ?
የኢሮብ ህዝብ አንድን ነገር ቶሎ አይቀበልም። ከተቀበለ ደግሞ ጽኑ ነው፡፡ እንዲቀበል ደግሞ የራሱን ሰው ይፈልጋል፡፡
የኢሮብ ህዝብ ዛሬ ላይ የኢሕአሠን ሠራዊት እንዴት ያስታውሰዋል?
የልጆቻችን ወንድሞች እና ጓደኞች እንደሆናችሁ ሰምተናል፡፡ እንደ ልጆቻችን እንቀበላችኋለን፡፡ ግን ከድታችሁን ለጠላት አጋልጣችሁን እንዳትሄዱ” ነበር ያሏቸው፡፡ አሁን ህዝቡን እንዴት ያዩታል ላልሽኝ፤ ኢሕአሠን በደንብ ነበር የተቀበሉት፡፡ ወደኋላ ግን በኔ እይታ  በጣም አዝነውበት ነበር፡፡
ለምን
ካዘኑባቸው ምክንያቶችም አንዱ፣ አንጃ ተብለው በተገደሉ ሰዎች ምክንያት ነው፡፡ አንጃ በሚል ተይዘው የነበሩትን ሰዎች አስመልክቶ የኢሮብ ህዝብ ሽማግሌ ልኳል፡፡ እነዚህን ልጆች እንዳትገድሉ ብሏል፡፡ በወቅቱ የፖሊት ቢሮ አባል የነበረው ዘርዑ ክህሸንም አይገደሉም ብሎ ቃል ገብቶላቸው ነበር። ግን ተገደሉ፡፡ ጨካኞች ናቸው አሉ፡፡ ሌላው ባልጠበቁት ሁኔታ ሲሸነፍ አዩት፡፡ ሀይል ነበረው ፣መሳሪያ ነበረው፡፡ ሠራዊት ነበረው ግን ተሸነፈ። አላማውን ሲያነሱ ግን እስከአሁን “ያ ሠራዊት” ይላሉ፡፡ ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል የተውጣጣ በመሆኑ ልዩ ነው፡፡ ስሜቱ የተዘበራረቀ ነው፡፡
መጽሐፍህ ላይ “ገበሬ የሀይል ሚዛን ወደሄደበት ፊቱን ያዞራል” ብለሀል፡፡ የኢሮብ ህዝብን ከዚህ አባባል ጋር በማገናኘት  አስረዳኝ?…
ይህ በሁሉም ገበሬ የሚታይ ነው፡፡  ኢሮብ አንደኛ ገበሬ አልነበረም፡፡ አርብቶ አደር ነበር። የጐሳ ትስስር ነው የነበረው፡፡ የኔ ወገን የሆነው ለኔ ሲል ለኔ ያደላል፤ ወደኋላ ግን ትክክለኛ የገበሬ ጥቅመኝነት አይቼበታለሁ፡፡ ሠራዊቱ አካባቢውን ለቆ ከወጣ በኋላ እኔ እዚያ ቆይቻለሁ፡፡ አጋፍጠው ሊሰጡኝ ባይፈልጉም ስጋት ግን አለባቸው፡፡ ብሄድላቸው ደስታቸው ነው፡፡ የገዛ ዘመዶቼ ከዚያ አካባቢ ብጠፋላቸው ደስ ይላቸው እንደነበር አውቃለሁ፡፡
ስለአባትህ ንገረኝ…
አባቴ በወቅቱ ዘመናዊ ትምህርት ከወሰዱት ውስጥ ነው፡፡
አባትህ ሽፍታ ነበሩ ይባላል ዕውነት ነው?
አዎን
የአካባቢው ዳኛም፣ አስተዳዳሪም፣ ፖሊስም ሁሉንም ነው፡፡ አባቴ በአካባቢው ተወዳጅ ነበር፡፡ በለቅሶም ሆነ በሠርግ ስሙ ይነሳል፡፡ ተስፋዬ ደበሳይ በእረፍት ጊዜው የሚውለው ከአባቴ ጋር ነበር፡፡ ብዙ የህግ እውቀት ከአባቴ እንዳገኘ ነግሮኛል፡፡ የትግል ሜዳ ላይ ከብርሃነመስቀል ጋር ሲያስተዋውቀኝ፣ አባቱ በህይወት ቢኖሩ ከኛ ጋር ይሠለፉ ነበር ብሎታል፡፡
በድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ መሠረት ለኤርትራ እንዲሰጡ የተወሰኑ የኢሮብ አካባቢዎችን አንተ እንዴት ነው የምታያቸው?
አባቴ በሀላፊነት ላይ በነበረ ጊዜ ትልቁ ራስምታቱ እሱ ነበር፡፡ በተለይ አይጋ የውጥረት ቦታ ነው፡፡ በደንብ ሳይካለል የቀረ ቦታ ነው፡፡
ኢሮብ በትግራይ በኩልና ኢሮብ በኤርትራ መሠረታቸው አንድ ነው?
አዎ አንድ ነው፡፡ የሶስት ወንድማማቾች ልጆች ናቸው፣ ኢሮቦች፡፡ ሀሳበላ፣ ቡክናይተአረ  እና ጋዳ ይባላሉ፡፡ ጋዳ በሰሜን በኩል ነው ወደ ኤርትራ የሚጠጋው፤ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ናቸው። የነሱ ግንኙነት ከኤርትራ ጋር ነው - በጣም ተቀላቅለዋል፡፡ ቋንቋው ትግርኛ እና ሳሆ ነው፡፡ መሀል ያለው ቡክናይታ ካቶሊክ ነው፤ ከነሱ  ወደ ሰሜን ስትሄጂ መነኩሲቶ የሚባል የኤርትራ ቦታ አ። እነሱም ካቶሊኮች ናቸው፡፡ የጋብቻ ግንኙነታቸው ከካቶሊኮቹ ጋር ነው፡፡ ብቻውን የሚቀረው ሃሰበላ ነው፤ ከአጋመ ጋር ይዋሰናል፤ ኦርቶዶክስ ነው፡፡ በዘር የተሳሰሩ ናቸው፤ በኮሚሽኑ ውሳኔ መሠረት፤ ብክናይተአረና ጋዳ ለኤርትራ  ተወስነው ሀሰበላ ነው ለኢትዮጵያ የቀረው፡፡ ቦታዎቹን ሳውቃቸው በኢትዮጵያ ግዛት ስር የነበሩ ናቸው፡፡
የታሪክ ተማሪ ነህ ድንበር ማስመር ላይ ስህተት እንዳለ ነግረኸኛል፡፡ እሰቲ ስለእሱ አብራልኝ …  
ከአድዋ ጦርነት በኋላ በማካለል ላይ የተደረገ ስህተት ነው፡፡ መረብ፣ በላሳ፣ ሙና የሚለው ነው። በካርታው ላይና መሬት ወርዶ ያለው ላይ ማለት ነው፡፡ በጣሊያን ጊዜ ራሱ ቦታው የአርበኞች ቦታ ነበር፡፡ ከኤርትራም ሆነ ከትግራይ በኩል ጣሊያንን የተዋጉ አርበኞች የተሸሸጉት ኢሮብ ነው፡፡ ኢሮብ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡
መጽሐፉን ለማዘጋጀት ያነሳሳህ ምንድንነው?
መጽሐፉን ለመፃፍ ካሰብኩ ቆይቻለሁ፡፡ ግን የጽሑፍ ችሎታ የለኝም፡፡ ብዙ መፃሕፍቶች እየወጡ ነው፤ አንብቤያለሁ፡፡ አንድ ሳይነኩዋት የሚያልፉዋት ቦታ አለ፤ ሁሌም ይከነክነኛል፡፡ ይህ ድርጅት በአንድ ወቅት በጣም ገንኖ የወጣ፣ ተቀባይነት ያገኘ ነበር፡፡ የተቀጨው ግን በአጭሩ ነው፡፡  
ለውድቀቱ መፍጠን አስተዋጽኦ ያደረጉት ምንድን ናቸው? ውስጣዊ ችግሩ ወይስ ውጫዊው? የሚለውን ለማሳየት በክፍፍሉ ላይ አተኮርኩ፡፡ የተወሰኑ ዶክመንቶች፣ ግለሰቦችና የራሴን ተመክሮ አካትቼ አስቀመጥኩ፡፡ የቀረውን ሌላው ሊሞላው ይችላል ብዬ ነው፡፡
መጽሐፉ ከዚህ በፊት በሌሎች መፃሕፍቶች ወይም ሰነዶች ላይ ያሉ መረጃዎችን ነው የገለበጠው የሚል አስተያየት ይሰነዘራል፡፡
አዎ ትክክል ነው፡፡ የማውቃቸውም ያነበብኳቸውም  የማምንባቸውም ስለሆኑ ነው የተጠቀምኩባቸው፡፡
ከኢሕአሠ ሸፍተህ ነበር፡፡ ከደርግም ሸፍተሃል ይሄ ነገር እንዴት ነው?
አዎ ሸፈትኩ ድርጅትህን ከድተህ መሳሪያ ይዘህ መጥፋት ከባድ ወንጀል ነበር፡፡ እኔ እርምጃ አልተወሰደብኝም፡፡ የሸፈትኩት እስር ቤት አያለሁ ለሠራዊቱ የነበረኝ ግምትና ስሄድ ያገኘሁት  በጣም የተለያየ ስለነበረ ነው፡፡ መጽሐፌ ላይ የአሊቴናን ካርታ ያስገባሁት ያለምክንያት አይደለም፡፡
አሊቴና በጣም ስትራቴጂክ ናት፣ ሁለት በር አላት፡፡ ያንን ጥሶ የህወሓት ሠራዊት ሲገባ ኢሕአሠ እንዳለቀለት ገባኝ፡፡ ከዛ ደግሞ ማጋለጥ ውስጥ ተገባ፡፡ ተጠርቼ ነበር አልሄድኩም፡፡ ሠራዊት ሆኖ መቀጠል አይችልም፡፡ ለውጥ ያስፈልገዋል ብዬ አሰብኩ፡፡ እና መጀመር አለብኝ ብዬ ከጓደኛዬ ጋር ተመካከርኩና እንገንጠል አልን፡፡ ለውጥ እናድርግ ወይ ለውጥ አድርገው ይቀላቅሉን አልን፡፡ ጓደኛዬ የትጥቅ እና ስንቅ ሃላፊ ነበረ፡፡ የተቀበሩ መሳሪያዎች ያሉበትን ቦታ ያውቃል፤ ችግር እንደማይገጥመን ደምደመን፤ ሄድን፡፡ ከዚያ ብዙ ሽማግሌዎች ተላኩብን በኋላ ግን ሃሳቤን የሚያስቀይር ሚስጥር አገኘንና ለመመለስ ወሰንኩ ፡፡ ህወሓት ለጦርነት እንደተዘጋጀ ሰማን፡፡ በዛ ሰአት ጥሎ መሄድ ስላልታየኝ ተመለስኩና ያገኘሁትን መረጃ ሰጠሁ፡፡ በዚህ ምክንያት ይመስለኛል ያልታሠርኩት፡፡
የመጨረሻዎቹ የኢሕአሠ ቀኖች  በትግል ሜዳ ላይ ምን ይመስሉ ነበር?
በጣም አስቀያሚ፡፡  ጦርነት እየገፋ መጣና ኢሮብ አካባቢ ደረሰ፡፡ ለመውጣት በኤርትራ በኩል  መንገድ መከፈት ነበረበት፡፡  ጀብሀ፤ አይሀ በምትባል ቦታ ብቻ ነው ማለፍ የሚቻለው ብሎ ቢስማማም  አንድ ጋንታ በሌላ መንገድ ለመግባት ስትሞክር ትያዛለች፡፡ ስንደርስ ትጥቅ አስፈትተዋቸው አናስገባም ይሉናል፡፡ ከዚያ መሳሪያቸውን ተረክበን ከሚሊሺያዎቹ ጋር አንድ ኮረብታ ላይ ቁጭ ብለን ሸመዛና በሚባል ሜዳማ ቦታ ላይ የኛ ሠራዊት ይተማል (ለቅሶ)፡፡
አንተ እዚያ ቀረህ?
ለአንድ አመት ኢሮብ ቆየሁ፡፡ መቆየቴ ጥሩ ነበር። ደርግ አዲስ አበባ ውስጥ ያደርግ የነበረውን ሰቆቃ ለማምለጥ የሚመጡትን እየተቀበልን እናሳልፍ ነበር፡፡ ማህተም ያለው ሰነድ እጃችን ላይ ነበር፡፡
በኋላስ አንተ ምን ሆንክ?
እዚ መቆየት ከባድ ነበር፡፡ የቀረሁት ከገበሬዎች ጋር ነው፡፡ ቀድሞ ያነሳነው የገበሬ ባህርይ እየገፋ ሲመጣ፣ መቆየት የሚፈልጉት እዚያው ቀሩ፡፡ ህወሓትን የሚቀላቀሉ፡፡ ተቀላቀሉ እኔ አዲስ አበባ ት/ቤት ገባሁ፡፡
ቀጣዮቹ አመታትስ?
አስተማሪ  ነው የምትሆነው፣ ተብዬ ጐጃም ተመደብኩ፡፡ ጐጃም ሳለሁ እስከ 1983 ድረስ ስለነበሩት ጓዶች እንዴት እንደነበሩ አውቃለሁ፡፡
እንዴት ነበሩ?
ቻግኒ  እና ዳንግላ እነሱን ለመፈለግ ሄጃለሁ።  ግን እኔ የማውቀው የኢሕአሠን አይነት ሆኖ አላየሁትም፡፡ በሽፍትነት ደረጃ እንደነበሩ ነው የሰማሁት፡፡
ከዚያስ
ወደ መጨረሻ አካባቢ (ከሁለት አመት በኋላ) የኢህድን ወሬ እሠማ ስለነበር “እነሱ ይሆኑ እንዴ እውነተኞቹ ኢህአፓዎች?” በሚል ማፈላለግ ጀመርኩ፡፡ 79 እና 80 አካባቢ ከማን ጋር እንደሆነ በትክክል ባላውቅም (ኢህዴን፣ ህወሓት፣ ሻዕቢያ) አዲስ አበባ ውስጥ በትክክል የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ነበርኩ፡፡
ደርግ እንዲወድቅ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉት ከማናቸውም ጋር በህቡዕ እሠራ ነበር፡፡ ደርግ ሲወድቅ ቀጥታ ያገኘኋቸው ኢህዴኖችን ነው፡፡ ፎረም 84 የሚመራው በነሱ ነበር፡፡  ከአመራሮቹ አንዱ ሆንኩ፡፡ እራሴን እንደ ኢህዴን ቆጠርኩ፡፡ የክልል 14 ፀሐፊ ነበርኩ፡፡
ኢህዴንን ለምን መረጥክ?
አንደኛ ከኢሕአሠ የማውቃቸው ስለነበሩ፡፡ ሲሆን ቀጥሎ ህብረ - ብሔራዊ ስለነበር ነው፡፡
ለምን ከሃላፊነትህ ለቀቅህ?
ኢህዴን ወደ ብአዴን ሲቀየር ወደ የብሔር ድርጅት የሚል ነገር  ሲመጣ ስላልተስማማኝ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ያነበብኳቸው መፃሕፍቶች በዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ላይ ያሳደሩብኝ ተጽእኖዎች ሊያስቀጥለኝ ስላልቻለ! አልቻለም፡፡ በ1989 ዓ.ም በፈቃዴ ለቀቅኩ፡፡

Published in ህብረተሰብ
Page 1 of 16