Administrator

Administrator

Saturday, 13 February 2016 11:01

ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት

/ባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን/


አዬ፣ ምነው እመ ብርሃን?
ኢትዮጵያን ጨከንሽባት?
ምነው ቀኝሽን ረሳሻት?
እስከመቼ ድረስ እንዲህ፣
መቀነትሽን ታጠብቂባት?
ልቦናሽን ታዞሪባት?
ፈተናዋን፣ ሰቀቀኗን፣ ጣሯን ይበቃል ሳትያት?
አላንቺ እኮ ማንም የላት….
አውሮጳ እንዲሁ ትናጋዋን፣ በፋሽስታዊ ነቀርሳ
ታርሳ፣ ተምሳ፣ በስብሳ
ሂትለራዊ እባጭ ጫንቃዋን፣
እንደኮረብታ ተጭኗት ቀና ብላ እውነት
እንዳታይ፣ አንገቷን ቁልቁል ጠምዝዟት
ነፍሷን ድጦ ያስበረከካት
ሥልጡን፣ ብኩን፣ መፃጉዕ ናት፤ ….
እና ፈርቼ እንዳልባክን፣ ሲርቀኝ የኃይልሽ ውጋገን
አንቺ ካጠገቤ አትራቂ፣ በርታ በይኝ እመ ብርሃን
ቃል ኪዳኔን እንዳልረሳት፣
እንዳልዘነጋት ኢትዮጵያን፡፡
አዎን፣ ብቻዬን ነኝ ፈራሁ
እሸሸግበት ጥግ አጣሁ
እምፀናበት ልብ አጣሁ
እማማ ኢትዮጵያን መንፈሴ፣
ተፈትቶ እንዳይከዳት ሠጋሁ …
አዋጅ፣ የምሥራች ብዬ፣ የትብት ምግቤን ገድፌ
ከእናቴ ማኅፀን አርፌ
ከአፈርዋ አጥንቴን ቀፍፌ
ደሜን ከደሟ አጠንፍፌ
ከወዟ ወዜን ቀፍፌ
በሕፃን እግሬ ድሄባት፣ በህልም አክናፌ ከንፌ
እረኝነቴን በሰብሏ፣ በምድሯ ላብ አሳልፌ
ከጫጩት እና ከጥጃ፣ ከግልገል ጋር ተቃቅፌ፤
በጋው የእረኛ አደባባይ፣ ክረምት እንደወንዙ ፍሳሽ
በገጠር የደመና ዳስ፣ በገደል ሸለቆ አዳራሽ
ከቆቅ እና ከሚዳቋ፣ ከዥግራ ጠረን ስተሻሽ
በወንዝ አፋፍ ሐረግ ዝላይ፣ መወርወር መንጠልጠል ጥሎሽ
ከፍልፈል ጋር ሩጫ ስገጥም፣ ከቀበሮ ድብብቆሽ
ከናዳ ጫፍ ሣር አጨዳ፣ ለግት ላሜ ትንሽ ግጦሽ
ለጥጃዬ የሌት ግርዶሽ
ለጥማድ በሬዎች ራት፣ ለማታቸው ትንሽ ድርቆሽ
ለግልገሌ ካውሬ ከለል
እማሳው ሥር ጎጆ መትከል
ለፀሐይ የሾላ ጠለል፣ ለዝናብ የገሳ ጠለል
ውሎ የንብ ቀፎ ማሰስ፣ ያበባ እምቡጥ ሲፈነዳ
የግጦሽ ሣር ሲለመልም፣ ሲሰማሩ ሰደድ ሜዳ
አዝመራው ጣል ከንበል ሲል፣ ከብቱ ለሆራ ሲነዳ
ፈረስ ግልቢያ ስሸመጥጥ፣ ከወፎች ዜማ ስቀዳ
ልቤ በንፋስ ተንሳፎ፣ በዋሽንት ዋይታ ሲከዳ …..
ያቺን ነው ኢትዮጵያ የምላት
እመ ብርሃን እረሳሻት?
ያቺን የልጅነት የምሥራች? የሕፃንነት ብሥራት
የሣቅ የፍንደቃ ዘመን፣ የምኞት የተስፋ ብፅአት
ያቺን የልጅነት እናት?
አዛኚቱ እንዴት ብለሽ፣ ጥርሶችሽን ትነክሺባት?
ሥሜን በሥምሽ ሰይሜ፣ ባገልግሎትሽ ስዋትት
ከዜማ ቤት እቅኔ ቤት፣ ከድጓ ቤት እመጻሕፍት
ካንቺ ተቆራኝታ ዕድሌ፣ ካንቺ ተቆራኝታ ነፍሴ
ከቀፈፋ ደጀሰላም፣ ከቤተልሔም ቅዳሴ
እኰ፣ ቀፎ ዳባ ለብሶ
ቅኔ ዘርፎ ግስ ገሦ
መቅደስ አጥኖ ማኅሌት ቆሞ
በልብስ ተክህኖ አጊጦ፣ በብር አክሊል ተሸልሞ
እመ ብርሃን ያንች ጽላት፣ ነፍስ ላይ በእሳት ታትሞ
የመናኒው ያባ ተድላ፣ ረድ ሆኜ፣ አብሮኝ ታድሞ
ሕይወቴ እምነትሽን ጸንሶ
ሥጋ ፈቃዴ ተድሶ
ለሕንፃሽ መዲና ቆሞ፣ ለክብርሽ ድባብ ምሰሶ
ሥሜን በሥምሽ ሰይሜ፣ ሆነሺኝ የእምነቴ ፋኖስ
ለዋዜማሽ ግሸን ማርያም፣ ለክብርሽ ደብረ ሊባኖስ
ስሮጥ፣ በወንበሩ አኖርሺኝ፣ በአንበሳው በቅዱስ ማርቆስ
ታዲያ ዛሬ ኢትዮጵያ ስትወድቅ፣ ከምትሰጪኝ የፍርሃት
ጦስ
ምነው በረኝነት እድሜ፣ ዓይኔን በጓጎጣት የሎስ
የጋኔል ጥንብ አንሳ ከንፎ፣ ወርዶ በጨለማ በርኖስ
ባክሽ እመ ብርሃን ይብቃሽ፣ ባክሽ ምስለ ፍቁር ወልዳ
ጽናት ስጪኝ እንድካፈል፣ የእናቴን የኢትዮጵያን ፍዳ፣
ከነከሳት መርዝ እንድቀምስ፣ ከነደደችበት እቶን
የሷን ሞት እኔ እንድሞታት፣ ገላዋ ገላዬ እንዲሆን፡፡
አዎን፣ ብቻዬን ነኝ ፈራሁ
እምፀናበት ልብ አጣሁ፡፡ …

ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ታዋቂ እሥር ቤት ውስጥ አንድ ታዋቂ ኮንትሮባንዲስት ይታሠራል፡፡ ታሥሮም እንደተለመደው ለምርመራ ይጠራል፡፡
መርማሪ
ለምን እንዳመጣንህ ታውቃለህ?
እሥረኛ
አላውቅም
መርማሪ
ሰሞኑን አንተና ግብረ - አበሮችህ ከጅቡቲ ወደ አዲስ አበባ ህጋዊ ሽፋን ያለው ብስኩት አላመጣችሁም?
እሥረኛ፤
እሱን አውቃለሁ
መርማሪ፤
አምጥተሃል አላመጣህም?
እሥረኛ፤
አምጥቻለሁ
መርማሪ
ከብስኩቱ ሥር ምን ነበር
እሥረኛ
ምንም
መርማሪ
እንግዲህ በቀላሉ አምነህ ምርመራችንን ብንጨርስ ይሻላል፡፡ አለበለዛ ወደ አስገዳጅ ምርመራ
መሄዳችን     ነው፡፡
እሥረኛ
እኔ የማውቀውን አውቃለሁ፡፡ የማላውቀውን አላውቅም ብያለሁ፡፡
መርማሪ
እኔ ደሞ እንዴት እንደማሳውቅህ አሳይሃለሁ፡፡ …
ይልና ወደ አስገዳጅ ምርመራ ይወስደውና ያስገርፈዋል፡፡ እሥረኛው ግርፉ ሲበዛበት “እናገራለሁ”
ይላል፡፡
መርማሪ
እሺ ከብስኩቱ ሥር ምን ነበር?... ብሎ ይጠይቃል
እሥረኛ
ውስኪ
መርማሪ
ሌላስ?
እሥረኛ
የታተመ ብር
መርማሪ
በጣም ጥሩ፡፡ አሁን ግብረ -አበሮችህ የት እንዳሉ ታሳየናለህ፣ ትመራለህ፡፡ ስለተደረገልህ ምርመራ
አንድ ቃል ትንፍሽ አትልም፡፡
አጃቢዎች ይመደቡለትና ግብረ - አበሮቹ ያሉበትን ይመራል፡፡ ግብረ - አበሮች ተይዘው ይመጣሉ፡፡
መርማሪ
ኮንትሮባንድ ተይዞባችኋል … በህጋዊ ብስኩት ሽፋን፡፡ ይሄን ታውቃላችሁ?
1ኛው ግብረ - አበር
አላውቅም
2ኛው ግብረ - አበር
አላውቅም
መርማሪ
በተያዘና እጃችን ላይ ባለ ጉዳይ ባንጨቃጨቅ ይሻላል!
ሁለቱም ግብረ - አበሮች “አናውቅም”፣ “አናውቅም” ብለው ድርቅ አሉ፡፡
ይሄኔ መርማሪው ወደ መጀመሪያው እሥረኛ ዞሮ፤
“እነዚህ ጓደኞችህ አናውቅም አሉ‘ኮ ምን ይሻላል?” ሲል ጠየቀው፡፡
እሥረኛውም፤
“እንግዲህ ለእኔ ያረጋችሁትን ማረግ ነዋ!”
***
አገር የሚበድል ተግባር በማናቸውም ገፁ እኩይ ነው፡፡ ፍትሕም ፍትሐዊ መንገድ ያሻዋል፡፡ በየኬላው፣ በየአየር ማረፊያው አልፎ ተርፎም በየቢሮው ውስጥ ኮንትሮባንድ ይጧጧፋል ይባላል፡፡ መገደቢያ ግን አልተበጀለትም፡፡ ጉዳዩን ገደብ ይሰጡታል የሚባሉት አካላት ራሳቸው ገብተውበታል የሚባለው ሐሜት ዕውነት ከሆነ አንዱ እንቅፋት እሱ ነው፡፡ ስለሱ መናገር አለመቻሉም የዛኑ ያህል እንቅፋት ነው፡፡ “እንደነፃው አገር ያሰብነውን ጽፈን፣ ተናግረን፣ ተወያይተን፣ በነፃ ምርጫ የመተዳደር ዕድል እግዚአብሔር ሊሰጠን አልፈቀደም የሚል ተስፋ አስቆራጭ ዕምነት አደረብኝ” እንዳሉት ነው ተክለፃድቅ መኩሪያ፡፡ አዋጅ ብናወጣ፣ መመሪያ ብንደረድር፣ ቀላጤ ብንልክ ውስጣችን ሙስና ካለ፤ ንፁህ ሥራ አይሠራም፡፡ ንፁህ ልማት አይገኝም፡፡ “አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ” ዓይነት አካሄድም ጊዜያዊ ምላሽ የሚመስል ትርዒት ነው፡፡ ግንዱን መገንደስ እንጂ ቅርንጫፉን መቀንጠብ፤ ሙስናን ከሥሩ ገርስሶ አይገላግለንም፡፡ ይብሱንም ሙሰኞች የሚያፌዙበት፣ ውስኪ የሚራጩበት ፌዝ የሆነ ይመስላል ጉዳዩ፡፡
ከተክለ ፃድቅ መኩሪያ “የህይወቴ ታሪክ” ለአብነት ብንጠቅስ የመንግሥት ባለሥልጣናት ብልሹነትና የሞራል ዝቅጠትን ሁኔታ ጥሩ ማፀህያ ይሆነናል፡፡
“ወጣቶች ሚኒስትሮች፤ ከንጉሠ ነገሥቱ የቅርብ ባለሟሎች አንዳንድ ወጣት ነጋዴዎች ጋር በየቪላው ውስኪ እንደውሃ እያፈሰሱ፣ ጮማና ክትፎ እየበሉ፣ አዝማሪ እያቆሙ፣ ከየሴቱ ወጣት ጋር ሆነው ዓለማቸውን ያያሉ” የሚባለው ወሬ ከሚነፍሰው ጋር፤ እያንዳንዱ የተቻለው በየቤቱ፣ በየምክንያቱ የሚደግሰው፤ የድግሱ፣ የመብሉና የመጠጡ ዓይነትና ብዛት በውጪ ካለው የሥራ ፈትና የድሃ ኑሮ ጋር ሲመዛዘን ልዩነቱ ዐይን ይመታል”
ይህን ከ50 ዓመታት በፊት የነበረ ዕውነታ፣ በየዘመኑ ብናጤነው፣ የሙስና ገጽታ ተደጋጋሚና ተመሳሳይ መሆኑን እስከዛሬም ለመገንዘብ አያዳግትም፡፡ የድህነታችንም አዘቅት የዛኑ ያህል ጠሊቅ እየሆነ ይመጣል፡፡
ነብስ ያወቀ ተቋም፣ ጥንካሬ ያለው መዋቅር፣ ፍትሐዊነት ያለው አሠራር፣ ኢ-ወገናዊ የሆነ ሥርዓት፣ ተመልሶ ቀስቱ እኛኑ የማይወጋበት (ቡመራንግ) አካሄድ ካልተፈጠረ፣ “ነገራችን ሁሉ የዕንቧይ ካብ የዕንቧይ ካብ” ይሆናል በአህያ ቆዳ የተሠራ ቤት፤ ጅብ የጮኸ ዕለት ይፈርሳል - ይሏልና!  



    በአዲስ አበባ ከተማ በታክሲ ሹፌርነት ላለፉት 18 ዓመታት የሰሩት አቶ ጥላሁን ቢሆነኝ፤ በትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶች ትርፋማ ሆነው በሥራቸው ለመቀጠል ወሳኙ ነዳጅ የሚገዙበት ዋጋ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ የነዳጅ ዋጋ እርካሽ ሲሆን ብቻ ነው ትርፋማ የሚሆኑት ይላሉ፡፡ ከአንድ አመት በላይ በአለም ገበያ ነዳጅ በከፍተኛ መጠን ዋጋው እያሽቆለቆለ ቢሄድም መንግስት የነዳጅ ዋጋ ማስተካከያ ባለማድረጉ፣ በየጊዜው ከሚንረው የመለዋወጫ እቃዎች ዋጋ ጋር ተደምሮ የትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፉን ክፉኛ ጐድቶታል ይላሉ አቶ ጥላሁን፡፡
ሰሞኑን በቤንዚን ችርቻሮ መሸጫ ላይ መንግስት ያደረገው የ82 ሳንቲም ቅናሽ እጅግ ከጠበቁት በታች እንደሆነባቸው የጠቆሙት የታክሲ  ሹፌሩ፤ ቢያንስ በሊትር እስከ 3 እና 4 ድረስ ብር ቅናሽ ይደረጋል የሚል ግምት እንደነበራቸው ተናግረዋል፡፡
ሌላው የታክሲ አሽከርካሪም የአቶ ጥላሁንን ሃሳብ ይጋራል፡፡ መንግስት የነዳጅ ዋጋን በደንብ ቀንሶ የትራንስፖርት ታሪፍ ላይ መጠነኛ ቅናሽ ቢያደርግ ሁላችንም ተጠቃሚ እንሆን ነበር ይላል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን አብዛኛው የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ በኪሳራ ነው የሚንቀሳቀሰው የሚለው ሹፌሩ፤ መንግስት  የታክሲ ታሪፍን ማስተካከል ከፈለገ፣ ነዳጅ ላይ ከፍተኛ የዋጋ ቅናሽ በማድረግ፣ ህብረተሰቡም ሣይጐዳ ተጠቃሚ ሊያደርገን ይችላል ባይ ነው፡፡
መቀመጫውን በአዲስ አበባ ባደረገ አንድ ዓለም አቀፍ ኩባንያ ውስጥ በኢኮኖሚ አማካሪነት የሚያገለግሉት ዶ/ር በላይ ተስፋ ኪሮስ እንደሚሉት፤ ነዳጅን ከውጭ የሚያስገቡ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገራት ከዓለም አቀፉ ከፍተኛ የዋጋ ቅናሽ ተጠቃሚ ናቸው፡፡ የአገር ውስጥ የነዳጅ ዋጋ ማስተካከያ ሲያደርጉ ግን በጥንቃቄ ሊሆን ይገባል ይላሉ፡፡ “መንግስት አሁን ካለው የአገሪቱ የነፍስ ወከፍ ገቢ ጋር የተመጣጠነ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ በማድረግ፣ ኢኮኖሚው የተረጋጋ ሆኖ እንዲቀጥል መትጋት አለበት፤ ከፍተኛ የነዳጅ ቅናሽ ካደረገ እየተረጋጋ የመጣውን  የግብይት ስርዓት ሊያናጋው ይችላል” ብለዋል - ባለሙያው፡፡ሌላው የኢኮኖሚ ባለሙያ ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ ግን በዚህ ሀሳብ አይስማሙም፡፡ መንግስት አለማቀፉን የነዳጅ ዋጋ መነሻ አድርጐ ከፍተኛ ቅናሽ ቢያደርግም በምንም መመዘኛ የኢኮኖሚ መናጋት እንደማይፈጥር ይገልፃሉ፡፡ “ነዳጅ በአለም ገበያ በከፍተኛ መጠን ሲቀንስ በዚያው ልክ በሀገር ውስጥም መቀነስ ይገባዋል” የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ ምናልባት መንግስት ቀደም ሲል ነዳጅ ላይ ሲያደርግ የነበረውን ድጐማ ለማካካስ ወይም ምናልባት ዋጋው እንደገና ቢጨምር ሰው እንዳይማረር በሚል በለመደው ይሂድ ብሎም ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን ይሄ አግባብ አይደለም፤ ዋጋ ሲጨምር እንደሚጨምረው ሁሉ ሲቀንስም በተገቢው መንገድ መቀነስ አለበት፤ ይላሉ፡፡ የዛሬ ዓመት አካባቢ ነዳጅ በአለም ገበያ ከ140 ወደ 100 ዶላር ሲቀንስ፣ በሀገር ውስጥ የነዳጅ ችርቻሮ መሸጫ ከ20 ብር ወደ 9 እና 10 ብር መቀነስ ነበረበት ያሉት የኢኮኖሚ ባለሙያው፤ አሁን በዓለም አቀፍ ገበያ ከ30 ዶላር በታች ሲሸጥም በሃገር ውስጥ 7 እና 8 ብር በሊትር መሸጥ እንደነበረበት ጠቁመዋል፡፡ መንግስት የዚህን ያህል የዋጋ ቅናሽ ቢያደርግ ራሱንም ሆነ አጠቃላይ ማክሮ ኢኮኖሚውን የሚጐዳው ነገር የለም ይላሉ - ባለሙያው፡፡
“እንደውም ነዳጅ በ7 ብር እና በ8 ብር እንዲሸጥ ሲያደርግ የትራንስፖርት ዋጋ ይቀንሳል፤ ዋጋው ሲቀንስ ከውጭ የሚመጡ እቃዎች፣ ከገበሬው ለከተሜው የሚቀርቡ ምርቶች፣ ለገበሬው የሚሄዱ እንደ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ያሉ ግብአቶች … ዋጋቸው ይቀንሳል” የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ በዚህም በተለይ ቋሚ ገቢ ያላቸው የመንግስት ሠራተኞችና ጡረተኞች የበለጠ ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል፡፡
ሠራተኞችና ጡረተኞች በኑሮ ውድነቱ ምክንያት ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ መሆናቸውን አውስተው፤ የትራንስፖርትና መሠል ወጪዎች ሲቀንስላቸው በኪሣቸው የሚቀመጠው ገንዘብ እየበረከተ ስለሚሄድ፣ ኑሮን መቋቋም ያስችላቸዋል ብለዋል፤ ባለሙያው፡፡ አሁን በአለማቀፍ ደረጃ ነዳጅ በከፍተኛ መጠን በመቀነሱ የውጭ ምንዛሬን ከመቆጠብ አንፃር ዋነኛ ተጠቃሚው መንግስት ቢሆንም በአገር ውስጥ ተገቢውን፤ የዋጋ ቅናሽ የማያደርገው ብቸኛ ነዳጅ አቅራቢ በመሆኑና የሚወዳደረው ባለመኖሩ ነው ያሉት ባለሙያው፤ ይሄም በነዳጅ ግብይት ላይ የገበያ መር ኢኮኖሚው እየሠራ አለመሆኑን ያሳያል ብለዋል፡፡የአገሪቱን የነዳጅ ዋጋ በየ 6 ወሩ እንደሚከልስ የጠቆመው መንግስት በበኩሉ፤ የነዳጅ ዋጋችን ከአፍሪካ የመጨረሻው ዝቅተኛው ነው ብሏል፡፡  በአለም አቀፉ ገበያ የነዳጅ ዋጋ ከዚህ በኋላ ይጨምራል ተብሎ እንደማይገመትና እንዲያውም ከ20 ዶላር በታች ሊወርድ እንደሚችል መተንበዩንም ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ ጠቁመዋል፡፡ በቅርቡ የንግድ ማዕቀብ የተነሣላት ኢራን በቀን 2 ቢሊዮን በርሜል ነዳጅ ለአለም ገበያ ለማቅረብ መወሰኗን ያስታወቀች ሲሆን ተፎካካሪዋ ሳኡዲ አረቢያ በበኩሏ፤ በቀን 10 ቢሊዮን በርሜል ነዳጅ ለገበያ እያቀረበች መሆኗ የነዳጅ ዋጋ እየቀነሰ ይሄዳል የሚለውን ትንበያ ያጠናክረዋል፡፡
ይህን መነሻ አድርጐ መንግስት የነዳጅ ዋጋን በከፍተኛ መጠን በመቀነስ፣ በተለይ ቋሚ ገቢ ያላቸውን ዜጐች ተጠቃሚ የሚያደርግበትን መንገድ ማመቻቸት እንዳለባት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ ይመክራሉ፡፡ በኢትዮጵያውያን ሚሊኒየም (2000 ዓ.ም) መግቢያ ላይ አለምአቀፍ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ65 - 100 ዶላር የነበረ ሲሆን በወቅቱ የአገር ውስጥ የቤንዚን ዋጋ በሊትር 7 ብር ከ77 ሣንቲም ነበር፡፡ በሀገር ውስጥ ገበያ ነዳጅ በከፍተኛ ዋጋ የተሸጠው ከግንቦት 1 ቀን 2003 እስከ መስከረም 26 ቀን 2004 በነበረው ጊዜ ውስጥ ሲሆን በወቅቱ 1 ሊትር ቤንዚን በ20 ብር ከ94 ሣንቲም ተሸጧል፡፡ በተመሳሳይ ወቅት በአለማቀፍ ገበያ የ1 በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ደግሞ ከ85 እስከ 118 ዶላር ነበር፡፡
በጥር 2007 የመጀመሪያ ሁለት ሣምንታት የነዳጅ ዓለም አቀፍ ዋጋ በበርሜል ከ95 ዶላር ወደ 50 ዶላር የወረደ ሲሆን የሀገር ውስጥ የነዳጅ ዋጋ ደግሞ በሊትር የ2 ብር ቅናሽ አሳይቷል፡፡ ይህም የነዳጅ ዋጋ ማሻቀብ ከጀመረበት ከ2000 ዓ.ም ወዲህ ከፍተኛው ቅናሽ ነበር፡፡  በወቅቱ መንግስት ቢያንስ የነዳጅ ዋጋን በሊትር እስከ 9 ብር ማውረድ እንደነበረበት አለማቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ጠቁመው መንግስት በእነዚህ ጊዜያት ከነዳጅ ሽያጭ ከፍተኛ ትርፍ መሰብሰቡን ያስታውሳሉ፡፡ የዓለም የነዳጅ ዋጋ በየጊዜው ቢለዋወጥም የአገር ውስጥ ታሪፍ ግን እስካለፈው ሣምንት ድረስ ሳይለውጥ ነው የቆየው፡፡
 ከ13 አመት በፊት የሀገር ውስጥ የነዳጅ ዋጋ በሊትር ከ5 ብር በታች እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማል፡፡ ለአንድ አመት ያህል ከጥር 23 ቀን 2007 እስከ ጥር 17 ቀን 2008 ዓ.ም የቆየው የነዳጅ ታሪፍ፤ በሚያዚያ ወር 2003 ዓ.ም ከነበረው ጋር ተቀራራቢ ሲሆን በወቅቱ በሰሜን አፍሪካና በአረብ ሀገራት የተነሳውን ተቃውሞና የመንግስት ግልበጣ ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ጭማሪ ያሳየበት ነበር፡፡ በሚያዚያ 2003 ዓ.ም የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል 100 ዶላር የነበረ ሲሆን በአገር ውስጥ አንድ ሊትር ቤንዚን በ17 ብር ከ88 ሣንቲም ይሸጥ ነበር፡፡ በጥር 2008 ዓ.ም ነዳጅ በአለማቀፍ ገበያ ከ30 እስከ 35 ዶላር ሆኖ፣ በአገር ውስጥ በሊትር 17 ብር 43 ሣንቲም ተሸጧል፡፡ ሰሞኑን የተደረገው ቅናሽም የ80 ሣንቲም ሲሆን በአሁኑ ሰዓት አንድ ሊትር ነዳጅ በ16 ብር 61 ሣንቲም እየተሸጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡
ከሠሞኑ መንግስት በነዳጅ የችርቻሮ ዋጋ ላይ ያደረገው የዋጋ ማስተካከያ የሸቀጦች ዋጋን እንደሚያረጋጋ የጠቆሙት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ በኢትዮጵያ ያለው የነዳጅ መሸጫ ዋጋም በአፍሪካ ዝቅተኛ የሚባል ነው ብለዋል፡፡  

በኦሮሚያ አካባቢዎች የተከሰተው ግጭት ሙሉ ለሙሉ አልቆመም
“በተወሰኑ አካባቢዎች ግርግር አጋጥሟል፤ ግን እየተረጋጋ ነው”
ከግብፅና ከሱዳን ጋር የሚደረገው ድርድር የግድቡን ህልውና የሚነካ አይደለም” (ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ)
          በአወዛጋቢው “ማስተር ፕላን”  መነሻነት ከሁለት ወራት በፊት በኦሮሚያ አካባቢዎች በተከሰተው ተቃውሞና ግጭት ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች የክልሉ መስተዳድር ካሳ ለመክፈል እንዳሰበ ተገለፀ፡፡
ግጭቱ ሙሉ ለሙሉ አለመቆሙ በየጊዜው ሲዘገብ የቆየ ሲሆን፤ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ፤ “ችግር ተፈጥሮባቸው በነበሩ አካባቢዎች መረጋጋት እየተፈጠረ ነው፤ ትምህርት ቤቶችም መደበኛ ተግባራቸውን እየቀጠሉ ነው” ብለዋል፡፡ በቅርቡ በቦረና ጉጂ አካባቢና በተወሰኑ መንደሮች ግን ግርግሮች አጋጥመዋል ብለዋል - ሚኒስትሩ ትናንት በሰጡት መግለጫ፡፡
ግጭቱን አባብሰዋል ተብለው የታሰሩ ሰዎች በህግ ይዳኛሉ ያሉት ሚኒስትሩ፤ ሳያውቁ የተሳተፉ ሰዎች ወደ ሰላማዊ ህይወታቸው ይመለሳሉ ብለዋል፡፡ በጎንደር አካባቢና በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች የተከሰተውን ግጭት አስመልክቶ ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ከቀረቡት የውሳኔ ሃሳቦች ላይም ሚኒስትሩ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ መንግስት ተቀብሎ ሊያጣራቸው የሚችሉ ሀሳቦች መኖራቸውን ሚኒስትሩ ጠቅሱው፤ በአጠቃላይ ግን ለአውሮፓ ፓርላማ ቀረበ ለተባለው የውሳኔ ሀሳብ መንግስት እምብዛም ትኩረት አይሰጠውም ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል የህዳሴ ግድብን በተመለከተ ከግብፅና ከሱዳን ጋር እየተደረገ ያለው ድርድር የግድቡን የወደፊት እጣ ፈንታ ለመወሰን የሚደረግ ድርድር አይደለም ብለዋል፡፡
ከግድቡ የጋራ ተጠቃሚ ለመሆንና በሁለቱ ሃገራት ላይ ጉዳት እንደማያደርስ በመወያየት የጋራ መግባባት ለመፍጠር ብቻ ያለመ ድርድር ነው ብለዋል -ሚኒስትር አቶ ጌታቸው፡፡

- “ኢትዮጵዊቷ የአሰሪዋን ልጅ ገድላ፣ ራሷን ለማጥፋት ሞክራለች”
- በኩዌት የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለጉዳዩ በቂ መረጃ የለንም ብለዋል

     በኩዌት አንዲት ኢትዮጵያዊ የቤት ሰራተኛ፤ የአሰሪዋን ልጅ ገድላ ራሷን ለማጥፋት ሞክራለች መባሉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ፓርላማ አባል የሆኑት ሳዶን ሃመድ አል ኦታቢ መንግስት በኩዌት በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ አፋጣኝ ጥብቅ እርምጃ እንዲወስድ ለአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የአገር ውስጥ ሚኒስትር ጥያቄ ማቅረባቸው ተዘገበ፡፡
በአገሪቱ በቤት ሰራተኝነት ተቀጥረው የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ከዚህ ቀደምም በአሰሪዎቻቸው ላይ አሰቃቂ ግድያ ፈጽመዋል ያሉት አል ኦታቢ፣ መንግስት በኢትዮጵውያን የቤት ሰራተኞች ላይ ወደ አገራቸው መመለስ፣ የስራ ቅጥር ውላቸውን የማቋረጥና የመኖሪያ ፈቃዳቸው እንዳይታደስ ማገድን የመሳሰሉ አፋጣኝ እርምጃዎችን መውሰድ ይገባዋል ማለታቸውን “አረብ ታይምስ” ትናንት ዘግቧል፡፡አንዲት ኢትዮጵያዊት የቤት ሰራተኛ የአሰሪዋን ልጅ በስለት ወግታ ከገደለች በኋላ ራሷን ወግታ ለመግደል ስትሞክር በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሏንና በአንድ ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እየተደረገላት እንደሚገኝ የዘገበው “ኩዌት ታይምስ”፣ ፖሊስ ጉዳዩን እያጣራ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡ በኩዌት የኢትዮጵያ አምባሳደር ሞሃመድ ጉደታ በበኩላቸው፣ ኤምባሲው ጉዳዩን በተመለከተ በቂና ይፋዊ መረጃ እንዳልደረሰው ጠቁመው፣ ጉዳዩን የሚከታተል ተወካይ ወደ ኩዌት አገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴርና ኢትዮጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ ወደምትታከምበት ሆስፒታል መላካቸውን እንደገለጹ ዘገባው አስረድቷል፡፡

ደንብ በሚተላለፉ አሽከርካሪዎች ላይ ከባድ ቅጣት ሊጣል ነው
       የደንብ ጥሰት በፈፀሙ አሽከርካሪዎች ላይ ከባድ ቅጣት የሚጥል አዲስ ህግ ሊተገበር ሲሆን በአሽከርካሪው ላይ ቅጣት ከመጣል በዘለለ በእያንዳንዱ ጥፋት ላይ በሚያዝ ነጥብ መሰረት፣ የመንጃ ፈቃድን ለስድስት ወራትና ለአንድ ዓመት ከማገድ አንስቶ ከእነአካቴው እስከ መሰረዝ የሚደርስ ነው፡፡
በክልሎች መንጃ ፈቃድ የማውጣት አሰራርም እንደሚቀርና ከአንድ ማዕከላዊ ሥፍራ ወጥ በሆነ መልኩ ብቃትን መሰረት አድርጐ መንጃ ፈቃድ የመስጠት አሰራር እንደሚጀመር ታውቋል፡፡የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመንገድ ትራፊክ ማኔጅመንት ኤጀንሲ፤ አዲሱ ህግ ተግባራዊ ስለሚደረግበት ሁኔታ ከሚዲያ ባለሙያዎች ጋር ለመወያየት ሰሞኑን አዘጋጅቶት በነበረው መድረክ ላይ የትራንስፖርት ባለስልጣን የመንገድ ትራፊክ ደህንነት፣ የግንዛቤ ትምህርት ዝግጅት ቡድን መሪ አቶ ድል አርጋቸው ለማ እንደተናገሩት፤ ህጉ በ2003 ዓ.ም በአዋጅ ደረጃ ቢወጣም በተለያዩ ምክንያቶች ተግባራዊ ሳይደረግ ቆይቷል፡፡ በቅርቡ ተግባራዊ መሆን ይጀምራል የተባለው ይኸው ህግ፤ ለአደጋ መንስኤ የሚሆኑ ተደጋጋሚ አጥፊዎችን ከመንገድ ለማስወጣት፣ በጥቂት ሥነ ምግባር የጐደላቸው አሽከርካሪዎች ምክንያት የሚጠፋውን ህይወት፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ለመከላከል፣ የአጥፊ አሽከርካሪዎችን ቁጥር ለመቀነስና ለህግና ደንብ የሚገዛ አሽከርካሪን ለማፍራት የሚያስችል ነው ብለዋል አቶ ድልአርጋቸው፡፡
በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ፎርጅድ መንጃ ፍቃዶች መሰራጨታቸው የተገለፀ ሲሆን ለዚህም ደግሞ ምክንያቱ የመንጃ ፍቃድ አሰጣጡ ወጥነት የጐደለው መሆኑ ነው ተብሏል፡፡ ይህንን ችግር ለማስወገድም ባለስልጣን መ/ቤቱ በአሻራ የተደገፈና በማዕከላዊነት ከአንድ ሥፍራ ላይ ብቻ የሚሰጥ አዲስ የመንጃ ፍቃድ አወጣጥ ተግባራዊ ለማድረግ ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀም ታውቋል፡፡ ይህ አሠራር የመንጃ ፍቃዶች በተለያዩ ክልሎችና ከተሞች የሚሰጡበትን ሁኔታ የሚያስቀር ሲሆን ወጥ የሆነ በአሽከርካሪው ብቃት ላይ ብቻ ተመስርቶ መንጃ ፍቃድን ለመስጠት የሚያስችል እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡
በአገሪቱ ባለፈው ዓመት ብቻ ከትራፊክ አደጋ ጋር በተያያዘ የ3847 ሰዎች ህይወት ያለፈ ሲሆን ከ11ሺህ በላይ ከባድና ቀላል የመቁሰል አደጋዎች እንደደረሱ የኤጀንሲው መረጃ ይጠቁማል፡፡

Saturday, 06 February 2016 11:34

ስምና ማንነት

 ከብዙ መነፋፈቅ በኋላ ካባቴ ታናሽ ወንድም፤ ካቶ አማረ በዳዳ ጋር ተገናኝተን አራት ኪሎ በሚገኘው ሮሚና ምግብ ቤት ምሳ በላን፡፡
አማረ ቢሏችሁ ቀላል ሰው እንዳይመስላችሁ፤ ከስድሳ ስድስት አብዮት ትንሽ ቀደም ብሎ በዩንቨርሲቲ ኮሌጅ በታሪክ ትምህርት ዘርፍ በዲግሪ ተመርቋል፡፡ በአብዮት ማግስት ዓመት በኢህአፓ አባልነት ተመልምሎ፣ በዚሁ ጦስ ተይዞ ዓለምበቃኝ አምስት ዓመት ታስሯል፡፡ እነ ማርታ ኩምሳ፣ ጌታቸው ኩምሳና ገነት ዘውዴ አብሮ ታሳሪዎቹ ነበሩ። ደራሲ ግርማይ አብርሃ በእሥር ቤት ማስታወሻው ላይ እንደጠቀሰው፤ አማረ በእሥር ቤት ቆይታው እሥረኞችን በነጻ የማስተማር አገልግሎት ከሚሰጡ ታራሚዎች አንዱ ነበር፡፡
እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የኢትዮጵያ ቤተሰብ መምርያ ያዲሳባ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ ሆኖ ሲሠራ ቆይቷል፡፡ አዲሳባ ዩኒቨርሲቲ በምማርበት ወቅት የሻይ መጠጫ የሚቆርጥልኝ አማረ ነበር፡፡
አባቴና አማረ ያንድ አባት ያንድ እናት ቢሆኑም በመልክና በእጣ ፈንታ የተለያዩ ነበሩ፡፡ አባቴ የቀይ ዳማ ሲሆን አማረ ክስል ያለ ጥቁር ነው፡፡ ወንድማማቾቹ የሚጋሩት አንድ ምልክት ቢኖር፣ ከጥቁር ጸጉራቸው ማኽል እንደባትሪ ቦግ ብሎ የሚታየው ሽበታቸው ነበር፡፡ ከአማረ በተቃራኒ አባቴ ለፖለቲካ ያለው ስሜት በጣም የቀዘቀዘ ነው፡፡ አማረ የቢሮ ሰው ሲሆን፣ አባቴ የተፈጥሮ ሰው ነው። ከትምህርት ቤት ውጭ ያለውን ጊዜውን ያሳለፈው ከልጆቹ የማያንስ ፍቅርና ጊዜ ለሚሰጣቸው የጓሮ አትክልቱ ነበር ማለት ይቻላል፡፡
በድህረ ምሳ ጨዋታ ላይ የዘመዳ-ዝማድ ጉዳይ ስናነሳ ስንጥል ቆይተን ልንሰነባት ስንል፣
“እስቲ ያባቴን የትውልድ ሐረግ ጻፍና ስጠኝ” አልኩት፡፡
“ምን አሳሰበህ” አለኝ በዋዛ፡፡
“እንዴት አያሳስበኝ፤ አባታዊነትን የሚያጋንን ማኅበረሰብ አባል ነኝ፡፡ አንድ ሰው ፍቅሩን ለመግለጽ “እንዲያው ምናባቴ ላርግህ” በሚልበት፤ ጠላቱ ክፉ እንደገጠመው ሲሰማ፣ “የታባቱ” ብሎ፣ በሚፈነጥዝበት ግራ ሲገባው፤ “ምናባቱ” እያለ በሚያጉተመትምበት ሀገር ውስጥ የምኖር ነኝ። አባት የነገሮች ሁሉ መስፈርያ ሆኖ የሚቀርብበት ማኅበረሰብ ውስጥ ስለአባቴ ማንነት ለማወቅ ብጥር ምን ይገርማል?”
በግርምት ለጥቂት ጊዜ አተኩሮ ሲያየኝ ከቆየ በኋላ ወደ መኪናው ውስጥ ይዞኝ ገባ፡፡ ከዚያ ከመኪና እረኛዋ (ከፓርኪንግ ሠራተኛዋ) እስክርቢቶ ተውሶ፣ በቢጫ ማስታወሻ ደብተሩ ውስጥ አንድ ቅጠል ገንጥሎ የሚከተለውን ጻፈልኝ፤
በዕውቀቱ ሥዩም - በዳዳ - ደስታ - ወየሳ
“ይሄው ነው?”
“እኔ የማውቀው እስከዚህ ድረስ ያለውን ነው፤ ሌላውን ደሞ የሁላችን ታላቅ የሆነችውን አበራሽን ጠይቃት”
ትንሽ አሰብ አድርጌ፤
“አባታችን አባቱ በዳዳ ተብሎ እንደሚጠራ ነፍስ ስናውቅ ጀምሮ ይነግረን ነበር፡፡ ግን በመሰለ ለምን እንደሚጠራ ጠይቀነው አናውቅም፡፡ ለምንድነው አባታችን በመሰለ የሚጠራው?  
አማረ ማብራራት ጀመረ፡፡
ምንጭ፡- (ከበዕውቀቱ ሥዩም
“ከአሜን ባሻገር”
አዲስ መፅሐፍ የተቀነጨበ፤ 2008 ዓ.ም)

Saturday, 06 February 2016 11:31

የኪነት ጥግ

(ስለ እግር ኳስ)
በእግር ኳስ ደስ የሚለው ነገር፣ ነገሮች በሰከንድ ውስጥ ሊቀየሩ ይችላሉ፡፡
ዲዲየር ድሮግባ
ከእግር ኳስ ውጭ ህይወቴ ከንቱ ነው፡፡
ክርስቲያኖ ሮናልዶ
ራሴን እንደ እግር ኳስ ተጫዋች ብቻ አልመለከትም፤ እንደ አዝናኝና ተምሳሌት እንጂ።
ካም ኒውተን
ለነገሩ እግር ኳስ ጨዋታ ነው ወይስ ሃይማኖት?
ጆሴ ሞሪኖ
የእግር ኳስ ቲፎዞ ነኝ፣ የስፖርት ቲፎዞ ነኝ፣ የውድድር ቲፎዞ ነኝ፡፡
ማቲው ማክኮናግሄይ
ብራዚል የምትበላው፣ የምትተኛውና የምትጠጣው እግር ኳስ ነው፡፡ የምትኖረው እግር ኳስን ነው!
ፔሌ
በህይወቴ የተማርኳቸውን የግብረ ገብነት እሴቶች የተማርኩት በእግር ኳስ ውስጥ ነው፡፡
አርሴን ቬንገር
እግር ኳስ ስህተት የመስራት ጨዋታ ነው፡፡ ጥቂት ስህተቶችን የሰራው ወገን ያሸንፋል፡፡
ጆሃን ክሩዩፍ
ዳንስ ጥበብ እንደሆነው ሁሉ የእግር ኳስም ጥበብ ነው - ነገር ግን በቅጡ ሲከናወን ብቻ ነው ጥበብ የሚሆነው፡፡
አርሴን ቬንገር
አንዳንድ ሰዎች እግር ኳስ የህይወትና የሞት ጉዳይ ይመስላቸዋል፡፡ እኔ ግን ከዚያም የጠነከረ መሆኑን አረጋግጥላችኋለሁ፡፡
ቢል ሻንክሊ
የመጀመሪያ ሴሚስተር ውጤቴ ሲወጣ እናትና አባቴ እግር ኳስ እንደማልጫወት ነገሩኝ፡፡
ጆ ቢዴን
እግር ኳስ ቅድመ ሁኔታ የሌለው ፍቅር ነው።
ቶም ብራዲ
ሚሊዬነር ለመሆን ፈፅሞ አልሜ አላውቅም - የእግር ኳስ ተጫዋች ለመሆን ነበር ያለምኩት፡፡
ቪክቶር ክሩዝ
መላ ህይወቴን እግር ኳስ ለመጫወት መስዋዕት አድርጌአለሁ፡፡
ብሪያን ቦስዎርዝ

 “ችግራቸው የቅርፅና የይዘት ነው”
(ደራሲ ኃይሉ ፀጋዬ)
የቴሌቪዥን ድራማዎች አልበዙም? መበራከታቸው በጥበቡ ላይ የሚያሳድረው አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖ ይኖራል?
 እኔ በግሌ የቲቪ ድራማዎች በዝተዋል ብዬ አላምንም፡፡ እዚህ ጎረቤት ኬንያ፣ በቀን 4 ተከታታይ ድራማ ይታያል፡፡ በMBC 2 አረብ ሳት፣ ቀንና ሌሊት ፊልም ነው የሚታየው፡፡ በሳምንት አንድ ድራማ ብቻ ይታይ ከነበረበት ጊዜ አንጻር ካየነው ጥሩ ነው፡፡ አዎንታዊ ጎኑ  በዋናነት፣ሰዎች አማራጭ የሚያዩት ነገር እንዲኖራቸው ማድረጉ ነው፡፡ አንድ ድራማ ብቻ በነበረ ወቅት ምርጫ የለም፤ መጥፎም ሆነ ጥሩ ያንኑ ማየት ብቻ ነው፡፡ ሌላው ለተከታታይ ድራማ እድገት በጎ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ እንግዲህ ብዛት ይቀድማል፤ጥራት የሚመጣው ዘግይቶ ነው፡፡ አሉታዊ ጎኑ ብዙ ሲሆኑ ተመሳሳይነትና ተደጋጋሚነት ይኖራቸዋል፤ በዚህም ተመልካቹን የማሰልቸት ነገር ሊፈጠር ይችላል፡፡  
የቲቪ ድራማዎች አጠቃላይ ይዘታቸው ምን ይመስላል?
እንግዲህ እንደነገርኩሽ በዙ ሲባል ያስቀኛል፡፡ የሚታየው ነገር ጥራት ቢኖረው እኮ ችግር የለውም፡፡ አሁን ትልቁ ችግር የቅርፅና የይዘት ነው፡፡ በድራማዎቹ ምንድን ነው እየተላለፈ ያለው መልእክት? ጥልቀትና ብስለት አለው ወይ? ግልብ ነገር መስራት የትም አያደርስም፡፡ እና በይዘትም በቅርፅም ገና ብዙ ይቀረናል፡፡ በእርግጥ አንዳንድ  የተሻሉ ስራዎች ይኖራሉ፡፡  
በድራማዎቹ መካከል --- ተወዳጅ ለመሆን እርስ በርስ የመፎካከር ነገር ይታያል?
 ገና አልተጀመረም፤ፉክክር የሚጀምረው ጥራት ሲመጣ ነው፡፡ ምናልባትም በቀጣዮቹ አምስትና አስር ዓመታት አሪፍ ስራዎችን ልናይ እንችላለን፡፡ ጥሩ የድራማ አፃፃፍና ምርጥ ፕሮዳክሽኖች ይመጣሉ፡፡   
አንዳንድ ድራማዎች በስፖንሰርሺፕ ገንዘብ ለማግኘት ብቻ ታልመው ስለሚሰሩ ደረጃቸው የወረደ ነው የሚሉ ትችቶች ይሰነዘራሉ፡፡ አንተ ምን ትላለህ? …
በአሁን ሰዓት የቴሌቪዥን ድራማ ገንዘብ ያስገኛል የሚል አስተሳሰብ ያላቸው ፕሮዲዩሰሮች ተበራክተዋል። ያለአቅማቸው የማይችሉትን እየጎረሱ ነው፡፡ ለገንዘብ መስራት ሃጢያት አይደለም፡፡ ግን ብቃት ያስፈልጋል። ገንዘብ ላይ ያተኮረ፣ ስምና ዝናን ያማከለ ስራ እየተሰራ ነው ያለው፡፡ ብቃት የሌላቸው ዳይሬክተሮችና ፕሮዱዩሰሮች ይገጥሙሻል፡፡ እነዚህ ጥራት እያደገ ሲመጣ ከጨዋታ ውጭ ይሆናሉ፡፡
“አንዳንድ የቲቪ ድራማዎች አይመጥኑም”
(ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ)
የቴሌቪዥን ድራማዎች አልበዙም? መበራከታቸው በጥበቡ ላይ የሚያሳድረው አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖ ይኖራል?
አዎንታዊ ጎኑ ሁልጊዜ ከብዛት ጥራት ይገኛል፡፡ ሰዎች ከጥንካሬ ብቻ ሳይሆን ከድክመትም ይማራሉ፡፡ ብዙ ጠንካሮች እድል ባላገኙበት ሁኔታ ከሆነ ነው አስቸጋሪ የሚሆነው፡፡ የቴሌቪዥን ድራማ ገና ብዙ ሊሰራበት የሚገባ ዘርፍ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ለልጆችና አዋቂዎች ተመሳሳይ ነገር ነው የሚቀርብላቸው፡፡ ለሁሉም አንድ ነው፡፡ እንደዚህ ያልጠራና ሁሉን ያላማከለ፣---- አቅጣጫ የሌለው ሲሆን ብዥታ ይፈጥራል፡፡
የቲቪ ድራማዎች አጠቃላይ ይዘታቸው ምን ይመስላል?
ምናልባት የኢቢሲ ኤዲቶሪያል ፖሊሲን መሰረት ተደርጎ ስለሚሰራ ይሆናል፡፡ የቲቪ ድራማዎች ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና መሰል ጉዳዮችን እንዲፈትሹ ይፈለጋል፡፡ ነገር ግን  በሳይኮሎጂ ህብረተሰቡን የማከምና ፆታዊ፣ማህበራዊና ሌሎች ጉዳዮችን መዳሰስ ይቻላል።  አንዳንዴ በድራማዎች መካከል መመሳሰል ሊከሰት ይችላል፡፡ ሆኖም አተያያቸውና የትኩረት አቅጣጫቸውም ሊመሳሰል አይችልም፡፡ አንዳንድ ችግሮች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ድራማዎች ብቃታቸው ታይቶ ነው አየር ላይ የሚቀርቡት? የሚያሰኙ ናቸው፡፡ በተለይ የተወሰኑት በህዝብ አይን፣ ጊዜ፣ አእምሮና ባህል ላይ እንደ መቀለድ የሚቆጠሩ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ በጭራሽ ለቲቪ ድራማ የማይመጥን ሥራ እያየን ነው፡፡ ምስሉ ያብረቀረቀ ሁሉ ያምራል ማለት አይደለም፡፡ አሁን በሚሄድበት ሃዲድ ምን ያህል ይጓዛል የሚለው ያጠያይቃል፡፡
ከብዛታቸው አንፃር የቲቪ ድራማዎች ያለባቸው ተግዳሮት ምንድን ነው?
ሰው ለምሳሌ እያየሁ ያለሁት “መለከት” ነው “ዋዜማ” ሊል ይችላል፡፡ ሎጎውን እስኪመለከት ድረስ ኢቢኤስ ነው ኢቢሲ በሚል መደነጋገርም ይፈጠራል፡፡ ይህን የሚያመጣው የገፀ ባህሪያት መመሳሰል ነው፡፡ ደግነቱ የኛ ተመልካች ቶሎ የሚሰለች አይደለም፡፡ በጊዜ ሂደት ግን አዲስ ነገር መፈለጉ አይቀርም፤ካላገኘ የተሰራውን ባለመመልከት፣ በመዝጋት መቅጣት ይጀምራል። አማራጮች ሲያገኝ ወደ ማወዳደር ይገባል፡፡ ሰው እስኪሰለች ድረስ መጠበቅ ግን አይገባም፡፡ ድራማዎችና በጥራትና በሚመጥን መልኩ መስራት አለባቸው፡፡
አንዳንድ ድራማዎች በስፖንሰርሺፕ ገንዘብ ለማግኘት ብቻ ታልመው ስለሚሰሩ ደረጃቸው የወረደ ነው የሚሉ ትችቶች ይሰነዘራሉ፡፡ አንተ ምን ትላለህ? …
የፊልሙ አካሄድ ወደ ቲቪ ድራማም እየመጣ ነው። ሰዎች ከፍለው ማፃፍ እየጀመሩ ነው፡፡ መኪናቸውን ሸጠው ወደዚህ ሥራ የሚገቡ አሉ፡፡ ታዲያ የተፃፈ ሁሉ ይታያል ማለት አይደለም፡፡ ገምጋሚው አካል ደረጃቸውን በጥራት ፈትሾ ማሳለፍ አለበት፡፡ ጥሩ ድራማ ከቀረበ እኮ የግዜ ጉዳይ ካልሆነ በቀር ነጋዴው በሰልፍ ይመጣል፡፡
አሁን ባለው ሁኔታ ከቀጠለ ግን ትውልዱ ለአደጋ ይጋለጣል፡፡ ልጆቻችን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አገራዊ ጉዳዮችን ለነሱ በሚመጥን መንገድ ተሰርቶ ማየት ካልቻሉ ልንለያይ ነው፡፡ እኔና ልጆቼ በጋራ ተቀምጠን የምናየው ፕሮግራም መሰራት አለበት፡፡ አሁን የእኔ ልጅ ሳይማር አረብኛ ይናገራል፡፡ በአገሩ ቴሌቪዥን ቋንቋና ባህሉን ማሳደግ ሲገባው፣ የአረብ ቻናል በማየት አረብኛ ችሏል፡፡ ስለዚህ ሁሉንም የሚመጥኑና ሁሉንም ያማከሉ፣ የጠሩ ስራዎች ሊቀርቡ ይገባል፡፡   
“ድራማ ለፅድቅ ልስራው የምትይው አይደለም;
(የፊልም ዳይሬክተር፤ ተስፋዬ ማሞ)
የቴሌቪዥን ድራማዎች አልበዙም? መበራከታቸው በጥበቡ ላይ የሚያሳድረው አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖ ይኖራል?
መብዛታቸው አዎንታዊ እንጂ አሉታዊ ተፅእኖ የለውም፡፡ መብዛት ችግር የለውም፡፡ ዋናው የበዙት ምን አይነቶቹ ናቸው የሚለው ነው፡፡ በተረፈ ብዙ መሆናቸው ውድድርና የእርስ በርስ ፉክክርን ያበረታታል፡፡
የቲቪ ድራማዎች አጠቃላይ ይዘታቸው ምን ይመስላል?
 የተጠና ነገር ሳይኖር በጅምላ መፈረጅ ይከብዳል። ግን የሚያስገርመው---- ስንት ዓመት ድራማ ስንሰራ ኖረን፣ገና ጀማሪ ስለሆንን፣ ሁሉም ይሞክር አይነት እየተባለ ነው፡፡ ይሄ “ጀማሪ ነኝ፣ ጀማሪ ነኝ” መቼ እንደሚቆም እግዜር ይወቀው፡፡ ብዙ ጊዜ ከድራማው ይልቅ ዝነኛ ሰዎችን፣ ታዋቂ ፊቶችን ---- ለማካተት ነው ትኩረት የሚሰጠው፡፡
ከብዛታቸው አንፃር የቲቪ ድራማዎች ያለባቸው ተግዳሮት ምንድን ነው?
ለምሳሌ በኢቢሲ እሁድ የመዝናኛ ፕሮግራም ላይ ሁለት ድራማ አይጠፋም፡፡ ድራማ ሲባል ለምን ረቡዕና እሁድ ብቻ እንደሚታሰብ አይገባኝም፡፡ በሌሎች ቀናት ለምን አይበተንም፡፡ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት ሲሆን ተመልካች ሳይወድ በግድ አንዱን ብቻ መርጦ እንዲመለከት ያደርገዋል፡፡ ወደፊት ቻናል እየበዛ ሲመጣ ደግሞ ውድድሩ በነሱ መካከል ይሆናል፡፡ ያኔ እኛም የተሻለ ነገር እናያለን፡፡
አንዳንድ ድራማዎች በስፖንሰርሺፕ ገንዘብ ለማግኘት ብቻ ታልመው ስለሚሰሩ ደረጃቸው የወረደ ነው የሚሉ ትችቶች ይሰነዘራሉ፡፡ አንተ ምን ትላለህ? …
 እንደሱ ብሎ መነሳት ይከብዳል፡፡ ለምሳሌ ገመናን ብናይ፣ገንዘብ የመሰብሰብ ሳይሆን በሙያ የማትረፍ አላማ ነበረው፡፡ ሰው ለሰውም እሱን ተከትሎ ስለመጣ፣ ከገመና የተሻለ ነገር ለማቅረብ በውድድር ስሜት በመሰራቱ፣ ጥሩ ነገር ለማየት ችለናል፡፡ አሁን አሁን  ሲጀመር ጥሩ ይሆንና በኋላ ጥድፊያ! በእርግጥ ድራማ ከፍተኛ ወጪ ያለው ስራ ነው፡፡ ለፅድቅ ልስራው የምትይው አይደለም፡፡ ግን እንደ ፊልሙ እየሆነ መጥቷል፤ ገንዘብ ስላለ ብቻ የሚገባበት፡፡
ገንዘብ ይዞ መምጣቱ ባልከፋ፤ግን የወጣውን ገንዘብ  ለመመለስ ሥራው ተወዳጅ መሆን አለበት፤ ያለበለዚያ ባለገንዘቡም ተመልካቹም አያተርፉበትም፡፡ እናም በተቻለ አቅም በባለሙያዎችና በጥራት መስራት ያስፈልጋል፡፡
*   *   *
“አማራጭ ከሌለሽ ያለውን ታያለሽ;
 “መብዛታቸው ጥሩ ነው ብዬ ነው የማስበው!አሁን አማራጭ ስላለ የምትፈልጊውን ታያለሽ፡፡ `ለምሳሌ ”በቀደሙት ሳእታት ኢቲቪ ላይ Up”ßእሮብና እሁድ ነው ያለው፡፡ አማራጭ ከሌለሽ ያለውን ጠብቀሽ ታያለሽ፡፡ አሁን ላይ በእኩል ሰዓት ለምሳሌ እሮብን ብታይ ኢቢኤስ ላይም አለ፣ ኢቢሲ ላይም አለ፡፡ የመረጥሽውን መከታተል ትችያለሽ፡፡;
(ወጣት ቤተል:ሔም ባህሩ)
“የሚንዛዙ ድራማዎች አሉ”
 “መብዛታቸው መልካም ቢሆንም እየተንዛዙ ያሉ ድራማዎች ደግሞ አሉ፡፡ ለምሳሉ አንድ ሂደት ለማሳየት ረጅም ሰዓት የመውሰድ ነገር አለ፡፡ ያ ደግሞ ጥራቱን ያጓድላል ብዬ አምናለሁ፡፡ ለተመልካችም ያሰለቻል። ሌላው ለምሳሌ ኢቢኤስና ኢቢሲ በተመሳሳይ ሰዓት ድራማ ያሳያሉ፡፡ ይሄ ለማንም ጥሩ አይደለም፤ተናበው ቢሰሩ ይመረጣል”
 (አካሉ ጴጥሮስ)
“መብዛታቸው ምርጫ ሰጥቶኛል”
“የተለያዩ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች ተከፍተዋል፡፡ ይህ ጥሩ ነው፡፡ በነሱ አማካኝነትም በርካታ ድራማዎች ይታያሉ፡፡
ምን ያህል ጥሩ ናቸው፣ አይደሉም የሚለውን ሙያዊ ትንታኔ ለመስጠት ይከብደኛል፡፡ ባለኝ እውቀትና እይታ ግን አብዛኞቹ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ትኩረታቸው ፍቅር ላይ ነው፤ መጨረሻቸውም ፍቅር ነው፡፡ ልክ ፊልም ላይ እንደምናየው /አሁን የተወሰኑ መሻሻሎች ቢኖሩም/ ሁሉም ፍቅር ላይ ነው፡፡ ሌሎች በፊልም፣ በድራማ፣ ትልቅ ደረጃ ላይ የደረሱ አገሮችን ሥራዎች ቨማየት፣ የአገራችንን የድራማ፣ ፊልምና ቲያትር እድገት ራሳችን ማሻሻል መቀየር እንችላለን፡፡ ተመሳሳይ ናቸው፤- የፍቅር ታሪኩ አመጣጡና ድንበሩ ይለያይ እንጂ ከመፋቀር አይዘልም፡፡ መሻሻል አለበት እላለሁ፡፡ ሆኖም መብዛታቸው ምርጫ ሰጥቶኛል፤ በምመርጠው ቴሌቪዝን የፈለግሁትን ለማየት ችያለሁ”
(ሄለን አይችሉም)  
“እኔ መብዛታቸው ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ድሮ ትዝ የሚለኝ ፣ድራማ ሲኖር ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ˜አንድ ብቻ ስለሆነ፤ ማታ እኮ እንትን ይታያል እል ነበር፡፡ አሁን ግን የመረጥኩትን ማየት አያለሁ፡፡”
(ትእግስት ወገኔ)

የታዋቂው ገጣሚና ደራሲ በእውቀቱ ስዩም “ከአሜን ባሻገር” የተሰኘ አዲስ መፅሃፍ የመጀመሪያው 20ሺ ቅጂ በግማሽ ቀን ውስጥ ተሸጦ ማለቁን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡
ባለፈው ሰኞ ጠዋት ገበያ ላይ የዋለው መፅሀፉ፤ ከሰዓት በኋላ ተሸጦ እንዳለቀ ታውቋል፡፡ ሁለተኛው ህትመት ከአስር ቀናት በኋላ በድጋሚ በገበያ ላይ ይውላል ተብሏል፡፡
የአንድ መፅሃፍ መደብር ባለቤት ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ “እስከዛሬ ከሸጥኳቸው መፃህፍት በአንድ ቀን ያለቀ አልገጠመኝም፡፡ ይሄ የመጀመሪያው ነው፡፡” ብሏል፡፡
ሌላው ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ የመፅሃፍ አከፋፋይ በበኩሉ፤ “ብዙ የመፃህፍት ሽያጭ እንቅስቃሴ በሌለበት በዚህ ወቅት በአጭር ጊዜ ተሸጦ ያለቀው “ከአሜን ባሻገር” የመፃህፍትን ገበያ አነቃቅቷል፡፡ እስካሁን ታትሞ በወጣ በግማሽ ቀን ውስጥ ተሸጦ ያለቀ መፅሃፍ አላየሁም፡፡ በህዝቡ ውስጥ የተለየ ስሜት የፈጠረና ሁሉም ነጋዴ የያዘው መፅሃፍ ነው፡፡” ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል። ሌሎች መፃህፍት የራሳቸው አንባቢ አላቸው፤ ይሄኛው ግን ወጣት አዛውንት ሳይል በሁሉም የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎች የጠየቁትና የገዙት መፅሃፍ ነው፡፡” ሲልም አክሏል አከፋፋዩ፡፡
“ይህች መጽሐፍ ጉዞ ቀመስ፣ ፖለቲካ ቀመስና ታሪክ ቀመስ መጣጥፎችን ይዛለች” በሚል ደራሲው በመግቢያው የገለፀው ይኸው መጽሐፍ፤ በ70 ብር ነው ለገበያ የቀረበው፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ በዕውቀቱ ስዩም በአሜሪካ ሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን በመከታተል ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡