Administrator

Administrator

  ከታክስ በፊት ከ428 ሚሊዮን ብር በላይ አተረፈ
       ሕብረት ባንክ ያለፈው ዓመት 2008 (ጁን 30 2016) የተጠናቀቀው በጀት ዓመት በአገሪቱ ላሉ ባንኮች ፈታኝ ሆኖ ቢያልፍም፣ ባንኩ ባደረገው ያላሰለሰ ጥረት አጠቃላይ ተቀማጭ ገንዘብ 13.63 ቢሊዮን ብር በማድረስ ከግል ባንኮች 4ኛ ደረጃ ሊይዝ መቻሉን አስታውቋል፡፡
ባንኩ የባለ አክሲዮኖች 18ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ከትናንት በስቲያ በሂልተን ሆቴል ያደረገ ሲሆን የባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ዛፉ እየሱስወርቅ ዛፉ ባቀረቡት ዓመታዊ ሪፖርት፣ የባንኩ ጠቅላላ ገቢ ከቀደመው ዓመት  ጋር ሲነፃፀር 25 በመቶ ዕድገት ማሳየቱና፣ ከግብር በፊት የተኘው ትርፍም አምና በተመሳሳይ ወቅት ከተገኘው 358.2 ሚሊዮን ብር ጋር ሲተያይ ወደ 428.5 ሚሊዮን ብር ከፍ ማለቱን ገልጸዋል፡፡
የባንኩ አጠቃላይ ተቀማጭ ገንዘብ ከቀደመው ዓመት (2007) ከነበረው 11.7 ቢሊዮን ብር 16.2 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 13.63 ቢሊዮን ብር መድረሱን የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ በብድር የተሰጠው ገንዘብ ከቀደመው  ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ1.7 ቢሊዮን ብር ወይም የ24.4 በመቶ ዕድገት በማሳየት 8.53 ቢሊዮን ብር በመድረሱ የተገኘው ውጤት አመርቂ ነው ብለዋል፡፡
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የአገሪቷ ወጪ ንግድ በመቀነሱ ከዓለም አቀፍ ባንክ አገልግሎት ዘርፍ የተገኘው ገቢ ከካቻምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲተያይ ቀንሷል፡፡ አምና ከዓለም አቀፍ ባንክ ዘርፍ የተገኘው ገቢ 2.98 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን የበጀት ዓመቱ 4.71 በመቶ ቀንሶ 2.84 ቢሊዮን ዶላር ወይም 400.9 ሚሊዮን ብር ሆኗል፡፡ ይህም የባንኩን አጠቃላይ ገቢ 23 በመቶ እንደሚሸፍን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አያደር ሲብስበት እንጂ ሲሻሻል የማይታየው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ለሥራቸው እንቅስቃሴ ስጋት መፍጠሩን የጠቀሱት አቶ ዛፉ፤ ስጋቱን ግምት ውስጥ በማስገባት ከዚህ በፊት ከነበረው በተጨማሪ ከሁለት ዓለም አቀፍ የካርድ አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች ማለትም ከቪዛ ኢንተርናሽናልና ከቻይና ዩኒየን ፔይ ጋር መሥራት ጀምረናል፡፡ የእነዚህ ድርጅቶች የባንኩ አጋር መሆን ለንግድ ተጓዦችና ቱሪስቶች የምናቀርበውን አገልግሎት ምቹና ቀልጣፋ ከማድረጉም በላይ የውጭ ምንዛሬ ከማሳደግ አኳያ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡
ባንኩ ጁን 30 2016 በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሙሉ በሙሉ በተከፈለ አክሲዮን ላይ 25 በመቶ የትርፍ ክፍያ አንዲደረግ የዲሬክተሮች ቦርድ የውሳኔ ሐሳብ አቅርቧል፡፡ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የባንኩ አጠቃላይ ሀብት 17.3 ቢሊዮን፤ አጠቃላይ የተከፈለ ካፒታል 1.25 ቢሊዮን ብር ሲሆን ባንኩ 2,998 ባለአክሲዮኖች እንዳሉት ታውቋል፡፡
ተደራሽነትን ከማስፋፋት አኳያ ባንኩ 161 ቅርንጫፎች ሲኖሩት፣ የሰው ኃይሉም 3,123 ደርሷል፡፡ በበጀት ዓመቱ 438 ሠራተኞ የተቀጠሩ ሲሆን ከባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲተያይ በ289 ሰራተኞች ብልጫ አለው፡፡ 149 ሠራተኞች ደግሞ ባንኩን ለቀዋል፡፡

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚካሄድ የአለም ፖስታ ህብረት ልዩ ጉባኤ እንድታዘጋጅ የተመረጠች ሲሆን ከ1 ሣምንት በላይ በሚዘልቀው ጉባኤ ከ3 ሺህ በላይ እንግዶች ከዓለም ዙሪያ እንደሚሳተፉ  ታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ግደይ ገ/ዮሐንስ ከትላንት በስቲያ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ በቅርቡ በቱርክ በተካሄደው 26ኛው የአለም የፖስታ ህብረት ኮንግረስ ላይ ኢትዮጵያ ከ2 አመት በኋላ የሚደረገውን የህብረቱን ልዩ ጉባኤ እንድታዘጋጅ በከፍተኛ ድምፅ መመረጧን አስታውቀዋል፡፡
ጉባኤው በኢትዮጵያ መካሄዱ የሃገሪቱን ገፅታ ለመገንባት፣ ሃገሪቱ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ፣ በአለማቀፍ ቱሪዝም አገሪቱን ለማስተዋወቅ ሃገሪቱ በፖስታ አገልግሎት ያላትን አቅም ለዓለም ለማሳየት ይጠቅማል ተብሏል፡፡
በጉባኤው ላይ ከ192 አባል ሃገራት የተውጣጡ የፖስታ አገልግሎት ሚኒስትሮች፣ ዋና ዳይሬክተሮች፣ የፖስታ ኤክስፐርቶች፣ ታዛቢዎች፣  አለማቀፍ ተቋማትና ህብረቶች ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በፖስታ አገልግሎት ኢትዮጵያ 4 አለማቀፍ እውቅናዎች ማግኘቷን የጠቆሙት ስራ አስኪያጁ በአገልግሎት ጥራት የ ‹‹ቢ›› ደረጃ ማግኘቱን አስታውቀዋል፡፡
በአሁን ወቅት የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት 16 ሺህ ያህል የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ለመክፈት እየተንቀሣቀሰ መሆኑን የጠቀሡት አቶ ግደይ፤ በ2 ዓመት ጊዜ ውስጥም ለግለሰብ ደንበኞች የቤት ለቤት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል እቅድ ተይዞ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
ድርጅቱ አምና ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱንና በዘንድሮ ዓመትም ወደ 1.2 ቢሊዮን ብር ገደማ ብር ለማግኘት ማቀዱን ስራ አስኪያጁ ጠቁመዋል፡፡ የፖስታ ድርጅት ዘመን አመጣሽ ቴክኖሎጂዎችን ለመወዳደር የተለያዩ ስልቶችን ነድፎ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቁመው፤ በየአመቱም ገቢውን በከፍተኛ መጠን እያሣደገ ለመጓዝ እንዳቀደ ተናግረዋል፤ አቶ ግደይ፡፡

“ስፒል ጫማ ካደረገች ዝንጀሮ” እስከ “ትራምፕ ፊርማ”

         በአፍ ይጠፉ፣ በለፈለፉ
በዌስት ቨርጂኒያ ግዛት ውስጥ የምትገኘው የክሌይ ከተማ ከንቲባ የሆኑት ቤቨርሊ ዋሊንግ እና ክሌይ ካውንቲ ኮርፖሬሽን የተባለ ድርጅት ዳይሬክተር የሆኑት ፓሜላ ቴለር፣ ከሰሞኑ የሚያጠፋቸውን አጉል ነገር በፌስቡክ ገጻቸው በኩል ለፈለፉ፡፡
መጀመሪያ...
“ስፒል ጫማ ያደረገች ዝንጀሮ!...” ሲሉ በገደምዳሜ ወረፏት ቴለር - የክቡር ፕሬዚዳንቱን ሚስት ሚሼል ኦባማን፡፡ ይሄን የፌስቡክ ዘለፋ ያነበቡት የከተማዋ ከንቲባ ዋሊንግም፣ ዘለፋውን የሚደግፍ አስተያየት ዝቅ ብለው አሰፈሩ፡፡
ዳይሬክተሯና ከንቲባዋ በቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ ላይ እንደዋዛ የሰነዘሩት ዘለፋ፣ በፍጥነት ከፌስቡክ ወደ መሬት ወርዶ አሜሪካውያንን ክፉኛ ያስቆጣ የዘረኝነት ንግግር ሆነ፡፡ ብዙዎች በዳይሬክተሯ ዘለፋና በከንቲባዋ ምላሽ በንዴት ጦፉ፡፡ የሁለቱ ሰዎች የዘረኝነት ፖስት ያስቆጣቸው አሜሪካውያን፣ በድረገጽ አማካይነት በጀመሩትና ሁለቱም ሴቶች ከስራቸው እንዲባረሩ በሚጠይቀው የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ፣ ከ170 ሺህ በላይ ሰዎች ፊርማቸውን አሰፈሩ፡፡
ዳይሬክተሯ እና ከንቲባዋ በሁኔታው እጅግ ደነገጡ። ሁለቱም ያንን ጦሰኛ ጽሁፍ ከፌስቡክ ገጻቸው ላይ ቢሰርዙትም፣ ቀድሞ በሺህዎች ተባዝቶ ምድረ ፌስቡክን አዳርሶት ነበርና፣ እንዳሰቡት አላመለጡም፡፡ በርካታ አሜሪካውያን ክፉኛ ያብጠለጥሏቸው ያዙ፡፡
ዳይሬክተሯ ሊያስተባብሉ ሞከሩ፡፡
“ለማለት የፈለግሁት አልገባችሁም!... እኔ እኮ ስፒል ጫማ ያደረገች ዝንጀሮ ያልኩት ሚሼልን ሳይሆን...” በሚል የጀመሩትን ማስተባበያ የሚቀበላቸው አላገኙም፡፡
ከንቲባዋም ዘረኝነትን የማራመድ ሃሳብ እንደሌላቸው በመግለጽ፣ ለሆነው ነገር ሁሉ ይቅርታ ቢጠይቁም፣ ጆሮ እሚሰጣቸው አልተገኘም፡፡
በስተመጨረሻም...
ከንቲባዋ ባለፈው ሰኞ በገዛ ፈቃዳቸው ስራ መልቀቃቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ ለከተማዋ ምክር ቤት አስገቡ፡፡ ዳይሬክተሯም ከስራ መባረራቸውን የሚገልጽ አስደንጋጭ ደብዳቤ ደረሳቸው - ይላል ቢቢሲ ባወጣው ዘገባ፡፡
የራሷ ሲያርባት የሰው ያማሰለቺው ቱርክ
መንበረ መንግስቴን ለመንጠቅ አሲራችኋል በሚል ከመቶ ሺህ በላይ ዜጎቿን ከስራ በማባረር፣ ... ሺህ ያህሉን በጅምላ እያፈሰች ወደ ወህኒ በመወርወር፣ ጋዜጠኞችን በማሰርና በማዋከብ የአለም መነጋገሪያ የሆነቺው ቱርክ፤ የራሷን ጉዳይ መላ መምታት ትታ፣ ወደ አሜሪካ ዞር አለችና የሰሞኑ ተቃውሞ ያሰጋኛል አለች፡፡
ዘ ኢንዲፔንደንት ማክሰኞ እንደዘገበው፣ ለተቃውሞ የወጡ ዜጎቿን ማሰርና መግደል የማይታክታት ቱርክ፣ በትራምፕ ላይ የተጀመረው ተቃውሞ ሊባባስ ይችላልና አደራችሁን ወደዚያ ድርሽ እንዳትሉ ስትል ዜጎቿን አስጠንቅቃለች። አሜሪካ በቱርክ መዲና ኢስታምቡል የሚገኙ የቆንስላ ሰራተኞች የሆኑ ዜጎቿን፣ የሽብር ጥቃት ሰለባ እንዳትሆኑ ወደ አገራችሁ ተመለሱ ስትል በተደጋጋሚ ማስጠንቀቋን ያስታወሰው ዘገባው፣ የቱርክ መንግስትም ለአሜሪካ ምላሽ ለመስጠት፣ ወግ ደርሶት ለዜጎቹ የማስጠንቀቂያ መልዕክት ማስተላለፉን ገልጧል። የቱርክ መንግስት ከሰሞኑ ባወጣው በዚህ መግለጫ፣ በአሜሪካ የሚገኙና ወደ አሜሪካ ለመጓዝ ያቀዱ ዜጎቹን፣ የጸረ-ትራምፕ ተቃውሞው ሰለባ እንዳትሆኑ ተጠንቀቁ ማለቱንም አስረድቷል፡፡
የትራምፕ ፊርማ ሲነበብ
“የስልጣን ጥም ያንገበገባቸው ሰው ናቸው!...” አለች ትሬሲ፡፡
እንግሊዛዊቷ ትሬሲ ትሩሴል፣ ስለ ዶናልድ ትራምፕ ነው እንዲህ በእርግጠኝነት ያወራቺው፡፡
ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፣የብሪቲሽ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ግራፎሎጂስትስ ባልደረባ የሆነቺው ትሬሲ ትሩሴል፣ ከሰሞኑ በአነጋጋሪው ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባህሪ ላይ ጥናት ድርጋለች። እሷና ባልደረቦቿ እንደሚያደርጉት፣ ጥናቷን የሰራቺው በትራምፕ የእጅ ጽሁፍ እና ፊርማ ላይ ነበር። የትራምፕን ፊርማ እና የእጅ ጽሁፍ አጣጣል በትኩረት ስታጤን የሰነበተቺው ትሬሲ፣ ከሰሞኑ ብቅ አለቺና እንዲህ አለች...
“ፊርማቸውን ልብ ብዬ ሳጤነው፣ ትራምፕ የስልጣን ጥም የሚያንገበግባቸው ሰው እንደሆኑ አረጋግጫለሁ!...”
እንዲህ ብላም አላበቃችም፡፡
የማይጨበጥ ምኞት የሚያጠቃቸው ትራምፕ፣ ምንም እንኳን ሃይለኝነት ቢጠናወታቸውም በተለይ ለቤተሰባቸው ጥላ ከለላ መሆን የሚያስደስታቸው ሰው እንደሆኑ ከፊርማቸው መረዳት መቻሏን ተናግራለች፡፡ እምብዛም ሌሎችን እንደማያደምጡና በድርድር ወቅት ፈርጠም ማለት የሚቀናቸው እንደሆኑም ገልጻለች፡፡
ዙክበርግ እንደ ጲላጦስ
ቀጣዩዋ የአሜሪካ መሪ እንደሚሆኑ ብዙዎች በልበ ሙሉነት ቢናገሩላቸውም ያልተሳካላቸው ሄላሪ ክሊንተን፣ ባልታሰበ መልኩ ለመሸነፋቸውና ያልተጠበቁት ዶናልድ ትራምፕ ለመመረጣቸው ብዙ ምክንያቶች መጠቀሳቸው እንደቀጠለ ነው፡፡
ሁሉም የየራሱን ሰበብ ሲሰነዝር ታዲያ፣ ለሄላሪ መሸነፍ ምክንያቱ ፌስቡክ ነው የሚሉም አልታጡም፡፡
በርካታ አሜሪካውያን ፌስቡክ ትራምፕ እንዲመረጥ የራሱን ጉልህ ሚና ተጫውቷል ብለው እንደሚያስቡ የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፣ በሄላሪ ዙሪያ ያልተጨበጡ አሉባልታዎችን በማናፈስ ተወዳጅነቷን ቀንሶታል በሚል ፌስቡክን ማብጠልጠል የያዙ እንደበረከቱ ገልጧል፡፡
ምርጫው ጥቂት ቀናት ሲቀሩት፣ በፌስቡክ ከ560 ሺህ ጊዜ በላይ ሼር የተደረገውንና የሄላሪን የኢሜል ቅሌት ሚስጥር ያወጣው የኤፍቢአይ መርማሪ ሞቶ እንደተገኘ ዘ ዴንቨር ጋርዲያን ዘገበ የሚለውን ጽሁፍ ለአብነት የሚጠቅሱት እነዚህ አሜሪካውያን፣ ቆየት ብሎ ግን ዘ ዴንቨር ጋርዲያን የተባለ ጋዜጣ እንደሌለ መረጋገጡንና መረጃው ሄላሪን ለማጥላላት ሆን ተብሎ የተሰራጨ እንደሆነ ይጠቁማሉ፡፡
ለትራምፕ ድል እና ለሄላሪ ሽንፈት ምክንያት ሆኗል በሚል ፌስቡክን የሚወነጅሉ መበራከታቸውን ተከትሎ ታዲያ፣ የኩባንያው መስራችና ባለቤት ማርክ ዙክበርግ፣ ከሰሞኑ አደባባይ ወጥቶ እንደ ጲላጦስ “ከደሙ ንጹህ ነኝ” ሲል በይፋ ማስተባበሉን ዘገባው ገልጧል፡፡
“ፌስቡክ ትራምፕ እንዲያሸንፍ ረድቶታል ብሎ መናገር የማይመስል ነገር ነው!... ሰዎች ለማን ድምጻቸውን እንደሚሰጡ የሚወስኑት፣ ተጨባጭ የህይወት ልምዳቸውን መሰረት አድርገው ነው!...” ብሏል ዙክበርግ፡፡
ትራምፕ እና ሂትለር ምን እና ምን ናቸው?...
ታሪካዊው ምርጫ፣ በታሪክ መምህሩ ታሪክ ላይ የራሱን አሻራ ጣለ ይላል፤ ዘ ቴሌግራፍ፡፡
የዘንድሮው የአሜሪካ ምርጫ፣ ላለፉት 40 አመታት በካሊፎርኒያው ማውንቴን ቪው አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተግተው ታሪክ ባስተማሩት መምህር ፍራንክ ናቫሮ ላይ በተለየ መልኩ ቀጥተኛ ተጽዕኖ እንደፈጠረ ዘገባው ያስረዳል፡፡ መምህሩ ሰሞኑንም እንደወትሯቸው ታሪክ ሊያስተምሩ ወደ ክፍል ገቡ፡፡
ማስተማርም ጀመሩ፡፡ በመሃል ላይ ግን፣ የሚያስተምሩትን ርዕሰ ጉዳይ በምሳሌ ማስደገፍ ነበረባቸው፡፡ ምሳሌ ፈለጉ። አገኙ። እንደዋዛ ጉዳያቸውን በምሳሌያቸው እያዋዙ ለደቀመዝሙራናቸው ማስረዳት ቀጠሉ፡፡
የዕለቱ የታሪክ ትምህርት ክፍለ ጊዜ ተጠናቀቀና፣ መምህር ናቫሮ ተማሪዎቻቸውን ተሰናብተው ከክፍል ወጡ፡፡
ከቀናት በኋላ...
እኒሁ መምህር ያልጠበቁት ነገር ገጠማቸው። የትምህርት ቤቱ አስተዳደር ከተማሪዎች ወላጆች ቅሬታ እንደቀረበባቸው ነገራቸው፡፡ የቅሬታውን ሰበብ ለማወቅ ጓጉተው ሲጠይቁ ታዲያ፣ ከቀናት በፊት ሲያስተምሩ የሰጡት ምሳሌ መሆኑ ተነገራቸው፡፡ ደንግጠው ሊያስታውሱ ሞከሩ፡፡
እውነት ነው፡፡ መምህሩ በዕለቱ ታሪክ ሲያስተምሩ በሰጡት ጦሰኛ ምሳሌ፣ ተመራጩን ዶናልድ ትራምፕ እና የናዚውን ጨፍጫፊ አዶልፍ ሂትለርን እያነጻጸሩ ሲያስተምሩ ነበር። ሁለቱም በምርጫ ለማሸነፍ ባደረጓቸው ቅስቀሳዎች ለአናሳዎች ያላቸውን አመለካከትና የዘረኝነት መንፈሳቸውን ማንጸባረቃቸው እንደሚያመሳስላቸው፤ ሁለቱም ዳግም ታላቅ ስለማድረግ ቃል መግባታቸው አንድ እንደሚያደርጋቸው ለተማሪዎቻቸው አስረድተው ነበር፡፡
በመሆኑም ትራምፕን ከሂትለር ጋር ማመሳሰል አግባብ አይደለም በሚል ተወነጀሉ፤ መምህሩ፡፡
“እኔ የፈለግኩት እንኳን፣ የ20ኛውን መቶ ክፍለ ዘመን ታሪክና አሁን እየሆነ ያለውን ታሪክ ለማስተሳሰር እንጂ ታላቁን መሪያችንን ከዚያ ሰው በላ ጋር ለማመሳሰል አልነበረም!...” በማለት የልባቸውን ተናግረው ለማስተባበል ሞከሩ፡፡
የሚሰማቸው አልተገኘም - “ላልተወሰነ ጊዜ ከስራ ታግደሃል!...” ተባሉ፡፡
ይህን የሰሙ ከ30 ሺህ በላይ አሜሪካውያን ባሰባሰቡት ፊርማ፣ መምህሩ ምህረት ተደርጎላቸው ወደ ስራቸው እንዲመለሱ የትምህርት ቤቱን አስተዳደር መጠየቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ከቀናት እገዳ በኋላ ባለፈው ረቡዕ ወደ ስራቸው እንዲመለሱ እንደተፈቀደላቸው ገልጧል፡፡

እስከ 15 አመት በሚደርስ እስር ሊቀጡ ይችላሉ
     የሩስያ የኢኮኖሚ ሚኒስትር አሌክሲ ኡሊካየቭ፣ በ2 ሚሊዮን ዶላር ሙስና መከሰሳቸውንና በፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ትዕዛዝ ባለፈው ማክሰኞ ከስልጣናቸው መነሳታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሚኒስትሩ የሙስና ተግባራትን እንደሚፈጽሙ የሚያመላክቱ መረጃዎች መገኘታቸውን ተከትሎ ጉዳዩን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ በግለሰቡ ላይ ለወራት የስውር ክትትልና ስለላ ሲያደርግ መቆየቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ሰኞ ሮዝኒፍት ከተባለው የአገሪቱ ቁጥር አንድ የነዳጅ ኩባንያ ባለስልጣናት፣ 2 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ መያዛቸውንም ገልጧል፡፡
ማክሰኞ ዕለት ፍርድ ቤት የቀረቡት የ60 አመቱ ኡሊካየቭ፣ በሮዝኒፍትና በባሽኔፍት የነዳጅ ኩባንያዎች መካከል በተፈጸመ ግዢ ስልጣናቸውን ተጠቅመው ያለ አግባብ ላሳለፉት ውሳኔ 2 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ ተቀብለዋል ተብለው የተወነጀሉበትን የሙስና ድርጊት አልፈጸምኩም ብለው መከራከራቸውን የዘገበው ሮይተርስ በበኩሉ፤ ጉዳዩን በመመርመር ላይ የሚገኘው የሞስኮ ፍርድ ቤት፣ ተከሳሹ ሚኒስትር እስከ መጪው ጥር ወር አጋማሽ በቤት ውስጥ የቁም እስር እንዲቆዩ ትዕዛዝ ማስተላለፉን አስነብቧል፡፡
ሚኒስትሩ በተከሰሱበት ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ እስከ 15 አመት የሚደርስ የእስር ቅጣት ሊጣልባቸው እንደሚችል የጠቆመው ዘገባው፣ ግለሰቡ እ.ኤ.አ ከ1991 ወዲህ በስልጣን ላይ እያሉ ክስ የተመሰረተባቸው የመጀመሪያው የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን እንደሆኑም አስታውሷል፡፡
ላለፉት 3 አመታት በኢኮኖሚ ሚኒስትርነት ያገለገሉት ኡሉካየቭ፣ በፕሬዚዳንት ፑቲን ትዕዛዝ ከስልጣን መነሳታቸውን ተከትሎ፣ በምክትል ሚኒስትርነት ሲሰሩ የቆዩት የቭጌኒ የሊን በጊዚያዊነት በቦታው ላይ  መሾማቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

በብሩንዲ 600 ሺህ ዜጎች የምግብ እጥረት ገጥሟቸዋል
     በሰሜን ምስራቃዊው የናይጀሪያ አካባቢ የሚኖሩ 75 ሺህ ያህል የአገሪቱ ህጻናት አስፈላጊው ፈጣን እርምጃ ካልተወሰደ በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ በርሃብ ሊያልቁ የሚችሉበት አሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታወቀ፡፡
በተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች አስተባባሪ ፒተር ሉንበርግን ጠቅሶ ቢቢሲ እንደዘገበው፣ በመጪው የፈረንጆች አመት 2017 በአካባቢው የሚኖሩ 14 ሚሊዮን ሰዎች የሰብዓዊ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው ሲሆን  ከእነዚህም መካከል 400 ሺህ ያህሉ ህጻናት ናቸው፡፡ፒተር ሉንበርግ አክለውም ድርጅቱ የሰብዓዊ ድጋፍ በማድረግ አደጋውን ለመቀልበስ የሚያስችል በቂ ገንዘብ እንደሌለው ማስታወቃቸውንና አለማቀፉ ማህበረሰብ ለዚህ አሳሳቢ ችግር አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ ጥሪ ማቅረባቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜና በብሩንዲ ባለፈው  አመት በተከሰተው ድርቅና የጎርፍ አደጋ ሳቢያ 600 ሺህ ያህል የአገሪቱ ዜጎች የምግብ እጥረት እንዳጋጠማቸው የአለም የምግብ ፕሮግራም ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ የምግብ እጥረት ያጋጠማቸው ዜጎች ቁጥር በመጪው አመት ወደ 700 ሺህ ከፍ ሊል ይችላል ያለው የአለም የምግብ ፕሮግራም፤ ችግሩ በተከሰተባቸው 5 የአገሪቱ አውራጃዎች ውስጥ የሚገኙ 65 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ከመኖሪያቸው መፈናቀላቸውንም ጠቁሟል፡፡

 3 ሺህ 200 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነውን ርቀት በ4 ወራት ለማጠናቀቅ አቅዷል
      ቤን ሆፐር የተባለው እንግሊዛዊ ከሴኔጋል በመነሳት አትላንቲክ ውቅያኖስን አቋርጦ ብራዚል የሚደርሰውንና 3 ሺህ 200 ኪሎሜትር የሚሸፍነውን የውሃ ዋና ባለፈው እሁድ መጀመሩን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የ38 አመቱ እንግሊዛዊ ረጅም ርቀት የሚሸፍነውን የውሃ ዋና ለማድረግ ከ3 አመታት በላይ መዘጋጀቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ዋናውን ለማጠናቀቅ አራት ወራት ያህል ጊዜ ይፈጅበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡ ሆፐር ዋናውን በሰላም ካጠናቀቀ አንድን ውቅያኖስ አቋርጦ ከአንድ አህጉር ወደሌላ አህጉር ረጅም ዋና በማድረግ በአለም የክብረ ወሰን መዝገብ እንደሚሰፍር የጠቆመው ዘገባው፣ ዋናተኛውን ሁለት ጀልባዎች እንደሚከተሉት አመልክቷል፡፡
የቀድሞ የእንግሊዝ የፖሊስ መኮንን የነበረው ሆፐር፤ በቀን ለ12 ሰዓት ያህል በመዋኘት ረጅሙን ርቀት ለማጠናቀቅ ማቀዱ የተነገረ ሲሆን፣ በዋናው የገቢ ማሰባሰቢያ በማድረግ 1 ሚሊዮን ዶላር ለግብረ ሰናይ ድርጅቶች ለመለገስ ማሰቡም ተዘግቧል፡፡

 • በፊፋ ስር ዝውውራቸውን ህጋዊ የሚያደርግ ዲፓርትመንት ተቋቁሞ መንቀሳቀስ ከጀመረ 6 ወራትተቆጥረዋል፡፡
    • በፕሪሚዬር ሊጉ ብዛታቸው ከ10 የተለያዩ አገራት 32 ተጨዋቾች ናቸው፡፡

                   
          በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የተጨዋቾች የደሞዝ መረጃ በከፊል
  ስም  ክለብ  ወርሃዊ ደሞዝ

ታደለ መንገሻ አርባ ምንጭ ከነማ 125,000.0
እንዳለ ከበደ አርባ ምንጭ ከነማ 104,166.0
ጌታነህ ከበደ ደደቢት 100,000.0
ሳሙኤል ሳኑሚ ኢትዮ.ቡና 100,000.0
አስራት መገርሳ ደደቢት 83,333.0
ተሾመ ታደለ አርባ ምንጭ ከነማ 79,166.7
አማኑኤል ጎበና አርባ ምንጭ ከነማ 79,166.0
ወንድወሰን ሚልኪያስ አርባ ምንጭ ከነማ 72,916.7
ሳምሶን ጥላሁን ደደቢት 68,205.0
አንተነህ መሳ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
አመለ ሚልኪያ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ምንተ ስኖት አበራ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ተመስገን ካስትሮ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ተካልኝ ደጀኔ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ወንድሜነህ ዘሪሁን አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ገብረ ሚካኤል ያእቆብ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
በረከት ቦጋለ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
ወርቅይታደስ አበበ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
አንድነት አዳነ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
ዳዊት ፈቃዱ ደደቢት 61,795.0
ስዩም ተስፋዬ ደደቢት 61,795.0
ዘሪሁን ታደለ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ፍሬው ጌትነት ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አሉላ ግርማ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አንዳርጋቸው የላቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አበባው ቡጣቆ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
መሃሪ መና ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አይዛክ ኢሴንዴ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አሰቻለው ታመነ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ሳላሃዲን ባርጌቾ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
በሃይሉ አሰፋ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ተስፋዬ አለባቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ምንተስኖት አዳነ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ምን ያህል ተሾመ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አዳነ ግርማ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አብዱልከሪም መሃመድ ኢትዮ.ቡና 58,333.0
አይናለም ሃይሉ ደደቢት 55,385.0
አክሊሉ አየነው ደደቢት 52,780.0
ብርሃኑ ቦጋለ ደደቢት 52,178.0
ጃክሰን ፊጣ አርባ ምንጭ ከነማ 50,000.0
ሰለሞን ሃብቴ ደደቢት 42,564.0
ዘካሪያስ ቱጂ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ደጉ ደበበ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ናትናኤል ዘለቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ራምኬል ሎክ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ሮበርት ኦዱንግካራ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
ያሳር ሙገረዋ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
አብዱልከሪም ዞኮ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
ሶፎኒያስ ሰይፈ ደደቢት 38,462.0
ታገስ አበበ አርባ ምንጭ ከነማ 33,333.2
ጸጋዬ አበራ አርባ ምንጭ ከነማ 33,300.0


       የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የፕሪሚዬር ሊግ  ክለቦች የውጭ ተጨዋቾችን ቅጥር አስመልክቶ የሚሰራ ክፍል አቋቁሞ መስራት ከጀመረ ስድስት ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ይህ የፌደሬሽኑ ዲፓርትመንት የአይቲሲ፤ የቲኤምኤስ እና የፊፋ ቲኤምኤስ ተግባራትን የሚያከናውን ሲሆን ሃላፊው አቶ ሚካኤል እምሩ ይባላል፡፡ አቶ ሚካኤል እምሩ ለስፖርት አድማስ እንደተናገረው ዲፓርትመንቱ በፊፋ ማኔጅመንት ሲስተም ስር የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ የውጭ ተጨዋቾች ዝውውርን ተከታትሎ ይመዘግባል፡፡ ከሌሎች አገራት ፌደሬሽኖች  ግንኙነት መፍጠር መረጃዎችን ያሳውቃል፤ ይመረምራል፤ የውጭ ተጨዋቾች ቅጥሮችን በፊፋ የማኔጅመንት ሲስተም ደንቦችና መመርያዎች መሰረትም ያረጋግጣል በመጨረሻም የሊጉ ክለቦች የሚፈፅሟቸውን ዝውውሮች የውጭ ተጨዋቾች ፓስፖርት በመስጠት ያፀድቃቸዋል፡፡
በየሊጉ ክለቦች የውጭ ተጨዋቾችን ለመቅጠር መፈለጋቸውን  በግልፅና ዝርዝር መረጃዎች ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ የፌደሬሽኑ ዲፓርትመንት ደግሞ የውጭ ተጨዋቾቹ ከሚመጡባቸው አገራት ፌደሬሽኖች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ህጋዊ ምዝገባ መከናወኑን ይጠይቃል። ከዚያም የሚገኘውን ምላሽ በዝውውሩ የሚያስፈልጉ የተጨዋቹ የቀድሞ ክለብ እና አዲስ ሊዛወርበት የፈለገው ክለብ የኮንትራት ውሎችና ሌሎች መረጃዎች ተገቢነትን ሙሉ ለሙሉ በመመርመር በድጋሚ ከሌላኛው አገር ፌደሬሽን በሚያደርገው ግንኙነት የሚያረጋጥ ይሆናል፡፡ በመጨረሻም በፊፋ የማኔጅመንት ሲስተም መረብ ተጨዋቹን ያስመዘግባል፡፡
በአጠቃላይ  የውጭ አገር ተጨዋቾች ለአንድ ክለብ ተገቢ ሆነው መጫወት የሚችሉት የፊፋ የዝውውር ስርዓት በሚጠብቅ አካሄድ ሆኗል፡፡
ተጨዋቹ የሚጫወትበትን ክለብ በደብዳቤ ጠይቆ   ስምምነት   ሲያገኝ፤ የሚጫወትበት ክለብ ለሀገሩ ፌዴሬሽን ስምምነቱን ሲያሳውቅ፤ ተጫዋቹ የሚጫወትበት አገር ፌዴሬሽን ዓለም አቀፍ የዝውውር መልቀቂያ ወረቀት እንዲልክለት የኢት/እግር ኳስ ፌዴሬሽንን ሲጠይቅና በዚህ ጥያቄ መሰረትም ፌዴሬሽኑ ተጨዋቹ የሚገኝበትን ሀገር ፌዴሬሽን በጽሁፍ ሲጠይቅ፤ ተጫዋቹ የሚጫወትበት አገር ፌዴሬሽን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዓለም አቀፍ የዝውውር መልቀቂያ ወረቀት /ITC/ በቀጥታ ሲልክ፤ ከሚጫወትበት ኢትዮጵያዊው ክለብ ጋር በዘመን የተደረገ የውል ስምምነት ለፌዴሬሽኑ ሲቀርብ ከሚመለከታቸው የመንግስት መ/ቤቶች የመኖሪያና የሥራ ፈቃድ ክለቡ አሟልቶ ሲያቀርብ የዝውውሩ ሂደት ህጋዊና በፊፋ ማኔጅመንት ሲስተም የተተገበረ ይሆናል ማለት ነው፡፡
 የፌደሬሽኑ  የአይቲሲ፤ የቲኤምኤስ እና የፊፋ ቲኤምኤስ  ሃላፊ አቶ ሚካኤል እምሩ ለስፖርት አድማስ እንደተናገሩት ዲፓርትመንታቸው መንቀሳቀስ በጀመረባቸው ባለፉት 6 ወራት 45 የውጭ ተጨዋቾች በኢትዮጵያ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች የዝውውር እንቅስቃሴ ተሳትፈዋል ሲሆን በተጨማሪም ዲፓርትመንቱ 4 የውጭ ተጨዋቾች ከኢትዮጵያ የለቀቁበትን ዝውውር ህጋዊነት መረጋገጡንና  በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ህጋዊ የውጭ ተጨዋች ፓስፖርታቸውን ያገኙ የውጭ ተጨዋቾች ብዛት 32 እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ እነዚህ ተጨዋቾች ከ10 የተለያዩ አገራት ማለትም፤ ከጋና፤ ናይጄርያ፤ አይቬሪኮስት፤ ብሩንዲ፤ ሴራሊዮን፤ ናይጄርያ፤ ኬንያ፤ ኡጋዳ፤ ቶጎና ቤኒን የመጡ ናቸው፡፡
ባለፈው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ እግር ኳስ የክለቦች ውድድር ከአፍሪካ 6 አገራት የተውጣጡ ከ26 በላይ የውጭ ተጨዋቾች በ7 ክለቦች ህጋዊ እውቅና  አግኝተው በመቀጠር ተጫውተዋል፡፡ ያኔ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ለሚዲያው አሰራጭቶት በነበረው ዝርዝር መሰረት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጫወቱ የነበሩት 26 የውጭ ተጨዋቾች 8 ከካሜሮን፤ 7 ከናይጄርያ፤ 6 ከጋና፤ 3 ከኡጋንዳ እንዲሁም የተቀሩት ከኬንያ እና ከደቡብ አፍሪካ የመጡ ነበሩ፡፡ ከ26ቱ ተጨዋቾች ጊዮርጊስ 7፤ መብራት ኃይል እና ሀረር ቢራ እያንዳንዳቸው 5፤ ደደቢት 4፤ ኢትዮጵያ ቡና እና ድሬዳዋ ከነማ እያንዳንዳቸው 2 እንዲሁም ኒያላ ለ1 ተጨዋች ቅጥር ፈፅመው በፌደሬሽኑ የእውቅና ማረጋገጫ በማግኘት የውድድር ዘመኑን አሳልፈዋል፡፡
“ሜዳዎች ለስላሳና ምቹ ሳር ቢነጠፍባቸው…”
ባሪ ሊድዮም ከናይጄርያ
በሙሉ ስሙ ባሪ ሌድዮም ተብሎ ይታወቃል። የ24 ዓመቱ ናይጄሪያዊ የአጥቂ መስመር ተጫዋች ነው፡፡ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ከተቀላቀለ ዘንድሮ 5ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን፤ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በናይጄርያ ትውልድ ከተማው ፖርት ሃርኮት በሚገኝ ክለብ በመጫወት አሳልፏል፡፡ ከዚያም በኋላ ወደ ህንድ በማቅናት በሙምባይ ኤፍ.ሲ ክለብ ለ1 ዓመት ተጫውቶ ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣው፡፡  የመጀመሪያ ክለቡ የሆነው በብሄራዊ ሊግ የሚወዳደረው ወልቂጤ ከነማ ሲሆን  ለ1 ዓመት ከ6 ወራት ተጫውቷል፡፡ ሁለተኛ ክለቡ በ2006 ዓመት በብሄራዊ ሊግ የነበረው የጂማ አባቡና ክለብ ሲሆን 1 ዓመት በዚያው አሳልፏል።  በሁለቱ ክለቦች በብሔራዊ ሊግ የ2 ዓመት ከ6 ወር ቆይታው የነበረውን አጠቃላይ ልምድ ባሪ ሌድዮም ለስፖርት አድማስ ሲናገር፣ የብሔራዊ ሊግ ተሳትፎ ወደ ፕሪሚዬር ሊግ ለመግባት ለሚፈልጉ ተጨዋቾች ከፍተኛ ልምድ የሚያስገኝ መሆኑን ገልፆ፤ ተወዳዳሪ ክለቦች በቂ የሚዲያ ሽፋን አለማግኘታቸውና በተሟሉ የስፖርት መሰረተ ልማቶች የሚንቀሳቀሱ ባለመሆናቸው የተጎዱ ናቸው ብሏል፡፡
ናይጄሪያዊው ባሪ በብሄራዊ ሊግ የነበረውን ቆይታ ካጠናቀቀ በኋላ ባለፈው የውድድር ዘመን በፕሪሚዬር ሊግ ተሳታፊ የሆነውን ሲዳማ ከነማን ተቀላቅሏል፡፡ በሲዳማ ከነማ ክለብ ባሳለፈው የመጀመሪያ የውድድር ዘመን ከሊጉ ጋር ለመላመድ መቻሉን ጠቅሶ፣ ዘንድሮ ከክለቡ ጋር በሊጉ ጠንካራ ብቃት ለማሳየት ተስፋ ማድረጉን ገልጿል፡፡  በሊጉ ክለቦች ናይጄሪያዊ ዜግነት ያላቸው ተጫዋቾች ብዛት እየቀነሰ መምጣቱን የገለፀው ባሪ፣ ከእሱ ሌላ ሁለት ተጫዋቾች በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እንዲሁም ሌላ ተጨዋች በቡና እንደሚገኙ አውቃለሁ ይላል፡፡ ባሪ ሊድዮም ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው አሁን በሚጫወትበት የሲዳማ ቡና ክለብ ሁለት ኬንያውያን አንድ የሃይቲ ተጫዋቾች ይገኛሉ፡፡ ደጋፊዎች በክለቡ ለሚገኙ የውጭ ተጫዋቾች ልዩ ማበረታቻ እና ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጾ፤ በየጊዜው ውጤታማ እንድንሆን መፈለጋቸው ጥሩ ሞራል እንደሚፈጥር ተናግሯል፡፡
ባሪ ሉድዮም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ባሳለፈው ልምድ ዙሪያ ለስፖርት አድማስ አስተያየቱን ሲሰጥ በአፍሪካ ደረጃ ሁሉም ነገር ተሟልቶ እንዲገኝ መጠበቅ አያስፈልግም ብሎ በተለይ የሊግ ውድድሩ በፉክክር ደረጃው መሻሻል እየታየበት መሆኑን ገልጿል፡፡  በተለይ ግን የሊጉ ተወዳዳሪ ክለቦች ለጨዋታ የሚጠቀሙባቸው ሜዳዎች ለስላሳና፣ ምቹ ሳር ቢነጠፍባቸው በማለትም ምክሩን ለግሷል፡፡
‹‹የማልያ ቁጥር መቀያየር የለበትም››
ሱሌማን አሊ ከጋና
የ31 ዓመቱ ሱሌማን አሊ በዜግነቱ ጋናዊ ነው፡፡ ዘንድሮ በሊጉ ተወዳዳሪ በሆነው መብራት ኃይል  ክለብ በግብ ጠባቂነት በመጫወት ላይ ይገኛል፡፡ ሱሌማን ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በታዋቂ የሞዛምቢክ ክለብ ለ5 ዓመታት ተጫውቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ የመጀመርያ ክለቡ ደደቢት የነበረ ሲሆን ለ6 ወራት ከተጫወተ በኋላ ኢትዮጵያን ለቅቆ በመውጣት በማልዲስ ለሚገኝ ክለብ ለ6 ወራት በመጫወት በኤሽያን ካፕ የመሳተፍ እድል ነበረው፡፡ በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለስ የተቀላቀለው መብራት ኃይልን ሲሆን የፈረመው ኮንትራት  ለ2 ዓመት ነው፡፡ በውድድር ዘመኑ መጀመርያ  ክለቡ የሲቲ ካፕ ዋንጫውን ማሸነፉ አስደሳች እንደሆነ የገለፀው ሱሌማን፤ በሊጉ ጠንካራ ተፎካካሪ ለመሆን የሚያነሳሳ ሲሆን  መነሻ እንደሚሆንና ከ1-5 ባለው ደረጃ ለመጨረስ ተስፋ ማድረጋቸውን ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሰጥቷል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ገና የሁለት አመት ልምድ ያለው ግብ ጠባቂው ቀስ በቀስ እድገት እያሳየ የሚሄድበትን አቅጣጫዎች መታዘቡን ተናግሯል፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አንዳንድ የክለብ ተጨዋቾች የማልያ ቁጥራቸውን በየጊዜው መቀያየራቸው ልክ እንዳልሆነ ያመለከተው ሱሌማን፤ ማንኛውም ተጨዋች ውድድር ዘመኑ ሲጀመር የለበሰውን የማልያ ቁጥር ዓመቱን ሙሉ ሳይቀይር እንዲጫወት የሚያስገድድ መመርያ መኖር አለበት ብሏል፡፡ በተጨማሪም የሊጉን የፉክክር ደረጃ ለማሳደግ ጨዋታዎችን በዝርዝር በመዘገብ ሚዲያዎች ሽፋን መስጠት ይኖርባቸዋል ብሎ ይህ አሰራር ለውጭ ተጫዋቾቹ የመተዋወቅ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን አስረድቷል፡፡
“የኢትዮጵያ ሊግ ተሻሽሏል …”  
አዳሙ አህመድ ከጋና
ጋናዊ አዳሙ አህመድ   የመሀል ተከላካይ መስመር ላይ የሚጫወት ሲሆን ላለፉት 7 ዓመታት በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ ከፍተኛ ልምድ አካብቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በጋና ፕሪሚየር ሊግ  ለ3 የተለያዩ ክለቦች የተጫወተ ሲሆን በቱርክ ክለብ ለ1 ዓመት፣ በአልቤንያ ክለብ ለ6 ወራት፣ በእስራኤል ክለብ ለ6 ወራት የተጫወተበት ልምድ ነበረው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላ ደደቢትን በመቀላቀል ለ6 ዓመታት የተጫወተ ሲሆን የፕሪሚየር ሊግ የሻምፒዮናነት ክብር ከማጣጣሙም በላይ፤ በሁለት የውድድር ዘመናት በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ እና በአንድ የውድድር ዘመን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በቅቷል፡፡
በደደቢት ክለብ የነበረውን ቆይታ ከጨረሰ በኋላ ወልዲያ ከነማን ተቀላቀለ፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በሱፐር ሊግ ስኬታማ የውድድር ዘመን ያሳለፈ ሲሆን   ዘንድሮ በፕሪሚየር ሊግ ደረጃ እየተጫወተ ነው፡፡ ባለፉት 5 እና 6 ዓመታት የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በየውድድር ዘመኑ መሻሻል እየታየበት ነው በማለት ለስፖርት አድማስ አስተያየቱን የሰጠው አዳሙ፤ በተለይ ክለቦች የፋይናንስ አቅማቸውን በማጠናከርና የስፖርት መሰረተ ልማታቸውን በማሳደግ ላይ መሆናቸው የሚበረታታ እንደሆነም ጠቅሷል፡፡
‹‹ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶች ደረጃን ማሻሻል ያስፈልጋል፡፡››
 ጋብሬል አህመድ ከጋና
የ26 ዓመቱ ጋናዊ ጋብሬል አህመድ የአማካይ መስመር ተጨዋች ሲሆን በደደቢት ክለብ ለ3 ዓመታት በመጫወት አሳልፏል፡፡ ከደደቢት ክለብ ጋር 1 ጊዜ የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን፤ በሁለት የውድድር ዘመናት ክለቡ በሁለተኛ ደረጃ ሊጉን ሲያጠናቅቅ አስተዋፅኦም ነበረው፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ካለው ልምድ ባሻገር በስዊድን ክለብ ለ2 ዓመታት እንዲሁም በዴንማርክ ክለብ ለ5 ወራት ለመጫወት ችሏል፡፡
ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ የሚያስታውሰው አገር ትመስለው የነበረችው የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ አዲስ አበባ ከተማ መሆኗን መገንዘቡ አስገርሞት እንደነበር የሚያታውሰው ጋብሬል፤ ከእንግሊዘኛ ተናጋሪ አገር በመምጣቱ በቋንቋ በኩል ከቡድን አጋሮቹ ጋር በቀላሉ ለመግባባት ቸግሮትም ነበር። ሌላው የውጭ ተጨዋች ፈተና የኢትዮጵያን ባህላዊ ምግቦች ከመላመድ አንፃር ነውም ብሏል፡፡
ጋብሬል አሁን በተያዘው የውድድር ዘመን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጨዋች ነው፡፡ ክለቡ በጣም ጥሩ አደረጃጀት እና ብቁ የአስተዳደር ሃላፊዎች ያሉበት፤ በልምምድ ሜዳ ደረጃ ያለውን መሰረተልማት ያሟላ በመሆኑ ደስተኛ ነው፡፡ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶችን ደረጃ ማሻሻል እንደሚያፈልግ ግን ጠቁሟል፡፡ ክለቦች ለሌሎች የመሰረተልማቶች የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ያህል ለተጨዋቾች ምቹ የሆኑ የትራስፖርት አገልግሎቶችን በማከናወን መስራት እንዳለባቸው ሲመክርም፤ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶች በቅዱስ ጊዮርጊስ እና በደደቢት ክለቦች እንደሚታየው ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ባሶች መሆን እንዳለባቸው፤ የክለቦችን ብራንድ የሚያስተዋውቁ ስለሆኑ በዚያ አቅጣጫ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በየዓመቱ ለውጥና መሻሻል እየታየበት ቢሆንም በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገራት በኬንያ፤ በታንዛኒያ እና በሱዳን የሚታዩ እንቅስቃሴዎችን ለመስተካከል ጥረት መደረግ አለበት ብሎ ምክሩን የሚለግሰው ጋብሬል አህመድ፤ የኬንያ ሊግ በዲኤስቲቪ መተላለፉ የታንዛኒያ እና የሱዳን ሊጎች በስፖንሰርሺፕ መንቀሳቀሳቸው ጠቃሚ መሆኑን መገንዘብ ይገባል ሲል ተናግሯል፡፡ በሌላ በኩል  መገናኛ ብዙሓናት ለውጭ አገር የሊግ ውድድሮች የሚሰጡት ሽፋን ለአገር ውስጥም ማድረግ እንዳለባቸው የጠቆመው ጋብሬል፤ በየትኛውም አገር ቅድሚያ የሚሰጥበትን አሰራር በኢትዮጵያም መተግበር ይገባል ብሏል፡፡ በኢትዮጵያ የፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ መሻሻል በአፍሪካ ደረጃ ለሚኖረው ተፎካካሪነት አስተዋፅኦ እንዳለው መታወቅ አለበት የሚለው ጋሬል አህመድ፤ የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ደረጃ በሚካሄዱ ውድድሮች እስከምድብ ድልድል ለመድረስ ከበቁ ከፍተኛ ስኬት ላይ መደረሱን ያረጋግጣል ብሏል፡፡
‹‹የውጭ ተጨዋቾች የሚገጥሟቸውን ፈተናዎች ተቋቁመው ማለፍ አለባቸው››
ሳሙኤል ሳኑዊ ከናይጄርያ
ናይጄርያዊው ሳሙኤል ሳኑዊ በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ የ6 ዓመታት ልምድ ያለው ሲሆን፤ በትልልቅ ክለቦች በመጫወት ከፍተኛ ልምድ ያካበተ ነው፡፡
በቤኒን ክለብ ልምድ የነበረው የ24 ዓመቱ የአጥቂ መስመር ተሰላፊ በኢትዮጵያ የመጀመርያ ክለቡ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሲሆን ለ2 የውድድር ዘመና በዚያ ክለብ ካሳለፈ በኋላ በቀጣይ ለ1 የውድድር ዘመን በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ በመጫወት የሲቲ ካፕ እና የፕሪሚዬር ሊግ ሁለት ዋንጫዎችን መጎናፀፍ ችሏል፡፡ ከጊዮርጊስ በኋላ ያለፉትን ሁለት የውድድድር ዘመና በደደቢት ሲጫወት ያሳለፈ ሲሆን አሁን የሚገኝበት ክለብ ኢትዮጵያ ቡና ሆኗል፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ከፍተኛ ዝና ያለው ሳሙኤል ሳኑዊ ሊጉ በየዓመቱ በተለያያየ የፉክክር ደረጃ የሚቀያየር መሆኑን ገልፆ ከውጭ የሚመጡ ተጨዋቾች እግር ኳስ ሙያችን ነው ብለው ከተነሱ የሚገጥሟቸውን ፈተናዎች ተቋቁመው ማለፍ እና ውጤታማ ለመሆን በትጋት መስራት አለባቸው ሲል ምክሩን ለስፖርት አድማስ ሰጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ እያገኘ ያለው ልምድ በቀጣይ የፕሮፌሽናል የእግር ኳስ ህይወቱን የማሳደግ ህልሙን እንደሚያጠናክርለት እምነት አለኝ የሚለው ሳሙኤል ሳኑዊ፤ እቅዱ ወደ አውሮፓ ክለብ ማቅናት እንደሆነና በተለይ አርሰናልን መቀላቀል ፍላጎቱ እንደሆነ  ተናግሯል።

በኢትዮጵያ ሱዳናውያን ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል
    ወደ ኢትዮጵያ የሚሰደዱት ደቡብ ሱዳናውያን ቁጥር እየጨመረ ነው ያለው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን፤ በየቀኑ በኣማካይ 547 ያህል ደቡብ ሱዳናውያን ድንበር አቋርጠው ጋምቤላ ውስጥ ወደሚገኘው ፓጋክ የስደተኞች ማዕከል እንደሚገቡ አስታወቀ፡፡
በኮሚሽኑ የኢትዮጵያ ቃል አቀባይ አቶ ክሱት ገብረ እግዚያብሄርን ጠቅሶ ‹‹አናዶሉ ኤጀንሲ›› ትናንት እንደዘገበው፣ ካለፈው መስከረም ወር መጀመሪያ አንስቶ 40 ሺህ የሚደርሱ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል 86 በመቶ ያህሉ ሴቶችና ህጻናት ናቸው፡፡ ከስደተኞቹ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ፈተና የሆነው የምግብ እጥረት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት መካከል 4 ሺህ 929 ያህሉ የምግብ እጥረት ተጠቂ መሆናቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
ኮሚሽኑ ከሳምንት በፊት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ እስካለፈው ህዳር አንድ ቀን ድረስ በጋምቤላና በአሶሳ የሚገኙ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል፡፡

3.1 ኪሎ ግራም ክብደት ያለው ወርቅ በህገ-ወጥ መንገድ በድብቅ ወደ ህንድ ለማስገባት የሞከረች ኢትዮጵያዊት፣ ከትናንት በስቲያ በአውሮፕላን ጣቢያ የጉምሩክ ፍተሻ ሰራተኞች ተይዛ መታሰሯን “ዚኒውስ” የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
ስሟ ያልተገለጸው ይህቺው ኢትዮጵያዊት፣ ከአዲስ አበባ በመነሳት ወደ ህንድ ያደረገቺውን ረጅም የአውሮፕላን ጉዞ አጠናቅቃ፣ ኒው ደልሂ በሚገኘው ኢንድራ ጋንዲ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስትደርስ፣ የጉምሩክ ሰራተኞች በሻንጣዋ ላይ ባደረጉት ፍተሻ፣ በህገወጥ መንገድ ልታስገባቸው የነበሩ በድምሩ 3.1 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ አምስት ቁራጭ ወርቆችና የወርቅ ጌጣጌጥ መያዛቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የኒው ዴልሂ የጉምሩክ መስሪያ ቤት ጉዳዩን በተመለከተ ትናንት ያወጣውን መግለጫ በመጥቀስ፣ ግለሰቧ በድብቅ ልታስገባቸው የነበሩት ወርቆች በፖሊስ እንደተያዙና እሷም ወደ እስር ቤት እንደገባችም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ትናንት በዋለው የብሄራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬና የወርቅ ዋጋ ተመን መሰረት፣ ኢትዮጵያዊቷ በህገ ወጥ መንገድ ወደ ህንድ ልታስገባው የሞከረቺው ወርቅ 3 ሚሊዮን ብር ያህል እንደሚያወጣ ይገመታል፡፡

  ከዳያስፖራ የተላከና በሃዋላ የመጣ፣ 990 ሚ. ዶላር ተቀብያለሁ ብሏል
      የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሃምሌ እስከ መስከረም፣ 7.7 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱንና 4 ቢሊዮን ብር ማትረፉን ለአዲስ አድማስ ገለፀ። የባንክ ሂሳብ የከፈቱ ደንበኞቹ ወደ 14 ሚሊዮን እንደሚጠጉ ባንኩ ጠቅሶ፣ በሩብ ዓመት ውስጥ ተቀማጭ ሂሳብን በ7.7 ቢሊዮን ብር በማሳደግና ወደ 296.1 ቢሊዮን ብር ማድረሱን አስታውቋል፡፡
በወጪ ንግድ ከሚያካሂዳቸው ስራዎች 210 ሚ. ዶላር እንዳስገባ በሩብ ዓመት ሪፖርቱ ጠቅሶ፤ ከዳያስፖራ በሃዋላ የመጣ 990 ሚ. ዶላር እንደሰበሰበ ገልጿል - ባንኩ፡፡ በብድርና በቦንድ ሽያጭ 17.7 ቢሊዮን ብር ለተበዳሪዎች በማቅረብ፣ 12 ቢሊዮን ብር ብድር ተመላሽ አድርጌያለሁ ብሏል። 14 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በመክፈት፤ ጠቅላላ የቅርንጫፍ ብዛቱን 1 ሺህ 151 ማድረሱን ሲገልፅ፤ 880ሺ ደንበኞች በሞባይል የባንክ አገልግሎት እየተጠቀሙ ናቸው ብሏል፡፡