Administrator

Administrator

   ቴለር ኤንድ ሰንስ የተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ፣ የአገሪቱን ኩባንያዎች የመመዝገብ ስልጣን በተሰጠው ካምፓኒስ ሃውስ የተሰኘ የመንግስት ተቋም ላይ፣ ስሜን ሲመዘግብ የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ለተለያዩ ቀውሶች ዳርጎኛል ሲል በመሰረተው ክስ የ9 ሚሊዮን ፓውንድ ካሳ እንዲከፈለው ፍርድ ቤት እንደበየነ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፍርዱ የተላለፈበት የመንግስት አካል በአገሪቱ በኪሳራ ላይ የሚገኙ ተስፋ ቢስ ኩባንያዎችን በሚመዘግብበት ሰነድ ላይ፣ ከስድስት አመታት በፊት በማንችስተር የሚገኝን ቴለር ኤንድ ሰን የተባለ የከሰረ ኩባንያ ለመመዝገብ ፈልጎ፣ በስህተት የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ቴለር ኤንድ ሰንስ ብሎ በመመዝገቡና መረጃውን ለህዝብ ይፋ በማድረጉ ነው የኩባንያው ሃላፊዎች ክስ የመሰረቱበት፡፡
ኩባንያው ስሙ ተዛብቶ መመዝገቡንና በኪሳራ ላይ እንደሚገኝ የሚያሳየው መረጃ ለህዝብ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ 250 ሰራተኞቹ ስራ መልቀቃቸውን፣ የብድር አቅራቢ ተቋማትና 3ሺህ ያህል አቅራቢዎችም ከኩባንያው ጋር የነበራቸውን የስራ ግንኙነት ማቋረጣቸውን የኩባንያው ጠበቆች ተናግረዋል፡፡
በምህንድስና ስራ ላይ የተሰማራውና ከ100 አመታት ጀምሮ ወታደራዊ መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው  ቴለር ኤንድ ሰንስ ኩባንያ የቀድሞ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፍሊፕ ዴቪሰን ሰብሪ፣ ከስድስት አመታት በኋላ የፊደል ግድፈቱ መከሰቱን ሰምተው ከሁለት ወራት በፊት ከኩባንያው አመራሮች ጋር ስብሰባ ማድረጋቸውንና ክሱን መመስረታቸውን ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዙ ሮያል ኮርት ኦፍ ጀስቲስ ፍርድ ቤት ካሳ እንዲከፍል የተወሰነበት የመንግስት ተቋም በበኩሉ፣ የፊደል ግድፈቱን መፈጸሙን ቢያምንም፣ በኩባንያው ላይ ለፈጠረው ስህተት ይሄን ያህል ገንዘብ በካሳ እንዲከፍል የተጣለበትን ቅጣት ተቃውሟል፡፡

ፕሬዚዳንቱና 160 ባለስልጣናት ጥቁር መኪና ትተው ነጭ ሊሙዚን መጠቀም ጀምረዋል

 በመካከለኛው እስያ የምትገኘው ቱርክሜኒስታን፣ የአገሪቱ ዜጎች ከአሁን በኋላ ጥቁር ቀለም ያላቸው መኪኖችን ወደ ግዛቷ እንዳያስገቡ መከልከሏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የቱርክሜኒስታን የጉምሩክ ባለስልጣናት፣ የአገሪቱ ዜጎች ጥቁር ቀለም ያላቸውን መኪኖች ከውጭ አገራት ገዝተው እንዳያስገቡ የሚከለክል ህግ ከሰሞኑ ይፋ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ክልከላውን በምን ምክንያት ተግባራዊ እንዳደረጉት ግልጽ አለማድረጋቸውን አስታውቋል፡፡
ባለስልጣናቱ ከውጭ አገራት መኪና ገዝተው የሚያስገቡ ኩባንያዎችን፣ ከጥቁር መኪኖች ይልቅ ነጭ ቀለም ያላቸውን መኪኖች እንዲያስገቡ እያግባቡ መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፣ ነጭ ቀለም የመልካም ዕድል ተምሳሌት እንደሆነ መግለጻቸውንም ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉርባንጉላይ በርዲሞሃመዶቭ፤ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ ጥቁር መኪና መጠቀም ማቆማቸውንና ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎችም ነጫጭ ሊሙዚኖችን መጠቀም መጀመራቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ እሳቸውን ተከትለውም 160 ያህል የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት በነጭ ሊሙዚን መዘዋወር እንደጀመሩ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የቅንጦት መኪና እንዳይገባ የሚከለክል፣ የተለየ ታርጋ ቁጥር መለጠፍና እይታን የሚጋርድ ሽፋን የተለጠፈባቸውን መኪኖች ማሽከርከር የሚያግድ እንዲሁም ሌሎች ከመኪኖች ጋር የተያያዙ ጥብቅ ህጎችን ማውጣቱንና ተግባራዊ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ዘገባው ያመለክታል፡፡

አንድ አፍሪካዊ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ለብዙ ዓመታት በምዕራብ አገራት ትምህርቱን ሲከታተልና ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ትውልድ ቀዬው ይመለሳል፡፡
የትውልድ መንደሩ እንደደረሰም አንድ የመንደር ልጅ ሃይቅ ዳር ቆሞ ይመለከታል፡፡ ልጁ ሰዎችን በታንኳ እያሳፈረ የዕለት ጉርሱን የሚቃርም ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ ጀልባው ላይ ተሳፍሮ አፍታ እንኳን ሳይቆይ ልጁን በጥያቄ ያጣድፈው ገባ፡፡
ፕሮፌሰር ፡- ፍልስፍና አንብበሃል?
ልጁ ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር ፡- ከንቱ ነህ!
ፕሮፌሰር - ሥነ ልቦናስ አንብበሃል?
ልጁ፡- በፍጹም!
ፕሮፌሰር፡- ውዳቂ ነህ!
ፕሮፌሰር ፡- እሺ ታሪክስ?
ልጁ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር፡- ለምንም የማትሆን አልባሌ ሰው ነህ!
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ አደገኛ ማዕበል ተነሳና ጀልባዋን እንደ ጉድ ይንጣት ጀመር፡፡
ፕሮፌሰሩ በታላቅ ፍርሃት እየራደ ልጁ እንዲረዳው ይጮህ ገባ፡፡ ልጁ ፕሮፌሰሩን በትዝብት እያየው፤ “ፕሮፌሰር፤ ዋና አልተማሩም?” ሲል ጠየቀው፡፡ (አሁን ከንቱው ማነው? በሚል ቅላፄ)

Saturday, 31 January 2015 12:48

ዝብርቅርቅ ጥያቄ

….. (እኔ ላንቺ ማሬ)
አበባ ሞልቶልኝ - ዕድሜዬን ቀጥፌ
ቄጤማ እያለ - እኔኑ አንጥፌ
ወፎች ስላልበቁኝ - ጥርሶቼን አርግፌ .....
እኔ ቀልጬልሽ -
ሜዳ ላይ ፈስሼ - ለፍቅሬ ሳበራ
በገዛ መብራቴ -
ልብሽ ሌላ ‘ያየ - ለግብዣ ከጠራ .....”
.
አይጣልብሽ አንቺው - ያ’ይምሮዬ ነገር
አንቺን እያሰብኩኝ - ትዝ የሚለኝ ሀገር
አሁን የኔን ነገር - ምን ይሉታል ማሬ?
ምን ያገናኝሻል - እስቲ አንቺን ካ’ገሬ?
“…..(እኔማ ላ’ገሬ - )
.
“ሀገሬ ተራራሽ” - እያልኩኝ ዘፍኜ
ያ ቀዳዳነቷን - በአፌ ደፍኜ
እየፆምኩ ስጸልይ - ለሀገሩ ጌታ
ሁሌ እያሰርኩኝ - ሁል ጊዜ ስፈታ ..... ”
.
ግድ የለሽም በቃ -
የምር አብጃለሁ - ሙች ለይቶልኛል
እንዴት “ሀገር” ሳስብ -
እግዜር ከነግርማው - ይደቀንብኛል?
.
“ ….(እግዜር ደ’ሞ እኔን - )
ደካማዋ ነፍሴ - ከእቅፉ ርቃ
ነገር ሲጋጭባት - ሺህ ጊዜ ጠይቃ
እሱ እንደሩቅ ሰው - ዝም - ጭጭ - በቃ
ይህን ጊዜ ነፍሴ - በሃሳቧ ደርቃ ....”
.
ገላጋይ እንቅልፌ - አፋፍሶኝ ይነጉዳል
ያ ባካኙ ልቤም - እንቅልፉን ይወዳል!
.
ማሬ
እኔና እግዜሩ - አንቺና ሀገሬ
ጥያቄዎች ነን - በልቤ ‘ስከዛሬ
ስላ’ንዳችን ሳስብ -
ሌላው ብቅ እያለ - እዛው ላይ ነኝ ዞሬ!!

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አይጥ ሁሌ እንደጉድ የሚጠላው ድመት ነበር አሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ህይወቱ ይረበሻል፡፡ መንፈሱ እረፍት ያጣል፡
አንድ ቀን ድንገተኛ አውሎ ንፋስ መጣ - በሀገሩ!
የትም መሄጃ ያጣው አይጥ፣ ለድመቶች ጥቃት ተጋለጠ፡፡
አይጥ እንግዲህ ወደ ከተማው ታዋቂ ጠንቋይ ሄደ፡፡ ችግሩንም አዋየው፡፡
ታላቁ ጠንቋይ ሁኔታውን በመገንዘብ፤ አይጡን ከአይጥነት ይልቅ ድመት ቢሆን ይሻለዋል፤ በሚል እሳቤ ወደ ድመት ለወጠው፡፡
ሆኖም አይጡ ወደ ድመት መለወጡ፣ ብዙ አልለወጠውም! የእንስሳት ባህሪ ሆኖበት ውሻን ክፉኛ መፍራት ጀመረ!
ይሄን ያስተዋለው አዋቂ ድመቱን ወደ ውሻ ለወጠው፡፡
ቀጠለና ያ ከድመትነት ወደ ውሻነት የተለወጠው እንስሳ፤ አሁን ደግሞ ነብርን መፍራት ተማረ!
ያ ታጋሽ አዋቂም፤ አስቦ አስተውሎ የድመቱን የመጨረሻ ደረጃ በመገንዘብና ትዕግሥት የበዛው በመሆኑ ነብር ላድርገው ብሎ ወሰነና ነብር አደረገው!
ያም ሆኖ ያ ነብር አዳኝ ቢመጣብኝስ? ብሎ ሥጋት በሥጋት ሆነ!
ይህንን ሁሉ ዕድል ሰጥቼው ካልተለወጠ የራሱ ጉዳይ ነው አለ፡፡ ከዚያም መልሶ ወደ አይጥነቱ መመለስ ዋናው ጉዳይ ነው! አለ!
ከዚያም አይጡ ወደ አይጥነት መመለሱ ግድ ሆነና ዛሬ አምነን ወደተቀበልነው አይጥ ተመለሰ!!
*   *   *
ማንነትን በማናቸውም አጋጣሚና አስገዳጅ ሁኔታ መለወጥ፣ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው! የትኛውንም ዓይነት ፍጡር እንሁን ብለን መከራን እናሳልፍ ብንል፤ ከተፈጥሮአችን ውጪ የረባ ፍሬ አናገኝም ወይም ልዩ ፍሬ አናተርፍም፡፡
አንድ ግብ ጋ ለመድረስ የግድ ሁለት የፍሬ ምንትነት መኖር የለበትም፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዘመን፤ በዚህም ሆነ በዚያ ቦታና ወቅት ልናገኝ የምንችለውን ነገር በዛሬ ሽኩቻ አናክሽፈው! ከህብረት ውጩ መከፋፈል ፋይዳ የለውም፡፡
ሙግታችንና ክርክራችን ተሰብስቦ ሲታሰብ ጥቅሙ “በግልፅም መረጃ” መንፈስ ታላቅ ነው ሊባል ቢችልም፤ “ለማን እየጠቀመ ነው?” የሚባለውን አንድምታ አለማሰብ ከንቱ ቦታ ይጥለናል! የፓርቲዎች ሁሉ ውክቢያና “ጫጫታ” ስለምን በአሁኑ ወቅት ሆነ? ብሎ መጠየቅ የአባት ነው፡፡ ስለማንስ ጥቅም? “ምርጫ አያስፈልግም!” ከሚል አስተሳሰብ እስከ “ምርጫ ከተሳተፍን ግልፅ አቋም፣ ግልፅ ማንነት፣ ግልፅ ውክልና ሊኖረን ይገባል!” እስከሚለው ድረስ መወያየት አለብን ማለት አገራዊ ጥያቄ ነው! ስንተዋወቅ - አንተናነቅ ድረስ ማሰብ ቢቻል ግን መልካም ነው!
የምረጡና ካርድ ውሰዱ ውትወታ ስሜት፣ የወጣት እንቅስቃሴ (በድሮው አባባል የአኢወማ ግዳጅ)፣ የሴቶች ጥያቄ፣ ድህነት ቅነሳና ልማት… ወዘተ፡፡ የእስከ ዛሬው እያንዳንዱ መንግስት ተደጋጋሚ (Replica) ነገሮች ቢመስሉም፣ ዲሞክራሲ ሂደት እንጂ ቁርጥ ክፍያ ስላልሆነ “ባመጣህበት ውሰደው” የሚለው የነጋዴ ቋንቋ የግሎባላይዜሽን አንዱ ገፅታ ነው እንለዋለን!
መተቸትንና መተቻቸትን ለማይቀበል ሥርዓት፤ ይሄን ተቀበል፣ ይሄንን አትሻ ለማለት ብዙ እንግልት እንዳለበት፣ ስለ ዲሞክራሲ ብለህ ይሄን እሻ፣ ይሄን አትሻ ብሎ አጉል እሰጣ ገባ ውስጥ መግባት ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ስለዲሞክራሲ፣ ስለፍትህ፣ ስለሰብዓዊነና ህዝባዊ መብት፣ ስለሙስና አደጋ ለማውራት የተገፋው፣ የተበደለውና መብት አጣሁ የሚለው ወገን ተናጋሪ፣ ካልሆነና ብሶቱን ካላስረዳ፣ በገዢው ፓርቲስ፣ በተቃዋሚስ ወገን ማን አቤት ይላል? “ሁሉም ፈረስ ላይ ከወጣ ማን ገደል ያሳያል?” የሚለው ተረት ቁምነገሩ ይሄው ነው ጎበዝ!


        ባለፈው ሚያዚያ የታሰሩት ሦስት ጋዜጠኞችና ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪዎች ላይ አቃቤ ህግ ያቀረበው የሽብር ክስ እንዲቀጥል ሰሞኑን በፍ/ቤት መፈቀዱ እንዳሳሰበው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገለፀ ሲሆን፤ የክሱ ሂደት በግንቦቱ ምርጫ ተአማኒነትና ዲሞክራሲያዊነት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያሳድራል ሲል ነቀፈ፡፡ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐሙስ እለት ባወጣው መግለጫ፤ በኢትዮጵያ የፀረ ሽብር ህጉ ላይ ቀጥተኛ ትችት ባይሰነዝርም፤ የህጉ አተገባበር ግን በህገመንግስት የተረጋገጡ የፕሬስ እና የሐሳብ ነፃነቶችን የሚቃረን እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ ከዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች በተጨማሪ፣ ካሁን ቀደም ሌሎች ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ አንቀሳቃሾችና የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችም በፀረ ሽብር ህጉ እንዲከሰሱ መደረጋቸውን የሚኒስቴሩ መግለጫ አስታውሷል፡፡
ይህም፤ የህጉ አተገባበር፣ በህገ መንግስቱ የተረጋገጡ የፕሬስና የሃሳብ ነጻነቶች ላይ ጉልህ ጥያቄዎችን አስነስቷል ብሏል፡፡
የፕሬስ፣ የሃሳብ ነጻነቶች የአንድ ዲሞክራሲያዊ ማህበረሰብ መሰረታዊ ባህሪያት ናቸው ያለው መግለጫው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ለእነዚህ ነጻነቶች መከበርና ለዲሞክራሲ ግንባታ ቁርጠኝነት እንዲያሳይ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች የፍርድ ሂደት ፍትሃዊነትና ግልፅነት የተላበሰ፣ እንዲሁም ከአገሪቱ ህገ መንግስቱና ከአለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ስምምነቶች ጋር በማይጣረስ መልኩ እንዲካሄድም ሚኒስቴሩ በመግለጫው ጠይቋል፡፡ የፍርድ ሂደቱ ከፖለቲካዊ ተጽዕኖ የጸዳና ለህዝብ እይታ ክፍት እንዲሆን ማድረግ ይገባል ብሏል - መግለጫው፡፡

አለማችን በመጪዎቹ 10 አመታት 28 ስጋቶች ይጠብቋታል

በመጪዎቹ አስር አመታት አለማችንን ይፈታተኗታል ተብለው ከሚጠበቁ ስጋቶች መካከል አለማቀፍ የእርስ በእርስ ግጭቶችና ከውሃ ጋር ተያያዥ የሆኑ ቀውሶች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዙ በመካሄድ ላይ በሚገኘው የ2015 የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ጉባኤ ላይ ተገለጸ፡፡የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ሪፖርት እንደሚለው፣ አለማቀፍ ግጭቶች የመከሰት ዕድላቸው ከአየር ንብረት ጋር ተያያዥ ከሆኑ የተፈጥሮ አደጋዎች፣ ከአገራት የአስተዳደር ችግሮች፣ ከመንግስታት ቀውሶችና ከስራ አጥነት የበለጠ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡የህዝቦችን ህልውና አደጋ ላይ በመጣልና ጉዳት በማድረስ ረገድም፣ ከሌሎች አደጋዎች የበለጠ ተጽዕኖ ይፈጥራል ተብሎ የሚሰጋው የውሃ እጥረት እንደሆነ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ በአገራት ውስጥ የሚፈጠሩ የእርስ በእርስ ግጭቶች፣ የተላላፊ በሽታዎች መዛመት፣ አውዳሚ የጦር መሳሪያዎችና ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያያዥ የሆኑ ቀውሶችም ጉዳት ያደርሳሉ ተብለው የሚጠበቁ ሌሎች የአለማችን ቀዳሚ ስጋቶች ናቸው፡፡
በዘንድሮው የአለም የኢኮኖሚ ፎረም በመጪዎቹ አስር አመታት አለማችንን ይገጥሟታል በሚል ያስቀመጣቸው ስጋቶች 28 ያህል ሲሆኑ፣ ስጋቶቹም ኢኮኖሚያዊ፣ አካባቢያዊ፣ ጂኦፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ከቴክኖሎጂ ጋር ተያያዥ ናቸው፡፡
በያዝነው የፈረንጆች አመት 2015 አለማችንን በከፋ ሁኔታ ያሰጓታል ተብለው የተቀመጡት ስጋቶች ጂኦፖለቲካዊ እንደሆኑ የጠቀሰው ሪፖርቱ፣ እነዚህ ስጋቶች በአገራት ውስጥ የሚከሰቱና ክልላዊ ተጽዕኖ የሚያደርሱ የእርስ በእርስ ግጭቶችን ያጠቃልላሉ ብሏል፡፡
በስዊዘርላንድ ዴቮስ በመካሄድ ላይ በሚገኘውና ዛሬ በሚጠናቀቀው 45ኛው የ2015 የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ጉባኤ ላይ ከ100 የአለማችን አገራት የተወከሉ ከ2ሺህ በላይ የአገር መሪዎች፣ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች፣ የኩባንያ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈውበታል፡፡
በተያያዘ ዜና ኦክስፋም ኢንተርናሽናል በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ያወጣው የጥናት ውጤት፣ ካለፉት ስድስት አመታት ወዲህ በአለማችን የሃብት ክፍፍል ኢ -ፍትሃዊነት እየጨመረ መምጣቱን ይጠቁማል፡፡
በመጪው አመት ከአለማችን አጠቃላይ ህዝብ 1 በመቶ የሚሆነው፣ ቀሪው 99 በመቶ ህዝብ ከሚኖረው ድምር የሃብት መጠን የሚበልጥ ሃብት ይኖረዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ይህ 1 በመቶ ህዝብ በመጪው አመት የዓለማችንን ሃብት ከግማሽ በላይ ጠቅልሎ ይይዛል ተብሎ እንደሚገመት ገልጿል፡፡

ዘመን አይሽሬ የሙዚቃ ስራዎቹን ለአለም ያበረከተው ጀርመናዊ የሙዚቃ ሊቅ ሉድዊንግ ቫን ቤትሆቨን ከፍተኛ ተወዳጅነት ያተረፉ ምርጥ ስራዎቹን የቀመረው፣ የልብ ምቱን መነሻ በማድረግ እንደሆነ በሙዚቃዎቹ ዙሪያ የተሰራ አንድ ጥናት ማስታወቁን ሃፊንግተን ፖስት ዘገበ፡፡ሰሞኑን የወጣው የዋሽንግተንና የሚቺጋን ዩኒቨርሲቲዎች የጋራ ጥናት እንዳለው፣ በአብዛኞቹ ተወዳጅ የሙዚቃ ስራዎቹ ውስጥ የሚደመጡት ያልተለመዱ ምቶች ቤትሆቨንን ለሞት እንዳበቃው የሚገመተው ካርዲያክ አሪዝሚያ የተባለ የልብ ህመም ከሚፈጥረው የልብ ምት መዛባት ጋር የተያያዘ ሊሆን ይችላል፡
ዩኒቨርሲቲዎቹ በጋራ ያሰሩትና የልብ ህክምና ዶክተሮች፣ የህክምና ታሪክ አጥኝዎችና የሙዚቃ ተመራማሪዎች የተሳተፉበት ይህ ጥናት፣ በቤትሆቨን የልብ ጤንነትና በሙዚቃዎቹ መካከል ያለውን ግንኙነት በተመለከተ ጥልቅ ፍተሻ እንዳደረገ ተነግሯል፡፡
ቤትሆቨን መስማት የተሳነው መሆኑ፣ ለልብ ምቱ ትኩረት የሚሰጥበትን ዕድል እንደፈጠረለትና፣ የልብ ምቱ በሙዚቃ ስራዎቹ ላይ ተጽዕኖ ሳይፈጥርበት እንዳልቀረ ተመራማሪዎቹ ገልጸዋል፡፡

በቅርቡ በሁለት ፈረንሳውያን ሙስሊም ወንድማማቾች ፓሪስ ውስጥ የተፈፀመውን የሽብር ጥቃት ተከትሎ በአውሮፓ በተለይም በፈረንሳይና በጀርመን የሚኖሩ አናሳ ሙስሊሞች ጫና በርክቶባቸው ውጥረት ውስጥ ገብተዋል፡፡
ከትላንት በስቲያ በሺዎች የሚቆጠሩ ጀርመናውያን የምዕራቡን አለም “እስላማዊነት” በመቃወም አደባባይ ወጥተው ድምፃቸውን አሰምተዋል፡፡ የነገርየው አያያዝ አላምራቸው ያለ ሙስሊሞችም የገባቸውን ስጋት ለመግለጽ በፊናቸው አደባባይ በመውጣት አቤት ብለዋል፡
ጉዳዩ መገረምን የፈጠረባቸው እጅግ በርካታ ሰዎች ታዲያ አውሮፓውያን አብረዋቸው በሚኖሩት ሙስሊሞች ይህን ያህል ስጋት የገባቸው ቁጥራቸው ምን ያህል ቢሆን ነው የሚል ጥያቄ ማንሳታቸው አልቀረም፡፡
በአውሮፓ የሚገኙ ሙስሊሞች ቁጥር ከተቀሩት ጋር ሲወዳደር አናሳ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ በፈረንሳይና በጀርመን አተካራው ያየለበት ዋነኛው ምክንያት ሌላ ሳይሆን በምዕራብ አውሮፓ ከሚገኙት ሙስሊሞች አብዛኞቹ የሚገኙት በሁለቱ አገራት በመሆኑ ነው፡፡ በሁለቱ ሀገራት ብቻ 4.7 ሚሊዮን ሙስሊሞች ይኖራሉ፡፡
63 ሚሊዮን ከሚሆኑት ፈረንሳውያን ውስጥ 7.5 በመቶ የሚሆኑት ሙስሊም ናቸው፡፡ ይህ ቁጥር ደግሞ በምዕራብ አውሮፓ ከፍተኛው ነው፡፡ 82 ሚሊዮን ከሚሆኑት ጀርመናውያን መካከል ደግሞ የሙስሊሞቹ ቁጥር 5.8 በመቶ ነው፡፡ በፈረንሳይ ከሚኖሩት ሙስሊሞች እጅግ አብዛኞቹ የሰሜን አፍሪካ ተወላጆች ሲሆኑ በጀርመን ከሚገኙት ሙስሊሞች ውስጥ ደግሞ እጅግ የሚበዙት ትውልዳቸውን ከቱርክ የሚቆጥሩ ናቸው፡፡
በእንግሊዝ 2.7 ሚሊዮን ሙስሊሞች ይኖራሉ፡፡ ይህም ከጠቅላላው የእንግሊዝ ህዝብ 4.8 በመቶ የሚሆነውን ይወክላል፡፡ ከነዚህ ሙስሊሞች ውስጥ በጣም የሚበዙት የዘር ሀረጋቸውን የሚመዙት የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ከነበሩት ፓኪስታንና ናይጄሪያ ነው፡፡
በምዕራብ አውሮፓ ከሚኖሩት ሙስሊሞች ውስጥ በብዛት አራተኛ ደረጃ የያዙት መኖሪያቸውን ያደረጉት ጣሊያን ነው፡፡ 2.2 ሚሊዮን የሚሆኑት ሙስሊሞች ከጠቅላላው የጣሊያን ህዝብ ብዛት 3.7 በመቶ የሚሆነውን ይወክላሉ፡፡

በሳኡዲ አረቢያ አንድን ውሻ በከፍተኛ ሁኔታ አሰቃይተው ገድለዋል በሚል ተከሰው ፍርድ ቤት የቀረቡ ሁለት ወጣቶች የ5 አመት እስር ወይም የ500 ሺህ የሳኡዲ ሪያል መቀጣታቸውን አረብ ኒውስ ዘገበ፡፡
ወጣቶቹ ከሳምንታት በፊት ውሻውን በከፍተኛ ሁኔታ ሲደበድቡና ሲያሰቃዩ ቆይተው ለሞት እንደዳረጉት የሚያሳየውና በአንደኛው ወጣት ሞባይል የተቀረጸው አስር ደቂቃ ያህል የሚረዝም የቪዲዮ ፊልም በማህበራዊ ድረገጾች አማካይነት በስፋት መሰራጨቱን ተከትሎ፣ ድርጊቱ ከፍተኛ ተቃውሞ ማስነሳቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ፖሊስ ወንጀለኞቹን ተከታትሎ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጿል፡፡
ፖሊስ ወንጀለኞቹ መኪና እያሽከረከሩ ውሻውን በመሬት ላይ በመጎተት ሲያሰቃዩት እንደነበር በሚያሳየው በዚህ ቪዲዮ ላይ የታየውን የመኪናዋን ታርጋ ቁጥር በመመዝገብ የድርጊቱን ፈጻሚዎች ተከታትሎ በሪያድ በቁጥጥር ስር ማዋሉንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
የአገሪቱ የግብርና ሚኒስትር ጃቢር አል ሸሪ፤ ወጣቶቹ በውሻው ላይ የማሰቃየት ወንጀል መፈጸማቸው በመረጋገጡ፣ በአገሪቱ ህግ እና የባህረ ሰላጤው አገራት ባወጡት እንስሳትን የማሰቃየት ወንጀል ህግ መሰረት፣ ፍርድ ቤት ቀርበው ቅጣት እንደተጣለባቸው አስታውቀዋል፡፡