
Administrator
የብልህነት መንገድ
ምንም ነገር ጥሩም ሁን መጥፎ እስከ ጽንፍ ድረስ አትውሰደው አንድ ብልህ ይሄን ጉዳይ በአንዲት አባባል ቀንብቦ አስቀምጧታል። ጽንፍ የወጣ ፍትህ ኢ-ፍትሐዊነት ይሆናል። ብርቱካንን አለአግባብ ብትጨምቀው ጭማቂው መራራ ይሆናል። ደስታም እንኳ ቢሆን መረኑን እስኪለቅ ድረስ መሆን የለበትም። ላምን አለቅጥ ማለብ ደም ያሳዣታል።
ለራስህ ትንሽ ስህተት ፍቀድለት እንደዚህ አይነት ግድየለሽነት በአብዛኛው ችሎታን ደግፎ ይገኛል። ቅናት የራሱ አይነት የተለየ ውግዘት አለው። መታወቅህ በጨመረ መጠን ወንጀልህ ይጨምራል። አንድ ነገር በሃጥያት አለመውደቅ መልሶ ራሱን በሀጥያተኛነት ይስከሰስዋል። ጽሩሕ በመሆኑ ብቻ ይወነጀላል። አርጎስ ይሆናል። ሂስ እንደ በረድ በነጻው ውስጥ ነቁጥን በመፈለግ፤ እንደ መብረቅ የተራራውን ጫፍ ትመታለች። የሆሜርን የጭንቅላት ውዝወዛ፣ ለጠላት መርዝ ማርከሻ እንዲሆን ፍቀድለት። ስለዚህ የማስተዋል ሳይሆን ያለማወቅ ትንሽ ዝንጉነትን ለጥላቻ ማብረጃ ፍቀድ።
ጠላቶችህን ተጠቀምባቸው ነገሮችን በሚቆርጠው ስለታቸው አትያዝ፤ በአፎታቸው እንጂ። በተለይ ከጠላቶችህ ጋር ባለህ ግንኙነት ይህ ህግ ከጉዳት ታደግሃል። አዋቂ ከጠላቶቹ ሚጠቀመውን ህል ነፍላላ ከወዳጆቹ አይጠቀምም። የጠላቶችህ ክፋት የማትወጣውን የችግር ተራራን ወደ ሜዳ የመዳመጥ ሃይል አለው። ብዙዎች በገዛ ጠላቶቻቸው ታላቅነት እንደ ስጦታ ተበርክቶላቸዋል። ቁልምጫ ቆሻሻን ስለሚደብቅ ከጥላቻ የባሰ መጥፎ ነገር ነው። ብልህ ክፋትን ወደ ጥሩ መስታወት ይቀይራል።
የረጅም ህይወት ምስጢር ጥሩ ህይወት መምራ ነው። ሁለት ነገሮች ህይወትን ወደ ፍጻሜዋ ያዳፏታል። ከንቱነት እና ሞራለ-ቢስነት። አንዳንድ ብልሃቱ ስለሌላቸው ብቻ ህይወትን ያጧታል፤ሌሎች ደግሙ ፈቃዱ ስለሌላቸው። ሰናይነት ለህይወት ሽልማት እንደሆነ ሁሉ ሃኬትም ቅጣቷ ነው። ወደ ሃኬት ፊቱን ለማዞር የቸኮለ ሁሉ ሁለት ሞትን ይሞታል። የመንፈስ ሐቀኝነት ወደ ስጋ ይሰርጻል። ህይወት በቆይታዋ ድምቀት ብቻም አይደል ጥሩ እምትባለው፤ በቆይታዋ ርዝመት ጭምር እንጂ።
እያመነታኽ አትስራ ጠርጣራ ህሊና ለሁሉም ግልጽ ነው። በተለይ ለባላንጣ። በተጋጋለው ግርግር መሃል ብያኔኸ የሚመስለውን ፍርድ ካላቀበለህ፣ ኋላ ነገሮች ሲረጋጉ ይክስሃል። ጥንቃቄ የሚያሻው አጠራጣሪ ነገር ሲያጋጥም ምንም አለመስራቱ ይሻላል። ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ ይሁንታን አይቀበልም። ሁሌም በምክንያታዊነት የቀትር ብርሃን ነው የሚጓዘው። ጅማሮህ ላይ ችግር ካለ አፈጻጸሙ እንዴት ሊያምር ይችላል? በመጀመሪያ ጥሩ የመሰለህ ውሳኔ ውዳኤው ካላማረ፣ ተጠራጥረህበት የነበረውስ እንዴት ይከፋ ይሆን?
እነሆ በሁሉም ዘርፍ የላቀ ጥበብ የባህርይ እና የንግግር ቀዳሚውና ዋነኛው ህግ ነው እላለሁ። በተለይ በስልጣን መሰላል ከፍ እያልህ በሄድህ ቁጥር ደግሞ አስፈላጊነቱ እየጨመረ ይመጣል። የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል ጥበብ ከጆንያ ሙሉ ብርታት ትልቃለች። ይሄ ብዙም ባይመሰገንም፣ በተፈጥሮ የተረጋገጠ ምንገድ ነው። የጥበበኛነት ክብር የዝናዎች ሁሉ የመጨረሻ ድል ነው። ብልሆችን ማርካት ከቻልክ በቂ ነው። ብያኔያቸው የስሜት ናሙና ስለሆነ።
ሁለገብ ሰው የፈርጀ ብዙ ብቃቶች ባለቤት የሆነ ሰው፤ ብቻውን ከብዙ ሰዎች እኩል ነው። ይህን ፍስሃ ለባልንጀሮቹ በማጋራት ህይወታቸውን አበልጽጎ አስደሳች ያደርጋታል። ማለቂያ ባላቸው ጉዳዮች ያለ ልዩነት፣ የህይወት ትፍስሕት ነው። ተፈጥሮ ሰውን በራሷ ረቂቅ አምሳያ እስካበጀችው ድረስ ጥበብ የሰው ልጅን ምርጫና ብልሃት በማሰልጠን፣ በውስጡ ደቂቅ ህዋን እንድትፈጥር ፍቀድላት።
የችሎታህን መጠን አታሳይ ብልህ በሁሉ ዘንድ መከበርን ከመረጠ የእውቀቱንና የችሎታውን ትግል አያሳይም። እንድታውቀው እንጂ እንድትረዳው አይፈቅድልህም።
ማንም የችሎታውን መጠን ማወቅ የለበትም። ካወቀ ይከፋል። ማንም ጥልቀቱን ለክቶት አያውቅም።
ምክንያቱም ስለሱ ችሎታ የሚሰነዘሩ ግምቶችና ጥርጣሬዎች ካለው ከትክክለኛው ችሎታ በላይ ክብርን ያቀዳጁታልና።
ተስፋ አንብረው፤ እያነሳሳህ አቆየው። ቃል በመግባትና በድርጊት ተስጥኦህን አለምልም። ያለህን ሁሉ አንጠፍጥፈኽ በአንድ ጉዳይ ላይ ማዋል የለብህም። ትልቁ ታክቲክ የጥንካሬና የእውቀት አጠቃቀምህን እየመጠንክ ወደ ስኬት ማምራት ነው።
አስተውሎት የምክንያታዊነት አክሊል ነው። የጥንቃቄ መሰረት። በዚህች ዘዴ ብቻ ስኬት በትንሽ ወጪ ይገኛል። የመጀመሪያው እና ጥሩው ችሎታ እስከሆነ ድረስ በጸሎትም ቢሆን መገኘት አለበት። የሰማያት ስጦታ የሆነው አስተውሎት፤ እጅግ በጣም ጠቃሚው ጋሻ ሲሆን፤ ማመዛዘንህን ማጣት ትልቁ ሽንፈት ሊባል ይችላል። ጉድለቱ ከርቀት ይታያል። የህይወት ሁሉም ትግበራዎች በሱ ተጽዕኖ ስለ የወደቁ የሱንም ይሁንታ የሚሹ እስከሆኑ ድረስ ሁሉም ነገር አስተውሎት ጋር ተጓድኖ መሄድ አለበት። አስተውሎት በተፈጥሮው ምክንያታዊነት ጋር ተቀላቅሎ ለሚገኝ እርግጠኛ አቅጣጫ የማላት ባህርይ አለው። ዝናን አግኛት አኑራትም… ታዋቂነትን ማግኘት ውድ ነው። ከታላቅነት ስለሚገኝ።
ተራ የሆኑ ነገሮች በብዛት የሚገኙትን ያህል ዝና ደግሞ ብርቅ ናት። አንዴ ከተገኘች ለመጠበቅ ትቀላለች።
ብዙ ግዴታዎችን ትፈጥራለች። ውጤትንም ታገኛለች። ዝና በፍጽምነትዋ ዋና በተገኘችበት የስራ ዘርፍ የተነሳ ወደ ክብር ሰለምትቀየር ዘውዳዊነትን ትቀዳጃለች። ነገር ግን በጽኑ መሰረት ላይ የተገነባ ዝና ብቻ ነው ዘላቂ የሚሆነው።
ምኞትህን ደብቅ፤ ጥልቅ ስሜቶች የነፍስ መግቢያ በሮች ናቸው። ተግባራዊው እውቀት እነሱን መደበቅ ያጠቃልላል። የያዘውን ካርታ ለእይታ አጋልጦ የሚጫወት የመበላት እድል አለው። ለተጠያቂዎች የማወቅ ፍላጎት ጥንቃቄ መደረግ አለበት። እንደ ዱር ድመት ካተኮሩ አይጦች፤ ከኩትል አሳ ቀለም ሁሉ መከለል አለበት። ፍላጎቶችህን በቅድሚያ በፍጥጫም ይሁን በቁልምጫ እንዳይገመቱ ደብቃቸው።
እውነታና ገጽታ ነገሮች በምንነታቸው ብቻ ተቀባይትን አያገኙም ፤በገጽታቸውም ጭምር እንጂ። ጥቂቶች ናቸው ወደ ውስጥ የሚያጮልቁት። አብዛኞች በገጽታ ብቻ ይደሰታሉ። ገጽታህ የተሳሳተ ከመሰለ ትክክል መሆን ብቻውን በቂ አይደለም።
***
(“ከየግሬሽያን ባልታሳር የብልህነት መንገድ” የተቀነጨበ)
‹‹ኩሉ አመክሩ ወዘሰናየ አጽንዑ››- ሁሉንም ሞክሩ የተሻለውን ያዙ
‹‹ሁሉንም ሞክሩ፤የተሻለውን ያዙ›› የሚለውን አባባል፣ ቢያንስ እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርስቲ (የዛሬው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ) ገብቶ የተማረ ተማሪ ያውቀዋል፡፡ በየድግሪው ላይ የተፃፈ መሪ ቃል እና ጥቅስ ነው፡፡ በህይወታችን ውስጥ በርካታ ውጣ ውረዶች ይገጥሙናል፤ እና በየፈርጅ በየፈርጃቸው እየሞከርን፣ እየወደቅን እየተነሳን፤ በጎና ሰናይ የሆኑትን እየለየን እና እያጠናከርን፤ የሚበጀንን መያዝ አለብን፤ ለማለት ነው፡፡ በእርግጥም በየአንዳንዱ ሙከራ ወቅት፤ እንቅፋት፣ ችግርና መከራ መኖሩ አይቀሬ ነው ለማለት ነው፡፡ ለዚህ አብነት ይሆነን ዘንድ የሚከተለውን የአበው ወግ እንይ፡፡
ሁለት ደገኛ ገበሬዎች ኑሮ አልገፋ ብሎ ቁም ስቅላቸውን ያሳያቸዋል፡፡ አንዴ ዝናቡ እንቢ ይላል፡፡ አንዴ በሬዎቹ ይለግማሉ፡፡ አንዴ ደቦ ወጪዎች አይመቻቸውም፡፡ አንዴ ደግሞ ሰብሉን ተባይ ይፈጀዋል፡፡ በእጅጉ ይቸገራሉ፡፡ አዝመራውም አልሰምር ይላል፡፡
አንደኛው ገበሬ አንድ ቀን መላ ዘየደ፡፡ ንግድ መጀመር አለብኝ ብሎ ወሰነና፣ አዲስ ሙከራ ጀመረ፡፡ በሬዎቹን ሁሉ ሸጠ፡፡ የዘር እህሉንም ከሰቀለበት አውርዶ፣ ለቤት የሚፈልገውን ያህል አስቀረና አውጥቶ ሸጠ፡፡ ከዚያም ባገኘው ገንዘብ ወደ ቆላ ወርዶ ለማረሻ ለዶማና ለማጭድ ወዘተ--መስሪያ የሚሆን ብረታ ብረት ገዛ፡፡ የገዛውንም ብረታ ብረት ወስዶ ለቸገረው ደገኛ ህዝብ ቸበቸበው፡፡ ቀስ በቀስ ኑሮው ተለወጠ፡፡ አዱኛም አገኘ፡፡ ለውጡ በቀዬውም በአገሩም ተወራ፤ ተሰማ፡፡ ሃብቱ ጣራ ነካ፡፡ ይጭነው አጋስስ ይለጉመው ፈረስ በደጅ በግቢው ሞላለት፡፡
‹‹አያ፤ እንዲህ በአንዴ ዲታ የሆንከው ምን ዘዴ ከውነህ ነው ጃል?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡
ያም የድሮ ገበሬ፣ የዛሬ ነጋዴ፤ የተሰማራበትን ሙያ ያስረዳዋል፡፡ ወደህ ስራ ቢገባም በቀላሉ ካብታም እንደሚሆን ይገልፅለታል፡፡
ሁለተኛው ገበሬ፤ ሳይውል ሳያድር ምክሩን ተቀብሎ፣ በስራ ላይ አዋለና፣ ያለ የሌለ ንብረቱን ወደ ገንዘብ ለወጠ፡፡ ንግድ ጀመረ፡፡
ቆላ ወረደ፡፡ ያገሩን ብረታ ብረት ገዛ፡፡ ተሸከመና ሽቅብ ወደ ደጋ መንገድ ጀመረ፡፡ ሆኖም፤ ገና ዳገቱን አጋምሶ ሳያበቃ በተሸከመው ብረታ ብረት ክብደት ሳቢያ ወገቡም ጉልበቱም ከዳውና ተዝለፍልፎ ወደቀ፡፡ አወዳደቁም አጉል ነበረና አረፋ አስደፈቀው ፡፡
አንድ መንገደኛ የሰፈር ሰው ድንገት ሲያልፍ አይቶት ኖሮ ወደሱ ቀርቦ፤
‹‹አያ እገሌ፤ምን ሆነህ ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ገበሬውም፤ ‹‹አይ ወዳጄ፤ ያ ጎረቤቴ አያ እገሌ የሰራኝን ስራ ለጠላት አይስጥ!›› አለና መለሰለት፡፡
‹‹ምን አደረገህ? የልብ ወዳጁ እማይደለህ እንዴ? በሞቴ ንገረኝ፤ ምን አደረገህ?››
‹‹ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳነግረኝ፤ ይሄው ለዚህ ዳረገኝ!!›› አለው፡፡
***
ሁሉም ስራ ችግሩ የሚታወቀው ሲሞከር ብቻ ነው፡፡ ንግዱ፣ትምህርቱ፣ ልማቱ፣አስተዳደሩ፣ ፓርላማዊ ስነስርዓቱ፣ ምርጫው፣ ፍትሃዊ ባህሉ ወዘተ ሁሉም ተሞክሮ፣ ተሰርቶ ታይቶ ነው፡፡ ካላዋጣ ደግሞ ካፈርኩ አይመልሰኝ ሳይሉ፣ የማይሰራውን ፈጥኖ ጥሎ ሌላ መንገድ መፈለግ ግድ ነው፡፡ ስህተትንም በወቅቱ አርሞ፣ ሰናዩን አለምልሞ፣ ጠንካራውን አጎልብቶ፣ መያዝ ደግ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ከአምናው ምን ተምረናል? ለነገስ ምን ጨብጠናል? የማለት ድፍረትና ግልፅነት እንዲኖረን ያሻል፡፡
አዲስ ፈር ለመቅደድ መስዋዕትን መክፈል፣ ያልተሞከረውን መሞከር ያልታየውን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ትላንት በሄድንበት መንገድ ዛሬም ብንመላለስበት ኮቴአችንን ከመጨረስ በቀር፣ ወደላቀ ግብ መድረስ እርም ነው፡፡ ትላንት በተሟገትንበት፣ በተዛለፍንበት፣ ላንደማመጥ በተጯጯህንበት ሸንጎ፣ ዛሬም ያንኑ እሪታና ጩኸት፣ ያንኑ ችኮላና ድንፋታ፣ ያንኑ እርግማንና ውግዘት ብናላዝን ብናስተጋባበት፤ ድምፃችን ከመዛሉ፤ ጉዟችን ከመሰናከሉ በቀር ብዙ አንራመድም፡፡ ከመበቃቀል መተራረም፣ ቂም ከማርገዝ የቂምን ሥነ-ነገር መርምሮ ለመንቀል መጣጣር ዋና ጉዳይ የሚሆነውም ለዚህ ነው፡፡
ከቶውንም ትላንት እጅግ ጨለማ የመሰለንን ንፍቀ ክበብ፣ ዛሬ በመጠኑ እንኳን ደብዛዛ ውጋጋን ካየንበት ውጋጋኑን ለማስፋት እንጂ ‹‹ይሄውላችሁ፣ ዛሬም በደምብ አላነጉትም!›› እያልን ቡራ-ከረዩ ብንል አንድም የለውጥን አዝጋሚ ሂደት መካድ፣ አንድም ያ ውጋጋን ብሩህ ፀዳል እንዳያገኝ የእኛን አስተዋፅዖ መንፈግ ይሆናል፡፡ ባለፈው፣ ባልሞከርነው ነገር ሳቢያ ባጠፋነው ጊዜ ስንፀፀት አዲስ ሙከራ የምናደርግበትን ሌላ ውድ ጊዜአችንን እንዳናጨልም መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ሀገራችን አሁን ላለችበት ቦታ የበቃችውኮ በደጉም በክፉውም ሂደት ሳቢያ ነው፡፡ ማህበረሰባችንም እንደዚያው፡፡ ክፉውን አስወግዶ አንድ እርምጃ ለመራመድ ግን አዲስ ሙከራ እንደሚስፈልግ በመገንዘብ መንቀሳቀስ ይጠይቃል፡፡ የሌሎችን ድምፅ በትዕግስት መስማት፣ መንገዳቸውን በጥሞና ማየት፣ እኛ ያደረግንላቸውን ያህል እነሱም ያደርጉ ዘንድ ሁኔታዎችን ማመቻቸት፡፡ ለዚህ ደግሞ ትርፉን ብቻ አውቀን መከራውን ሳናውቅ ከተጓዝን ህልማችን ሁሉ ከላይ እንደተጠቀሰው ገበሬ ጉልበት አጥቶ ይወድቃል፡፡ የራእያችንም ክንፉ ከወዲሁ ይሰባበራል፡፡ ተስፋችን ሳይጫር ይከስማል፡፡ በዚህ መንገድ የሄዱ ቄሱም፣ ሼኪውም፣ ሹሙም ዜጋውም፣ የፖለቲካ ቡድኖቹም፣ መንግስታዊ የሆኑና ያልሆኑ ድርጅቶቹም አበክረው ማስተዋል ያለባቸው ቁምነገር ይሄ ይመስለናል፡፡
‹‹ያለፈ ጥረታችንን ሳስታምመው ትዝ ሲለኝ፣ ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው እሚቆጨኝ››
ለማለት መቻል አለብን፤ እንደ ‹‹ቴዎድሮስ››፡፡ ያልሞከርነውን ለመሞከር ዝግጁነት ወሳኝ ነው!! የመንፈስም የአካልም፡፡
ከዚያ በኋላ፤ ‹‹ሁሉንም ሞክሩ፣ የተሻለውን ያዙ››! ለመባባል እንችላለን፡፡
ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ እና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች
• ከፍተኛ የጨው አጠቃቀም ለደም ግፊት በማጋለጥ፣ የልብና ደም ቧንቧ እንዲሁም ስትሮክ አደጋን ይጨምራል
• በኢትዮጵያ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሞት ምጣኔ 43 በመቶ ደርሷል
• እ.ኤ.አ በ2017 ከ2.8 ሚ. በላይ ሰዎች በልብና ደም ቧንቧ በሽታ ተጠቅተዋል
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች፣ ሥር የሰደዱ በሽታዎች በመባል የሚታወቁ ሲሆን፤ ከአንድ ሰው ወደ ሌላ ሰው የማይተላለፉና ለረዥም ጊዜ የሚቆዩ የጀነቲክ፣ የፊዚዮሎጂ፣ የአካባቢና የባህርይ ሁኔታ ውጤቶች ናቸው፡፡ እነዚህም የልብና የደም ቧንቧ በሽታዎች፣ የልብ ድካምና ስትሮክ፣ ካንሠር፣ ሥር የሰደዱ የመተንፈሻ አካላት ህመሞች፣ ሥር የሰደደ የሳምባ ምችና አስም እንዲሁም የስኳር በሽታዎች ናቸው፡፡
ለእነዚህ በሽታዎች ዋና ዋና አጋላጮች ከሚባሉት መካከል ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ፣ ትምባሆ ማጨስ፣ ጎጂ የአልኮል አጠቃቀም፣ ጫት መቃምና የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግ ይጠቀሳሉ፡፡
“ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር” ባሰራጨው ጥናታዊ መረጃ መሠረት፤ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች የሚባሉት የስኳር፣ የጨውና በመደበኛ የቤት ውስጥ ሙቀት የሚረጋ ዘይትና የአትክልቅ ቅቤ (Transfat and Saturatedfat) መጠናቸው የበዛባቸው ፈጣንና በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምግቦችና መጠጦች ሲሆኑ፤ እነዚህን አብዝቶ መመገብ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎችና ለሌሎች የጤና እክሎች እንደሚያጋልጥ ተረጋግጧል፡፡
የከተሞች መስፋፋትና የአኗኗር ዘይቤ መለወጥ የአመጋገብ ሥርዓትን እየቀየሩና ከዚህ ጋር ተያይዞ በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምግቦች አቅርቦት በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን የጠቆመው ጥናታዊ መረጃው፤ ሰዎች እነዚህን የረጋ ስብ (Transfat and Saturatedfat)፤ የስኳርና የጨው ይዘት ያላቸው ምግቦችና መጠጦች አዘወትረው በመመገብ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች እንደሚጋለጡ አመልክቷል፡፡
በጤናማ አመጋገብ ላይ የማህበረሰቡ የግንዛቤ ማሳደጊያ ሥራዎች ባለመሰራታቸው፣ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት በርካታ ዜጎች ለህመምና ለሞት እየተዳረጉ ነው ያለው “ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር”፤ የመገናኛ ብዙኃንና የማህበራዊ ሚዲያ ጋዜጠኞች ይህን ክፈተት በመሙላት የበኩላቸውን ሚና እንዲጫወቱ በዛሬው ዕለት በርዕሰ ጉዳዩ ዙሪያ የግማሽ ቀን የአቅም ግንባታ ሥልጠና በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል ሰጥቷል፡፡
በርካታ የሚዲያ ባለሙያዎች በተሳተፉበት በዛሬው ዎርክሾፕ ላይ፤ ከጤና ሚኒስቴር እንዲሁም ከኢትዮጵያ ምግብ እና መድሃኒት ባለሥልጣን የመጡ ባለሙያዎች ጥናታዊ ጽሁፍና ማብራሪያ አቅርበዋል፡፡
በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ከፍተኛ ኤክስፐርት የሆኑት ዶ/ር ሙሴ ገ/ሚካኤል፣ “ጤናማ ያልሆኑ አመጋገቦች በጤና ላይ የሚፈጥሩት አሉታዊ ተጽዕኖና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሚያሳድሩት ኢኮኖሚያዊ ጫና” በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናት፤ ጤናማ ያልሆኑ አመጋገቦች ለስኳር በሽታ፣ ለካንሰርና ስትሮክ እንደሚዳርጉ አስረድተዋል፡፡ በቂ አትክልትና ፍራፍሬ አለመመገብ ለልብ ህመምና ለካንሰር የመጠቃት ዕድልን ይጨምራልም ብለዋል፡፡ በየሁለት ሰከንዱ አንድ ሰው ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች አማካኝነት ያለዕድሜው እንደሚሞትም ነው የጠቆሙት፡፡ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በኢትዮጵያ ጤና እና ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ከፍተኛ ስጋት መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን ያለጊዜ ሞትና ህመም እንዲከሰት በማድረግ፣ የሃገሪቱን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት በማዘግየት ትልቅ ጫና ማሳደራቸው ተመልክቷል፡፡ እ.ኤ.አ በ2017 ዓ.ም፣ 313 ቢሊዮን ብር (ቀጥተኛና ቀጥተኛ ባልሆነ ወጪ) የኢኮኖሚ ኪሳራ መድረሱ ታውቋል፡፡ በልብና የደም ቧንቧ በሽታ 1.97 ቢ. ብር፣ በካንሰር 0.98 ቢ. ብር፣ በስኳር በሽታ 0.58 ቢ.ብር እንዲሁም ሥር በሰደዱ የመተንፈሻ አካላት በሽታዎች 0.85 ቢ.ብር እና በሥራ ላይ አቅም መቀነስና ሞት 26.9 ሚ. ብር ኪሳራ ደርሷል ተብሏል፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት፣ አገራት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመቆጣጠር እንዲያስችላቸው “ቤስት ባይ” በሚል ካስቀመጣቸው የፖሊሲ ምክረ ሃሳቦች መካከል፡- ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችን ለመቆጣጠር የሚያስችል አስገዳጅ ህግ ማውጣት አንዱ ሲሆን፤ ይህም በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምርቶች የፊት ለፊት ማሸጊያዎች ላይ የሚቀመጡ የማስጠንቀቂያ ምልክቶች እንዲኖር ማስገደድ፤ የገበያ ቁጥጥር ማድረግ፣ የማስታወቂያ ገደብና ከፍተኛ ታክስ መጣል በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡
ከፍተኛ የጨው፣ ስኳርና ስብ መጠን ያላቸው የታሸጉ ምግቦች ላይ የሚቀመጥ የፊት ለፊት የማስጠንቀቂያ ምልክት ከሚጠቀሙ አገራት መካከል ቺሊ፣ አርጀንቲና፣ ብራዚልና ሜክሲኮ የሚገኙበት ሲሆን፤ ይህም መደረጉ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች ግዢ እንዲቀንስና ሸማቾች ጤናማ ምግቦችን መለየት እንዲችሉ አድርጓቸዋል ተብሏል፡፡
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ሥርጭት መጠን በኢትዮጵያ
• በ2016 በተደረገ ጥናት፣ አንድ ኢትዮጵያዊ ዋና ዋና በሚባሉት ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ያለዕድሜው ወይም ከ70 ዓመት በፊት የመሞት ዕድሉ 18.3 በመቶ ነው፡፡
• እ.ኤ.አ በ2018 የዓለም ጤና ድርጅት እንዳስታወቀው፤ በኢትዮጵያ በልብና ደም ቧንቧ በሽታ፣ የሟች ቁጥር 47ሺ712 ደርሷል፡፡
• እንደ “ግሎባል በርደን ኦፍ ዲዚስስ” ጥናት፤ ስትሮክ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ፣ 44 በመቶ ለልብና የደም ቧንቧ በሽታ ያጋልጣል፡፡
• እ.ኤ.አ በ2019 ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች የተከሰተው ሞት 34.2 በመቶ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ 14 በመቶ በልብና የደም ቧንቧ፣ 12 በመቶ ሥር በሰደዱ የመተንፈሻ አካላት፣ 4 በመቶ ደግሞ በስኳርና ኩላሊት በሽታዎች ነው፡፡
(ምንጭ፡- “ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር”)
“ማርደን” ማር እና ሰም ለአገር ውስጥ ገበያ መቅረብ ጀመረ
“ማር ሲሰፍሩ፤ማር ይናገሩ”
ከ2010 ጀምሮ ኦርጋኒክ ማርና ሰም በከፍተኛ የጥራት ደረጃ ለአሜሪካ፣ አውሮፓና ጃፓን ገበያዎች ሲያቀርብ የቆየው ግሪን ፌስ ትሬዲንግ ኃ.የተ.ግ.ማህበር፤አሁን ደግሞ ኦርጋኒክ ማርና ሰም ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ሀሙስ ሚያዚያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከ8፡30 ጀምሮ በኢሊሊ ሆቴል ባዘጋጀው የማብሰሪያ ሥነስርዓት ላይ “ማርደን” በሚል ሥያሜ ኦርጋኒክ ማርና ሰም፣ በፋብሪካው እያቀነባበረ፣ ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን በይፋ አስተዋውቋል፡፡
ኢትዮጵያ ከዓለም የመጀመሪያዎቹ አሥር የማር አምራቾች አንዷ ስትሆን፤ከአፍሪካ ቀዳሚዊ የማር አምራች እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ሆኖም የአምራችነቷን ያህል ማርን የመመገብ ባህል በአገሪቱ አላደገም ተብሏል፡፡
በአገሪቱ ማር የመመገብ ባህል ያልዳበረበት አንዱ ምክንያት ተብሎ የተጠቀሰው፣ በከተማዋ ለሽያጭ የሚዘዋወረው ማር፣ ባዕድ ነገሮች ያልተቀላቀሉበት ንጹህ መሆኑን ማረጋገጥ ከባድ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡
በመርሃግብሩ ላይ የአገር ውስጥ የማር አቅርቦት ጥራትን በተመለከተ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት አቶ ተረፈ ዳምጠውም፣ በጥናታቸው ያረጋገጡት ይህንኑ ነው፡፡
ይህንን ችግር በሚገባ የተገነዘበው ግሪን ፌስ ትሬዲንግ፤በአውሮፓ ስታንዳርድተመርምሮ ተቀባይነት ያገኘውን ንጹህ ኦርጋኒክ ማር በማምረት፣ የህብረተሰቡን ፍላጎት ለማሟላት፣ ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩ ተነግሯል፡፡
የግሪን ፌስ ትሬዲንግ ኃ.የተ.ግ.ማህበር መሥራችና ባለቤት አቶ ጆኒ ግርማ፤ በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ ድርጅታቸው፣ “ማርደን” በሚል ስያሜ፣ ኦርጋኒክ ማርና ሰም ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን አብስረዋል፡፡
***
በነገራችን ላይ የመድረኩ አጋፋሪ፣ በየመድረኩ ከሚያጋጥሙንና የሚናገሩበትን ርዕሰ ጉዳይ ከማያውቁ ወይም ተዘጋጅተው ከማይመጡ ብዙዎች በእጅጉ ይለያል፡፡ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ፣ በቅጡ ተዘጋጅቶና ተለማምዶ (Rehearse አድርጎ) መምጣቱን አለመመስከርና አለማድነቅ ንፉግነት ነው፡፡ የመድረክ አጋፋሪነቱን ማር ማር በሚሉ ተረቶችና ቀልዶች አሽሞንሙኑ ነው ያቀረበው፡፡ ሳቅ ብርቅ በሆነበት በዚህ ዘመን፤ ታዳሚውን ሁለት ሦስቴ ማሳቅ ድንቅ ችሎታ ይጠይቃል፡፡
ሲልከን ቫሊ ኮሌጅ የመጀመሪያ የጥናትና ምርምር ጉባኤውን አካሄደ
በቢዝነስና ቴክኖሎጂ የትምህርት ዘርፎች ላይ አተኩሮ የሚሰራው ሲልከን ቫሊ ኮሌጅ፤ የመጀመሪያውን የጥናትና ምርምር ጉባኤ፣ ትላንት ካዛንቺስ በሚገኘው ነጋ ሲሳ ቲሞል የኢንተርፕረነር ልማት ኢንስቲትዩት አዳራሽ አካሄደ።
ለጉባኤው ከ30 በላይ የሚሆኑ የጥንት ወረቀቶች ለውድድር ቀርበው የነበረ ሲሆን፤ በዕለቱ የተመረጡት ሰባት የጥናት ወረቀቶች መቅረባቸውን የሲልከን ቬሊ ኮሌጅ ስራ አስኪያጅ አቶ እሱባለው ታሪኩ ተናግረዋል። ጉባኤው በዋናነት አንተርፕረነርሽፕ፣ እንዲሁም ትምህርትና ቴክኖሎጂን ያማከለ ነው ተብሏል።የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ንጉሱ ጥላሁን በቦታው ተገኝተው ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፣ ኢንተርፕረነርሽፕ፣ ትምህርትና ቴክኖሎጂ የማይነጣጠሉና ተቆራኝተው ውጤት የሚያመጡ እንደመሆኑ ኮሌጁ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ አተኩሮ ጉባኤውን ማዘጋጀቱ ትልቅ ተግባር ነው ብለዋል።
ሰባቱም የጥናት ወረቀቶች በአንተርፕረነርሽፕ በትምህርትና በቴክኖሎጂ ዙሪያ ያሉትን ተስፋዎችና ተግዳሮቶች ብሎም የመፍትሄ አቅጣጫዎችን የሚጠቁሙ መሆናቸው ተናግሯል።
ኮሌጁ በዚሁ ዙሪያ ከኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጋር በጋራ ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረመ ሲሆን የጥናትና ምርምር ጉባኤውም ከኢኒስቲትዩቱ ጋር በመተባበር መዘጋጀቱ ታውቋል።
ሲልከን ቫሊ ኮሌጅ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የቢዝነስና የቴክኖሎጂ የትምህርት ዘርፎች በማስተርስና በዲግሪ ደረጃ ትምህርትና ስልጠና እየሰጠ የሚገኝ እውቅ ኮሌጅ ስለመሆኑም ተብራርቷል። በጉባኤው ላይ የተለያዩ ኮሌጆች አመራሮችና ምሁራን እንዲሁም የኢኒስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር፣ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
የቀጥተኛ ሽያጭ ሥርዓትና ፒራሚዳዊ አሠራር ምንና ምን ናቸው?
ኢቲኬር የግማሽ ቀን አውደ ጥናት በጌትፋም ሆቴል አካሂዷል
ኢቲኬር የውበት መጠበቂያ ምርቶች ሽያጭ ኃ.የተ.የግ.ማህበር፣ “የቀጥተኛ ሽያጭ ገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት በኢትዮጵያ የህግ ማዕቀፍ አጠቃላይ ዕይታ” በሚል ርዕስ፣ ባለፈው ሰኞ፣የግማሽ ቀን አውደ ጥናት በጌትፋም ሆቴል አካሂዷል፡፡የአውደ ጥናቱ ዓላማ፣ በቀጥተኛ ሽያጭ ገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት መካከል ስላሉ ጉልህ ልዩነቶች ግንዛቤ ለማስጨበጥ ነው ተብሏል፡፡
በአውደ ጥናቱ ላይ የኢቲኬር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማቲዮስ መባን ጨምሮ የኢኮኖሚና የህግ ባለሙያዎች፣ በርዕሰ ጉዳዮቹ ዙሪያ ጥናታዊ ጽሁፍና ማብራሪያ ለታዳሚዎች ሰጥተዋል፡፡
ኩባንያው ባዘጋጀውና ለግማሽ ቀን በተካሄደው በዚህ አውደ ጥናት ላይ፤ በቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ስልት መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው፣ የቀጥተኛ ሽያጭና ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት በኢትዮጵያ ህግ እንዴት ይታያል፣ በገበያው የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች ምንድን ናቸው፣ እንዲሁም የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት ለሃገር የሚያበረክተው የኢኮኖሚ ጠቀሜታ--- የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ተዳስሰዋል፡፡ የኢቲኬር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማቲዮስ መባ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ፣ የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓትና ፒራሚዳዊ አሰራር ስልት ያላቸውን ልዩነቶች በዓለም አቀፍ ተሞክሮ አስደግፈው ያብራሩ ሲሆን፤ የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት ለአገር ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን ጥቅምና ፋይዳ የራሳቸውን ኩባንያ በማስረጃነት በመጥቀስ አስረድተዋል፡፡
የአዲስአበባ ዩኒቨርሲቲ የሕግ ት/ቤት መምህሩ ዶ/ር ሰለሞን አባይ በበኩላቸው፤ ሕገወጡ ፒራሚዳዊ የንግድ ስልት፣ የቁማር ዓይነት ባህርይ እንደሚታይበት ጠቁመው፤ ሙሉ ትኩረቱ ሰዎችን ምልመላና ገንዘብ መዋጮ መሰብሰብ ላይ ነው፤ብለዋል።
“በፒራሚዱ ሰንሰለትም ወደ ታች እየተዘረጋ ሲመጣ የላይኛዎቹ እየተደበቁ ይኼዳሉ ያሉት ዶ/ርሰለሞን፤ዚህም ምክንያት አንድ ችግር ቢፈጠር ኃላፊነትን የሚወስድ ተጠያቂ አይኖርም፡፡፡” ብለዋል፡፡
በግንዛቤ ማስጨበጪያ አውደ ጥናቱ ላይ እንደተገለጸው፤የቀጥተኛ ሽያጭ ሥርዓትን የሚከተሉ ድርጅቶች፣ የሚታወቅና በህግ የተመዘገበ አድራሻና የንግድ ፈቃድ ያላቸው ሲሆኑ፤ ለመንግሥትም ተገቢውን ግብር ይከፍላሉ፤ ፒራሚዳዊ አሰራርን የሚከተሉቱ ግን አድራሻቸው የማይታወቅና ህጋዊ ፈቃድ የሌላቸው በመሆኑ ለመንግሥት ግብር የማይከፍሉና በአየር ላይ የሚንሳፈፉ ናቸው ተብሏል፡፡የሕግ ባለሙያው አቶ አብዱልራዛቅ ነስሮ፣ በኢትዮጵያ የንግድ ውድድርና እና የሸማቾች ጥበቃ አዋጅ፤ የቀጥተኛ ሽያጭና የገበያ ሥርዓትን በተመለከተ የጠቀሰው ነገር እንደሌለ ጠቁመው፣ በአንጻሩ ግልፅና የተብራራ ባይሆንም፣ የፒራሚዳዊ አሰራር መጠቀሱን አንስተዋል፡፡ የፒራሚዳዊ አሰራር ግልፅ ሆኖ ቢቀመጥ፣ ከቀጥታ ሽያጭ የንግድ አሰራር ጋር ያለውን ብዥታ ለማጥራት እንደሚጠቅም ተመልክቷል፡፡ኩባንያው በአውደ ጥናቱ ላይ ያሰራጨው አጭር የቅኝት ጽሁፍ፤”የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት የሚከተሉ ድርጅቶች፣ ጥራት ያላቸውን ምርቶች ለገበያ የሚያቀርቡ ሲሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ባለው ልምምድ፣ እነዚህ ድርጅቶች የሰዎችን የአኗኗር ዘይቤና ፍላጎቶች ለማሟላት ለፈጠራ ሥራና ለምርምር ከፍተኛ ገንዘብ ይመድባሉ፡፡
በአንጻሩ በፒራሚድ ሥልት የተሰማሩት ደግሞ ምንም ዓይነት ምርት የሌላቸው ወይም ቢኖራቸውም ለይስሙላና የገበያ ዋጋ የሌለው ሲሆን ፤ ዋነኛ ዓላማቸው ከሰዎች የገንዘብ መዋጮን መሰብሰብ ነው፡፡” ይላል፡፡ የቅኝት ጽሁፉ አክሎም፤”የቀጥተኛ ሽያጭ ሥርዓት በአቋራጭና በፍጥነት በአንዴ ሃብት የሚሰበሰብበት ሳይሆን፤ በዚህ የገበያ ሥርዓት ውስጥ ጠንክሮ በመሥራት፣ ብዙ ደንበኞችን በማፍራትና ብዙ ሽያጭ በማስመዝገብ የኮሚሽን ክፍያ የሚገኝበት ነው:: የፒራሚዳዊ አሰራር በአንጻሩ፣ በአንድ ጊዜ የሚከበርበት እንደሆነና ሃብት ለማፍራት ብዙ የገንዘብ መዋጮ የሚያደርጉ ሰዎችን መመልመል የሚያስፈልግበት ነው፡፡፡” ሲል ያብራራል፡፡ኢቲኬር፤ በውበት መጠበቂያ ምርቶች ሽያጭ ላይ የተሰማራ ኩባንያ ሲሆን፤ ለ100 ያህል ቋሚ ሠራተኞች የሥራ ዕድል የፈጠረና ባለፉት 10 ወራት ለመንግሥት 10 ሚሊዮን ብር ግብር የከፈለ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ኩባንያው በተጨማሪም፣ ባለፉት አሥር ወራት ወደ 1 ሺህ ለሚደርሱ የምርት አስተዋዋቂዎች 50 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ክፍያ መክፈሉንና እኒህ የምርት አስተዋዋቂዎች ፈቃድ አውጥተው ለመንግሥት ግብር እንዲከፍሉ ማድረጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የአትሌት በላይነህ ዴንሳሞ ‘የተፈተነ ፅናት’ መፅሐፍ በኃይሌ ግራንድ ሆቴል ተመረቀ
የአትሌት መቶ አለቃ በላይነህ ዴንሳሞን የአትሌቲክስ የህይወት ታሪክ የሚዳስስ ‘የተፈተነ ፅናት’ የተሰኘ መፅሐፍ ዛሬ ምሽት በኃይሌ ግራንድ ሆቴል ተመረቀ፡፡
አትሌቱ 1000 ካሬ ሜትር ቦታ እንደተበረከተለት የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ።
በፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሊዳሞ፣ ለአትሌት በላይነህ ዴንሳሞ የ1ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ እንደሚሰጠው ቃል ገብተዋል።
ኢቲኬር የግማሽ ቀን አውደ ጥናት በጌትፋም ሆቴል አካሄደ
ኢቲኬር የውበት መጠበቂያ ምርቶች ሽያጭ ኃ.የተ.የግ.ማህበር፣ "የቀጥተኛ ሽያጭ ገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት በኢትዮጵያ የህግ ማዕቀፍ አጠቃላይ ዕይታ" በሚል ርዕስ፣ በዛሬው ዕለት ለግማሽ ቀን የዘለቀ አውደ ጥናት በጌትፋም ሆቴል አካሄደ፡፡
የአውደ ጥናቱ ዓላማ፣ በቀጥተኛ ሽያጭ ገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት መካከል ስላሉ ጉልህ ልዩነቶች ግንዛቤ ለማስጨበጥ ነው ተብሏል፡፡
በአውደ ጥናቱ ላይ የኢቲኬር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማቲዮስ መባን ጨምሮ የኢኮኖሚና የህግ ባለሙያዎች በርዕሰ ጉዳዮቹ ዙሪያ ጥናታዊ ጽሁፍና ማብራሪያ ለታዳሚዎች ሰጥተዋል፡፡
ኩባንያው ባዘጋጀውና ለግማሽ ቀን በተካሄደው በዚህ አውደ ጥናት ላይ፤ በቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓትና ህገወጥ ፒራሚዳዊ አሰራር ስልት መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው፣ የቀጥተኛ ሽያጭና ፒራሚዳዊ አሰራር ሥልት በኢትዮጵያ ህግ እንዴት ይታያል፣ በገበያው የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች ምንድን ናቸው፣ እንዲሁም የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት ለሃገር የሚያበረክተው የኢኮኖሚ ጠቀሜታ--- የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ተዳስሰዋል፡፡
የኢቲኬር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማቲዮስ መባ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ፣ የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓትና ፒራሚዳዊ አሰራር ስልት ያላቸውን ልዩነቶች በዓለም አቀፍ ተሞክሮ አስደግፈው ያብራሩ ሲሆን፤ የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት ለአገር ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን ጥቅምና ፋይዳ የራሳቸውን ኩባንያ በማስረጃነት በመጥቀስ አስረድተዋል፡፡
በግንዛቤ ማስጨበጪያ አውደ ጥናቱ ላይ እንደተገለጸው፤የቀጥተኛ ሽያጭ ሥርዓትን የሚከተሉ ድርጅቶች የሚታወቅና በህግ የተመዘገበ አድራሻና የንግድ ፈቃድ ያላቸው ሲሆኑ፤ ለመንግሥትም ተገቢውን ግብር ይከፍላሉ፤ ፒራሚዳዊ አሰራርን የሚከተሉቱ ግን አድራሻቸው የማይታወቅና ህጋዊ ፈቃድ የሌላቸው በመሆኑ ለመንግሥት ግብር የማይከፍሉና በአየር ላይ የሚንቀሳቀሱ ናቸው ተብሏል፡፡
ኩባንያው በአውደ ጥናቱ ላይ ያሰራጨው አጭር የቅኝት ጽሁፍ፤"የቀጥተኛ ሽያጭ የገበያ ሥርዓት የሚከተሉ ድርጅቶች ጥራት ያላቸውን ምርቶች ለገበያ የሚያቀርቡ ሲሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ባለው ልምምድ እነዚህ ድርጅቶች የሰዎችን የአኗኗር ዘይቤና ፍላጎቶች ለማሟላት ለፈጠራ ሥራና ለምርምር ከፍተኛ ገንዘብ ይመድባሉ፡፡ በአንጻሩ በፒራሚድ ሥልት የተሰማሩት ደግሞ ምንም ዓይነት ምርት የሌላቸው ወይም ቢኖራቸውም ለይስሙላና የገበያ ዋጋ የሌላቸው ሲሆን ዋነኛ ዓላማቸው ከሰዎች የገንዘብ መዋጮን መሰብሰብ ነው፡፡" ይላል፡፡
የቅኝት ጽሁፉ አክሎም፤"የቀጥተኛ ሽያጭ ሥርዓት በአቋራጭና በፍጥነት በአንዴ ሃብት የሚሰበሰብበት ሳይሆን በዚህ የገበያ ሥርዓት ውስጥ ጠንክሮ በመሥራት፣ ብዙ ደንበኞችን በማፍራትና ብዙ ሽያጭ በማስመዝገብ ኮሚሽን የሚገኝበት ሲሆን፤ የፒራሚዳዊ አሰራር በአንጻሩ፣ በአንድ ጊዜ የሚከበርበት እንደሆነና ሃብት ለማፍራት ብዙ የገንዘብ መዋጮ የሚያደርጉ ሰዎችን መመልመል እንደሚያስፈልግ ይታወቃል፡፡" ሲል ያብራራል፡፡
ከተማ አቀፍ የህክምና መሣሪያዎችና ዕቃዎች ጥገና ዘመቻ በይፋ ተጀመረ
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ፣ በተግባረ ዕድ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅና በቶም የህክምና መሳሪያዎች ተከላና ጥገና ማዕከል በጋራ የተዘጋጀው ከተማ አቀፍ የህክምና መሳሪያዎችና ዕቃዎች ጥገና ዘመቻ፣ “የህክምና መሳሪያዎችና ዕቃዎች ብክነትን በጋራ እንከላከል!” በሚል መሪ ቃል፣ ዛሬ ሚያዝያ 16 ቀን 2015 ዓ.ም በተግባረ ዕድ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በይፋ ተከፍቷል።
በፕሮግራሙ ላይ የአዲስ አበባ የምግብ የመድሀኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ታደሰ አጥላባቸው ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ወንድሙ፣ የተግባረ ዕድ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዋና ዲን አቶ ግሩም ግርማ ፣ የቶም የህክምና መሳሪያዎች ተከላና ጥገና ማዕከል ባለቤትና ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ቶማስ ገ/መስቀል እና ጥሪ የተደረገላቸው የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል።
ፕሮግራሙን በንግግር የከፈቱት የኮሌጁ ዲን አቶ ግሩም ግርማ፤ ዘመቻው መከፈቱ ለሀገር የሚያበረክተው አስተዋጽኦ እጅግ ከፍተኛ መሆኑን የተናገሩ ሲሆን ፤ የዕለቱ የክብር እንግዳ አቶ ታደሰ አጥላባቸው በበኩላቸው፣ ይህ ዘመቻ በተለያዩ ምክንያቶች የጥገና አገልግሎት ሳያገኙ ቁጭ ላሉ የህክምና መሳሪያዎች ትልቅ ዕድል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አቶ ታደሰ አክለውም፤ በዚህ ዘመቻ ሁሉም የግልና የመንግስት ጤና ተቋማት ያላቸውን አገልግሎት የማይሰጡ ወይም የተበላሹ የህክምና መሳሪያዎች ወደ ዘመቻው በማምጣትና እንዲጠገኑ በማድረግ የዘመቻው አካል ከመሆን ባለፈ ያለአግባብ የሚባክኑ ሀብቶችን እንዲታደጉ ጥሪ አቅርበዋል።
በተመሳሳይ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ወንድሙ ደግሞ ይህ ዘመቻ ለህክምና አገልግሎት ጥራት የሚኖረው ፋይዳ ትልቅ መሆኑን ጠቁመው፣በከተማ አስተዳደሩ ስር የሚገኙ ሆስፒታሎችና በአስራ አንዱም ክፍለ ከተሞች ስር የሚገኙ ጤና ጣቢያቸው እንደሚሳተፉም ገልፀዋል።
ዘመቻው በአዲስ አበባ ተግባረ ዕድ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚካሄድ ሲሆን ከሚያዝያ 16 ቀን 2015 ዓ.ም እስከ ሰኔ 16 ቀን 2015 ዓ.ም ለሁለት ወራት የሚቆይ መሆኑ በፕሮግራሙ ላይ ተገልጿል።
“ገባው አልገባው አይደለም የፖለቲካ- ቁም ነገሩ ተቀበለ ወይስ አልተቀበለም ነው! “
ሁለት ወዳጆች በመንገድ ሲሄዱ አንድ አሮጌ ግድግዳ ላይ የተሰቀለ አንድ ያረጀ የሚመስል ስዕል ያያሉ። ሁለቱም ስዕል አድናቂዎች ነን ይሉ ነበርና ወደዚያ ስዕል ተጠግተው ቆመው ያስተውሉ ጀመር።
አንደኛው - “እንዴት ግሩም አድርጎ ስሎታል! እንደዚህ ያለ የጀምበር ጥልቂያ ስዕል (sun-set) እስከዛሬ አይቼ አላውቅም” አለ።
ሁለተኛው - “ይሄ እኮ ጀምበር ስትጠልቅ የሚያሳይ ስዕል አይደለም። ይሄ ጸሃይ ስትወጣ የሚያሳይ (Sun-rise) የንጋት ጎህ ስዕል ነው” አለው።
አንደኛው- “ምንም አትጠራጠር የጀምበር ጥልቂያ ስዕል ነው”
ሁለተኛው- “ማንም ይመስክር የጸሐይ መውጪያ ስዕል ነው”
ሙግታቸው በረታ። ተካረሩ። ሙግታቸውን የሰማው ሰው ሁሉ በአቅራቢያቸው እየመጣ ሀሳብ መስጠት ጀመረ።
ከፊሉ - “ይሄ ተጥለግለግ (አመሻሽ) ነው። ፀሐይ አይኖቿን እየጨፈነች እንጂ እየገለጠች አይደለም እያለ ከአንደኛው ጀርባ ቆመ።
ከፊሉ ደግሞ- “በጭራሽ አካባቢዋን ሁሉ እያፈካች ዙሪያ ገባውን ጸዳል ልታለብሰው ተዘጋጅታለች። ሊነጋ ነው” ሲል ከሁለተኛው ጀርባ ቆመ። በመጨረሻ አንድ አረጋዊ የሰፈሩ ነዋሪ የተባሉ መጡ። እሳቸው ይናገሩ ተባለ።
አረጋዊውም- “ስዕሉ የጀምበር ጥልቂያ ማለትም የፀሐይ መግቢያ ይመስለኛል” አሉ፡፡ የተቃራኒው ወገን ህዝብ በማጉረምረም፤ “ምክንያቱን ያስረዱና!” አሏቸው።
አረጋዊውም- “ምክንያቱማ፣ እኔ ሰዓሊውን አውቀዋለሁ። በጭራሽ ጠዋት ጠዋት ከእንቅልፉ አይነሳም። ስለዚህም የንጋት ፀሐይ አይቶ አያውቅም። ካላየ ደግሞ አይስልም”
***
ጊዜው የህማማት ነው። ብዙ ህመም አለ። የሀገራችን የወደፊት እጣ ፈንታ ምን እንደሆነ አለማወቅ በህዝብ ዘንድ ትልቅ ግርታን ፈጥሯል። ሕዝብ ኢንፎርሜሽን ካላገኘ ውሃ እንደአጣ አትክልት ነው። ይጠወልጋል። በዚያው መጠን ልቡን ያሸሻል። ሰብአዊ መብቱን መጠየቅ ካልቻለና ካልተከበረለት ህመሙ ይበረታል። ሲቪል ህብረተሰብ መፍጠርም ዘበት ይሆናል። ህመም ሲጎነጎን እምቢተኝነትና አመጻም ይወልዳል። እያንዳንዷ ቀን ትናንሽ ምሬት መጸነሷ መጥፎ ምልኪ ነው! ሕዝብ በሀገር ውስጥ የሚፈጠር የሚደረገውን ሁሉ በዝርዝር ካላወቀ አይረጋጋም። መንግሥትና ሕዝብ ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ይሆናል። መብቶቹ ቢረገጡ ቀና ብሎ “ለምን?” ለማለት ድፍረት አይኖረውም። ድብቅነትን እንደ ዘይቤ ይይዘዋል። ህዝብ ካልተረጋጋ ሀገር ችግር ላይ ናት ማለት ነው። ሰሞኑን ለሚታየው የፖለቲካ ሁኔታ ሁሉ በምክንያትነት የተለያዩ ሀሳቦች ሲሰነዘሩ ከርመዋል። አንዳንዴ ዝርዝሩ ከጥቅሉ ይጋጫል። ተጻራሪ ወገኖች አቋም የሚነጣጠቁ ያህል የአንደኛው አቋም የሌላው የሚመስልበት ጊዜ አለ። በትክክል እነዚህ እነዚህ ጉዳዮች ዋነኛ የልዩነት መንስዔ ናቸው ተብለው ነጥረው የወጡ ናቸው ለማለት አሁንም ያስቸግራል። ነገሩ ይበልጥ እየቀረብነው ስንሄድ ይበልጥ እየተሸሸገ ይሄዳል ለማለት ነው።
“የእንጀራ እናትን እንጀራ፣ ወድቆም አታገኘውም” እንደሚባለው ተረት ሊሆን ይቃጣዋል።
በዚህ ላይ ከባለ ጉዳዩ በላይ በመሃል በመሃል የሚያዶሸድሸው መአት ነው። እንደ ቀንድ አውጣ ከሰንኮፉ ያልወጣ፣ የስልጣን-ጥማቱን ማርኪያ ሊያደርገው ወንዝ አቋርጦ የሚመጣ አለ። “በጠብታ ውሃ ውስጥ ጉማሬ አየሁ” እያለ የሚያጋንን የመኖሩን ያህል “ቢሆን አትጨፍሪ፣ ከጨፈርሽ አታበላሺ” መባል ያለበት አዲስ ዛር በአናቱ የፈላበት አፋሽ-አጎንባሽም ሞልቷል።
Beware of yes- men of Athens
They keep on saying ‘ Yes` ‘ Yes`
Till they put you into a mess
(“እሺ ጌታዬ” ከሚሉ አቴናውያን ተጠንቀቅ
“እሺ እሺ” እያሉ እየገፉህ ትርምስ ውስጥ እንዳትወድቅ) የሚባሉም አይጠፉም። በእነዚህ በእነዚህ ሳቢያ ኢንፎርሜሽን ይበልጥ እየተዥጎረጎረ ይጠራል የተባለው እየጎሸ፣ ተሰማ የተባለው እየተዳፈነ ይሄዳል። ጥርት ያለ ኢንፎርሜሽን ባለመቅረቡ ነገ ሀገሪቱን የሚጠብቃት የጀምበር ጥልቂያ ይሁን የፀሐይ መውጣት ከባቢ አየሯ አጠያያቂ ይሆናል። “በመጨረሻስ ለህዝቡ የሚተርፈው ምንድን ይሆን?” የሚለው ጥያቄ ይበረክታል። ይሄ ደግሞ የሁሉ ነገር ቁልፍ ነው!
ትላንትና ተጠይቀው ወይ ከነአካቴው ያልተመለሱ፣ ወይ በከፊል ብቻ የተመለሱ ዲሞክራሲያዊ ጥያቄዎች “መጨረሻቸው ምን ሊሆን ነው?” ማለት ግድ ይሆናል። የፖለቲካ ክፍፍል ያለነገር አይከሰትምና ስር ነቀልም ይሁን ጠጋኝ ለውጥ በመጣ ጊዜ ነባሮቹንም ሆነ አዲሶቹን ጥያቄዎች ዋነኛው ኢላማ እንኳ ቢስታቸው ፍንጣሪው ሳይመታቸው አይቀርም።
ከቶውንም የእስከዛሬው ዲሞክራሲ ውስጠ-ነገር ሲመረመር ታክሞ ተጠግኖ የሚድን ቁስል ይሆን ይሆን፣ ወይም አንቶኒዮ ግራምሺ እንዳለው፤ “ፓርቲ ሲነቅዝ የሚፈጠር፣ ጨርሶ የማይድንና የሚዛመት የፖለቲካ ደዌ (poltical gangrene) እመሆን ደረጃ ደርሶ ይሆን? መፍትሄውስ በሙሉ ኦፕራሲዮን ቆርጦ መጣል ነው ወይስ ሌላ መላ አለው? ማደንዘዣስ ያሻዋል አያሻውም?... ስለሁሉም ህዝብ ማወቅ ይፈልጋል። የሰማውን መረዳት የራሱ ፋንታ ነው።
እንጂ፤ በእናት- ዓለም ጠኑ ቲያትር እንደተጠቀሰው ዓይነት “ገባው አልገባው አይደለም የፖለቲካ ቁምነገሩ። ተቀበለ አልተቀበለም ነው!” የሚል አስተሳሰብ፤ ለመቼም ለማንም የማይበጅ መሆኑን ልብ ልንል የሚገባን አሁን ነው።