Administrator

Administrator

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) እና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ከሌሎች ሃይሎች ጋር በመሆን በኦሮሚያ ክልል የሽግግር መንግስት ለማቋቋም ያወጡትን መግለጫ አራት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተቃወሙት ሲሆን፤ ፓርቲዎቹ መግለጫውን “እሳት ላይ ቤንዚን እንደ ማርከፍከፍ የሚቆጠርና ቀን አይቶ የመጣል አዝማሚያ ያለው ነው” ሲሉ ነቅፈውታል።
ኢሕአፓ፣ መኢአድ፣ አማራ ጊዮናዊ ንቅናቄ እና እናት ፓርቲ ሐሙስ የካቲት 27 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጡት የጋራ መግለጫ፤ "ኦፌኮ እና ኦነግ ያወጡት መግለጫ፣ በአመዛኙ እሳት ላይ ቤንዚን እንደ ማርከፍከፍ የሚቆጠርና ቀን አይቶ የመጣል አዝማሚያ ያለው ሆኖ አግኝተነዋል” ብለዋል፡፡
ሁለቱ ፓርቲዎች የተስማሙባቸውንና በመግለጫቸው ያወጧቸውን ጉዳዮች ያወሱት አራቱ ፓርቲዎች፤ “እኛ የትብብር ፓርቲዎች በኦሮሚያ ክልል ብቻ አይደለም፤ በመላ አገራችን ሰላም እንዲሰፍን ለዚህም መንግሥት ግንባር ቀደም ሚና እንዲጫወት ያለመታከት ስንወተውት ቆይተናል” ብለዋል። አክለውም፣ አሁን ለአገሪቱ ሰላም በጋራ መታገል የሚያስፈልግበት ወቅት መሆኑን አስምረውበታል፡፡
“በተናጠል ያውም በክልል ደረጃ ወርደን የሚመጣ ሰላም አይኖርም፣ የአገራችንን አንድነትም ማስጠበቅ አይቻልም” ያሉት አራቱ ፓርቲዎች፤ “በአንድ ክልል ሊቋቋም የታሰበው የሽግግር መንግሥት አገራችንን አሁን ከምትገኝበት ሁኔታ የበለጠ ያመሰቃቅላታል፣ ችግሮችንም ያባብሳል እንጂ መፍትሄ ሊሆን እንደማይችል መገንዘብ ያስፈልጋል” ሲሉ አስረድተዋል።
በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ሰላም ካልሰፈነ “ማንም ወገን ብቻውን ነጻ እንደማይወጣ” ጠቅሰውም፤ የተናጠል ሰላም እንደማይሰፍን አብራርተዋል።
በመሆኑም፣ በኦፌኮ እና ኦነግ መግለጫ አማካይነት ይፋ የተደረገው የሽግግር መንግሥት የማቋቋም እንቅስቃሴን አጥብቀው እንደሚቃወሙ ፓርቲዎቹ አስታውቀዋል። እንቅስቃሴው ኦሮሚያ ክልልን “ጥቂት ፖለቲከኞችና የፖለቲካ ፓርቲዎች በሞኖፖል የያዙት ደሴት በማድረግና ራስን ብቸኛ ወኪል አድርጎ በማስቀመጥ አሁንም የተጠቂ ፖለቲካና የመጡብህ ዓይነት ቅስቀሳ የማራመድ” አካሄድ መሆኑን ጠቁመዋል።
“ይህን አካሄድ በአገር ፍርስራሽ ላይ የራስን ጎጆ ለመቀለስ ያለመ ቅርብ አዳሪ፣ ፍትሕ አልባ፣ ኢ-ሕገ መንግስታዊና ኢ-ሞራላዊ ሆኖ አግኝተነዋል” ሲሉ የተቹት ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ፤ በኦፌኮ እና ኦነግ መካከል “ተደርጓል” ያሉት ስምምነት አገሪቱን በበርካታ አስርት ዓመታት “ወደ ኋላ የሚመልስ” ነው ብለውታል፡፡
በቅርቡ ኦፌኮ እና ኦነግ ባወጡት መግለጫ፣ በጋራ ይፋ ያደረጉት አቋማቸው፣ ለሕብረተሰቡ እንቅፋት የሆነውን በኦሮሚያ ክልል ያለውን የሰላም ችግር በትብብር ለመፍታት ያለመ ብቻ መሆኑን ጠቁመው፣ ከመንግሥት ጋር ለመወያየት አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረጋቸውንም ገልጸው ነበር፡፡

እግዚአብሔር ከሁሉም ፍጡራን አብልጦ ለሰዎች እውቀትና ፍቅር ሰጥቶናል፡፡ እውቀት ነገር ለመለየት ይጠቅማል፡፡ ፍቅር ተግባብቶ ለመኖር ይረዳል፡፡ የዘመኑ ስልጣኔ የሰረፀውም በእነዚህ ፀጋዎች እንደሆነ ይታሰባል፡፡ ተፈጥሮ ሚስጥር ነች፤ ተለዋዋጭ ነች፣ ዘላለማዊም ነች ይባላል፡፡ የለውጥ ምንጩ ፀሐይና ኮከቦች ውስጥ ያለው ሀይድሮጅን በከፍተኛ ሙቀት ሲቃጠል የሚሰርፀው ጨረር (ኢነርጂ) እንደሆነ ይታመናል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን ለውጥ የሚመጣው በጊዜ ተፅእኖ ይመስላቸዋል፡፡ እናም “አወይ ጊዜ” እያሉ ያንጐራጉራሉ፡፡ ጨረር ቁስ አካልን እየወዘወዘ ይቀያይረዋል፡፡ ውሁዶች ይፈጥራል ያፈርሳል፣ ሕይወትም ይገነባል፡፡
እኛ ሰዎች ስንሞት ገነት ለመግባት እንመኛለን፡፡ ከሞት በፊት ግን የሕይወትን ፀጋ በደንብ ብናጣጥመው ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ሕይወት ልዩ የተፈጥሮ ፀጋ ናት፡፡ ራሷን በራሷ ታውቃለች፣ ነገር ትለያለች፣ ምግብ እየበላች፣ ቆሻሻ እያስወገደች፣ እየተዋለደች ትዘልቃለች፣ ትንሽ ቆይታም ትከስማለች፡፡ ከሞት በኋላ ስለ ጽድቅ ወይም ኩነኔ ከማሰባችን በፊት ግን “በእጅ የያዙትን ወርቅ ላለመጣል” ብለን ሕልውናን ለማዝለቅ ብንጥር ትክክል ይመስለኛል:: ብቃቱም አለን፤ ከእግዜር ተሰጥቶናል፡፡ በዚች ምድር ብዙ ዓይነት ፍጡር አለ፡፡ አንዱ የሚለያዩበት ነገር እድሜ ነው፡፡ ዝንብ አንድ ቀን ትኖራለች፣ ውሻ 25 ዓመት፣ ኤሊ 200፣ ሰኮያ ዛፍ 4600 (አሜሪካ)፣ ሌላ ዓይነት ዛፍ (ደ/አፍሪካ) 6000 ዓመት ይኖራሉ ይባላል፡፡ ይህ የሕይወት ፀጋ ነው፡፡ በሰው ዘንድ ፀጋውን ብናዳብረው የበለጠ ተጠቃሚ እንሆናለን፡፡ ከዚያ በኋላ ብንፀድቅ ደግሞ ድርብ ፀጋ ይሆናል ማለት ነው፡፡ አምላክ መቼም ዝም ብላችሁ ሙቱ የሚል አይመስለኝም፡፡ ፍጡራን እድሜያችን የተለያየው እንደ ብቃታችን ሊሆን ይችላል፡፡
በዚች ተፈጥሮ አምላክ ራሱ ለዘላለም እንዴት እንደሚኖር ግራ ይገባል፡፡ እኛ ሰዎች አንድ ነገር ደጋግመን ስናደርግ ይሰለቸናል:: ማር እንኳን ሲደጋገም “ቋቅ ይላል” ይባላል:: እኛ ይህን ስሜት የምናንፀባርቀው በውዴታ ሳይሆን ተፈጥሯዊ ስለሆነ ነው፡፡ አምላክ ኑሮው “ቋቅ” እንዳይለው ምን ይሆን የሚያደርገው? ምናልባት በእለታዊው ለውጥ ውስጥ አብሮ ይለዋወጥ ይሆን?
የኛ እድሜ ምጥን ነው፡፡ በጊዜ ሒደት ነገር ስለሚቀያየር ደግሞ ፍጡርም ይቀያየራል ይባላል፡፡ በአለፈው 4½ ቢሊየን የሕይወት ዓመት ብዙ ዓይነት ፍጡራን ሰርፀዋል፣ አብዛኛው ግን ከስመዋል ይባላል፡፡ ጨረር ሲጠፋ ሕይወት ራሱ እንደሚከስም ይታሰባል፡፡ እውቀት ካለንና እስከዚያም ድረስ ከዘለቅን ሒደቱን መከታተል ይቻል ይሆናል፡፡ በእውቀት ግን ውሱን ነን፡፡ ስለ ውሱንነታችን ለማወቅ ለምሳሌ አንዱን ተራ ዜጋ ድንጋይ ከመሬት አንስተን፣ ይህ ምንድነው? ብንለው ድንጋይ ነው ይለናል፡፡ ድንጋይ ምንድነው? ካልነው ደግሞ “ድንጋይ ነዋ” ነው የሚለን፡፡ ስለ ድንጋይ ያለን እውቀት እዚህ ላይ አበቃ ማለት ነው፡፡ ስለ አምላክም ያለን እውቀት ተመሳሳይ ሊሆን ይችላል፡፡
ስለ ፍቅር ያለን ግንዛቤ ፈሩን ሳይለቅ አይቀርም፡፡ ፍቅር በሰው ዘንድ የሰረፀው በሴትና ወንድ ግንኙነት እንደሆነ ይታሰባል፡፡ ዓላማውም ረጅም እንክብካቤ የሚፈልገውን ሕፃን ልጃችንን ለአቅመ - መዋለድ ለማድረስ እንደሆነ ይነገራል:: አንዳንድ ሰዎች ለልጆች ፍቅር ስጧቸው ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ ፍቅር እንደ ብር ለሰው አይሰጥም:: በፍቅር ያደገ ልጅ ግን ከቤተሰቡ ይወርሳል፡፡ ሰው ይወዳል፣ ከሰው ይግባባል፣ የጋራ ችግርን ለመወጣትም ይተባበራል፡፡ በአንፃሩ ፍቅር ያጣ ልጅ ሰው አይወድም፤ ከሰው አይግባባም፣ አይተባበርም፡፡ እንዲያውም ማሕበረሰቡን ለመጉዳት በቀል ያደርጋል ይባላል፡፡ እናም ሰላማዊ ኑሮ ለመቋደስ በፍቅር መጋባትና ልጅን ተንከባክቦ ማሳደግ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡
የፍቅር ዓላማው ቢገባን ኖሮ የክርስቶስን ትምህርት ተከትለን፣ ሴትና ወንድ በፍቅር አንድ ለአንድ ተወስነን እንኖር ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ የልጅ ብዛትንና የምርት መጠንን ማጣጣም ያስፈልጋል፡፡ እንደሚታወቀው መዋለድና ማምረት እኩል አይሄዱም፡፡ መዋለድ ፈጣን፣ ማምረት ግን ዘገምተኛ ነው:: ሕዝብ ሲበዛ ደግሞ ትርፉ ድህነት፣ የተፈጥሮ ሀብት ብክነትና የእርስ በርስ ግጭት እንደሆነ ይታወቃል:: ይህን ሒደት ባለማወቃችን አለገደብ እየተባዛን ድህነትን ተከናንበን፣ እርስ በርስ እየተጋጨን እንኖራለን፡፡ የችግሩ መፍትሔ (ከ1-2 ልጅ በቤተሰብ መውለድ) በሰለጠኑ ሀገሮች ቢታወቅም፣ እኛ ግን በአጉል ባህል ተተብትበን መኮረጅ እንኳን ተቸግረናል:: መሪዎቻችንም ስለ ሕዝብ ብዛት ትንፍሽ አይሉም፡፡ ይህን የግጭት ምንጭ ካልፈቱልን እንዴት ሰላምና መረጋጋት ያመጡልናል? ከድሮ መሪዎቻችንስ በምንድነው የሚለዩት?
እኛ ኢትዮጵያውያን በረጅም የአብሮነት ታሪካችን፣ እርስ በርስ በእጅጉ ተካሰናል፡፡ የግራኝ አህመድ ወረራ፣ የኦሮሞ ፍልሰት፣ የአፄ ምኒልክ ግዛት ማስፋፋትና የአድዋ ጦርነት ድል እንዲሁም የአፄ ኃይለስላሴና የደርግ የአንድነት አስተዳደር፤ በዚህ አቅጣጫ ጥሩ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን በሕወሓት ከፋፋይነት እንዲሁም በጊዜ ሒደት፣ የሕዝብ ብዛትና የኑሮ ፍላጐት ባለመጣጣሙ፣ እውቀትና ፍቅር የጐደላቸው “እንግዴ ልጆች” በሚቀሰቅሱት ነገር ግንኙነታችን እየሻከረ መጥቷል፡፡
እንደ ማሕብረተሰብ ስንኖር ማወቅ ያለብን ጉዳይ፣ በፍጡራን መካከል ስለሚከሰተው ሽሚያ ነው፡፡ የባዮሎጂ ሊቆች እንደሚሉን፤ ፍጡር ሁሉ ለምግብና ውሃ፣ ለፍቅርና ለቦታ ወዘተ… እርስ በርሱ ይሻማል ይሻኮታል፡፡ ሽሚያው ደግሞ በቅርብ ዘመዳሞች መካከል ይግላል ይባላል፡፡ ይህም ማለት በሰው ዘንድ ወንድም ከወንድሙ፣ እህት ከእህቷ፤ የበለጠ ይሻኮታሉ ማለት ነው፡፡ እኛ ሰዎች በዚች ምድር ስንኖር ደግሞ ዋና ፀጋ ብለን የምናስበው ተወልደንና አድገን፣ ልጆች ወልደንና አሳድገን ማለፍን ነው፡፡ ታድያ ይህን ምኞት እንዴት ልናሳካው እንችላለን? ለዚህ ችግር ግልጽ መፍትሔው ዲሞክራሲ ወይም የእኩልነትና የነፃነት ስርዓት ነው፡፡ እኩልነት አንድነትን ያጠናክራል፣ ምርታማነትንና ራስ መቻልን ያበለፅጋል፡፡ ነፃነት፤ ግልፅ ያልሆነችውን ተፈጥሮ በአግባቡ እየዳሰስን እንድናውቃትና እንድንጠቀምባት፣ የእርስ በርስ ግንኙነታችንንም በእውነተኛ መንገድ እንድናሰርፅ ይጠቅመናል:: በጥቅም ምክንያት የሚደርስ ግጭትን ደግሞ የፍትሕ አካሉ (ፍርድ ቤት) ይፈታዋል፡፡ ቂም በቀል ግን አይኖርም፡፡
እኛ በባህላችን የለመድነው ስርዓት የበላይነት ወይም ሌሎችን መግዛት ነው፡፡ ገዢው አካል የኑሮ ፍላጐቱን በሌሎች ጉልበትና ልፋት ያሳካል:: በዚህ ስርዓት ለረጅም ጊዜ ስለቆየን በግልጽ ያካበትናቸው ባህሪዎች ውሸት፣ ማታለል፣ ማስመሰል፣ መስረቅ፣ መንጠቅ፣ መክላትና ቂም በቀል ናቸው፡፡ ባህሪዎቹ በማንኛውም ዓይነት ግንኙነታችን (ለምሳሌ፡- በምርት፣ በንግድ፣ በፍቅር፣ በሀዘን፣ በጦርነት ወዘተ…) በግልጽ ይንፀባረቃሉ፡፡ ችግሮቹ በተለይ በፍቅር፣ በጦርነት፣ በሀዘን ወዘተ-- ላይ ሲንፀባረቁ የበለጠ ይመርራሉ፡፡ በዚህ ዓይነት ጉዞ ለረጅም ጊዜ ስንገጫገጭ በመቆየታችን ከስልጣኔ ጎዳና ከሞላ ጎደል ወጥተናል። ምክንያቱም ስልጣኔ የሚሰርፀው እውነትና መልካም ግንኙነት ሲኖር ነው፡፡
እንስት እንደ አንዳንድ ወንድ ‹‹እውነትን ተናግሮ እመሸበት ማደር›› እምብዛም አትልም ይባላል፡፡ እንደ ሁኔታው ግን ታድራለች:: ልጅ ወልዳ ተንከባክባ በማሳደግ ደግሞ ስኬታማ እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ዘመኑ ለነጋዴ ይመቻል፤ ከሰለጠኑ አገሮች የኢንዱስትሪ ውጤቶች ይጎርፍለታል፡፡ ነጋዴው ግን ጥሩ ያልሆነውን እቃ ጥሩ ነው እያለ፣ ከዋጋው በላይ እያስከፈለ ይበዘብዘናል፡፡ በእንቡጥ ሴቶችም እያማለለ ያታልለናል፡፡ ጥሩ ሰው ለመምሰል ግን የማያደርገው  የለም፡፡ በአለባበሱና በአነጋገሩ ቅዱስ ይመስላል፡፡ ለድሆች ይመፀውታል። በእምነት ቤት ዙሪያም ሽር ጉድ ሲል ይታያል:: ድርጊቱ ግን እኛን ብቻ ሳይሆን ራሱ አምላክንም ጭምር እንደ ማታለል ይቆጠራል:: በድንቁርናችን በተዘፈቅንበት የበላይነት ሥርዓት እነሆ በፍሬቢስ ግንኙነት ዘወትር እንታመሳለን፡፡ ስርዓቱ ልዩ የተፈጥሮ ፀጋ የሆነችውን ሕይወታችንን ከእነ ጭራሹ እንዳያሳጣን ያሳስባል፡፡
ኢትዮጵያዊነት የሰፈነው በጥቂት አርቆ አሳቢ ገዢዎቻችንና የአንድነቱ ጥቅም በገባቸው ንቁ ብሔር ብሔረሰቦች ትብብር ይመስለኛል፡፡ በቅድሚያ አፄ ቴዎድሮስ ተበታትኖ የቆየውን የመሳፍንት ግዛት በወቅቱ አሰባሰቡት፡፡ ብልሁ አፄ ምኒልክ የአንድነት በትሩን ከአፄ ቴዎድሮስ ወርሰው ግዛቶችን አስፋፍተውና ሕዝቡን አስተባብረው፣ የኢጣሊያን የቅኝ ግዛት ጦርነት አድዋ ላይ መክተን፣ ከባርነት እንድንድን በቆራጥነት መርተውናል፡፡ በአሁኑ ዘመን ደግሞ ተመሳሳይ ችግር እየመጣ ሳይሆን አይቀርም፡፡ በአለም ደረጃ በካርቦን ልቀት ምክንያት የአየር ሙቀት እየጨመረ መጥቷል፡፡
ዝናብ በዝቷል፣ በየዋልታው ያለው በረዶ ይቀልጣል፤ የባህር ወለልም እያደገ ነው፡፡ ችግሩ እየተባባሰ ከሄደ የአንዳንድ የሰለጠኑ አገሮች መሬት በውሃ ስለሚሸረሸር፣ ውድ አገራችንን እናት ኢትዮጵያን በከፍታ ቦታነቷ ምናልባት ለቅኝ ግዛት ያጯት ይሆን? ማን ያውቃል? ለማንኛውም ጊዜው አሳሳቢ ነው:: ሕብረታችንን እንደ ልማዳችን አጠናክረን፣ የአድዋን ድል እንደገና መድገም ያስፈልገን ይሆናል፡፡
አሁን ‹‹ተረኛ›› መጥቷል ይባላል፡፡ ተረኛ የመጣው ለመግዛት ይሆን? መግዛት ረሀብንና ጥማትን ለጊዜው ያስታግስ እንደሆነ እንጂ ለዘለቄታው አያዋጣም:: በታሪካችን ገዢዎቻችን ሁሉ (ንጉሶች፣ ወታደሮች፣ ታጋዮች) ለጊዜው አለሁ አለሁ ቢሉም በስተመጨረሻ ግን ፈርሰዋል:: እኛንም ረግጠውናል፡፡ ተረኛው፤ አፍራሽነትን ትቶ ‹‹ኢትዮጵያዊነት›› ላይ ቢያተኩርና የራሱን የለውጥ አሻራ ቢያሳርፍ ለሁላችንም ይጠቅመናል፡፡ በቅድሚያ ማወቅ ያለበት ሐቅ ግን በዙሪያው ቆራጥና ጀግና አብሮ አደሮች እንዳሉ ነው፡፡ ከእነርሱ ጋር በመተባበር ዲሞክራሲን ማስረጽ ይጠበቅብናል። ዲሞክራሲ ከተዘፈቅንበት መሻኮትና መቆራቆዝ ያላቅቀናል::
ተረጋግቶ በመኖር ስልጣኔ ይሰርጻል:: በሒደቱም 1/ ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑትን ምግብ፣ ውሃ፣ እቃና ልብስ ማምረት ወይም ማቅረብ 2/ ከሰውነት ከቤትና ከስራ ቦታ የሚወጣውን ቆሻሻ በአግባቡ ማስወገድ 3/ በጀርም የሚመጡ በሽታዎችን እንዲሁም ተውሳኮችን መከላከል 4/ የኑሮ ተቀናቃኝን በዘመናዊ ዘዴ መመከት ያስችላል:: በአንድ በኩል፣ ስልጣኔ ሊሰርጽ በሌላ በኩል ደግሞ ችግርም ይከማች ይሆናል:: ችግር ሲበዛም ስልጣኔው ይሰናከላል:: ታሪክ እንደሚናገረው፤ ብዙ ስልጣኔዎች ከስመዋል፡፡ አሁን ከተረኛው የምንፈልገው ቁም ነገር፣ ስልጣኔን ተንቀሳቅሶ ከመኖር ጋር እንዲያዛምድልን ነው፡፡ እንደሚታወቀው፤ በተፈጥሮ ሁሉም ነገር ይንቀሳቀሳል ይባላል:: በሰው ዘንድ ደግሞ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ ሰውነትን ያፍታታል፤ ሕሊናንም ያድሳል:: በመንቀሳቀስ የሕዝቦች ግንኙነት ይሻሻላል፣ ስልጣኔውም እያደር ይታደሳል፡፡ ዘዴው አዲስ ነው፤ እንሞክረው፡፡ በእንቅስቃሴ ባሕላችን ሕልውናችንን እናድስ!!
እናት ኢትዮጵያ በስኬት ትገስግስ!!  

 ከአድማስ ትውስታ

Wednesday, 05 March 2025 00:00

ምዕራፍ 7

እስካርሌት በሁለት ሳምንቶች ውስጥ ሚስት ሆነች፡፡ ከዚያ በቀጠሉት ሁለት ወራት ውስጥ ደግሞ የሙት ሚስት ሆነች፡፡ በእርግጥ ምንም ሳታስብበትና በጥድፊያ ባለትዳር ብትሆንም ወዲያው ከዚህ ከትዳር ሰንሰለት እፎይ ብላ ለመገላል ችላለች፡፡ ዳሩ ግን እነዚያን ከትዳር በፊት የነበሩ የመዝናናትና እንደልብ የመጨፈር የምንግዴ ሕይወት መብትና ነፃነቷን፤ መልሳ ለማግኘት አልቻለችም፡፡ ከሰርጓ ማግስት ቀጥሎ በነበሩት ወራት የባሏ መሞት ሐዘን ተከተለባት፡፡ በልቧ እፎይ አለች እንጂ በሌላ ወገን የከፋት ነገር ተፈጥሯል- የልጅ እናት መሆን ተክሎባታል፡፡ ባንድ ጀምበር ሚስት፣ በሌላ ጀምበር የሙት ሚስት፣ ደሞ በሌላ ጀምበር እናት፡፡


ዓመታት ካለፉ በኋላ እስካርሌት የእነዚያን 1861 የሚያዚያ ቀናት ከነዝርዝር ውሎ- አመሻሻቸው ለማስታወስ በጭራሽ አትችልም፡፡ ጊዜና ክንውኖቹ ሁሉ እንደህልም፣ እንደቅዠት እየተደራረቡ ያላንዳች እውንነት ወይም ተጨባጭ ምክንያት ብዥ እንዳለ ፊልም አልፈዋል፡፡ መቼም እስክትሞት ድረስ እነዚያ ቀናት በትዝታዋ መዝገብ ውስጥ ባዶ ገጽ ሆነው ይቀራሉ፡፡ በተለይ ቻርለስ ለጋብቻ ሲጠይቃት እሺ ባለችበት ቀንና በሠርጋቸው ቀን ማህል ያለው ትውስታ ጭራሽ ጭልምልም ያለ ነው፡፡ ሁለት ሳምንት፣ መቼም በሰላሙ ጊዜ እንኳን ጋብቻ ፍጥምጥም የማይደረግበት ጊዜ ነው፡፡ ከፍጥምጥም ወዲያ ደግሞ የአንድ ዓመት ወይም ቢያንስ ቢያንስ የስድስት ወር ሞቅ ያሉ ቀናት ተጠብቆ ነበር ጋብቻ የሚፈጸም፡፡ ዳሩ ግን ደቡብ በእሳት በተያያዘበት ጊዜ በመሆኑ ድርጊቶቹ ሁሉ ንፋስ ተሸክሟቸው እንደሚነጉድ ሁሉ በከፍተኛ ፍጥነት ስለሚበሩ የጥንቶቹ ቀናት የእርጋታ ጉዞ ውበት፤ ለዛው ሙጥጥ ብሎ ጠፍቷል፡፡ ያኔ፣ ኤለን እጆቿን አጣጥፋ የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል እያለች እስካርሌትን በመምከር፣ ደግማ ደጋግማ ነገሯን ሁሉ እንድታስብበት ሞክራ ነበር፡፡ ሆኖም እስካርሌት የእናቷን ልመና ሁሉ ጆሮ ዳባ ልበስ ብላ ሜዳ አፈሰሰችው፡፡ ማግባቱን አገባች፡፡ ያውም ባንዳፍታ- በሁለት ሳምንት ውስጥ፡፡


አሽሌይ ከሰራዊቱ ጋር በተጠራ ጊዜ ለመሄድ እንዲያመቸው የሠርጉን ቀን ከበጋው መጀመሪያ ወደ ግንቦት መግቢያ ሲያዟዙረው እስካርሌት የሠርጓን ቀን ከሱ ሰርግ በፊት አደረገችወ፡፡ ኤለን እምቢ ብላ ነበር፡፡ ነገር ግን ከዋድ ሐምፕተን ሻለቃ ጦር ጋር ወደ ደቡብ ካሮላይና ለመሄድ ቻርለስ በጣም በመጣደፉ፣ በአዲስ ፍቅሩም ግፊት በመወትወቱ፣ ጄራልድም ሁለቱን ወጣቶች በመደገፉ፣ የተባለው ሠርግ እሷ በፈለገችው ቀን ለመሠረግ በቃ፡፡ ጄራልድ፣ አንድም በጦርነቱ ትኩሳት ምክንያት፤ አንድም እስካርሌት ጥሩ አቻ፣ አልፋም እኩያ ለመምረጥ በመቻሏ ተደስቶ የሠርጉን መፋጠን ይሁን አለ፡፡ ለዛውስ ጦርነቱ መጣሁ መጣሁ እያለ በሚፎክርበት ሰዓት በሁለት ፍቅረኛሞች ማህል ጣልቃ ገብቶ-አርጉ አታርጉ የሚለው፤ እሱ ማን ነውና ነው? ኤለን ሌሎች የደቡብ ሴቶች እንደሚያደርጉት ሁሉ ተሟግታ ተሟግታ በመጨረሻው እጇን ሰጠች፡፡ በእርጋታና በትርፍ ጊዜ የመዝናናት ወግ የተሞላው ዓላማቸው፤ ግርግር በበዛበት ዝባዝንኬ ሕይወት በመተካቱ፤ ልመናቸው፣ ፀሎታቸውና ምክራቸው ሁሉ ከንቱ ቀርቶ፤ እንደ ጎርፍ እየጠራረገ ከሚወስዳቸው ጠንካራ ንፋስ ጋር አብረው እንዲነፍሱ ተገደዱ፡፡
ደቡብ በጉጉትና በጦርነት ስሜት ተሳክሯል፡፡ መቼም ጦርነቱን በአንድ ውጊያ ከፍፃሜ እንደሚያደርሱት ማንም ያውቃል፡፡ በዚህ ምክንያት እያንዳንዱ ወጣት በጥድፊያ ለጦርነቱ ይመዘገባል፡፡ ስለዚህ ለፍቅረኛው በጥድፊያ ቀለበት ያስራል፡፡ ቀለበት ያሰረው ደግሞ በአጭር ጊዜ ሠርጉን ይደግሳል፡፡ እንዲህ በቶሎ አቀለጣጥፎ ጋብቻውን ውል እያስያዘ ወደ ቨርጂኒያ ሄዶ ያንኪዎችን ድባቅ ለመምታት ልቡ ተነሳስቷል፡፡ በደርዘን የሚቆጠሩ ከጦርነቱ በፊት የሚፈጸሙ የጋብቻ ሥነ-ስርዓቶች ስላሉ፣ ሰው ሁሉ ለመለያያ ለቅሶና ለሀዘን ምንም ጊዜ የለውም፡፡ ሴት ሴቶቹ ዩኒፎርም ይሰፋሉ፣ ካልሲዎች ይጠልፋሉ፣ የሚጠቀለሉ ፋሻዎችን ያዘጋጃሉ፡፡ ወንድ ወንዱ የሰልፍ ልምምዱንና ተኩሱን ተያይዞታል፡፡ ከአትላንታ በስተሰሜን ወደምትገኘው ወደ ቨርጂኒያ የሚሄዱ በሠራዊት የተሞሉ ባቡሮች በጆንስቦሮ እያቋረጡ እንደጉድ ይግተለተላሉ፡፡ ለሚሊሺያው ዩኒፎርም ለማዘጋጀት በተመረጡ ሕዝባዊ ኩባንያዎች የተሰፉትን፤ ደማቅ ቀይ፣ ውሃ ሰማያዊና አረንጓዴ ዩኒፎርሞች የለበሱ የተለያዩ ክፍሎች በደስታ ይተምማሉ፡፡ አንዳንድ ትናንሽ ቡድኖች ደግሞ እቤት የተሰፉ ባርኔጣዎችን አድርገዋል፡፡ ሌሎች ከናካቴው ዩኒፎርም ያልለበሱም አሉባቸው፡፡ ሁሉም ቢሆኑ በግማሽ ሥልጠናና በግማሽ ትጥቅ የሚጓዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን በስሜት ተሞልተው ሊፈነዱ ከመድረሳቸው የተነሳ እየጮኹ ወደ ሽርሽር የሚሄዱ ይመስላሉ፡፡ እነዚህን ዘማቾች የሚመለከቱት ገና በዝግጅት ላይ ያሉት ወጣቶች ልምምዱን አገባደው ቨርጂኒያ ከመድረሳቸው በፊት ጦርነቱ አልቆ ጉድ እንዳይሆኑ ሰግተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ሠራዊቱን ቶሎ የማዝመት ተግባር በጣም በጥድፊያ እየተሠራ ነው፡፡


በዚህ የጦርነት ጥድፊያ ማህል የእስካርሌት ሠርግ ድግስ ደግሞ እየተጧጧፈ ነው፡፡ በዚህ ተብሎ በዚያ እሷ ራሷ እንኳ መቼ ተገባደደ ብላ ባላሰበችበት ሰዓት የኤለንን የሙሽራ ልብስ ከነቩዋሉ ለብሳ፣ የአባቷን ክንድ ይዛ፣ የታራን ደረጃ በከፍተኛ አጀብ ወርዳ በእንግዶች ጢም ብሎ ወደተሞላው አዳራሽ ገባች፡፡ ሁሉ ነገር ካለፈ በኋላ እንደህልም ውል ውል የሚላት- ግድግዳው ላይ የተሰቀሉት በመቶ የሚቆጠሩ የሚንቦገቦጉ ሻማዎች፣ የእናቷ በፍቅር የተሞላ ፊትና በመጠኑ ደንገጥ ያለ አኳኋን፣ እንዲሁም ጋብቻዋ የአብርሃም የሣራ እንዲሆን ስትጸልይላት በዝግታ ይንቀሳቀሱ የነበሩ ከንፈሮቿ፣ ጄራልድ በብራንዲና በኩራት ፊቱ በላብ ቸፍ ብሎ፣ ሴት ልጁ ገንዘብም፣ መልካም ስምም፣ ደህና ዘርም ያገባች መሆኗ ሲያስፈነድቀው፣ አሽሌይ ደግሞ ከደረጃዎቹ ግርጌ ክንዱን ከሜላኒ ክንድ ጋር እንዳቆላለፈ ቆሞ፣ የሚታየው ትርዒት ነው፡፡ በአሸሌይ ፊት ላይ የሚነበበውን ሁኔታ ስታይ የሚከተለው ሀሳብ መጣባት- “ይሄ እውን ሊሆን አይችልም፡፡ ሊሆን አይችልም፡፡ ቅዠት ነው፡፡ ሕልም ነው፡፡ አሁን ባላስበው ይሻላል እንጂ በዚህ ሁሉ ሰው ፊት ጩኸቴን እለቀዋለሁ፡፡ አሁን በጭራሽ ለማሰብ አልችልም፡፡ ሌላ ጊዜ፣ ዓይኖቹን ለማየት በማልችልበት ጊዜ አስብበታለሁ፡፡”
ፈገግ ባሉትና በተሰበሰቡት እንግዶች ማህል ማለፉም ቢሆን ህልም የመሰለ ነገር ነው፡፡ የቻርለስ ሳምባ የመሰለ ፊትና የሚንቀጠቀጥ ድምጽ፣ የሷም ቀዝቃዛና ግራ የተጋባ መልክ ይታያል፡፡ በመጨረሻ እንኳን ደስ ያለሽ የመባሏ፣ የመሳሟ፣ የጥብስ ግብዣው፤ ዳንሱ ሁሉ እንደህልም ያለፈ ነገር ነበር፡፡ አሽሌይ ጉንጯን ሲስማት የተሰማት ስሜት፣ የሜላኒ “አሁን በእርግጥ እውነተኛ እህትማማቾች ሆንን” የሚል ለስላሳ ድምፅ-ይሄ ሁሉ እውን ያልሆነ ቅዠት ነበር፡፡ የቻርለስን አክስት ወይዘሮ ፒቲፓት ሐሚልተንን ከመቀመጫቸው ያስነሳቸው የስሜት ግንፋሎት እንኳን ሳይቀር፤ የሰመመን መንፈስ እንደዋጠው ባለ ሕልም ነው የሚታያት፡፡
ሊነጋጋ ሲል ዳንሱም ግብዣውም ሲገባደድ፤ ታራንና የምስለኔውን ቤት አጨናንቀውት የነበሩት ከአትላንታ የመጡት እንግዶች፤ በየአልጋው፣ በየሶፋውና በየምንጣፉ ላይ ሲተኙ፤የጎረቤቶችም ሰዎች ሁሉ በሚቀጥለው ቀን በ”አሥራ ሁለቱ ዋርካዎች” መናፈሻ ቦታ ለሚደረገው ሰርግ ለመዘጋጀት ወደየቤታቸው ሲሄዱና አካባቢው ሁሉ እርጭ ሲል፤ ያ ሁሉ እንደህልም እንደ ቅዠት የታየ ነገር ከገሃዱ ዓለም ጋር ተጋጨና እንደ መኪና መስታወት እንክትክቱ ወጥቶ ዱቄት ሆነ፡፡ ገሃዱ ዓለም፤ አንገቷ ድረስ አንሶላውን ስባ የማይጥም መልኳን ስታሳየው እንኳ ከምንም ሳይቆጥራት በደስታ የሚፈነድቀውን ቻርለስን አሳያት፡፡
እስካርሌት ባልና ሚስት በአንድ አልጋ ውስጥ እንደሚያድሩ በደንብ ታውቃለች፡፡ ነገር ግን እስከዚህም ከጉዳይ ጽፋ አስባበት አታውቅም፡፡ ከእናቷና ከአባቷ አንፃር ስታየው ነገሩ ትክክል ነው፡፡ በራሷ ላይ ደርሶ ስታየው ግን በጭራሽ አልዋጥ አላት፡፡ አሁን ለመጀመሪያ ጊዜ ከዛ ከ”አሥራ ሁለቱ ዋርካዎች” ግብዣ በኋላ በራሷ ላይ ምን ዓይነት መዘዝ እንዳመጣች ተገነዘበች፡፡ ለራሷ በችኮላ የማይሆን ውሳኔ በመወሰኗ የፀፀት ምጥ በሚያሰቃያትና አሽሌይን ለዘለዓለም የማጣቷ ነገር እንደ እግር እሳት በሚለበልባት ሰዓት፤ የዚህ ልታገባው ፈጽሞ እቅድ ያልነበራት ልጅ አብሯት አንድ አልጋ ውስጥ ማደር፤ በጭራሽ ልትሸከመው ከምትችለው በላይ ሆኖባታል፡፡ እሱ እያመነታ ወደ አልጋው ሲጠጋ በጎረነነ ድምጿ አንሾካሾከችለት፡፡
“እንዲች ብለህ ብትጠጋኝ እሪ ብዬ ነው የምጮኸው! ላንቃዬ እስከሚሰነጠቅ አገሩን አደባልቀዋለሁ! በል ካጠገቤ ጥፋ! ጫፌን ንካኝና ወዮልህ!”
ቻርለስ ሐሚልተን በዚህ ዓይነት የሠርጉ ዕለት ማታ በመኝታ ቤቱ ጥግ ባለ፣ ባለመደገፊያ ወንበር ላይ ጉልበቱን ታቅፎ አደረ፡፡ ይህን ያህልም አልከፋውም፡፡ ምክንያቱም የሙሽራይቱን ትህትናና ልስላሴ ስለተረዳው ወይም የተረዳው ስለመሰለው ነው፡፡ ፍራቻዋ ሁሉ ሟሙቶ እስኪጠፋና እሱን ለመቀበል ዝግጁ እስክትሆን ድረስ ለመጠበቅ ፈቃደኛ ሆነ፡፡ ብቻ…ብቻ እየተገላበጠ፣ ለመመቻቸት እየሞከረ በጣም በቅርቡ ወደ ጦርነት እንደሚሄድ አሰበና አንዴ በኃይል ተነፈሰ፡፡


የእስካርሌት ሠርግ እንደሕልም እንደቅዠት እንዳለፈ ሁሉ የአሽሌይ ደግሞ ከሷ በባሰ የሕልም ጭጋግ ውስጥ እንደተሸፈነ አለፈ፡፡ እስካርሌት በ”አሥራ ሁለቱ ዋርካዎች” መናፈሻ እልፍኝ፣ ውሃ አረንጓዴውን “የሠርግ ማግስት ቀሚሷን” እንደለበሰች ከትላንት ማታ ጀምሮ እየበሩ ባሉት በመቶ በሚቆጠሩ ሻማዎች ማህል ቆማ፤ የሜላኒ ሐሚልተን ትንሿ ፊት የውበት ፀዳል ስትጎናፀፍ ተመለከተች፡፡ ወ/ት ሜላኒ ሐሚልተን ወ/ሮ ሜላኒ ዊክስ በምትሆንባት በዚህች ቅፅበት ፊቷ ላይ የሚበራው ቁንጅና እጅግ አስደንጋጭ ነው፡፡ እንግዲህ አሽሌይ ለአንዴም ለሁሌም መሄዱ ነው፡፡ ከጭብጧ ተፈልቅቆ ወጥቶ ማምለጡ ነው፡፡ የሷው አሽሌይ፡፡ አዬ! ምኑን የሷው ሆነው፣ አሁንማ የሰው አሽሌይ ሆኗል፡፡ ለመሆኑ የሷ ሆኖስ ያውቃል እንዴ? እስካርሌት በጭንቅላቷ ውስጥ መዓት ነገሮች እየተርመሰመሱ የምታስብ የምታልመውን ሁሉ አሳጧት፡፡ ጭንቅላቷም ለማሰብ ከሚችለው በላይ ስለበዛበት ደከመው፡፡ ተረባበሸ፡፡ አሽሌይ አፈቅርሻለሁ ሲላት አልነበረም እንዴ? ታዲያ ምን ለያያቸው? ይሄን ለማስታወስ ብትችል በጣም ጥሩ ነበር፡፡ ቻርለስን በማግባቷ የመንደሩን ሰዎች ሐሜተኛ ምላስ እንዲታጠፍ አድርጋ፣ አፋቸውን አስዘግታ ነበር፡፡ ዳሩ ያ አሁን ለሷ ምን ረባት? በዚያን ጊዜ በጣም ትልቅ ጉዳይ ነበር፡፡ አሁን ግን ከቁጥር የሚጣፍ ነገር አይደለም፡፡ ያም ቢሆን ለሷ ትልቁና አስፈላጊው ጉዳይዋ አሽሌይ ብቻ ነበር፡፡ አሁን እሱም አመለጣት፡፡ እሷም ብትሆን፤ አለማፍቀር ብቻ ሳይሆን በጣም ከምትጠላው ሰው ጋር ተጋብታ አርፋለች፡፡
(ከነቢይ መኮንን “ነገም ሌላ ቀን ነው” መጽሐፍ የተቀነጨበ)

 

ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ለመያዝ ለሁለት ሺ ዓመታት ያህል የተደጋገመ ሙከራ ተደርጓል፡፡ ኢትዮጵያውያን ግን አገራቸውን በሌላ ባዕድ ሳያሲዙ ባላቸው ኃይል ሲከላከሉ ቆይተዋል። በኤሮፓም ሆነ በአሲያ ወይም በአፍሪካ የሚነሱ ታላላቅ መንግሥታት ጉልበት እያገኙ ግዛታቸውን በሚያሰፉበት ጊዜ ኢትዮጵያንም ለመደረብ ብዙ ጊዜ ሞክረዋል = ኢትዮጵያውያን ግን ለማንም ሳይበገሩና ሳይገብሩ እስካ ሁን አገራችንን አስከብረው ቆይተዋል።
መለስ ብለን ከታሪካችን ውስጥ በመጠኑ ብንመለከት፣ የሚያኮራንንና የሚያስመካንን ታሪክ ማግኘት እንችላለን። ከክርስቶስ በፊት በ336 በግሪክ ላይ ነግሶ የነበረው ታላቁ አሌክሳንደር ግዛቱን እያሰፋ ከመቆዶንያ’ ግብጽ ድረስ ተሻገረ። ብዙ አገሮችም በጦር ሳይሆን ገና በዝናው እየፈሩ ገበሩለት። ኩዌንቱስ ኩርቲውስ የተባለው የዘመኑ ታሪክ ፀሐፊ የአሌክሳንደርን ግዛት ማስፋፋትና ለጦርነት መነሳት ሲገልጽ፤ “…ወጣቱ ንጉሥ ለጦርነት ሲነሳ የምወረው ግብጽን ብቻ አይደለም። ኢትዮጵያንም ጭምር ነው።…” ማለቱን ጽፏል። አሌክሳንደር ዝቶ እንደተነሳው ከግብጽ ጀምሮ እስከ ህንድ ድረስ አስገበረ። በመሀል ግን ኢትዮጵያ ከገባሪዎች ተነጥላ ቀረች። አሌክሳንደር ስለ ኢትዮጵያውያን ጀግንነት ሰምቶ ነበርና ከኢትዮጵያውያን ጋር ጦርነት ለመግጠም ፈራ። ስለኢትዮጵያውያን የሚነገረው ጀግንነትም እውነት ስላልመሰለው ራሱ አሌክሳንደር ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቶ ለመሰለል ተነሳ። ክሮኒክልስ ኦፍ ጆን ፣ ቢሾፕ ኦፍ ኒኩ በሚባለው መጽሐፍ ላይ እንደሚተርከው፤ “አሌክሳንደር ከምርጥ የጦር አለቆቹ ጋር ሆኖ ሁሉም ተራ ሰው መስለው ለመሰለል ወደ ኢትዮጵያ ገቡ። ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ህንደኬም አሌክሳንደር ተራ ሰው መስሎ ወደ ኢትዮጵያ ለመሰለል መግባቱን ሰማች። ንግሥቲቱ እነኚያን እንግዳ ተራ ሰዎች ወደ ቤተ መንግሥትዋ አስጠርታ እንዲህ አለች፤ ‘ዓለምን አንቀጥቅጠህ የገዛህ ታላቁ እስክንድር ሆይ ፧ ዛሬ በሴት እጅ ተይዘሃል’ ስትለው ንጉሡ በመታወቁ ደንግጦ ጥበቧን አደነቀ። የኢትዮጵያን ወታደር ብዛትና የሰላዮቿን ጥበብ አድንቆ “ንግሥት ሆይ፤ የተነገረኝ ሁሉ እውነት ነው = ይህ በጦር የማይፈታ ሕዝብ ነውና እኔና አንቺ ተጋብተን ዓለምን እንግዛ አላት” ይላል።
ኢትዮጵያን ለማስገበር ከተነሱት ታላላቅ የኤሮፓ ነገሥታት መሀል አንዱ አወጉስቶስ ቄሳር ነው። የሮማው አግውስቶስ ቄሣር ኤሮፓንና አፍሪካን፣ ኤስያንም ጭምር አስገብሮ በሥልጣኑ ሥር ካደረገ በኋላ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ29 ዓመት ላይ አይሎስ ጋሎስ በሚባል ጦር አዛዥ የሚመራ 10,000 እግረኛና 8,000 ፈረሰኛ ጦር ወደ ኢትዮጵያ ላከ። በዚያን ዘመን የአክሱም መንግሥት ገንኖ ስለነበር፣ የኢትዮጵያ የባህር ኃይል ፈጽሞ የማይበገር መሆኑን ያወቀው አይሎስ ጋሎስ፤ ጦሩን በግብጽና በዛሬው ሱዳን በኩል አሻግሮ የአክሱምን መንግሥት ለመውጋት ገሠገሠ = ይህን የሰሙ ኢትዮጵያውያን ጦራቸውን ከትተው የአውግስቶስ ቄሣርን ጦር ከወሰናቸው ማዶ አቆሙት። ለብዙ ዓመታት ውጊያው ተካሂዶ ኢትዮጵያውያን አልበገር በማለታቸውና ከሮማ የመጣው ጦርም እየመነመነ በመሄዱ፣ የሮማው ጦር አዛዥ አይሎስ ጋሎስ ከሮማው ንጉሥ በታዘዘው መሠረት፣ ጦርነቱ በእርቅ አልቆ የተረፈው የሮማ ጦር ወደ አገሩ ተመለሰ።
በቅርቡ የአድዋን ጦርነት ብድር ለመመለስ ፋሺስቶች በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት እንዳወጁት ሁሉ በአውግስቶስ ቄሣር የደረሰውን ሽንፈት ብድር ለመመለስ፣ በ54 ዓ.ም በሮማ የነገሰው ኔሮ ፎክሮ ተነሳ- የኔሮ አማካሪዎችም፣ ኢትዮጵያውያን አገራቸውን የማያስነኩና በጦርነትም የማይሸነፉ ሕዝቦች መሆናቸውን ነግረው፣ ያሁኑ ወደ ኢትዮጵያ ጦር መላክ የባሰ ውርደት ይሆናል በማለት አስጠነቀቁት፡፡
ኔሮ የአማካሪዎቹን ምክር ቢሰማም የዘመኑን የኢትዮጵያን ጦር የሚሰልል የስለላ ቡድን ወደ ኢትዮጵያ ላከ። እዚህ ላይ ሮማዊው የዘመኑ ታሪክ ፀሐፊ ሴኔካ ከፃፈው ታሪክ በጥቂቱ እንጥቀስ፤ “ኔሮ የአባቶቹን ምኞት ለመፈፀም የአባይን ምንጭ የሚፈልጉ ናቸው ብሎ ለኢትዮጵያው ንጉሥ ደብዳቤ ጽፎ ሰላዮቹን ወደ ኢትዮጵያ ላከን = የተላክነው ሰላዮች ኢትዮጵያ ውስጥ ከርመን ስንመለስ ሕዝቡ ጦረኛ መሆኑንና በአሁኑ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ጦር መላክ እንደማያዋጣ ነገርነው፡፡ አገሪቱ ግን እጅግ በጣም ለም ናት አልነው” ሲል ከስለላ ቡድኑ ጋር አብሮ የነበረው ሴኔካ ጽፏል።
ይህ ሁሉ ቢሆንም ኔሮ አባቶቹ ያልቻሉትን ኢትዮጵያን የማስገበር ምኞት እሱ እንደሚችል ተማምኖ ካምቤይስ በሚባል ጦር መሪ የሚመራ ጦር፣ ወደ ኢትዮጵያ ልኮ ጦሩ ድል ሆኖ መመለሱን ታሪክ ፀሐፊዎቹ ዲዩ ካሲዮ እና ፕሊኒ ጽፈዋል።
ዛሬ በዓለም ላይ አሉ እንደሚባሉት አራቱ ኃያላን መንግሥታት ሁሉ፤ ኢትዮጵያም በሦስተኛው መቶ ዓመት በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉት አራቱ ኃያላን መንግሥታት አንዲቱ ነበረች፡፡ ሂስቶሪካ አውጉስታ በሚባለው የታሪክ መጽሐፉ ማኒ በ275 ዓ.ም እንደፃፈው፤ “…… በዓለም ካሉት አራቱ ታላላቅ መንግሥታት አንዷ ኢትዮጵያ ናት = የኢትዮጵያው የአክሱም መንግሥት በወታደርና በጦር መሣሪያ የበለፀገ በመሆኑ ለወዳጁ አገሮች ርዳታ በመስጠት የታወቀ ነው….” ብሏል፡፡ እነ ኮንቲ ሮስኒም ይህን አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያን አስገብሮ ለመያዝ የተደጋገመ የውጭ ጦር ቢመጣም ኢትዮጵያውያን ባላቸው ኃይል የማይበገሩ ሆነው የሚመጣውን የውጭ ጦር ሁሉ መልሰዋል። ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን የማይለቁና የሌላ አገር የማይፈልጉ በመሆናቸው እንጂ እንደ ታሪክ ፀሐፊዎች መስካሪነት ከሆነ፣ ኤሮፕንም ሆነ እስያን እያለፉ የሚይዙበት ብዙ ዘመን ነበር = በ1298 የባህር ላይ ጉዞውን የጀመረው ማርኮ ፖሎ በፃፈው ታሪክ ስለ ኢትዮጵያውያን ሲገልጽ እንዲህ ይላል፤ “…ልታውቁት የሚገባ - ነገር አለ = በአበሻ ምድር ምርጥ የሆኑ ወታደሮች አሉ፡፡ አብዛኛዎቹ ወታደሮችም ፈረሰኞች ናቸው። ፈረስም በብዛት አላቸው። በዚህም ምክንያት ተዋጊዎችና ኃይለኞች ናቸው። በህንድ አገር ስላሉትና ከምናደንቃቸው እውቅ የሕንድ ወታደሮችም የሚበልጡ ናቸው ……” ብሏል = ባጭሩ በዚሁ ይብቃን።
(“የኢትዮጵያና የኢጣሊያ ጦርነት” ከተሰኘው የጳውሎስ ኞኞ መጽሐፍ መግቢያ የተወሰደ)

 

 

 

በወንዶች ታደሰ ታከለ ሲያሸንፍ በሴቶች ደግሞ አትሌት ሱቱሜ አሰፋ በበላይነት አሸንፋለች።

በዓለም አትሌቲክስ የፕላቲኒየም ደረጃ በተሰጠው ማራቶን በሴቶች አትሌት ሱቱሜ አሰፋ 2 ሰዓት ከ16 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ በመግባት በአንደኝነት አሸንፋለች።

በወንዶች የቶክዮ ማራቶን አትሌት ታደሰ ታከለ በ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ23 ሰከንድ በመግባት የግል ምርጥ ሰአቱን በማሻሻል ጭምር አሸንፏል።

ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ደረሳ ገለታ በ2 ሰዓት ከ3 ደቂቃ ከ51 ሰከንድ በመግባት ሁለተኛ ደረጃ ይዞ አጠናቋል፡፡

በአገራችን አዲስ አበባ የተገነባው ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን እና የኮንቬንሽን ማዕከል ከቱሪዝም ገቢ በተጨማሪም፣ የኤግዚቢሽንና የጉባኤ ማዕከል በርካታ ጥቅሞችን ያበረክታል። በዙሪያው የቢዝነስና የስራ ዕድሎችን የሚያስፋፋ፣ የእድገትና የብልጽግና ግንኙነቶችን የሚፈጥር የኢኮኖሚ መነሃሪያ (Hub) በመሆን ያገለግላል። ባሕላዊ፣ ጥበባዊና ማኅበራዊ ፋይዳዎችን የሚያበራክትም ነው - የሚሰጣቸው አገልግሎቶች በዓይነታቸው ብዙ ናቸው።
የኢንዱስትሪ፣ የቴክኖሎጂ፣ የምርትና የአገልግሎቶች ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን ሲዘጋጅ፣ የዕውቀት ሽግግርን ያቀላጥፋል። የኢንቨስትመንትና የቢዝነስ አማራጮችን ይከፍታል። የንግድና የገበያ ግንኙነቶችን ለመፍጠር፣ ውል ለመፈራረም፣ ሽያጭና ግዢ ለመጀመር መልካም አጋጣሚዎችን ይፈጥራል።
ዓለም አቀፍ ጉባኤዎችንና ዝግጅቶችን የሚያስተናግድ አገር፣ በዓለማቀፍ የዲፕሎማሲና ኢኮኖሚ መድረክ ተሰሚነቱ ይጨምራል። የኢኮኖሚ ድርሻው  እያደገ ይሄዳል።
አዲስ አበባ የኤግዚቢሽንና የኮንቬንሽን ማዕከል ያስፈልጋታል። ለዚያውም፣ በዓለማቀፍ ደረጃ መወዳደርና ተመራጭነትን ማግኘት የሚችል፣ በላቀ የጥራት ደረጃ አስፈላጊ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ማዕከል እንደሆነ ከንቲባ አዳነች አበቤ ይናገራሉ።
አዲስ ዓለማ ዓቀፍ ኤግዚቢሽንና ኮንቬንሽን ማዕከል፤ 5ሺ እና 2ሺ ተሳታፊዎችን የሚያስተናግዱ ትልልቅ አዳራሾች ፣ ለኤግዚቢሽኖች እንዲሁም ለጉባኤዎች በስምንት ንዑስ አዳራሽ በርካታ ስብሰባዎችን በአንድ ጊዜ ማስተናገድ የሚያስችል ነው። በዓለም የኤግዚቢሽንና የኮንፈረንስ ቱሪዝም ካርታ ላይ የኢትዮጵያ ስምና ድርሻ ጎልቶ እንዲታይ የሚያደርግ ሰፊ ፕሮጀክት። ከተጓዳኝ ግንባታዎች ጋር 15 ሄክታር ይሸፍናል። በዓለም ደረጃ የመወዳደርና ተመራጭነትን የማግኘት ብቃት እንዲኖረው ታስቦ የተገነባ።


መዲናችን አዲስ አበባ ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችን፣ ጉባኤዎችንና ስብሰባዎችን በአንድ ማዕከል የማስተናገድ አቅም አልነበራትም፤ ይህን የአገራችንን ጉድለት የሚያሟላ ማዕከል ተገንብቶ ለምርቃት የደረሰ ፕሮጀክት፤ ለከተማችንና ለአገራችን ተጨማሪ የስበት ማዕከል ይሆንልናል።
በመሀል ከተማ የዓድዋ ድል መታሰቢያ ግንባታ፣ ከአኩሪ ታሪካችን ጋር የተያያ ጥሩ ነገር ፈጥሮልናል።
የትልቅ ታሪክ መዘክር ከመሆኑም በተጨማሪ፣ በግንባታው ጥራትና ውበት፣ በጠቅላላ ይዘቱና በተሟላ አገልግሎቱ ምን ያህል ተመራጭነትን እንዳገኘ በተግባር አይተናል። የኮንፈረንስ ቱሪዝም ስበት ለመሆን ችሏል። አዲስ አበባ የዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችና ጉባኤዎች መነሃሪያነቷን የምናረጋግጥበት፣ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከልነቷን በኩራት የምንመሰክርበት ይሆናል።
አገራችን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መሥራችም ናት። የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የሚገኘው በአዲስ አበባ ነው። ከዚህም ጋር ተያይዞ በርካታ የተመድ ተቋማት በአዲስ አበባ ከትመዋል። ይሄ ሌሎች አገራት የማያገኙት ዕድል ነው። የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከላት ተብለው የሚጠቀሱ የዓለማችን አገራት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው። ኢትዮጵያ ከእነዚህ መካከል አንዷ ናት።
በታሪካዊ ሀብቶችና በተፈጥሮ ጸጋዎች የታደለች ቢሆንም ግን፣ በዓለም ዓቀፍ የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ዘርፍ ውስጥ ተገቢውን ጥቅምና ድርሻ እያገኘች አይደለችም። በተመድና በአፍሪካ ሕብረት ስር የተካተቱ ብዙ ተቋማት በከተማችን አሉ። ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችንና ጉባኤዎችን ማካሄድ ይፈልጋሉ። እዚሁ አገራችን ውስጥ ቢሆንላቸው ይመርጣሉ - ብዙዎቹ። ነገር ግን፣ ተስማሚ ማዕከላትና አማራጮች ፍለጋ ወደ ሌሎች አገራት ያማትራሉ።
ትልልቅ ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችን በብቃት ለማስተናገድ የምንችልበት፣ ዓለም ዓቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት የሚሰጥና ዘመናዊ መሠረተ ልማቶች የተሟሉለት ማዕከል በብቃት ሳናሰናዳ ስለቆየን በየዓመቱ ብዙ ዕድሎችን ያስቀርብናል። የአገራችንን ኢኮኖሚ ሊያሳድጉ የሚችሉ የሥራና የገበያ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ዕድሎች ዓይናችን እያየ ያመልጡን ነበር። አሁን ግን በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ጥራቱን የጠበቀና የተሟላ አገልግሎት የሚሰጥ ማዕከል ተገንብቷል።
የማዕከሉ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሲሳይ ገመቹ እንደሚሉት፣ የግንባታውን ጥራትና ውበት በርካታ ባለ ሙያዎች አይተው መስክረውለታል።
ትልቁ ሁለገብ አዳራሽ - ለስብሰባም ለኤግዚቢሽን ማሰናጃም የሚሆንና 5 ሺ ተሳታፊዎችን ማስተናገድ የሚችል ነው፡፡
ዲዛይኑ የሕንጻውን ንድፍ በግላጭ የሚያሳይ “ስቲል ስትራክቸር” እንደሆነ ጠቅሰው፣ በባለ ሙያዎችም ሆነ በተመልካቾች ዐይን ሲታይ ያምራል ብለዋል። ለእያንዳንዱ የስብሰባ ወይም የኤግዚቢሽን ይዘት በሚስማማ መንገድ አዳራሹን ለማስጌጥ እንዲያመች ታስቦበት የተሠራ እንደሆነም ገልጸዋል።
በርካታ ሺ ሰዎችን በአንዴ የሚያስተናግድ ሰፊ አዳራሽ ቢሆንም፣ አየር እንደ ልብ ስለሚያንሸራሽር፣ የጣሪያው ከፍታም 28 ሜትር ስለሆነ የሙቀት መቆጣጠሪያ አያስፈልገውም። በተፈጥሯዊ ብርሃን አዳራሹን የሚያጥለቀልቁ ረዣዥምና ሰፋፊ መስኮቶች አሉት። የፊልም ምስሎችን ለማየት ወይም የኤሌክትሪክ መብራት መጠቀም ካስፈለገም፣ መስኮቶቹን ሙሉ ለሙሉ መጋረድ ይቻላል።
ሁለት የምግብ አቅርቦት ማስተናገጃ ስፍራ፣ እንዲሁም የእረፍት ሰዓት የሻይ የቡና መስተናገጃ ሰፊ ቦታ አለው። ከአዳራሹ ሥር በታችኛው ፎቅ ወደ ተዘጋጁት በርካታ የመጸዳጃ ቤቶች የሚያደርስ መተላለፊያ የሚገኘውም በዚሁ አቅጣጫ ነው። በአዳራሹ ሌላኛው ጎን የክብር እንግዶች መቆያ ቦታና ተጨማሪ የመጸዳጃ አገልግሎት ስፍራዎች ተሰርተውለታል።
የኤግዚቢሽን አዳራሽ - በ5 ሺ ካሬ ሜትር ስፋት የተገነባ፣ ከሁለገብ አዳራሽ ቀጥሎ ከላይ የምናገኘው ትልቅ አዳራሽ ዋና አገልግሎቱ ለኤግዚቢሽን ነው።
መካከለኛ አዳራሽ - አንድ ሺ ሰዎችን ያስተናግዳል። ዘና ያለ መንፈስ እንዲኖረው፣ አየር በደንብ እንዲንሸራሸር፣ የተፈጥሮ ብርሃን በሰፊው እንዲያስገባ ታስቦበት የተሰራው አዳራሽ፣ ጣሪያው 28 ሜትር ቁመት አለው።
ከመደበኛ የኤሌክትሪክ መስመሮች በተጨማሪ ወለል ሥር የተቀበሩ መስመሮችም ተዘርግተውለታል። ኤግዚቢሽን የሚያቀርቡ ተሳታፊዎች፣ ከአዳራሹ ወለል ላይ ከዳር እስከ ዳር የኤሌክትሪክ ሶኬቶችን በአጠገባቸው ስለሚያገኙ፣ ግራ ቀኝ የሚዝረከረኩ ገመዶች አይኖሩም።
ከአንድ አቅጣጫ በኩል፣ ከአዳራሹ አጠገብ የመጋዘን ክፍሎች አሉት። በሌላኛው አቅጣጫ ደግሞ ቢሮዎችን ይዟል። በአጠቃላይ ከኤግዚቢሽን ዝግጅት ጋር የተዛመዱ  አገልግሎቶችን ሁሉ እንዲያሟላ ተድርጎ ነው የተሠራው።
ሰፊ የትዕይንት አዳራሽ - በተገጣጣሚ ግድግዳም ሲከፋፍሉት ደግሞ ሰባት ንዑስ አዳራሾች ያሉት ሲሆን አራተኛ ፎቅ ላይ የምናገኘው ሰፊ አዳራሽ፣ 2 ሺ ሰዎችን ማስተናገድ ይችላል። ለትልቅ ጉባኤ ሊያገለግል ይችላል።
ስዕሎችን ለማሳየት ወይም ሌላ ለእይታ የሚቀርቡ ድግሶችን ለማዘጋጀትም የአዳራሹ ቅርጽ ይመቻል። ተመልካቾች በአንዱ ጫፍ ገብተው፣ በእይታ ድግሶች ተስተናግደው ዓይናቸውን ረክቶ በሌላኛው ጥግ ይወጣሉ። ካስፈለገ ደግሞ ረዥሙ አዳራሽ ውስጥ ተገጣጣሚ ግድግዳዎች ተዘርግተው፣ ለንዑስ ስብሰባዎች የሚያገለግሉ 7 መካከለኛና አነስተኛ አዳራሾች ይወጣዋል።
ግድግዳዎቹ ተጣጣፊ ተገጣጣሚ ቢሆኑም፣ ከመደበኛ ግድግዳ አይተናነሱም። ድምጽ አያሳልፉም፤ ሲታዩም ያምራሉ ብለዋል - የማዕከሉ ዋና ስራ አስፈጻሚ።
አዳራሹ አራተኛ ፎቅ ላይ ቢሆንም፣ ከበቂ በላይ መተላለፊያዎች አሉት። በየአቅጣጫው በተሠሩ በርካታ ሰፋፊ ደረጃዎች አማካኝነት መግባትና መውጣት ይቻላል። ከደረጃዎች ጎን “ስካሌተሮች” አሉ። ከእነዚህ በተጨማሪም አሳንሰሮች (ሊፍቶችን) መጠቀም ይቻላል። መጨናነቅም ሆነ መጣበብ አይኖርም።
የአዳራሾቹን አገልግሎት በትክክል ለማከናወንና ለመቆጣጠር የሚያገለግሉ የቴክኒክና የቴክኖሎጂ ክፍሎችን ጨምሮ፣ የጥበቃና የክትትል ስራውም በሚገባ እንደታሰበበት ስራ አስፈጻሚው ያስረዳሉ። ለዚህም የጥበቃ ካሜራዎችና መከታተያ ቴክኖሎጂዎችን አሟልተናል ይላሉ - አቶ ሲሳይ። የጥበቃ ባለሙያዎች የተሰብሳቢዎችን ትኩረት በማይረብሽ ሁኔታ ስራቸውን ያከናውናሉ።
የኤግዚቢሽንና የጉባኤ አዳራሾች በተጨማሪ፣ ማዕከሉ ሌሎች በርካታ ግንባታዎችንንና አገልግሎቶችን ያካትታል።
ባለ 5 ኮከብ ሆቴል - 980 የእንግዶች ማረፊያ ያለው።
በሆቴል አገልግሎት በከተማችን በትልቅነቱ ቀዳሚነትን የያዘ ሆቴል እንደሚሆን የተናገሩት ከንቲባ አዳነች አበቤ፣ 980 የእንግዳ ማረፊያዎችን መያዝ ይችላል ብለዋል።
እዚህ አካባቢ ምንም ሆቴል አልነበረም ይላሉ - ከንቲባ አዳነች። አሁን ሦስት ሆቴሎች ተሰርተዋል። አራተኛው ከማዶ በኩል አለ። ተደማምረው 1400 የእንግዳ ማረፊያ አገልግሎት የማቅረብ ዓቅም አላቸው።
ምርጥ ምርጥ አፓርትመንቶች በአካባቢው ተሰርተዋል። ለሕዝብ አገልግሎት ክፍት የሚሆኑ አረንጓዴ ስፍራዎችና ተቋማትም ተዘጋጅተዋል።
ፊት ለፊት ለሚ ፓርክ አለ። ሰፊ ነው። ከመስቀል አደባባይ በመቀጠል የሚጠቀስ የከተማችን ትልቅ አደባባይ ነው። ከኤግዚቢሽንና ከጉባኤ ማዕከሉ ጋር ተያይዞ ነው ስራው የሚከናወነው።
ይህ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ ግዙፍ እና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ “አዲስ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ማዕከል”  ትላልቅ አህጉር አቀፍ እና ዓለምአቀፍ ሁነቶችን ለማስተናገድ በሚያስችል ደረጃ ለምረቃ መብቃቱ ለከተማዋ ተጨማሪ ግርማ ሞገስን ያጎናፀፈ ነው፡፡

(የሚጬነ ከናስ አቻ ቦታ እሜስ ዴሬቄነ ኩቶስ አይፌ ዞኡዋ እሜስ) የወላይታ ተረት


ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ደቃቃ ጥንቸል፤ እህል ውሃ ፍለጋ በጫካ ውስጥ ስትዘዋወር፤ አንድ ዝንጀሮ ታገኛታለች፡፡ ጥንቸሏ ግዙፍ ስላልሆነች በየቅጠላ ቅጠሉ ውስጥ እየተሹለከለከች መሄድ እንደምትችል ዝንጀሮ ያውቃል፡፡ ሆኖም አንድ ምክር ሊመክራት ፈልጓል፡፡
“እመት ጥንቸል! የረዥም ጊዜ ወዳጅነታችንን መሰረት በማድረግ ምክር ልለግስሽ እፈልጋለሁ” አላት፡፡
ጥንቸልም፤
“ምን ዓይነት ምክር?” ስትል ጠየቀችው
ዝንጀሮም፤
“ይህን ጫካ አትመኝው፡፡ ሰሞኑን አዳኞች መጥተው ለአውሬ ማጥመጃ የሚሆን ትላልቅ ጉድጓድ ሲቆፍሩ እኔ ዛፍ ላይ ሆኜ አይቻቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ጫካው እንደድሮው ሰላም መስሎሽ ወዲህ ወዲያ አትበይ”
ጥንቸልም፤
“አመሰግናለሁ፡፡ ወጥመዱን የሰሩት ለእኔ አይመስለኝም፡፡ እንደ አንበሳ፣ እንደ ነብር፣ እንደ ዝሆን ላሉት እንጂ እንደኔ ቀጫጫ ለሆነ ፍጡር አይደለም፡፡ ባጋጣሚ ጉድጓድ ውስጥ ብወድቅም መውጫ ብልሃት አላጣም!” ትለዋለች፡፡
ዝንጀሮም፤
“እንግዲህ የወንድምነቴን መክሬሻለሁ፡፡ ብታውቂ እወቂበት” አላትና ሄደ፡፡
ጥንቸል እየተዘዋወረች ቅጠል መበጠሷን ትቀጥላለች፡፡ ጥቂት እንደሄደች ዝንጀሮ እንደፈራው አንድ በቅጠል የተሸፈነ ትልቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳታስበው ትወድቃለች፡፡ ጉድጓዱ በጣም ጥልቀት ያለው በመሆኑ በጭራሽ በቀላሉ ልትወጣ የምትችልበት አይደለም፡፡ ስለዚህ አላፊ-አግዳሚውን እንዲያወጣት ለመለመን ተገደደች፡፡
“እባካችሁ አውጡኝ፡፡ እባካችሁ እርዱኝ!” እያለች መጮህ ጀመረች፡፡ ተኩላ ድምጿን ይሰማና ወደ ጉድጓዱ አፍ ይሄዳል፡፡ አጎንብሶም ወደ ጥንቸሏ ያይ ጀመር፡፡
ጥንቸልም፤
“አያ ተኩላ! እባክህ ዘወር በል፡፡ ይሄ ጉድጓድ ለሁለታችን አይበቃንም፡፡ አንተ ያለህበት ቦታ እንደበረሀ የሚያቃጥል አየር ነው ያለው፡፡ እዚህ ግን በጣም ነፋሻና ቅዝቅዝ ያለ አየር ነው ያለው፡፡ ለእኔ በጣም ተስማምቶኛል፡፡ ሆኖም ወደዚህ ለመውረድ ብትችልም እንኳን ቦታው አይበቃንም” አለችው፡፡
ተኩላ፤ የጥንቸሏ ንግግር በጣም አጓጓውና፤ “ልውረድስ ብል በምኔ እወርዳለሁ?” ሲል ጠየቃት፡፡
ጥንቸልም፤
“እዚያ ጉድጓድ አፍ አጠገብ አንድ በገመድ የታሰረ ባሊ አለልህ፡፡ ባሊው ውስጥ ገብተህ በገመዱ ተንሸራተህ መውረድ ትችላለች” አለችው፡፡
ዕውነትም አንድ ባሊ አጠገቡ እንዳለ አየ፡፡ ባሊው ወደ ታች ሲወርድ ጉድጓዱ ውስጥ ያለው ገመድ ጫፍ ወደ ላይ የሚወጣ ነው፡፡ እንደ ፑሊ የሚሰራ ገመድ ነው፡፡ ጉድጓድ ውስጥ ያለውን ጫፍ ጥንቸሏ ይዛለች፡፡
አያ ተኩላ ባሊው ውስጥ ገብቶ ቁልቁል ተምዘግዝጎ ሲወርድ ጥንቸል የገመዱን ጫፍ ይዛ ወደ ላይ ወጣች፡፡
እሱ እየወረደ፣ እሷ እየወጣች መንገድ ላይ ሲተላለፉ፤ ከት ብላ እየሳቀች፤
“አየህ አያ ተኩላ፤ ህይወት ማለት እንደዚህ ናት፡፡ አንዱ ሲወርድ አንዱ ይወጣል!” አለችው፡፡
ተኩላ መሬት ሲደርስ ጥንቸሏ ጉድጓዱ አፋፍ ወጣች!

*   *   *
አንዳንድ ሰዎች አንድ ችግር ውስጥ ሲገቡ ሌላውን እዚያ ውስጥ ነክረው እራሳቸውን ማዳን ይችሉበታል፡፡ ተታልለው እዚያ ችግር ውስጥ የሚገቡት ሞኞች የሚሳሳቱት በአልጠግብ ባይነታቸውና እጉድጓዱ ውስጥ እንኳ ያለው ነገር እንዳያመልጠኝ ብለው ሲስገበገቡ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በርካታ ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ገብተው ቀርተዋል፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁለቱም ለሀገርና ለህዝብ አይጠቅሙም፡፡ አደጋን ከሩቅ አይተው የሚያስጠነቅቁ እንደ ዝንጀሮው ያሉ አስተዋዮች ቢኖሩም፣ እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው ሰው አያገኙም፡፡ ባንዱ እግር ሌላው እየገባ፣ ህይወት ትቀጥላለች፡፡
ማይ ግሪንፊልድ የተባለ ፀሐፊ፤
“ታሪክ ራሱን ይደግማል፤ ይላል ታሪከኛ ሁሉ
እኔን ያሳሰበኝ ግና፣
ታሪክ በደገመ ቁጥር፣ ዋጋው ይብስ መቀጠሉ” ይላል፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ እየባሰ የሚመጣው እኛ ከታሪክ ለመማር ባለመቻላችን ነው፡፡ የቀደመው የሰራውን ስህተት የኋለኛው ይደግመዋል - ያውም በዚያኛው እየሳቀ፣ እየተሳለቀ! “በእገሌ ጊዜ የተበደላችሁ እጃችሁን አውጡ!” እያለ፡፡ ከንቲባዎች ተቀያይረዋል፡፡ አስተዳዳሪዎች ተቀያይረዋል፡፡ ሚኒስትሮች ተቀያይረዋል ወዘተ… ማንም ከማንም አይማርም፡፡ ሁሌ እኔ ከወደቀው የተሻልኩ ነኝ የሚለውን ለማረጋገጥ የቀደመውን እየረገሙ መቀጠል ነው!! በዚህ ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እመሰርታለሁ ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ከተነሳው ሹም መውሰድ ያለብንን ደግ ነገር ካላወቅን ከዜሮ እንደ መጀመር የከበደ ነው ጉዟችን፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ጀርመኖች ለንደንን በቦምብ በደበደቡ ጊዜ ሦስት ዓይነት ህዝቦች ተፈጥረው ነበር ይባላል፡፡ 1) የተገደሉ 2) ለጥቂት የተሳቱና 3) በርቀት የተሳቱ፡፡ የተገደሉት ሟቾች ናቸውና ስለአደጋው ወሬ አይነዙም፡፡ ለጥቂት የተሳቱት በሰቀቀንና ስቃዩን በማስታወስ የሚኖሩ ሆኑ፡፡ በሩቅ የተሳቱት ግን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹን ለመዷቸውና ልበ ሙሉ ሰዎች ሆኑ፤ ይለናል ፀሐፊው ማልኮልም ግላድዌል፡፡ ችግርን መልመድ ደፋርና ልበ - ሙሉ ያደርጋል ነው ነገሩ! ከዚህ ተነስቶ ለአገርና ህዝብ መቆርቆር መቻል መታደል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ደሞ ማየት፣ በትክክለኛው ቦታ መገኘትና የሚሰሩትን በቅጡ ማወቅ ግዴታ ነው፡፡ ችግርን ለምዶ መተኛት ግን ሌላ ችግር ነው! ሁሉ በጄ ሁሉ በደጄ እያሉ አግባብነት ያለው ተግባር የማይፈፅሙ አያሌ ናቸው፡፡ የተማሩትና የሰለጠኑበት ሌላ የሚሰሩት ሌላ፤ የሆኑም አያሌ ናቸው! ስለ ግንባታ እያወሩ የማይገነቡ ከአፈረሰ አንድ ናቸው፡፡
መንገድ ሰርቶ በቅጡ ሳንሄድበትና ሳናጣጥመው ከፈረሰ ወይ ሰሪው በቅጡ አላበጀውም፣ ወይ ሂያጆቹ መሄድ አይችሉም፣ አሊያም ሆነ ብለው የሚያጠፉ አሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በቅጡ ራስን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “የነቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ”ንም ልብ ማለት መልካም ነው፡፡ ሁሉን በውል በውሉ ካላስቀመጥንና ታማኝነትን ብቻ መለኪያ እናድርግ ካልን፣ የተወዛገበ አካሄድ ውስጥ እንሰነቀራለን፡፡ እመጫት እንደ በዛው ፅሁፍ ከዋናው ማረሚያው ይበረክታል፡፡ ከተቃወምንም ዕድሉን ባግባቡ እንጠቀም፡፡
እንዳያማህ ጥራውንም እንተው! በእጃችን ያለውን በወጉ መጠቀም ያስፈልጋል፤ በሁሉም ወገን፡፡ አለበለዚያ “ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ፣ ለማይገላምጥ ዶሮ፣ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል” የሚለው የወላይተኛ ተረት ይመጣል፡፡ “ቆሎ ለዘር፤ እንዶድ ለድግር አይሆንም” እንደሚባለው ማለት ነው፡፡    

Saturday, 01 March 2025 21:39

አድዋ፤ ኩራትም ቁጭትም!

ደሳለኝ የኔአካል - ጠበቃና የህግ አማካሪ

 


የአድዋ ድል መልከ ብዙ ነው። ሁሉም ራሱን እያስመሰለ ይስለዋል። ራሱን እያስመሰለ ቢስለው ችግር አይደለም። ምክንያቱም የሁላችንም መልክ አድዋ ላይ አለ። ችግር የሚሆነው አድዋ እኔን ብቻ ይመስላል ካልን ነው። ለምሳሌ በእግዚአብሔር አምሳል ተፈጥረናልና፣ ‘እግዚአብሔርን እመስላለሁ’ ብንል ስህተት አይሆንም። እግዚአብሔርን የምመስለው እኔ ብቻ ነኝ ካልን ግን ስህተትም ኃጢአትም ይሆናል።
እንግዲህ ወሩ የካቲት ነውና፣ ሁላችንንም የሚመስለውን አድዋን እናስታውሳለን። ዛሬ አድዋን የምናስታውሰው ብቻውን አይደለም። የተለመደውንና ስለ አድዋ በጠቀስን ቁጥር ከአፋችን የማንነጥለውን የአዘቦት አረፍተ-ነገራችንን አብረን እናስበዋለን። ይህ አረፍተ ነገራችን “እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” ብሎ የሚጀምር፣ ከድሉ እኩል ዝነኛ የሆነ አረፍተ ነገር ነው። ይህ አረፍተ ነገር ተራ አረፍተ ነገር አይደለም። ጀግንነታችንን ከስንፍናችን አጣምሮ የተሸከመ የማንነታችን መልክ ነው። ራሳችንን ያሞገስንበትና የሰደብንበት የአፋችን ቃል ነው። ለኢትዮጵያውያን (በተለይ ከአክሱም ስልጣኔ ውድቀት በኋላ ለበቀልነው ኢትዮጵያውያን) ፓስፖርትና መታወቂያችን ላይ ከጉርድ ፎቶግራፋችን ይልቅ ይህ አረፍተነገር ቢቀመጥ፣ እኛነታችንን የበለጠ ሊገልፅ ይችላል። ሁሉም መርህ (principle) በስተቀር (exception) አያጣውምና፣ ‘ከአክሱም ውድቀት በኋላ’ ብዬ በአንድ ሀረግ በጠቀለልኩት ሰፊ የዘመን ጥቁር ሰማይ ላይ ሽው እልም ያሉ ተወርዋሪ ኮከቦች መኖራቸው እርግጥ ነው። ይሁን እንጅ ትኩረታችን ከጥቂት ግለሰቦች ግላዊ ጥረትና ስኬት ይልቅ በአጠቃላዩ ማኅበረሰብና ሀገራችን ላይ ስለሆነ መደምደሚያዬን ችኩል ድምዳሜ (hasty generalization) አያደርገውም። መሠረታዊው ጥያቄ፤‘አድዋ እንዴት የኩራትና የቁጭት ምንጭ ሆነ?’ ከፍ ሲል የተጠቀሰው አረፍተ ነገርስ እንዴት የማንነታችን መልክ ሆኖ መጣ? የሚለው ነው።
፩) አድዋ እንደ ኩራት…
የአድዋን ድል ኩራትነት መፃፍ አስቸጋሪ ነገር ነው። እንኳን እኛ የነጭ ዘር ያውቀዋል። አያቶቻችን እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን ሰራዊት አፍንጫውን ብለው መመለሳቸው እንደ ፀሐይ፡ እንደ ጨረቃ የዓለምን አንድ ገጽ ይዞ ፍንትው ያለ አጠቃላይ እውነት (geberal truth) ነው። በአንድ ግጥሜ ላይ ያልኩትን ደግሜ ብቻ ርዕሱን እዘለዋለሁ።
አድዋ ማለትኮ…
በእናት ሀገር አንገት - የአጥንት አበባ - የደም ጉንጉን ማጥለቅ፣
መስዋዕት እየሆኑ - የነፃነት ጠበል - ላገር መሬት ማፍለቅ።
አድዋ ማለትኮ…
የተግባር መልስ ነው - ለኡምቤርቶ ንቀት - ላንቶኔሊ ስድብ፣
በሞት መሻገር ነው…
የመቀሌን ምሽግ - ያምባላጌን ጉድብ፤
በባርነት ገደል በግዞት ሸለቆ…
ክቡር ደም ነስንሶ - አጥንት ጎዝጉዞ
ባህርን ሰንጥቆ - ሞቶ ማሻገር ነው - ያገርን እጅ ይዞ።
(ተይው ፖለቲን ዝም ብለሽ
ሳሚኝ - 2014 ዓ.ም)

፪) አድዋ እንደ ቁጭት…
“እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” የሚለው ወዝ ጠገብ (እና ጆሮ ጠገብ) አረፍተ-ነገር በአንድ በኩል ስልጡን የኢጣልያ ሰራዊት፣ በሌላ በኩል ኋላቀር የኢትዮጵያ ሰራዊት ግንባር ለግንባር የተፋጠጡበት አረፍተ ነገር ነው።
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያችን የሦስት ሺህ ዓመት (አምስት ሺህ የሚያደርጉትም አሉ) የመንግሥትነት ታሪክ ያላት፣ ዓለም ከመንቃቱ በፊት በሰማይ በራሪ በምድር ተሽከርካሪ የፈለሰፈች (በራሪ ሰዎችም የነበሯት)፣ ባህር ተሻግራ፣ ዱር መንጥራ በዚህ እስከ ምስርና የመን፣ በዚያ እስከ ማዳጋስካር የገዛች፣ ሱዳንን አስገብራ ወርቅ የምታፍስ (ሰርዶ አልግጥም አለ የፋሲል ፈረሱ፣
ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለእሱ፤ የሚለው ሕዝባዊ ግጥም ለዚህ ምስክር ነው)፣ የአትላንቲክ ውቅያኖስ ደቡባዊ ግማሽ ኢትዮጵያ ውቅያኖስ ተብሎ ለስሟ ክብር የተሰየመላት (ለሙሽርነቷ ስም ሲወጣላት ዳቦ ሳይሆን ውቅያኖስ የተቆረሰላት ሀገር ናት ልንል እንችላለን)፣ ከሮማ ግዛተ-አጼ (Roman empire) ጋር የሚገዳደርና ትከሻ ለትከሻ የሚገፋፋ የአክሱም ስልጣኔ የሚባል ግዙፍ ስልጣኔ የነበራት፣ የመስቀል ጦረኞች (Crusaders) ቄስ ንጉሥ ዮሐንስ (Prester John) የሚባል ንጉሥ መጥቶ ያድነናል የዚያ ንጉሥ ሀገርም ኢትዮጵያ ነች ብለው ተስፋ ያደረጉባት፣ የተስፋቸው ምድር (ከተስፋቸውም ከኢትዮጵያ የተነሳ እንዲል ታላቁ መፅሐፍ) ነበረች። ከአክሱም ውድቀት በኋላ አንዱ በአንዱ ላይ እየተነባበረ እንደ ህልም ሩጫ እያንሸራተተ ሲደፍቃት በኖረው ተከታታይና ተቀጣጣይ ጦርነት ምክንያት ስትወድቅ ስትነሳ ኖረች። የጎንደሩ ማዕከላዊ መንግሥት እየፈዘዘ መምጣቱን ተከትሎም፣ በስሁል ሚካኤል እግር የገባው ዘመነ መሳፍንት ከትልቁ ራስ አሊ እስከ ትንሹ ራስ አሊ ድረስ ለሰባ አመታት ያህል ሀገሪቱን በመሳፍንቱ ኮቴ ስር ሲያስደከድካት ቆዬ። በኋላም የቋራው ካሳ ራዕዩን ስሎ ጦሩን ወልውሎ መጣ። መሳፍንቱ በጦርና በቁማር (Conspiracy) የተካፈሏትን ሀገር፣ ከየእጃቸው ነጥቆ አንድ ላይ ሰበሰባት። ይህ የሆነው እ.ኤ.አ በ1855 (1848 ዓ.ም) ነው።
ኢጣልያ በሌላ አንፃር ከስመ ገናናው የሮማ ግዛተ አጼ (Roman Empire) መፈራረስ በኋላ አንድነት ያልነበራት፣ የናፖሊዮኗ ፈረንሳይ ፍዳዋን የምታበላት በኋላም፣ ኦስትሪያ የተፅዕኖ መዳፏን ትከሻዋ ላይ የጫነችባት፣ ጳጳሳትና ፊውዳል መሳፍንት እንደ ጉሊት ሸቀጥ በመደብ በመደብ ከፍለው የሚሸጧቸው የሚለውጧቸው ግዛቶችና የከተማ መንግስታት መደብር ነበረች። እ.ኤ.አ ከ1830ዎቹ ጀምሮ ያቆጠቆጠውና በዋናነትም በአብዮተኛው ጉሴፔ ጋሪባልዲና በቀይ ለባሽ ጦሩ የተመራው የውህደት እንቅስቃሴ ተጀምሮ በፔድሞንቱ ንጉሥ ዳግማዊ ቪክቶር ኢማኑኤል ንግሥና ተጠናቀቀ። ጣልያኖች Risorgimento (እንደገና መነሳት) ብለው የሚጠሩት የውህደት ንቅናቄ እ.ኤ.አ በ1861 ተጠናቋል የሚሉ ቢኖሩም፣ የጳጳሱ መዲና የነበረችውን ሮምን የመላው ኢጣልያ ዋና ከተማው አድርጎ የተጠናቀቀው ግን እ.ኤ.አ በ1871 ነው። በብዙ ፍላጎቶች መፋተር ወዲያና ወዲህ ተወጥሮ የነበረው የውህደት መንገድ፣ የኢጣልያ ውህደት እ.ኤ.አ በ1871 ተጠናቀቀ።
1861ን እንኳን ብንይዝ ኢትዮጵያ ሀገራችን ከመሳፍንቱ የፍዳ ዘመን ከተላቀቀችና ካሳም ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ ከነገሠ (እ.ኤ.አ 1855) ከስድስት ዓመት በኋላ መሆኑ ነው። የሁለቱንም ሀገራት ውህደት መጠናቀቂያ እንያዝ ካልንም እንጦጦ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1871 ዓ.ም ዋና ከተማ የነበረች በመሆኑ አነሰም በዛም ተቀራራቢ ጊዜ ላይ ውህደት የጨረሱ ሀገራት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳል።
እንግዲህ ጣልያኖች ከእኛ በፊት ወድቀው… ከእኛ በኋላ ተነስተው… እ.ኤ.አ በ1896 (ውህደታቸውን ጨርሰው ሀገር ከሆኑ ከ25 ዓመት በኋላ) ባህር ተሻግሮ ሀገራትን ማብረክረክ የቻለ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ዘመናዊ ሰራዊት እና ክንደ ብርቱ ሀገር ገነቡ። በዚያ ፍጥነት አፍሪካ ተሻግረው እግራቸውን በቀይ ባህር ውሃ ታጠቡ። እኛ ከእነሱ በኋላ ወድቀን… ከእነሱ ቀድመን ተነስተን… እ.ኤ.አ በ1896 (1888 ዓ.ም) (ዘመነ መሳፍንትን ካጠፋን ከ41 ዓመት በኋላ) አድዋ ላይ ምን ይዘን ተሰለፍን? ብለን ስንጠይቅ ጋሻ፣ ጦር፣ በጣም ጥቂት ‘ቁመህ ጠብቀኝ’ ጠበንጃዎች (እነ ወጨፎ) እና በባዶ እጅም ቢሆን የሚተናነቁ ጀግና ተዋጊዎችን። በጀግኖቻችን ሞት አይፈሬነት ምክንያት አሸነፍን። በ41 ዓመቱ ጉዞ ምን ገነባን ስንል ግን መልሱ ነፍስ የሚያሸማቅቅ ሆኖ ብቅ ይላል። እነሱ እንዴት ሰለጠኑ? እንዴት ኋላ ቀረን? ትንሳኤያችን ከትንሳኤያቸው ስድስት ዓመት ቀድሞ እያለ እንዴት ቆመን አሳለፍናቸው? ከእኛ በኋላ ተወልደው ምን ቢንቁን አጥራችንን ነቀነቁ? አያያዛችን እንዴት ሆኖ ቢታያቸው ስንቃችንን ለመቀማት ተራኮቱ? ከአድዋ በኋላም ሳንነቃ ቀረን። የዳግማዊ ምኒልክን ሽፍን ጫማ መልበስ ስናሽሟጥጥ፣ ከውጭ ያስመጣነውን መኪና እንኳ መልመድ አቅቶን የሰይጣን ፈረስ እያልን በየግብር አዳራሹ አፍ ገጥመን ስናንሾካሹክ፣ የድንጋይ ወፎጯችንን መጅ ወርውረን ወደ ዘመን አመጣሹ ወፍጮ ለመራመድ እንደ እግረ-ተከል ህፃን ስንከነበል ጣልያን ግን ከአርባ ዓመት በኋላ አውሮፕላንና መድፍ ሰርታ ድጋሜ መጣችብን። እነሱ ስልጡን እኛ ኋላቀር የሚለውን ሀረግ ክፉኛ ከመላመዳችን የተነሳ ስንናገረውም የምንኮራበት ይመስለኛል።
ዶጋሊ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
አድዋ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ማይጨው ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ካራማራ ላይ ሶማሌ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
መቼ ይሆን ግልባጩን ታሪክ ሰርተን ‘እኛ ስልጡን እነሱ ኋላቀር’ የሚል ትርክት ገልብጠን የምንፅፈው? መቼ ይሆን ሀገራችን እኩል ለእኩል፣ ስልጣኔ ለስልጣኔ፣ ቴክኖሎጅ ለቴክኖሎጂ የምትገዳደረው? መቼ ይሆን ከጦር ሜዳ መልስም ሀገር እንዳለችን የምንረዳው? መቼ?

Saturday, 01 March 2025 21:39

አድዋ፤ ኩራትም ቁጭትም!

ደሳለኝ የኔአካል - ጠበቃና የህግ አማካሪ

 


የአድዋ ድል መልከ ብዙ ነው። ሁሉም ራሱን እያስመሰለ ይስለዋል። ራሱን እያስመሰለ ቢስለው ችግር አይደለም። ምክንያቱም የሁላችንም መልክ አድዋ ላይ አለ። ችግር የሚሆነው አድዋ እኔን ብቻ ይመስላል ካልን ነው። ለምሳሌ በእግዚአብሔር አምሳል ተፈጥረናልና፣ ‘እግዚአብሔርን እመስላለሁ’ ብንል ስህተት አይሆንም። እግዚአብሔርን የምመስለው እኔ ብቻ ነኝ ካልን ግን ስህተትም ኃጢአትም ይሆናል።
እንግዲህ ወሩ የካቲት ነውና፣ ሁላችንንም የሚመስለውን አድዋን እናስታውሳለን። ዛሬ አድዋን የምናስታውሰው ብቻውን አይደለም። የተለመደውንና ስለ አድዋ በጠቀስን ቁጥር ከአፋችን የማንነጥለውን የአዘቦት አረፍተ-ነገራችንን አብረን እናስበዋለን። ይህ አረፍተ ነገራችን “እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” ብሎ የሚጀምር፣ ከድሉ እኩል ዝነኛ የሆነ አረፍተ ነገር ነው። ይህ አረፍተ ነገር ተራ አረፍተ ነገር አይደለም። ጀግንነታችንን ከስንፍናችን አጣምሮ የተሸከመ የማንነታችን መልክ ነው። ራሳችንን ያሞገስንበትና የሰደብንበት የአፋችን ቃል ነው። ለኢትዮጵያውያን (በተለይ ከአክሱም ስልጣኔ ውድቀት በኋላ ለበቀልነው ኢትዮጵያውያን) ፓስፖርትና መታወቂያችን ላይ ከጉርድ ፎቶግራፋችን ይልቅ ይህ አረፍተነገር ቢቀመጥ፣ እኛነታችንን የበለጠ ሊገልፅ ይችላል። ሁሉም መርህ (principle) በስተቀር (exception) አያጣውምና፣ ‘ከአክሱም ውድቀት በኋላ’ ብዬ በአንድ ሀረግ በጠቀለልኩት ሰፊ የዘመን ጥቁር ሰማይ ላይ ሽው እልም ያሉ ተወርዋሪ ኮከቦች መኖራቸው እርግጥ ነው። ይሁን እንጅ ትኩረታችን ከጥቂት ግለሰቦች ግላዊ ጥረትና ስኬት ይልቅ በአጠቃላዩ ማኅበረሰብና ሀገራችን ላይ ስለሆነ መደምደሚያዬን ችኩል ድምዳሜ (hasty generalization) አያደርገውም። መሠረታዊው ጥያቄ፤‘አድዋ እንዴት የኩራትና የቁጭት ምንጭ ሆነ?’ ከፍ ሲል የተጠቀሰው አረፍተ ነገርስ እንዴት የማንነታችን መልክ ሆኖ መጣ? የሚለው ነው።
፩) አድዋ እንደ ኩራት…
የአድዋን ድል ኩራትነት መፃፍ አስቸጋሪ ነገር ነው። እንኳን እኛ የነጭ ዘር ያውቀዋል። አያቶቻችን እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን ሰራዊት አፍንጫውን ብለው መመለሳቸው እንደ ፀሐይ፡ እንደ ጨረቃ የዓለምን አንድ ገጽ ይዞ ፍንትው ያለ አጠቃላይ እውነት (geberal truth) ነው። በአንድ ግጥሜ ላይ ያልኩትን ደግሜ ብቻ ርዕሱን እዘለዋለሁ።
አድዋ ማለትኮ…
በእናት ሀገር አንገት - የአጥንት አበባ - የደም ጉንጉን ማጥለቅ፣
መስዋዕት እየሆኑ - የነፃነት ጠበል - ላገር መሬት ማፍለቅ።
አድዋ ማለትኮ…
የተግባር መልስ ነው - ለኡምቤርቶ ንቀት - ላንቶኔሊ ስድብ፣
በሞት መሻገር ነው…
የመቀሌን ምሽግ - ያምባላጌን ጉድብ፤
በባርነት ገደል በግዞት ሸለቆ…
ክቡር ደም ነስንሶ - አጥንት ጎዝጉዞ
ባህርን ሰንጥቆ - ሞቶ ማሻገር ነው - ያገርን እጅ ይዞ።
(ተይው ፖለቲን ዝም ብለሽ
ሳሚኝ - 2014 ዓ.ም)

፪) አድዋ እንደ ቁጭት…
“እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” የሚለው ወዝ ጠገብ (እና ጆሮ ጠገብ) አረፍተ-ነገር በአንድ በኩል ስልጡን የኢጣልያ ሰራዊት፣ በሌላ በኩል ኋላቀር የኢትዮጵያ ሰራዊት ግንባር ለግንባር የተፋጠጡበት አረፍተ ነገር ነው።
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያችን የሦስት ሺህ ዓመት (አምስት ሺህ የሚያደርጉትም አሉ) የመንግሥትነት ታሪክ ያላት፣ ዓለም ከመንቃቱ በፊት በሰማይ በራሪ በምድር ተሽከርካሪ የፈለሰፈች (በራሪ ሰዎችም የነበሯት)፣ ባህር ተሻግራ፣ ዱር መንጥራ በዚህ እስከ ምስርና የመን፣ በዚያ እስከ ማዳጋስካር የገዛች፣ ሱዳንን አስገብራ ወርቅ የምታፍስ (ሰርዶ አልግጥም አለ የፋሲል ፈረሱ፣
ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለእሱ፤ የሚለው ሕዝባዊ ግጥም ለዚህ ምስክር ነው)፣ የአትላንቲክ ውቅያኖስ ደቡባዊ ግማሽ ኢትዮጵያ ውቅያኖስ ተብሎ ለስሟ ክብር የተሰየመላት (ለሙሽርነቷ ስም ሲወጣላት ዳቦ ሳይሆን ውቅያኖስ የተቆረሰላት ሀገር ናት ልንል እንችላለን)፣ ከሮማ ግዛተ-አጼ (Roman empire) ጋር የሚገዳደርና ትከሻ ለትከሻ የሚገፋፋ የአክሱም ስልጣኔ የሚባል ግዙፍ ስልጣኔ የነበራት፣ የመስቀል ጦረኞች (Crusaders) ቄስ ንጉሥ ዮሐንስ (Prester John) የሚባል ንጉሥ መጥቶ ያድነናል የዚያ ንጉሥ ሀገርም ኢትዮጵያ ነች ብለው ተስፋ ያደረጉባት፣ የተስፋቸው ምድር (ከተስፋቸውም ከኢትዮጵያ የተነሳ እንዲል ታላቁ መፅሐፍ) ነበረች። ከአክሱም ውድቀት በኋላ አንዱ በአንዱ ላይ እየተነባበረ እንደ ህልም ሩጫ እያንሸራተተ ሲደፍቃት በኖረው ተከታታይና ተቀጣጣይ ጦርነት ምክንያት ስትወድቅ ስትነሳ ኖረች። የጎንደሩ ማዕከላዊ መንግሥት እየፈዘዘ መምጣቱን ተከትሎም፣ በስሁል ሚካኤል እግር የገባው ዘመነ መሳፍንት ከትልቁ ራስ አሊ እስከ ትንሹ ራስ አሊ ድረስ ለሰባ አመታት ያህል ሀገሪቱን በመሳፍንቱ ኮቴ ስር ሲያስደከድካት ቆዬ። በኋላም የቋራው ካሳ ራዕዩን ስሎ ጦሩን ወልውሎ መጣ። መሳፍንቱ በጦርና በቁማር (Conspiracy) የተካፈሏትን ሀገር፣ ከየእጃቸው ነጥቆ አንድ ላይ ሰበሰባት። ይህ የሆነው እ.ኤ.አ በ1855 (1848 ዓ.ም) ነው።
ኢጣልያ በሌላ አንፃር ከስመ ገናናው የሮማ ግዛተ አጼ (Roman Empire) መፈራረስ በኋላ አንድነት ያልነበራት፣ የናፖሊዮኗ ፈረንሳይ ፍዳዋን የምታበላት በኋላም፣ ኦስትሪያ የተፅዕኖ መዳፏን ትከሻዋ ላይ የጫነችባት፣ ጳጳሳትና ፊውዳል መሳፍንት እንደ ጉሊት ሸቀጥ በመደብ በመደብ ከፍለው የሚሸጧቸው የሚለውጧቸው ግዛቶችና የከተማ መንግስታት መደብር ነበረች። እ.ኤ.አ ከ1830ዎቹ ጀምሮ ያቆጠቆጠውና በዋናነትም በአብዮተኛው ጉሴፔ ጋሪባልዲና በቀይ ለባሽ ጦሩ የተመራው የውህደት እንቅስቃሴ ተጀምሮ በፔድሞንቱ ንጉሥ ዳግማዊ ቪክቶር ኢማኑኤል ንግሥና ተጠናቀቀ። ጣልያኖች Risorgimento (እንደገና መነሳት) ብለው የሚጠሩት የውህደት ንቅናቄ እ.ኤ.አ በ1861 ተጠናቋል የሚሉ ቢኖሩም፣ የጳጳሱ መዲና የነበረችውን ሮምን የመላው ኢጣልያ ዋና ከተማው አድርጎ የተጠናቀቀው ግን እ.ኤ.አ በ1871 ነው። በብዙ ፍላጎቶች መፋተር ወዲያና ወዲህ ተወጥሮ የነበረው የውህደት መንገድ፣ የኢጣልያ ውህደት እ.ኤ.አ በ1871 ተጠናቀቀ።
1861ን እንኳን ብንይዝ ኢትዮጵያ ሀገራችን ከመሳፍንቱ የፍዳ ዘመን ከተላቀቀችና ካሳም ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ ከነገሠ (እ.ኤ.አ 1855) ከስድስት ዓመት በኋላ መሆኑ ነው። የሁለቱንም ሀገራት ውህደት መጠናቀቂያ እንያዝ ካልንም እንጦጦ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1871 ዓ.ም ዋና ከተማ የነበረች በመሆኑ አነሰም በዛም ተቀራራቢ ጊዜ ላይ ውህደት የጨረሱ ሀገራት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳል።
እንግዲህ ጣልያኖች ከእኛ በፊት ወድቀው… ከእኛ በኋላ ተነስተው… እ.ኤ.አ በ1896 (ውህደታቸውን ጨርሰው ሀገር ከሆኑ ከ25 ዓመት በኋላ) ባህር ተሻግሮ ሀገራትን ማብረክረክ የቻለ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ዘመናዊ ሰራዊት እና ክንደ ብርቱ ሀገር ገነቡ። በዚያ ፍጥነት አፍሪካ ተሻግረው እግራቸውን በቀይ ባህር ውሃ ታጠቡ። እኛ ከእነሱ በኋላ ወድቀን… ከእነሱ ቀድመን ተነስተን… እ.ኤ.አ በ1896 (1888 ዓ.ም) (ዘመነ መሳፍንትን ካጠፋን ከ41 ዓመት በኋላ) አድዋ ላይ ምን ይዘን ተሰለፍን? ብለን ስንጠይቅ ጋሻ፣ ጦር፣ በጣም ጥቂት ‘ቁመህ ጠብቀኝ’ ጠበንጃዎች (እነ ወጨፎ) እና በባዶ እጅም ቢሆን የሚተናነቁ ጀግና ተዋጊዎችን። በጀግኖቻችን ሞት አይፈሬነት ምክንያት አሸነፍን። በ41 ዓመቱ ጉዞ ምን ገነባን ስንል ግን መልሱ ነፍስ የሚያሸማቅቅ ሆኖ ብቅ ይላል። እነሱ እንዴት ሰለጠኑ? እንዴት ኋላ ቀረን? ትንሳኤያችን ከትንሳኤያቸው ስድስት ዓመት ቀድሞ እያለ እንዴት ቆመን አሳለፍናቸው? ከእኛ በኋላ ተወልደው ምን ቢንቁን አጥራችንን ነቀነቁ? አያያዛችን እንዴት ሆኖ ቢታያቸው ስንቃችንን ለመቀማት ተራኮቱ? ከአድዋ በኋላም ሳንነቃ ቀረን። የዳግማዊ ምኒልክን ሽፍን ጫማ መልበስ ስናሽሟጥጥ፣ ከውጭ ያስመጣነውን መኪና እንኳ መልመድ አቅቶን የሰይጣን ፈረስ እያልን በየግብር አዳራሹ አፍ ገጥመን ስናንሾካሹክ፣ የድንጋይ ወፎጯችንን መጅ ወርውረን ወደ ዘመን አመጣሹ ወፍጮ ለመራመድ እንደ እግረ-ተከል ህፃን ስንከነበል ጣልያን ግን ከአርባ ዓመት በኋላ አውሮፕላንና መድፍ ሰርታ ድጋሜ መጣችብን። እነሱ ስልጡን እኛ ኋላቀር የሚለውን ሀረግ ክፉኛ ከመላመዳችን የተነሳ ስንናገረውም የምንኮራበት ይመስለኛል።
ዶጋሊ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
አድዋ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ማይጨው ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ካራማራ ላይ ሶማሌ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
መቼ ይሆን ግልባጩን ታሪክ ሰርተን ‘እኛ ስልጡን እነሱ ኋላቀር’ የሚል ትርክት ገልብጠን የምንፅፈው? መቼ ይሆን ሀገራችን እኩል ለእኩል፣ ስልጣኔ ለስልጣኔ፣ ቴክኖሎጅ ለቴክኖሎጂ የምትገዳደረው? መቼ ይሆን ከጦር ሜዳ መልስም ሀገር እንዳለችን የምንረዳው? መቼ?

የኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥታት ወደ ጦርነት ከሚያስገቡ ጠብ አጫሪ ድርጊቶች መቆጠብ እንዳለባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ ለሁለቱም አገራት የተሻለ ቀረቤታ ያላቸው ወገኖች የእርቅ ጥረት ማድረግ አለባቸው ተብሏል፡፡
ከሰሞኑ በኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥታት መካከል የተፈጠረው የቃላት ጦርነት የብዙዎችን ትኩረት የሳበ ሲሆን፤ አገራቱ ወደ ጦርነት እንዳይንደረደሩ በርካቶች ስጋታቸውን ገልጸዋል። የአፍሪካ ቀንድ ጉዳዮች ተመራማሪና የዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ምሁር አቶ ኢያሱ ሃይለሚካኤል ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ለረዥም ጊዜ የቆየ ፍትጊያ እንደነበረና አሁን የሚስተዋለው የቃላት ግጭት ከፖለቲካዊና መልክዓምድራዊ ጉዳዮች ጋር እንደሚገናኝ ይገልጻሉ፡፡
“የሁለቱ አገራት ፍትጊያ በበርካታ ታሪካዊ አጋጣሚዎች ውስጥና በተለዋዋጭ ሁኔታዎች መካከል የዘለቀ ነው” የሚሉት አቶ ኢያሱ፤ በተለይም ኤርትራ ነጻነቷን ካወጀችበት ጊዜ በኋላ የተፈጠሩ አለመግባባቶች በሰፊው መስተዋላቸውን ያስታውሳሉ፡፡ አክለውም፤ በቀድሞው የኢሕአዴግ መንግስትና በኤርትራ መንግስት መካከል የኢኮኖሚ ፖሊሲ አቅጣጫ ልዩነቶች እንደነበሩ ጠቁመዋል፡፡
ለአብነት ያህል፣ ግንቦት 4 ቀን 1990 ዓ.ም. የተቀሰቀሰው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ከድንበር ይልቅ የኢኮኖሚ ጉዳይ መነሻ ምክንያት እንደነበር እኚሁ ምሁር አስረድተዋል። ጦርነቱ በአልጀርስ ስምምነት ከተቋጨ በኋላ የዘለቀው ጦርነትም ሆነ ሰላም የሌለበት ሁኔታ፣ በመጋቢት ወር 2010 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ የሁለቱ አገራት ግንኙነት እንደታደሰ ጠቅሰዋል።
በኢጣልያ ለረዥም ዓመታት በኤርትራ የተተከለው የቅኝ ግዛትና ዓለም አቀፉ የፖለቲካ ሁኔታ ያስከተለው ተጽዕኖ ኢትዮጵያና ኤርትራን ሲያጋጭ መቆየቱን ያወሱት አቶ ኢያሱ፤ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ተቀስቅሶ ለሁለት ዓመታት ሲካሄድ የከረመው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት በፕሪቶሪያ ዘላቂ የግጭት ማቆም ስምምነት ሲቋጭ፣ ከኢትዮጵያ መንግስት አዳዲስ ጥያቄዎች እንደቀረቡ አመልክተዋል። ከእነዚህም ጥያቄዎች ውስጥ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄ አንዱ እንደሆነ በማንሳት፣ ይህንን ጥያቄ ለማሳካት የኢትዮጵያ መንግስት አጥቂ (offensive) የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ መከተሉን አስረድተዋል።
አቶ ኢያሱ “የባሕር በር ጥያቄ ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጋር እያደገ የሚመጣ ጥያቄ ነው። ይኸው ጥያቄ ግጭትና ጦርነትን ሊፈጥር ይችላል። በእነዚሁ ሁኔታዎች የሚፈጠረው ጉዳት ከፍተኛ ይሆናል” በማለት ማብራሪያቸውን ቀጥለው፣ የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ላይ ውጥረትን እንደፈጠረ ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የሚስተዋሉ በሁለቱ አገራት የሚሰነዘሩ የቃላት ምልልሶች፣ በአገራቱ መካከል የተፈጠረው የዲፕሎማሲ ግንኙነት መቀዛቀዝ ምልክት መሆናቸውን አያይዘው ገልጸዋል።
“የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት መርገብ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ያለውን ግንኙነት እያሻከረው መጥቷል” ያሉት ምሁሩ፤ “ሁለቱም አገራት ወደ ጦርነት የሚሄዱበት ጊዜ አጭር ባይሆንም፣ የተወሰኑ የእርስ በርስ ትንኮሳዎች ሊኖር እንደሚችሉ ግምታቸውን ሰጥተዋል።
“እንደ አገር ከአሁኑ መፍትሔ መፈለግ ያስፈልጋል። የቀይ ባሕር ጉዳይ ቀላል አይደለም። ምክንያቱም ዓለም አቀፍ ፍላጎቶች ያሉበት አካባቢ ነው” ያሉት አቶ ኢያሱ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ የውጭ ሃይሎች ተጽዕኖ ሊታከልበት እንደሚችል ጠቅሰዋል። “የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት ወደ ጡዘት ደረጃ ደርሷል። ከዚህም ባሻገር፣ የውክልና ጦርነት ሊኖር ይችላል። ነገር ግን ኤርትራ ይህንን ጦርነት ለማድረግ የኢኮኖሚ አቅም ‘አላት ወይ?’ የሚለው ጉዳይ አጠያያቂ ነው” ብለዋል።
ከዚህ የጦርነት ስጋት ለመውጣት “መፍትሔው ምንድን ነው?” የሚል ጥያቄ ከአዲስ አድማስ የቀረበላቸው አቶ ኢያሱ በሰጡት ምላሽ፣ ለኢትዮጵያም ሆነ ለኤርትራ ቀረቤታ ያላቸው መንግስታት፣ ተቋማትና ቡድኖች የእርቅ እንቅስቃሴ የሚጀምሩበት መንገድ ቢፈጠር፣ መልካም መሆኑን ጠቁመው፤ በምሳሌነት ሩሲያ፣ ቻይና እና እንደ ኢጣልያ ያሉ የአውሮጳ አገራት፣ ብሎም የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶችና ሳዑዲ አረቢያ ይህንን የእርቅ እንቅስቃሴ “መጀመር ይኖርባቸዋል” ብለዋል፡፡
በተጨማሪም፣ በሁለቱም አገራት በኩል ከጠብ አጫሪ ድርጊቶች መቆጠብ እንደሚያስፈልግ ያሳሰቡት አቶ ኢያሱ፤ “ከብሔራዊ ጥቅም አንጻር በኢትዮጵያ በኩል ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል” ሲሉ አስረድተዋል።
ከሁሉም በላይ የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በጥንቃቄ መያዝ ያለበት መሆኑን አጽንዖት ሰጥተዋል።

Page 9 of 765