Administrator

Administrator

  የማይመልሱ ሰዎችን ፎቶና ማንነት በሚዲያ ይፋ አደርጋለሁ ብሏል
         - የራስ ያልሆነ ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እስከ 25 ዓመት እስራት ያስቀጣል
         - የአካውንቶች መታገድ ገንዘቡን ለመመለስ እንቅፋት ፈጥሯል ተብሏል


          የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አጋጠመኝ ባለው  የሲስተም ችግር ምክንያት ያለአግባብ  ገንዘብ ከባንኩ  የወሰዱ ወይም ወደ አካውንቶች  ያስተላለፉ ግለሰቦች የወሠዱትን ገንዘብ ለባንኩ እንዲመልሱ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ያበቃል።  በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ገንዘቡን  ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግም ገልጿል ።
ባንኩ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም በተፈጠረው የሲስተም ችግር ምክንያት ከባንኩ  ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች ገንዘቡን ተመላሽ እንዲያደርጉ ተደጋጋሚ ጥሪ ያቀረበ መሆኑን አመልክቶ፤  የመጨረሻ  ያለውን ጥሪ ከትላንት በስቲያ  ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.  አስተላልፏል። በዚህ ጥሪ መሠረትም ባንኩ ገንዘቡን ለማስመለስ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ይጠናቀቃል ።
ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች፤ ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ እንደሚያደርግም አስታውቋል። ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን እንደሚከተሉም  ገልጿል። በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም አሳስቧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ከንግድ ባንክ የራሳቸው ያልሆነ ገንዘብ ያንቀሳቀሱ ግለሰቦች የማይመልሱ ከሆነ፣ በህግ እንደሚጠየቁ የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ከትላንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ከባንኩ ጋር በጋራ እየሰራ እንደሚገኝ የገለፀው የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎቱ፤ የራስ ያልሆነን ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እንደ ወንጀሉ ክብደት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ እስራት እደሚያስቀጣ አሳስቧል፡፡
ባንኩ አርብ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም. ምሽት ላይ የሲስተም ችግር በገጠመው ወቅት የተወሰደበት ገንዘብ  መጠን ከባንኩ በይፋ ባይገለጽም ፣ በዕለቱ የተወሰደው የገንዘብ መጠን 2.4 ቢሊዮን ብር (40 ሚሊዮን ዶላር) መሆኑን አሶሺየትድ ፕሬስ  ዘግቧል።

  -  ባለፈው ዓመት 7 ሺህ የሚጠጉ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል
ኢትዮጵያ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ካሉ ሀገራት  መካከል አንዷ እንደሆነችና የሳይበር ጥቃቶቹ  የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ ባንኮችን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ሃይል ያሉ  ተቋማትን፣ መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ እንደሆኑ  ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን ገልጿል።
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ  ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው፤  ዓለማችን በኢንተርኔት መተሳሰሯና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ጥገኝነቷ በፍጥነት እያደገ መሄዱን ተከትሎ የሳይበር ጥቃትም ፈተና ሆኖባታል። ባለፈው የፈረንጆቹ አመት ከ340 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ተጎጂ ያደረጉ የሳይበር ጥቃቶች ተፈጽመዋል ።
ግለሰቦችን፣ ተቋማትን እና የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ኢላማ ባደረጉ የሳይበር ጥቃቶች፣ በ2023 ብቻ ከ8 ትሪሊየን ዶላር በላይ የሚገመት ጉዳት ደርሷል።
የሳይበር ጥቃት የትኛውንም ሀገር ወይም ተቋም ለይቶ እንደማይተው የሚገልጸው ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን፥ ጠንካራ የሳይበር ደህንነት ህግና ቴክኖሎጂ ያላቸው ሀገራት አደጋውን መቀነስ መቻላቸውን ገልጿል።
በአንጻሩ ደካማ የሳይበር ደህንነት ህግ ያላቸው አልያም ከነጭራሹ የሌላቸውና ጥቃቶችን አስቀድሞ ለመመከት የሚጠቀሟቸው ቴክኖሎጂዎች ከፈጣኑ የዲጂታል አለም ጋር አብሮ በማይሄድባቸው ሀገራት አደጋው እንደሚከፋም ጠቁሟል።
በዚህም መሰረት ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ያሉ ናቸው በሚል  በተቋሙ  ከተጠቀሱ ሀገራት መካከል  ኢትዮጵያ የምትገኝ ሲሆን፤ አገሪቱ  ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ በመሆን ከአለማችን  በ8ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች  ብሏል።
ባለፉት ጥቂት አመታት በኢትዮጵያ የሳይበር ምህዳሩን የሚጠቀሙ ሰዎች ቁጥር መጨመርን ተከትሎ፣ በግለሰቦችና ተቋማት ላይ የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችን ጨምሮ በሀገሪቱ  ቁልፍ የመንግስት መሰረተ-ልማቶች ላይ እየደረሱ ያሉ ጥቃቶች የብሄራዊ ደህንነት ስጋት መሆናቸውን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ  የሚታወስ ሲሆን፤  ባሳለፍነው ዓመት 2015 ዓ.ም  ከ 6 ሺ 959 በላይ  የሳይበር ጥቶች መፈጸማቸውንም ጠቁመዋል።
ከሳይበር ጥቃቶቹ ውስጥም 2 ሺ 559 ያህሉ በድረ ገጽ ላይ የተፈጸሙ ሲሆኑ፤ 1 ሺህ 295 ያህሉ ደግሞ የማልዌርና የፒሺግ መሆናቸው ተጠቁሟል። እንዲሁም 603 በመሰረተ ልማት ቅኝት፣ 1 ሺህ 493 መሰረት ልማት የማቋረጥ (አብዛኛው የፋይናንስ ተቋማትን ኢላማ ያደረገ)፣ 695 ሰርጎ የመግባት ሙከራ እና 145 ሌሎች የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል።
የሳይበር ጥቃቶቹ የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ያሉ ቁልፍ ተቋማት መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ ነበሩ ተብሏል። በ2015 የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎችን መከላከል በመቻሉም፣ በሀገር ላይ ሊደርስ የነበረ 23.2 ቢሊየን ብር ኪሳራ ማዳን መቻሉን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ ማስታወቃቸው አይዘነጋም ።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባጋጠመው የሲስተም ችግር ወቅት ገንዘብ የወሰዱ ወይም ያስተላለፉ ግለሰቦች እስከ መጪው ቅዳሜ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም. ድረስ ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግ አስታወቀ።

ባንኩ ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች “ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ አደርጋለሁ” ሲል አሳስቧል።

ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ የባንኩ ቅርንጫፎች በመቅረብ እንዲመልሱም የመጨረሻ ጥሪውንው ዛሬ ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስተላልፏል።

ነገር ግን ይህ ሳይሆን ገንዘቡን በተቀመጠው ጊዜ ገደብ ተመላሽ የማያደርጉ ግለሰቦች ላይ የተለያዩ እርምጃዎችን እወስዳለሁ ሲል አስጠንቅቋል።

የሚወስዳቸው እርምጃዎች ደረጃ በደረጃና በተከታታይ ጠንከር ያሉ እንደሚሆኑ የገለጸው ባንኩ፤ ለሕግ አካላት ማሳወቅ አንዱ እንደሚሆንም አስታውቋል።

“ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን” እንደሚከተሉ አስታውቋል።

በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም” አሳስቧል።

የባንኩ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ ረቡዕ ዕለት ለቢቢሲ ኒውስ ዴይ፣ የራሳቸው ያልሆነን ገንዘብ የወሰዱ ደንበኞች እስከ ሳምንቱ መጨረሻ ድረስ ካልመለሱ ማንነታቸውን ለፖሊስ እንደሚያሳውቁ ተናግረው ነበር።

“ማዕከሉ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ 1ሺ ህፃናትን የመቀበል አቅም ይኖረዋል”
አርቲስት መቅደስ ፀጋዬ ወላጆቻቸውን በሞት ላጡ ህጻናት፣ "መቅደስ የልጆች አድማስ" የተሰኘ ማዕከል በ1 ቢሊዮን ብር ወጪ ልትገነባ መሆኑ ተገለጸ፡፡
አርቲስቷ የምታቋቁመውን የበጎ አድራጎት ድርጅት አስመልክቶ በዛሬው ዕለት በካፒታል ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
ድርጅቱን ለማቋቋም ሃሳቡ የተፀነሰው ከ6 ዓመታት በፊት እንደነበር አርቲስት መቅደስ ጸጋዬ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተናግራለች፡፡
የድርጅቱ የቦርድ አባል ደራሲ ውድነህ ክፍሌ እንደገለጸው፤ ማዕከሉ በዋናነት ልዩ ትኩረትና ጥበቃ ለሚያስፈልጋቸው ወላጅ አልባ ህፃናት አስፈላጊውንና ሁሉን አቀፍ እንከብካቤ በመስጠት በቀጣይ የሕይወት ጉዟቸው ስኬታማ ይሆኑ ዘንድ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ነው፡፡
በማዕከሉ ውስጥ ለሚቆዩ ልጆች ደረጃውን የጠበቀ የመኖሪያ፣ የትምህርትና የጤና አገልግሎቶችን ከመስጠትና፣ የአካል ብቃት ማጎልመሻ ከማደራጀት ባሻገር፣ የማኅበራዊ ሕይወትና የአእምሮ ማበልፀጊያ ስልጠናዎችን በመስጠት ሙሉ ጤንነታቸው የተረጋገጠ፣ በአካላዊ እድገታቸው የበቁ፣ በሥነ ልቦና፣ በግልና በማሕበራዊ ሕይወታቸው ጠንካራ የሆኑ እንዲሁም በአእምሮአዊ የጠራ ችሎታቸው የተደነቁና በዕውቀት የዳበሩ ሆነው የመጪው ጊዜ ብሩህና ስኬታማ ዜጎችን እንዲሆኑ በትኩረት ይሰራል ተብሏል።
“መቅደስ የልጆች አድማስ” በማእከሉ የሚያድጉ ልጆች በሁሉም ረገድ ኢትዮጵያዊ እሴቶችን የተላበሱና አዎንታዊ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ ማድረግ ዋና ትኩረቱ እንደሆነ ተገልጿል።
በሃያ አንድ ሺ ካሬ ሜትር ላይ እንደሚያርፍ የተነገረለት ማዕከሉ፤ ሙሉ ለሙሉ ለመገንባትና በሙሉ አቅሙ ስራውን እንዲጀምር ለማድረግ እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ይፈጃል ተብሏል፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቱ የመጀመሪያ ማዕከሉን የሚገነባው በአዲስ አበባ ሲሆን፤ ቀስ በቀስም ወደ ከልሎች ቅርንጫፎቹን የሚያሰፋ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡ ማዕከሉ በመጀመሪያው ዙር 200 ህፃናትን ከመላው ኢትዮጵያ የሚቀበል ሲሆን፤ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ ደግሞ 1000 ህፃናትን የመቀበል አቅም እንደሚኖረው ተጠቁሟል፡፡
ማእከሉን እውን ለማድረግ መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል በይፋ ገቢ በማሰባሰብ ወደ ስራ የሚገባበት ቀን ሲሆን፤ በዚህ መርሃ ግብር ላይ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ባለሃብቶች፣ የኤምባሲ ተወካዮች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ሃሳቡን የሚደግፉና ቀና ልብ ያላቸው ሰዎች ይታደሙበታል ተብሏል።
• በፊልሙ ላይ 30ሺ ሰዎች ተሳትፈውበታል ተብሏል
በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ የተሰራውና “ስለ እናት ምድር” የተሰኘው ዶክመንተሪ ፊቸር ፊልም፣ ከነገ ወዲያ ቅዳሜ ከቀኑ 8 ሰዓት በአድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡
አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ በዛሬው ዕለት በግዮን ሆቴል፣ ግሮቭ ጋርደን ወክ፣ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገረው፣ በፊልሙ ላይ ሰላሳ ሺ ሰዎች የተሳተፉበት ሲሆን፤ የሦስት ሰዓት እርዝማኔ እንዳለውና ታሪኩንም በሰሜኑ ኢትዮጵያ ጦርነት ላይ ያደረገ መሆኑን ጠቁሟል።
ፊልሙ በአሜሪካን ሀገር ሎሳንጀለስ ከተማ በተካሄደ የፊልም ፌስቲቫል ላይ ሁለት መቶ ከሚሆኑ ፊልሞች ውስጥ ከተመረጡ ሦስት ፊልሞች አንዱ ለመሆን እንደበቃ አርቲስት ቴዎድሮስ ለጋዜጠኞች ተናግሯል።
ፊልሙ አዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ አላማጣ፣ ዞብል፣ ወልድያ፣ ቆቦ፣ ኮምቦልቻ እንዲሁም ጅማ ከተማና ደነባ በተሰኙ ቦታዎች ላይ የዘመኑ የመጨረሻ ቴክኖሎጂ በሆነው 12 k የተሰኘ የቪዲዮ ካሜራ እንደተቀረፀ የተገለፀ ሲሆን፤ ቀረፃውም ዓመት ከስምንት ወር እንደፈጀ ተብራርቷል።
በፊልሙ ላይ በቲክቶክ ስራዎቿ የምትታወቀው ፅጌ ሮያል መሪ ተዋናይ ስትሆን፣ አንጋፋው አርቲስት ደበበ እሸቱም ተውኖበታል ተብሏል። በዚህ ፊልም ላይ ከሆሊውድና ከቦሊውድ የመጡ ባለሙያዎችም እንደተሳተፉበት ተነግሯል፡፡
“ስለ እናት ምድር” የተሰኘው ፊልም ከምርቃቱ በኋላ በሁሉም ሲኒማ ቤቶች ለዕይታ እንደሚቀርብም ታውቋል፡፡

ሰሞኑን አዲስ አበባ እጅጉን ተዋክባለች፡፡ በተስፋና በስጋት ማዕበል እየተናጠች ነው፡፡ ተስፋው ከተማውን በማደስ ላይ በሚገኙት የመንግሥት ኃላፊዎች ፊት ላይ ሲታይ፣ ስጋቱ ደግሞ ቦታው በሚፈርስባቸው አካላትና በአልፎ ሂያጁ መንገደኛ ላይ ይስተዋላል፡፡ በተለይ ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ መገናኛ፣ ቦሌና የመሳሰሉት አካባቢዎች  የነውጥና የለውጥ አየር እየነፈሰባቸው ነው፡፡ አዲስ አበባን እንደ አዲስ ለመሥራት፣ መልሶ እራሷን ለማዋለድ እየተደረገ ያለው ይህ እሽቅድምድም፣ ፍጥነቱም ክብደቱም፣ ለእኔ ቢጤው ድንገቴ ነው፡፡ አዲስ አበባችን ተዋክባለች፡፡ ሁለ ነገሯ፣ ‹አሁኑኑ ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ!› የምትል ሆናለች፡፡
ዘንድሮም አዲስ አበባ ለድሆች ‹ከወዲሁ ቦታችሁን ፈልጉ!› እያለች ነው፡፡ ‹ጠጋ በሉ!› እያለች ጥግ ያስያዘቻቸውና ‹ጫፍ ላይ ወራጅ አለ› ብላ ገፍትራ የጣለቻቸው ልጆቿ ቁጥር ጨምሯል፡፡ ‹እያለህ ካልሆነ ከሌለህ የለህም!› ሆኗል የዘፈን ምርጫዋ፡፡ አታስቆማቸውም፤ አታስቀምጣቸውም፤ ምናልባት  እንዲጎበኟት የመመላለሻ ፍቃድ ትሰጣቸው ይሆናል፡፡ ኮሪደሩ ግን የእነሱ አይደለም፡፡
ደግሞም ታሪክ እንደ ዘበት የተሳለማቸውና  ዘመን ያስቆጠሩ ቅርሶቿን በጥንቃቄ ሰንዳ  እንዳላስቀመጠች ያስታውቅባታል፡፡ ለእሷ አሮጌ ነገር ሁሉ አይጠቅምም፡፡
‹የገዛኸውን አዲስ ባልዲ ውሃ መያዝ አለመያዙን ሳታረጋግጥ አሮጌውን ባልዲ አትጣል!› የሚለው ብሂል ለአዲስ አበባ የሚሠራ አይመስልም፡፡
የተበጠሰው ነገር፣ ተበጥሶም እንደ አዲስ የተቀጠለው ነገር ብዙ ነው፡፡
ከእንግዲህ የምናውቃቸው ሰፈሮች እንደማናውቃቸው ሆነዋል፡፡  በነጋችን ውስጥ እነሱ የሉም፡፡ ከእንግዲህ ስማቸውና የቀደመ ምስላቸው ብቻ ነው በአንደበቶቻችን የሚደመጡት፣ በዕይታችን የሚመላለሱት፡፡ ከእንግዲህ ከላይ በተጠቀሱ ቦታዎች የተሠሩ የዘፈን ክሊፖች፣ ሥዕሎች እና ምስሎች ቅርስ ይሆናሉ፤ ከንፈር እየተመጠጡ የሚታዩ፤ ‹ለካስ ነበር እንዲህ ኖሯልና ቅርብ› የሚያስብሉ፡፡
ከእንግዲህ የዓለማየሁ ገላጋይ  ‹አጥቢያ› ልቦለድ፣ የመሀመድ ሰልማን ‹ፒያሳ ማህሙድ ጋ ጠብቂኝ› እና እነዚህን መሰል ድርሰቶች ልቦለዶች ብቻ አይደሉም፤ በራሮታዊ ስሜት የሚነበቡ መዘክሮችም ጭምር እንጂ! ሰሞኑን፣ ‹ኧረ ጎበዝ ምን እየተደረገ ነው?› ብለው ለሚጠይቁ መንግሥት፣ ‹ስጨርስ የማደርገውን ታያላችሁ› እያለ ይመስላል፡፡ እንዲህ ያለው ጉርምርምታ በፊትም ነበር፤ ወደፊትም ይኖራል፤ ነበር ይኖራልም ማለት ግን የጥያቄውን ዕድሜ ይናገራል እንጂ የአፍራሹንም የገንቢውንም ልክነት አያሳይም፡፡  ልዑል ራስ መንገሻ ሥዩም ‹የትውልድ አደራ› በሚለው መጽሐፋቸው፣ የቦሌን አይሮፕላን ማረፊያ ሜዳ ሲከልሉ ስላጋጠማቸው ችግር ሲያስታውሱ፣ ‹‹…ብዙዎቹ ጓደኞቼ የመሬቱ ባለቤቶች ነበሩ፤ መንገዱ በመቶ ሜትር ስፋት፣ አራት ኪሎ ሜትር ሲሄድ፣ የብዙዎቹን መሬት እየቆራረጠ መሄዱ አይጠረጠርም፡፡ በሀሜት መልክ ይሁን በወቀሳ መልክ ይሁን ‹ይሄ ስንዝር መሬት የሌለው ትግሬ እኮ መጥቶ ርስታችንን በሙሉ ነቀለን› የሚሉበትም ጊዜ ነበር፡፡ እኔም በዚሁ በቀልድና በዋዛ መልስ ‹አዎን ዛሬ ታለቅሳላችሁ፤ ነገ ግን የልጅ ልጆቻችሁ የሚደሰቱበት ሳይሆን አይቀርም፡፡ /…/ ላገሪቱ ደግሞ ታላቅ ሃብትና ለሕዝቡም ዕድገት ደህና መንገድ ሊሆንይችላል…እላቸው ነበር›› ብለዋል፡፡
መንግሥት አገር እየሠራሁ ነው፣ ነው የሚለው፤ ‹ከተማዋን እያበለጸግሁ!›፡፡ ለሚከፉበትም ከላይ ልዑል ራስ መንገሻ የመለሱት ዓይነት መልስ ነው የሚሰጠው፡፡
እርግጥ በፈረሱ ቦታዎች ያማሩ ነገሮች እናያለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፤ ሆኖም ያ ያማረ ነገር ለማየት ተብሎ ደሃ የበደለኞችና የሀብታሞች መሸጋገርያ ድልድይ እንዲሆን መፍቀድ ተገቢ አይደለም፡፡ ምን ተደረገለት ነው? ጥያቄው፡፡ አቤቱታው የት ወደቀ?
መውደቂያቸውን ሳያዘጋጁ፣ ሳይዘጋጅላቸው፣ አዋክቦ ማስወጣት ‹ምን እንዳታመጡ!› የሚል ድምጸት አለው፡፡ ይሄ ደግሞ ውጤቱ ግልጽ ነው፡፡ የተበዳይን ጩኸት የማይሰማ መንግሥት አንድም የነቃፊውን ቁጥር ያበዛል፤ አንድም የህልሙን ተጋሪ ዜጎች  በፈቃዱ ያሰናብታል፡፡
ትልቁ ነገር ሰፈር ብቻውን እንደማይፈርስ መገንዘቡ ላይ ነው፡፡ ሰፈር ቋተ ብዙ፡፡  ሰፈር መስፈርያም መሳፈርያም ነው፡፡ ራሱን በሰፈሩ ቁና የሚሰፍር ጥቂት አይደለም፡፡ በሰፈሩ ወደ ሚፈልገው ዓለም ኳትኖ የሚመለስ ተሳፋሪም ጥቂት አይደለም፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት ደግሞ ሰው የሚሠራው መጀመርያ ቤቱ ውስጥ ነው፤ ቀጥሎ ሰፈሩ፤ ቀጥሎ ቤተ እምነቱ፤ ቀጥሎ ቤተ ትምህርቱ፡፡ የሰፈሩ ግን ጥብቅ ነው፡፡ ለዚህም ነው፣ የአንድ አካባቢ ሰው ሲነሳ ጎረቤታማሞች ሳይነጣጠሉ በአንድ ሰፈር ቢሰፍሩ ይሻላል የሚባለው፤ ዕድሩም ማኅበሩም ተጠናክሮ እንዲቀጥል፡፡
አንዳንዱ እንኳንስ የተወለደበትና ያደገበት፣ የሚውልበት ሰፈር መፍረሱ ሲነገረው ሰውነቱ የመፍረስ ስሜት ይሰማዋል፡፡ ይሄ ሰውኛ ባህርይ ነው፡፡ ፈልገህ አታመጣውም፤ አስገድደህ አታባርረውም፡፡ ሰፈሩ እየፈረሰበት፣ ትልቅ ታሪካዊ ነገር ሊገነባበት ነው ሲባል፣ ነፍሱ ‹ጉሮ ወሸባዬ› እያለች አታዜምለትም፡፡ ምን ቢለወጥ፣ ምን ቢታደስ ባይነኩበት የሚመርጣቸው ጥቂት እጅግ በጣም ጥቂት ነገሮች ይኖሩታልና ሊከበሩለት ይገባል፡፡
አንድ ሰፈር በከፊልም ሆነ ሙሉ ለሙሉ ይፍረስ  ሲባል፣ ምንም ጥርጥር የለውም፣ መንግሥት ለተሻለ ነገር ቦታውን አጭቼዋለሁ ማለቱ ነው፡፡ ሰፈሩ ጨለማም፣ ኮተታም፣ የድህነት ጎተራና ማፈርያ ስለመሰለውም ጭምር ነው፡፡ ራሱን የሚያይበትና ለሌላው (በተለይ ለቀጣዩ ትውልድ) ራሱን ሊያሳይበት የሚፈልገው መስታወቱ እንዲሆን በመመኘቱ ነው፡፡  የመጣው የሄደው መንግሥት ሁሉ ማኅተሙን ከሚሰፍርባቸው ሥፍራዎች መካከል ከተሞች ዋነኛው ናቸውና እንዲህ ቢሰማው ስህተት አይሆንም፡፡
ጉዳዩ፣ የሚፈርስበት ቤተሰብ አዕምሮው እንዲዘጋጅ ተደርጓል ወይ? ነው፡፡ ምነው ቢባል የሰው ልጅ ከጊዜና ከቦታ ጋር ያለው ቁርኝት ከባድ ነው፡፡
አንዳንዱ ባይጠቀምበትም ባይጠቅመውም አሮጌ ዕቃውን አይጥለውም፤ ዕቃው ትናንትናን የሚያይበት መነጽሩ ነው፡፡ ለማንም ግልጽ እንደሚሆነው፣ ለልማት ከቦታቸው ከመነሳታቸው በፊትም ሆነ በኋላ ተነሺው ቤተሰብ አዕምሮው ዝግጁ እንዲሆን ሊደረግ ይገባል፡፡ ተከታታይ የማነቃቃት ሥራ ከተሰራ እያንዳንዱ የልማት ተነሺ ነገ ከነገ ወዲያ ወደተዘጋጀለት ስፍራ ሲያቀና አይወናበድም፡፡ እንደሰው ተቆጥሮ፣ እንደ ዜጋ ተመድቦ ወደተዘጋጀለት ስፍራ እንዲያቀና ሊጋበዝ ይገባል፡፡ በተጨማሪም፣ ቦታው ላይ ምን ዓይነት ልማት ሊከናወን እንደታሰበ በዝርዝር ቢነገረው፣ ‹ታዲያ እኔ እዚህ በመዘግየቴ ለውጡን ለምን አደናቅፈዋለሁ?› ማስባል ነበረበት፡፡
ይህ የመልሶ ማልማት እንቅስቃሴ ካለፉት ዓመታት ጀምሮ መልሶ ማድማት ሲሆን አስተውለናል፤ ብዙ ተብሎለታል፤ ከየቦታው የተነሱ ሰዎች ማኅበራዊ ሕይወታቸው ተመሳቅሎዋል፤ እሴታቸውን በግድ ተነጥቀዋል፤ ያልተገባ የካሳ ክፍያ እንዲቀበሉ ተገደዋል፤ እዳ ውስጥ ተዘፍቀዋል፡፡ ከተከበሩበት ቦታ ተነስተው ወደ ባዶነት የተሸጋገሩ፣ በዝቅተኛነት መደብ የኖሩ ብዙ ናቸው፡፡
ዜጋ ዜጋ ነው፤ አንድም ይሁን አስራ አንድ፣ ሰባ ሰባትም ሆነ ሰባት መቶ ሰባ ሰባት ያው ነው፡፡ ቁጥር አይደለም ጉዳዩ፡፡ እናም የማንም ሰብዓዊ መብት መረገጥ የለበትም፤ ማንም ለጭንቀት መዳረግ የለበትም፤ የእሱ ክፉኛ መጎዳት እኔንም ይመለከተኛል፤ ውሎዬን ያጨልመዋል ብሎ ማሰቡ ነው የሚያዋጣው፡፡
ሌላው ጉዳይ -ከምንም ነገር በላይ - እነዚህ ከየቦታው በልማት ሰበብ የተነሱ ቤተሰቦች ሰማዕታት ናቸውና በቂ ዕውቅና/ክብር ሊሰጣቸው ይገባል ብዬ እምናለሁ! ወደድንም ጠላንም እነሱ ባይነሱ፣ እነሱ ዋጋ ባይከፍሉ፣ በውድም ሆነ በግድ ተነሱ ሲባሉ እሺ ባይሉ፣ ለሁከት ቢነሳሱ የምናያቸውን ነገሮች አናያቸውም ነበር፡፡ ‹እንበለ ደም ሰማዕትነት› የሚባል ነገር አለ በሃይማኖት ትምህርት፡፡ እኔ እንደገባኝ ‹እንበለ ደም ሰማዕት› የሚባሉት በሰደፍ ባይመቱም፣ በሰይፍ ባይቀሉም ከሰማዕትነት እኩል ሊያስቆጥር የሚችል ተጋድሎ የፈጸሙ ናቸው፡፡ እነዚህ በየስፍራው በልማት ተነሺነት ተመዝግበው ኑሯቸውን የቀጠሉ፣ የሰፈሩበት ቦታ ምቹ ስሜት ያልፈጠረባቸው፣ በግድም ቢሆን ከራሳቸው ቀንሰው ሰጥተዋልና ክብር ሊሰጣቸው ይገባል፡፡
**

ሲጮሁ “ያልተሰሙት” የቤተክርስቲያን ደወሎች!

 

 


ከአዘጋጁ፡-
 እንዳለጌታ ከበደ፤  የ14 መጻሕፍት ደራሲ ሲሆን፣  ከሥራዎቹ መካከል፣ ‹ከጥቁር ሰማይ ሥር›፣ ‹ደርሶ መልስ›፣  ‹በዓሉ ግርማ ሕይወቱና ሥራዎቹ› እና  ‹ኬር  ሻዶ›.  ይጠቀሳሉ፤  የዛጎል የመጻሕፍት ባንክ መሥራች፣  የነገረ መጻሕፍት የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጅ፤ የፎክሎርና የሥነጽሑፍ ተመራማሪም ነው፡፡

* በ36 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች 285 ሜዳልያዎች (107 የወርቅ፣ 115 የብርና 63 የነሐስ) ተገኝተዋል፤ የሻምፒዮናውን ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡት የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸዉ።
* አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ታሪክ 27 ሜዳልያዎችን (16 ወርቅ፣ 7ብር ና 2 ነሐስ) በመሰብሰብ ከዓለም አንደኛ ነው፡፡  በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ወርቅነሽ ኪዳኔ 21 ሜዳልያዎችን (11 የወርቅ፣ 6 የብር እና 4 የነሐስ) በመሰብሰብ ዓለምን ትመራለች፡
45ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ከ2 ሳምንት በኋላ   በሰርቢያዋ ዋና ከተማ  ቤልግሬድ ላይ ይካሄዳል። በሻምፒዮናው የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ቡድን ከ2 ሳምንት በፊት ተሰባስቦ የመጨረሻ ዝግጅቱን በአዲስ አበባና  በዙርያዋ በሚገኙት ከተሞች ሲያከናውን ቆይቷል።
ይህ የስፖርት አድማስ ዘገባ ለዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ስለሚያደርገው ዝግጅት፤ ስለ አዘጋጇ ቤልግሬድ መሠናዶ፤ ስለቀረበው የሽልማት ገንዘብ፤ ስለኢትዮጵያ ከፍተኛ የውጤት ታሪክና ስለ ዓለምአቀፍ ሻምፒዮናው አዘጋጅነት የሚዳስስ ነው።
የኢትዮጵያ ቡድን ዝግጅት
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያን ቡድን 28 አትሌቶች (14 ወንድና 14 ሴት ) ይገኙበታል። ይህን ቡድን ለመምረጥ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በጃን ሜዳ አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ የተመዘገበውን ውጤት ዋና መነሻ አድርጓል። በአገር አቀፍ ሻምፒዮናው ላይ በአዋቂና ወጣት  የውድድር መደቦች ላይ
ያሸነፉና ደረጃ ውስጥ የገቡ አትሌቶችን የሚያካትት ነው። ቡድኑን በዋና አሰልጣኝነት የሚመሩት አንጋፋው አሰልጣኝ ሁሴን ሸቦ ሲሆኑ በምክትል አሰልጣኝነት ደግሞ ቶሌራ ዲንቃ አብሯቸው ይሰራል። በኢትዮጵያ  ቡድን ዝግጅት  ከቤልግሬድ የዓየር ንብረትና መልክአ ምድር ጋር የተጣጣሙ የልምምድ መርሐግብሮችን የተከተለ ነው።  ባለፈው ሰሞን ቡድኑ ወደ ሰንዳፋ በመውጣት የመስክ ልምምድ ያከናወነ ሲሆን በትራክ ላይ መጠነኛ የፍጥነት ልምምዱን ደግሞ በኢትዮጵያ ወጣቶቹ ስፖርት አካዳሚ ሰርቷል። በሳምንቱ አጋማሽ ላይ  በአሸዋማ ስፍራ ገላን አካባቢ የቀጠለው ዝግጅት ትናንት ወደ እንጦጦ በመውጣትም ተጠናክሮ መቀጠሉን ለማወቅ ተችሏል።
ቤልግሬድ ከፍተኛ ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል በተጠበቀው ቡድን በተለይ በወንዶች በሪሁ አረጋዊ በአዋቂ 10ኪሜ ውድድር ከፍተኛ ግምት የተሰጠው ሲሆን ቦኪ ድሪባና ታደሰ ወርቁም ከፍተኛ ተፎካካሪዎች ሆነው ተጠቅሰዋል። በሴቶች ደግሞ ለኢትዮጵያ ስኬት ግምት የተሰጣቸው በጃንሜዳውው ውድድር ያሸነፉ አትሌቶች ናቸው። የኢትዮጵያ ቡድን ባለፉት 4 ሻምፒዮናዎች  በነበረው ተሳትፎ የተቀዛቀዘውን የውጤት  የበላይነት እንደሚመልስ ተስፋ የተጣለበት ሲሆን ዘንድሮ በተለይ በአዋቂዎች ውድድር በሁለቱም ፆታዎች የራቀውን የወርቅ የሜዳልያ  በማግኘት ታሪኩን ማደሱ ይጠበቃል።
የቤልግሬድ መሠናዶ
45ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የምታስተናግደው  ቤልግሬድ ከ2 ዓመት በፊት የኢትዮጵያ አትሌቶች በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ ከዓለም አንደኛ ደረጃ ይዘው የደመቁባት ከተማ ናት።
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው 60 በላይ አገራትን የሚወክሉ ከ500 በላይ አትሌቶችን ተሳታፊ ናቸው። ቤልግሬድ ውስጥ በሚገኘው ፍሬንድሽፕ ፓርክ ውድድሩን በብቃት የሚያስተናግድ ሲሆን አቀበት የበዛበት መሮጫው  አትሌቶችን እንደሚፈትን ተወስቷል። ሰርቢያ ከ2022 ወዲህ የዓለም አትሌቲክስ 2 ትልልቅ ውድድሮች ለማዘጋጀት የቻለች አገር ሆናለች። በ2022 እ.ኤ.አ ላይ 18ኛውን የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮናን  በማስተናገድ በአውሮፓ አትሌቲክስ ላይ ከፍተኛ መነቃቃት ነበር የፈጠረችው።
የቤልግሬድ 24 አዘጋጅ ኮሚቴ ለሻምፒዮናው የተዘጋጁትን ሜዳሊያዎች ከሳምንት በፊት አስተዋውቋል።
“ሜዳሊያዎቹ የብረት ቁርጥራጭ ብቻ አይደሉም። በሻምፒዮናው የሚሳተፉ ተወዳዳሪዎች ሁሉ የጥረትና የትጋት ምልክት ናቸው ”በማለት ለዓለም አትሌቲክስ ማህበር ድረገፅ የተናገሩት የኮሚቴው ፕሬዝዳንት ስሎቦዳን ብራንኮቪች ናቸው። የሰርቢያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከሻምፒዮናው በፊት በአለም እና በአውሮፓ ደረጃ  ውድድሮችን በብቃት ማዘጋጀቱን በመጥቀስ ከሜዳሊያ ዲዛይን አንስቶ በመስተንግዶ ብቃት ልዮና የተዋጣለት ሻምፒዮና  እንዲሆን  እንፈልጋለንንም ብለዋል።
310ሺ ዶላር የገንዘብ ሽልማት
የዓለም አትሌቲክስ ማህበር ለሻምፒዮናው በድምሩ ከ310 ሺ ዶላር  በላይ የሽልማት ገንዘብ ያዘጋጃል፡፡  በግልና በቡድን  ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች የሽልማት ገንዘቡ ይከፋፈላል፡፡ በአዋቂ አትሌቶች የሁለቱም ፆታዎች የውድድር መደቦች በግል  ውጤት ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች ለ1ኛ 30ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 15ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 7ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 5ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 3ሺ ዶላር ይበረከታል፡፡ በቡድን ውጤት ለሚያሸንፉ አገራት ደግሞ ለ1ኛ 20ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 16ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 8ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 4ሺ ዶላር የሚታሰብ ሲሆን በሁለቱም ፆታዎች ድብልቅ የዱላ ቅብብል ውድድር ለ1ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 8ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 6ሺ ዶላር፣ እንዲሁም ለ4ኛ 4ሺ ዶላር እንደሚሸለም ታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከፍተኛ ውጤትና አዘጋጅነቱ ወደፊት
ኢትዮጵያ ከቤልግሬድ በፊት  ከተከናወኑት 44 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች በ36 ለመካፈል በቅታለች። የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የስታትስቲክስ መፅሐፍ እንደሚያለክተው ኢትዮጵያ በተሳተፈችባቸው 36 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች 285 ሜዳልያዎች (107 የወርቅ፣ 115 የብርና 63 የነሐስ) በማግኘት በከፍተኛ ውጤት  ከዓለም ሁለተኛ ደረጃ ላይ ናት።
የኢትዮጵያ አትሌቶችም በሻምፒዮናው ታሪክ ከፍተኛውን የሜዳልያ ስብስብ በማግኘት ግንባር ቀደም ናቸው፡፡ አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ታሪክ 27 ሜዳልያዎችን (16 ወርቅ፣ 7ብር ና 2 ነሐስ) በመሰብሰብ ከዓለም አንደኛ ነው፡፡  በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ወርቅነሽ ኪዳኔ 21 ሜዳልያዎችን (11 የወርቅ፣ 6 የብር እና 4 የነሐስ) በመሰብሰብ ዓለምን ትመራለች፡፡
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና  በኢትዮጵያ   ታላላቅ ውጤቶች የተመዘገበበት ውድድር ከመሆኑም  በላይ  በኦሎምፒኮችና በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ታላላቅ ስኬት ያገኙ አትሌቶችም    ተገኝተውበታል፡፡
ይህ ታሪክ ውድድሩን በኢትዮጵያ ለማስተናገድ ምክንያት መሆን አለበት።
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው በማዘጋጀት የአውሮፓና የአፍሪካ አገራት ከፍተኛ ድርሻ ይወስዳሉ።
በአፍሪካ እህጉር ሻምፒዮናው ለሶስት ጊዜያት ተዘጋጅቷል፡፡ ከ7 ዓመት በፊት የሻምፒዮናውን አዘጋጅነት የምስራቅ አፍሪካዋ ኡጋንዳ አግኝታ በተሳካ ሁኔታ ማስተናገዷ የሚታወስ ሲሆን ከዚያ በፊት በ1998 በማራካሽ ሞሮኮ እንዲሁም በ2007 እኤአ በሞምባሳ ኬንያ ሻምፒዮናው ተካሂዷል፡፡ በ2026 እኤአ ላይ 46ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአሜሪካ ታሀላሴ እንዲካሄድ ተወስኗል። በአፍሪካ አህጉር ለ4ኛ ጊዜ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናውን በ2028 ወይንም በ2030 ለማዘጋጀት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን መስራት ይኖርበታል፡፡
የዓዎች አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ከመላው ዓለም  ከ140 በላይ ሚዲያዎች በስፍራው ተገኝተው የሚዘግቡትና በዓለም አቀፍ የቲቪ ስርጭት ከ5 ሚሊዮን በላይ ተመልካቾችን የሚያገኝ ነው።፡
 በዋናዎቹ ውድድሮችና ሌሎች መርሃ ግብሮች ከ2ሺ በላይ ተሳታፊዎች ያሉት ሲሆን ከመላው ዓለም ተሰባስበው አዘጋጅ ከተማ ድረስ የሚገኙ ከ10ሺ በላይ የአትሌቲክስ አፍቃሪዎአ ናቸው።  ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ማህበር በሰራው ጥናት የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናውን ለማዘጋጀት አስፈላጊውን የመወዳደርያ ስፍራና የስፖርት መሰረተልማቶች ከማሟላት ባሻገር እስከ 2.3 ሚሊዮን ዶላር በጀት መመደብን ይጠይቃል፡፡     ከስታድዬም የመግቢያ ትኬቶች፤ ከስፖንሰርሺፕ እና ከሚዲያ መብት በአጠቃላይ ከ 3.07 ሚሊዮን ዶላር በላይ በቀጥታ ገቢ ይሆንበታል።

በቢዝነስ ማማከርና  በሎጂስቲክ ተግባራት ላይ የተሰማራው “ዋን ስቶፕ“ የተባለ ድርጅት በዛሬው ዕለት የማስፋፊያ  ሥራውን በደንበል ሲቲ  ሴንተር  የጀመረ ሲሆን፤  አዲሱ ቢሮውንም አስመርቋል፡፡

ድርጅቱ  ከ20 በላይ ለሚሆኑ ኢትዮጵያውያን  የሥራ እድል መፍጠሩ ተነግሯል፡፡

የ“ዋን ስቶፕ” መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሚክያስ አበራ፣ ይህን ተቋም ከመመስረቱ በፊት የባህር ማዶ ባለሀብቶች አገር ውስጥ ኢንቨስት የሚያደርጉበትን መንገድ የማመቻቸት ስራዎችን  ሲሰራ እንደቆየ ጠቁሞ፤ በሂደት ግን አንድ ተቋም መስርቶ በተደራጀ መልክ መስራት እንደሚያዋጣ በማመን ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ድርጅቱን  እውን ለማድረግ መቻላቸውን ተናግሯል፡፡

በምረቃ መርሀ ግብሩ ላይ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዳያስፖራ አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ተገኝተው፣ እንደ “ዋን ስቶፕ” አይነት ተቋማት ለውጭ ባለሀብቶች የሚያቀርቡት አገልግሎት  ወሳኝነት አለው ብለዋል።

አንድ በአገር ውስጥ ኢንቨስት ለማድረግ የሚሻ ባለሀብት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የህግ  አሰራር በወጉ ተረድቶ ስራውን ለማከናወን እንዲችል ”ዋን ስቶፕ” ተገቢውን ሙያዊ እገዛ እንደሚሰጥ የገለጸው ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ይህም  እቃዎችን  በጉምሩክ በኩል ከማስመጣት ጀምሮ ሀገር ውስጥ እስከሚገቡ ድረስ ያለውን ሙሉ ሂደት መከታተልን እንደሚጨምር ጠቁሟል፡፡

ከቀረጥ ነጻ የሆኑ እቃዎች፣ ፍራንኮ ቫሉታ ኤልሲ የመሳሰሉ ኢንቨስትመንቱን እውን ለማድረግ የሚያግዙ ስርአቶችን በማሳወቅና ተገቢ ሰነዶች እንዲሟሉ በማድረግ ድርጅቱ  የማማከር ሚናውን በአግባቡ ይወጣል ተብሏል፡፡

በአሁኑ ሰአት የውጭ ኢንቨስተሮች ሀገር ውስጥ ገብተው እንዲሰሩ የአማካሪ ድርጅቶች ሚና ከፍተኛ መሆኑን የሚናገሩ  ባለሙያዎች ፤ ኢትዮጵያ በውጭ ምንዛሪ የደረጀች እንድትሆንና ባለሀብቱም እንዲመጣ ሀገር ውስጥ ያለው አሰራር በዘመናዊነትና በቅልጥፍና የታጀበ ሊሆን ይገባል ይላሉ፡፡  

“ዋን ስቶፕ” ከሚያማክራቸው የኢንቨስትመንት ተቋማት መካከል ኤን ኤች ቤይ ፈርኒቸር፣ አቢሲኒያ ግሩፕ ኦፍ ኢንቨስትመንት፣ የአሊባባ ግሩፕ የሆነው ዌል ክላውድ ይጠቀሳሉ፡፡

(ምንጭ፡-ተወዳጅ የመረጃ ማእከል)

 ከሊዮ ቶልስይ ተረቶች ውስጥ እንዲህ የሚል ይገኝበታል።
አንድ ንሥር በዛፍ ላይ ጎጆትሠራለች። እዚያ ውስጥ ጫጩት ትፈለፍላች። አንዲት አሣማ ደግሞ ግልገሎቿን ይዛ ዛፉ ሥር ትመጣለች። ንሥሩዋ ሩቅ በርራ አድን  ልጆቿን ትቀልባለች። አሣማዋ ዛፉ ሥር እየኖረች እጫካው ውስጥ እየገባች እያደነች ውላ ማታ ለልጆቿ ምግብ ታመጣላቸዋለች። በዚህ ዓይነት ንሥርና አሣማ እንደ ጥሩ ጎረቤት እየተማመኑ፣ እየተዋረዱ፣ አንዳቸው ባንዳቸው ላይ ክፉ ላያስ ተስማምተው መኖራቸውን ቀጥላ። በመሰረቱ ንሥርና አሳማ ባንዳቸው ላይ ክፉ ላያስቡ ተስማምተው መኖራቸውን ይቀጥላሉ። በመሠረቱ ንሥርና አሣማ በተፈጥሯቸው አንዳቸው ያንዳቸውን ግልገል ካገኙ የማይምሩ ተፃራሪ ፀባይ ያላቸውና ሊጠፋፉ የሚችሉ ናቸው። አንድ ቀን አንዲት አሮጊት ድመት ወደ ሁለተሩ ሰፈር መጣች። የንስሯንም ጫጩቶች ጡት የሚጠቡትንም የአሳማዋን ግልገሎች፣ ልትበላቸው አሰበች።
ወደ ንሥሯ ሄዳ፤
“ንሥር ሆይ! ለምግና ለአደን ብለሽ ከእንግዲህ ሩቅ መንገድ እንዳትሄጂ። ይቺ አሣማ የምትተኛሽ አይምሰልሽ። መጥፎ ተንኮል እያሰበችብሽ ነው። የዛፉን ሥር እየበጣጠሰችው ነው። እንደምታይው በየቀኑ የሥሩን አፈር እየማሰች ነው” አለቻት። ንስርም ስለምክሯ አመስግናት ተለያዩ
ቀጥላ ደግሞ ወደ አሳማዋ ዘንድ ሄዳ፤
“አሣማ ሆይ! ዘንድሮ ጥሩ ጎረቤት አልተዋጣልሽም። ትላንት ማታ ንሥሯ ለጫጭቶቿ እንዲህ ስትል ሰማኋት፡- ወዳጄ ስለሆንሽ ሆዴ አልችል ብኝ ልነግርሽ መጣሁ” አለች። አሣማም፤ “ምን አለችኝ እባክሽ?” ብላ በጉጉት ጠየቀች።
ድመትም፤ “ምን ስትል ሰማኋት መሰለሽ፡-” ‘ልጆቼ፤ ከእንግዲህ አትራቡም። እንዲያውም ጥሩ ጥሩ ግልገል አሣሞች እያመታሁ እቀልባችኋለሁ። አይዟችሁ፤ ይቺ አሳማ የምትኖርበት ድረስ መጥታ ግልገሎቿን መሬት ላይ አፍስሳልናለች። እናታቸው ራቅ ብላ ስትሄድ ቆንጆ ቆንጆ ግልገሎቿን እያመጣሁ አበላኋቸው’” አለች።
ከዚህ ቀን ጀምሮ ንስር ወደ ሩቅ ቦታ እየሄደች ማደኗን አቆመች።
አሳማዋም ከዚህ ቀን ጀምሮ ወደ ጫካ መሄዷን አቆመች።
የንስርም ቻጩቶች፣ የአሳማም ግልገሎች ከቀን ወደ ቀን ለረሃብ እየተጋለጡ ሄዱ። ውሎ አድሮ፤ የንስር ልጆች አንድ በአንድ ከዛፍ ላይ እየተፈነቸሩ ይወድቁ ጀመር። የአሳማም ግልገሎች እናታቸው ለመኖሪያ ወደማሰችው ጉድጓድ ውስጥ ሞተው ይገኙ ጀመር።
አሮጊቷ ድመት የሞቱትን ጫጩቶችና ግልገሎች እያፈራረቀች “ተመጣጠነ ምግብ ማለት ይሄ ነው!”፤ እየተመገበች፤ ፌሽታ ስታደርግ ከረመች።
ንስርና አሳማ ሲያለቅሱ ሰነበቱ።
***
 ከላይ ዛፍ ከታች መሬት ለመኖሪያ ካተመቸ አገር አማን አትሆንም።
የህዝቡ ኑሮ አስተማማኝ አይንም። በዜጎች መካከል መተማመን አይኖርም። አንድም ፍትሃዊት እየጠፋ “በጨው ደንደስ በርበሬ ተወደስ ይሆናል”። አንድም ደግሞ ቃልኪዳን ፈርሶ፣ የተደላደሉበት ተንሸራቶ “ያመኑት ፈረስ ጣለው በደንደስ” ይሆናል። ከላይ በተረቱ እንዳየነው፤ ተቻችለውና ተስማምተው ለመኖር የሚችሉትን በማቆር፤ እንጠቀማለን ለሚሉ አለመመቸት ተገቢ ነው።
እጅግ የከረሩ አቋሞች ሚያመጡትን ጉዳት አንዳንዴ ከህዝብና ከሀገር ጥቅም ጋር ማየት ተገቢ ነው። በፓርቲዎች ደረጃ ሲታሰብ የኔ ልማት የሌላው ጥፋት የሚል እሳቤ ብዙ አያራምድም። በአገርኛ አባባል፤ “ሞትሽ እውነት በሆነና ልጅሽን ማሳደጉ እኔ በቸገረኝ፤ አለች አሉት” እንደተባለው ማለት ነው።
በዓለም ላይ እንደታየው ብዙ ለሥልጣን ሚታገሉ የፖለቲካ ሃይሎች ሁኔታዎች በውጥረት ሲሞሉ ምክንያታዊ መሆናቸው እየላላ በአጭር ጊዜ መፍትሄ ላይ ይተማመናሉ።
ይኸውም በአብዛኛው ስሜታዊና ጉልበተኛነት የሞላ ሆኖ ነው የሚገኘው። ይሄ በፈንታው ሰላም ያሳጣናል። በሀገራችን በተካሄደው ምርጫ ህዝቡበነቂስ ቀጥቶ ድምጹን ለፈለገው ወኪሉ መስጠቱ ለዲሞክራሲዊ ጎዳና ጥርጊያውን የማመቻቸቱን ያህል፤ በቸልተኝነት በማንአለብኝም በሚሰሩ ስህተቶች መካከል ፍጻሜ እንዳናይ ከተደረግን፤ በዲሞክራሲያዊነት ስም ሀሳዊ- ዲሞክራሲ ይጫነናል።
አንድ ጸሐፊ ስለተሳትፎአዊ ዲሞክራሲ ሲጽፍ፤ “በጥረት ህዝብን ማሳተፍ የመቻሉን ያህል በጉልበት የተሳትፎውን ፍሬ መከልከል ከቶ አይቻልም” እንዳለው በሀገራችን ዲሞክራሲያዊ ንፍቀ-ክበብ እንዳይጨልም ማድረግ ወሳኝ ነገር ነው።
በየትኛውም መልኩ ሰላምንም፣ ዲሞክራሲንም ማጣት ሀገራችን ዛሬ ልትቋቋመው የማትችለው እዳ ነው። የተረገመን እግር፤ በቅሎም ጫማም ይነሳዋል እንደሚባለው ሲሆን ነው። ማለት ነው።
“ከቶውንም ትላንት የነበረውን ምርጫ ሆነ ፖለቲካዊ አካሄድ ዛሬ ለምንሰራው ስህተት፤ መሸፈኛ አልያም መጸጸቻ እስከመቼ ነው? ግትርነት፣ ጉልበትና ስሜታዊነት ባላንጣ ላይ ብቻ ሳይሆን የራስንም ወገን እንደሚያሳጣህ ቀደምት ጸሀፍት ይናገራሉ። ሸክስፒር እንዲህ ይጠይቀናል፡- “… እልህ እስከምን ይዘልቃል።”
የት ድረስ ነው ግትር ጽንፉ
በባላንጣ ሰበብ ምክንያት፣
የራሱን ወገን ማርገፉ?...”
ዲሞክራሲ ስንል በህዝብ መወከል፣ በፖለቲካ ጉልበት የሆነበት ግን የህዝብ ተአማኒ አገልጋይ የሚኮንበት አትበጀኝም ሲል ህዝብ በቃኸኝ፣ አትወክለኝም ሊል የሚችልበት፤ የሲቪልና የፖለቲካ መብት እንዲከበር የሚደረግበት፤ ህዝብ ህጋዊና ህገ-ወጥ የሆነውን ነገር በውል አውቆና መብቱን ተረድቶ ሊያስከብር የሚነሳበት መነሳቱን እንደወንጀል የሚቆጠርበት፣ የማይሰጥ-የማይነጠቅ ነጻነት የሚቀዳጅበት ማለት ነው።
ይህንን ስንልም ዲሞክራሲ ምሉዕ ይሆን ዘንድ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶቹንም ያካተተ መሆኑን ከቶም ሳንዘነጋ ነው።
ወደ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ የሚያራምደንን ምርጫ አንድ እርምጃ ብለን ለመጓዝ የምርጫውን ዘላቂ ውጤት፣ የድጋሚ ምርቸውን ወሳኝ ቁጥርና አግባብ ያለው ቆጠራ እንዲኖር ታዛቢዎች እውነተኛ ውሳኔ፣ የስሞታዎች የተጣራ ውጤት ወዘተ ተደምረው ነው ፍሬ የሚገኘው፤ ሁሉም ተፎካካሪ ወገኖች ትልቁን የሀገር ስብእና ዘላቂውን የህዝብ ጥቅም ቀዳሚ አድርገው ካስተዋሉ ነው። አለበለዚያ ቻይናውያን እንደሚሉት “የባህር-ዳርቻ የወፍና የባህር አሣ ሲታገሉ አሣ-አጥማጅ አይቀማውም።”

ቶሎ ማስረከብና ልዩ ዲዛይን ዋና መገለጫዎቼ ናቸው ብሏል

ባለፉት 27 ዓመታት በመንገድ ግንባታ ሥራ ልምድ እንዳካበተ የገለጸው ዲ ኤም ሲ ሪል ስቴት ወደ መኖሪያ ቤት ማልማት መግባቱንና ለነባር ደንበኞቹ ልዩ ቅናሽ ማቅረቡን አስታወቀ። ድርጅቱ ይህንን ያስታወቀው ከትላንት በስቲያ ለቡ መብራት ሃይል በሚገኘው የግንባታ ሳይት ለመገናኛ ብዙሃን ባደረገው የጉብኝትና የመግለጫ መርሃ ግብር ነው። ዲ ኤም ሲ ሪል እስቴት በዳንኤል ማሞ ኮንስትራክሽን (ዲ ኤም ሲ) ስር ካሉ አምስት ኩባንያዎች አንዱ ሲሆን በተለይም በሀዋሳ በአርባ ምንጭና በሌሎች አካባቢዎች ላለፉት 27 ዓመታት ያካበተውን የመንገድ ግንባታ ልምድ ወደ ሪል እስቴት ልማት በማምጣት ለቤት ፈላጊዎች ሲኖሩበት የሚደሰቱበት ቤት ለማስረከብ አዳዲስ ቴክሎጂዎችንና 24 ሰዓት የሚሰሩ ሰራተኖችን ይዞ ወደ ስራ መግባቱን የኩባንያው ሃፊዎች አብራተዋል።
ዲኤምሲ ወደ ሪል እስቴት ልማት ከመግባቱ በፊት በዘርፉ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመለየት አንድ ዓመት ተኩል የፈጀ ጥናት ማካሄዱ የተገለጸ ሲሆን በጥናቱም ከተለዩት ዋና ዋና ችግሮች ቤቶቹን ለነዋሪዎቹ በወቅቱ የማስረከብና የዲዛይን ችግር ቀዳሚዎቹ ናቸው ሲሉ ከኩባንያው ሃፊዎች አንዱ አቶ ፋንታሁን ግርማ ገልጸው ዲኤምሲ ይህን ለመቅረፍ አንድ ስላፕ በ10 ቀን የሚሞላ ቴክኖሎጂ ከጣውላና ከእንጨት የጸዳ አሉሙኒየም ፍሬም ወርክ ቴክሎጂን በመጠቀም እስከ ሁለት ዓመት ከስድስት ወር ባለ ጊዜ ውስጥ ለማስረከብ 24 ሰዓት እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል። በለቡ መብራት ሃይል በ65ሺ 395 ካ.ሜ ዋናው መንገድ ላይ በሚገነባው ትልቅ የመኖሪያ መንደር ለነባር ደንበኞቹ እስከ 1 ነጥ አራት ሚሊዮን ብር ቅናሽ ማድረጉን የገለጸ ሲሆን በአንድ ህንፃ ላይ እስከ 200 አባዎራ እንደሚኖርና በየህንፃው ለ200 አባወራ አንድ ቤት በእጣ ለእድለኛ እንደሚሰጥም ተነግሯል።
ከስቱዲዮ እስከ ባለ 4 መኝታ ቤት ለገበያ ያቀረበው ኩባንያው ቤቶቹ ከ6 ሚሊዮን እስከ 20 ሚሊዮን የሚደርስ ዋጋ እንዳላቸው የተገለፀ ሲሆን ባለ 186 ካ.ሜ ባለ አራት መኝታ ቤት  ወዲያው ከፍሎ ለሚገዛ 6 ሚሊዮን ማለትም የ1 ስቱዲዮ መግዛ ያህል ቅናሽ ይደረጋል ብለዋል የዲ ኤም ሲ ሃላፊዎች።
ቤቶቹን በጊዜ ማስረከብ ስለመቻላቸው ለቤት ፈላጊዎች ዋስትናቸው ምንድን ነው በሚል ከጋዜጠኞች ለተነሳው ጥያቄ ሃላፊዎቹ ሲመልሱ ቤቶቹን በ2 ዓመት ከስድስት ወር ለማስረከብ ውል መገባቱን ነገር ግን ከአቅም በላይ የሆነና አስገዳጅ ጉዳይ ካጋጠመ  ከ3-6 ወር የጊዜ ገደብ ጭማሪ ኩባንያው እንደሚጠይቅ ሆኖም በዚህ ጊዜ ማስረከብ ካልቻለ የቤቱን ዋጋ 20 በመቶ ኩባንያው እንደሚቀጣ በውሉ ላይ መቀመጡን ሃላፊዎቹ አብራተዋል።
 ለደንበኞች ተዓማኒ ለመሆንም ሆነ በወቅቱ ባለማስረከብ ከሚመጣው ቅጣት ኩባንያው ራሱን ለመጠበቅ ለሰራተኞች በግንባታው ሳይት ላይ መኖሪያ፣ ምግብና ሌሎች አስፈላጊ ቁሳቁሶችን አሟልቶ 24 ሰዓት ግንባታው መቀጠሉም ተብራቷል። ዲ ኤም ሲ ሪል ስቴት በአሁኑ ወቅት ቤቶቹን በካሬ 90 ሺህ ብር ለሽያጭ ያቀረበ ሲሆን በቀጣይ በፒያሳ፣ በቦሌና በሌሎች ተመራጭ ቦታዎች ቤቶቹን ለማልት መዘጋጀቱን ገልጿል።
ዲኤም ሲ ሪል ስቴት የሚገነባቸው ቤቶች በልዩ ዲዛይን የተገነቡና ለኗሪው አስደሳች ናቸው የተባለ ሲሆን በየአንዳንዱ ህንፃ ላይ አምስት አሳንሰሮች የሚገጠሙና ከአምስቱ አንዱ እስከ ዛሬ በሪል እስቴት ባልተለመደ መልኩ ትልልቅ እቃዎችን የሚያጓጉዝ ሰርቪስ ሊፍት ይኖረዋል ተብሏል። መናፈሻ፣ ጂም ፣ የመዋኛ ገንዳዎች፣ የመኪና  ማቆሚያ፣ የህፃናት መጫዎቻ ቦታና ሌሎችም ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑ መሰረተ ልማቶች የሚገኙበት ቅንጡ መንደር እንደሚሆን የገለጹት ኃላፊዎቹ በቀጣይ ከሚዲያ ባለሙያዎች ጋር ያለውን ቁርኝት ለማጠናከር በማሰብ ጋዜጠኞቹ በተመቻቸው ጊዜ ቀረፃና ኤዲቲንግ የሚሰሩበት ትልቅና ዘመናዊ ስቱዲዮ በመገንባት ላይ መሆኑንም ዲኤምሲ ሪል እስቴት ሀሙስ ረፋድ ላይ ለቡ መብራት ሀይል በሚገኘው የሽያጭ ቢሮው በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ  አብራሯል።

Page 6 of 700