Administrator

Administrator

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሌባ በአንድ መለስተኛ ሆቴል አንድ ክፍል ለመኝታው ይከራያል፡፡ እዚህ መኝታ ክፍል ብዙ ቀናት በመቆየት የሚሰርቀው ነገር ሲፈልግ ቆየ፡፡ ዕድሉ አልተገኘለትም፡፡ አንድ ቀን ግን አንድ አጋጣሚ ተከሰተ፡፡ አንድ ድል ያለ ድግስ ተደግሷል፡፡ የሆቴሉ ባለቤት አንድ ምርጥ ውድ ኮት ለብሷል፡፡ እግሩን አንፈራጦ በሩ አካባቢ ተቀምጧል፡፡ ሌባው ያንን ኮት የመስረቅ ስሜቱ ወዲያውኑ ተነሳሳ፡፡ ሌላ የሚሠራው ነገር ስለሌለው ቀጥ ብሎ መጥቶ የሆቴሉ ጌታ ጐን ተቀመጠና በወሬ ጠመደው፡፡ ለተወሰነ ጊዜ ሲያወጉ ቆዩ፡፡ በመካከል ሌባው ወሬውን ትቶ እንደ ተኩላ አዛጋና መጮህ ጀመረ፡፡
የሆቴሉ ጌታ ደንግጦ፤
“ምነው አመመህ እንዴ?”
ሌባውም፤
“ጌታዬ የዚህን ሚስጥር እነግርሃለሁ፡፡ ሆኖም ያንን ላንተ ከመንገሬ በፊት አንድ ነገር ቃል ግባልኝ፡፡ እኔ ስሄድ ልብሴን እንድትጠብቅልኝ እፈልጋለሁ፡፡ ላንተ እተወዋለሁ ልብሴን፤ ምክንያቱም ራቅ ብዬ መሄዴ ስለሆነ ነው”
ጌታው፤
“የዚህ የማዛጋትህ ሚስጥር ግን ምንድነው?”
ሌባውም፤ “ጌታዬ፤ ምናልባት ከላይ እንደ እርግማን ተልኮብኝ ይሆን ይሆናል፡፡ ብቻ ዞሮ ዞሮ፤ ሰበቡ ምንም ይሁን ምን፣ ሦስት ጊዜ አዛግቼ ከጮህኩ ወደ ቁጡ ተኩላነት እለወጥና የሰው ጉሮሮ ማነቅ ነው ቀጥሎ፡፡”
ሌባው ንግግሩን እንዳበቃ ለሁለተኛ ጊዜ አዛጋ፣ አንፋሸከ፡፡ ይሄኔ የውቴሉ ጌታ ሌባው ያለውን እያንዳንዱን ቃል በማመንና በተኩላ የመበላት ነገር እየሰቀቀው፣ በጥድፊያ ተነስቶ ወደ ጓዳ መሮጥ ጀመረ፡፡ ሌባው ግን የጌታውን ኮት ከኋላ ጨምድዶ ያዘውና እየጮኸ፤
“ጌታዬ ጌታዬ፤ እባክዎ ልብሶቼን ይጠብቁልኝ፡፡ አለዚያ ይጠፉብኛል” አለና ለሶስተኛ ጊዜ ማዛጋቱን ቀጠለ፡፡ ጌትዬው ለሦስተኛ ጊዜ ሌባው ካዛጋ አይለቀኝም፣ መበላቴ ነው፤ ብሎ በፍርሃት ተጥለቅልቆ ኮቱን አውልቆ ለሌባው ትቶ መጭ አለ፡፡ ጓዳ ገብቶም በሩን ከርችሞ ቁጭ አለ፡፡
ሌባው እጁ ላይ ታላቁ ኮቱ ቀርቶለታል፡፡ አጅሬ ሌባ፤ ያን ውድ ኮት ተሸክሞ በኩራት እየሳቀ ከሆቴሉ ወጥቶ ሄደ!
*   *   *
ሌብነት የተሰራቂውን አስተሳሰብ ይፈልጋል፡፡ ተሰራቂው ሲፈራ፣ ሰራቂው ልብ ያገኛል፡፡ በቁማችን ኮታችንን ከሚገፍ ጃውሳ ይሰውረን፡፡ ሰው እንደ አውሬ ጮሆ ከሚያስፈራራን ጊዜ ያውጣን፡፡ የሰውን ማንነት እያወቅን ተኩላ ነኝ ሲለን ወደ ማመንና ወደ መፍራት ከተሸጋገርን ሁኔታው አደገኛ ነው ማለት ነው፡፡ በየራሳችን ንፅህና መተማመን፣ በየራሳችን ጥንካሬ መጽናት ያስፈልገናል፡፡ ራዕያችን መገደብ የለበትም፡፡ ይሄን ይሄን ግብ እንመታለን ብለን ስናበቃ፤ ቀጥሎስ ወዴት እንደርሳለን ማለት አለብን፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የማይቆም የማይገታ ራዕይ ምንጊዜም ወሳኝ መሆኑን አንዘንጋ፡፡
ዱሮ ከማንነት የሚመነጭ ክብር ነበረን፡፡ መልካም ስም ያኮራን ነበር፡፡ ስማችንን ከምንም ነገር በላይ እንጠብቀው፣ ቦታ እንሰጠው ነበር፡፡ ሼክስፒር በኦቴሎ ውስጥ በሎሬት ፀጋዬ አንደበት እንዲህ ብሎ ነበር፡-
“ገንዘቤን የወሰደ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር
 ዋጋ አለው ግን ከንቱም ነው፣
የእኔም የእሱም የዛም ነበር
ግና ስሜን የሰረቀኝ
የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልጽ አደኸየኝ”
ይሄ ትላንትና ነበር፡፡ ዛሬ የስም ጉዳይ ሳይሆን ፈተናው የገንዘብ፣ የንብረት፣ የቤት፣ የመሬት ብቻ ሆኗል!! ከህዝብ ቆጠራ ወደ ቤት ቆጠራ መሸጋገራችን የዚህ ውጤት ነው፡፡ ቤት የሚቆጠረው ትርፍ ቤቶች ያሏቸውን ሰዎች ኢ-ህጋዊ መንገዶችን ለማጠር ነው፤ ይላሉ፡፡ ከዚያ የከፋ ነገር ሳይኖር አይቀርም፡፡ ባለሥልጣኑ ለእገሌ ስጡ ያላቸው ቤቶች የቶቹ እንደሆኑ አይታወቁም፡፡ በር እየሰበረ፣ ቤት እየመዘበረ የገባው ጉልቤ ብዙ ነው፡፡ ደላላ “ባለቤት የለውም” እያለ የቸበቸበውም አይጠፋም፡፡ ይሄን ፈተና ለመወጣት መንግሥት አያሌ ቆጣሪዎችን መድቦ ማሰራቱ የሚያስመሰግን ቢሆንም፤ ቆጣሪዎቹም ሙስና ውስጥ ቢገቡ የሚደርሰውን ጥፋት ከወዲሁ ማጤን ተገቢ ይሆናል፡፡ ልክ “የትራፊክ አዲሱ ህግ ትራፊኩን ያበለፅገዋል” እያለ ህዝቡ እንደሚያማ ግንዛቤ ወስደን መጠንቀቅ አስፈላጊ ነው እንደሚባለው ማለት ነው፡፡ ሲጀመር የሚሰጥ አደራ ሲጨረስ ከሚሰጥ ትችት የተሻለ ነው በሚል ነው ከወዲሁ መናገራችን ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፣ ጧት ታቅደው ማታ ስለሚሞቱ ዕቅዶችና ሀሳቦች አንዳንድ ፍልስፍናዊ አባባሎችን አኑሯል፡፡ እነሆ
“አሁን እንደጥሬ ፍሬ፣ ሃሳብሽ ግንዱ ላይ ታዝሏል
ነገር ግን በስሎ ሲሟዥቅ፣ ማንም ሳይነካው ይወድቃል”
ራዕያችን በጥሬው ሲቀመጥና ሲበስል ልዩ ባህሪ አለው፡፡ በጥሬው እምንፈክርለት ሃሳብ፣ ሲበስል ምን እንደሚመስል ማስተዋል መሠረታዊ ሃላፊነታችን ነው፡፡ ያደገ የተመነደገ ሃሳብ የራሱ ምስል አለው፡፡ የራሱን አስተውሎት ይሻል፡፡
የአካባቢ ቀውስ፣ የተጠራቀመ ምሬት ውጤት መሆኑን አለማስተዋል ደካማነት ነው፡፡ የህዝብ እንቅስቃሴ፣ ወይም ሁከት እንደው በዘልማድ የረብሻ ሱስ ውጤት ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ፈርጀ ብዙ ጉዳዮች፣ ብሶቶች ጥርቅም ውጤት ሊሆን እንደሚችል በማጤን “የመልካም አስተዳደር ጉድለት” ብቻ ምክንያት ብሎ ማሰብ የራሱ ችግር ሊኖረው የሚችለውን ያህል፤ የሌሎች እጅ አለበት ብሎ መደምደምም የራሱን ጥንቃቄ ይሻላል፡፡ ህዝቡን ከልብ የማሳተፍ ባህል እንጂ ዘመቻ አይደለም መፍትሔው፤ ዘመቻ ጊዜያዊ ነው፡፡ ባህል ዘላቂ ነው!  የሌሎች እጅ አለበት ስንል ህዝብ ያላሰባቸውን በርካታ ባዕድ እጆች በማሰብ እንዳይውዥበረበር መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ሌላው ህዝብ የሚለውን ከመመሪያ ጋር ለማጣጣም በሚልም ሀቅ እንዳይጣመም ለማድረግ መጣር ሌላው ተገቢ አካሄድ ነው፡፡
ባንድ አንፃር ሁኔታዎች እየደፈረሱ መላ እንዳያጡ መታገል፤ ሥርወ አመጣጣቸውን መፈተሽ፣ መፍትሔአቸውን መሻት፣ አንዱ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ በሌላ አንፃር ወደ ታላቅ የአገር ፋይዳ የሚሸጋገሩ አገራዊ ዕቅዶችን ከሚያነቅፉ የኢ-ፍትሕ፣ የሙስና የኢ-ዲሞክራሲና የኢ-መልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ጋር መጋፈጥ የሀገራችን ነባራዊ- ዕውነታዎች ሆነዋል፡፡ ይህ ማለት አንዳች አጣብቂኝ ነው - በሁለት ጐሽ ማህል የተደበቀ በሬ መሆን! ከዚህ እንወጣ ዘንደ ቆፍጣና መላ ይስጠን! እንደጥርስ ህመም ማታ ማታ የሚያመንን በሽታ ቀን ማዳመጥ እንድንችል ልብ ይስጠን!”

የኦፌኮ ሊቀመንበር ዶ/ር መረራ ጉዲና በኦሮሚያ በተከሰተው ግጭት፣መንግስት ሰሞኑን በሰጠው መግለጫና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ተከታዩን አጭር የስልክ ቃለ-ምልልስ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ
አለማየሁ አንበሴ ጋር አድርገዋል፡፡

ቢሮአችሁ ሰሞኑን በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር ውሎ እንደነበር በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ተነግሯል -----
አዎ፡፡
ምን ነበር የተፈጠረው?
በቃ በእለቱ ሰው መግባትና መውጣት አይችልም ነበር ያሉን፡፡
ቢሮአችሁ ፍተሻ ተካሂዶበታል?
አልተካሄደም፡፡
የታሰረ ሰው አለ?
የለም፡፡
መቼ ነበር ይህ የሆነው?  
እሁድ፡፡
ከእሁድ በኋላስ ቢሮ መግባት ቻላችሁ ?
አዎ፡፡
በኦሮሚያ የተፈጠረውን ግጭትና የመንግስትን እርምጃ እንዴት ገመገማችሁት?
የህዝቡ እንቅስቃሴ አሁንም ቀጥሏል። መንግስትም እርምጃ መውሰዱን ቀጥሏል፡፡ እኛ ደግሞ ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ እየጠየቅን ነው፡፡ ይሄ ነው ያለው ነገር፡፡
ፓርቲያችሁ ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ ጥያቄ ያቀርባል?
አዎ! በፊትም ስናቀርብ ነበር፤አሁንም ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ በውይይት እንዲፈታ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
መንግስት በኦሮሞ ህዝብ ስም የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች በተከሰተው ግጭት ውስጥ እጃቸው እንዳለበት እየገለጸ ነው፡፡ ቀደም ሲል የእናንተ አባላትና አመራሮችም ታስረዋል፡፡ በተቃውሞው የኦፌኮ ሚና ምን ያህል ነው?
ህዝቡ ማንም ሳይቀሰቅሰው ከዳር እስከ ዳር ለመብቱ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ በአንድ ፓርቲ ቅስቀሳ ብቻ አይነሳም፡፡ የህዝቡን ብሶት ራሱ ኦህዴድም ያውቀዋል እኮ፤እኛ የተለየ ነገር የለንም፡፡
መንግስት ችግሮቹን እንዴት መፍታት አለበት ይላሉ?
ኢህአዴግ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ቁጭ ብሎ መነጋገር አለበት፡፡
እንዴት ነው ህዝቡን ማረጋጋት የሚቻለው፣ ምን አይነት የፖለቲካ ድርድር መደረግ አለበት --- በሚሉት ዙሪያ መወያየት ያስፈልጋል፡፡ አሁን ብሄራዊ መግባባት፣ ብሄራዊ እርቀ ሰላም መፈጠር አለበት፤ ነገር ግን ኢህአዴግ በዚህ መንገድ እየሄደ አይደለም፡፡
ከሰሞኑ ግጭት ጋር በተያያዘ የታሰሩባችሁ አባላት አሉ?
እስርማ ሁሌም አለ፡፡ እስሩ አሁንም ቀጥሏል፡፡

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል

   የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩንና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍሊፕ ሃሞንድ በእንግሊዝና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት የበለጠ በማሳደግ ላይ ትኩረት ያደረገ ጉብኝት ለማድረግ በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ ከትናንት በስቲያ በድረ-ገጹ አስታወቀ፡፡ባለስልጣናቱ ኢትዮጵያን የመጎብኘት እቅድ እንዳላቸው ያስታወቁት፣ ባለፈው ረቡዕ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ የመከሩት የእንግሊዝ የአገር ውስጥ ጉዳይ ቢሮ ሁለተኛ ቋሚ ጸሃፊ ኦሊቨር ሮቢንስ መሆናቸውን ቢገልጽም፣ ጉብኝቱ የሚከናወንበትን ጊዜ በተመለከተ ግን ያለው ነገር የለም፡፡ ሁለቱ የእንግሊዝ ባለስልጣናት በኢትዮጵያ በእስር ላይ የሚገኙትና እንግሊዛዊ ዜግነት ያላቸው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱና በቆንስላ ተወካዮች የሚጎበኙበት ሁኔታ እንዲመቻች የሚጠይቅ ደብዳቤ ለኢትዮጵያ መንግስት በተደጋጋሚ ቢልኩም መንግስት ግን ይህ ነው የሚባል ምላሽ አለመስጠቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ጉብኝቱ ዴቪድ ካሜሩን በጠቅላይ ሚኒስትርነት ስልጣን ላይ ከወጡ ወዲህ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡበት የመጀመሪያው ጉብኝት ይሆናል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ የቀድሞው የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር እ.ኤ.አ በ2004 ኢትዮጵያን ጎብኝተው እንደነበር ይታወሳል፡፡

    ሪንጊንግ ቤልስ የተባለው የህንድ የሞባይል ቀፎዎች አምራች ኩባንያ፣ በዓለማችን የስማርት ፎን ገበያ እጅግ ርካሽ ዋጋ የተተመነለትን ፍሪደም 251 የተባለ አዲስ የሞባይል ቀፎ ምርቱን በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ለገበያ እንደሚያቀርብ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡ከጥቂት ወራት በፊት የተቋቋመው ኩባንያው፣ለዚህ የሞባይል ቀፎ 7.3 ዶላር የመሸጫ ዋጋ የተመነለት ሲሆን የሞባይል ቀፎው 8 ጊጋ ባይት ሚሞሪ ያለውና በፊቱና በኋላው ሁለት ካሜራዎች የተገጠሙለት ነው ተብሏል፡፡ ኩባንያው በቅርቡም በአገሪቱ የ4ጂ የሞባይል ቀፎ ገበያ እጅግ እርካሹ ዋጋ የተተመነለትን ምርቱን ለገበያ ማብቃቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ አዲሱን የሞባይል ቀፎውን የመገጣጠም ስራውን እንደጀመረና ምርቱን በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ለአገር ውስጥ ገበያ ያቀርባል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድቷል፡፡
ህንድ በአለማችን የሞባይል ቀፎ ገበያ ሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ በአገሪቱ አንድ ቢሊዮን ያህል የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች እንዳሉም ገልጧል፡፡

   በምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገራት የሚገኙ 1 ሚሊዮን ያህል ህጻናት የኤሊኖ ክስተት ባስከተለው ድርቅ ሳቢያ የከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂዎች መሆናቸውንና አስቸኳይ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ዩኒሴፍ አስታወቀ፡፡ በአካባቢው አገራት የሚገኙት እነዚህ ህጻናት የምግብና የውሃ እጥረት እንዳለባቸውና የክብደት መጠናቸው እየቀነሰ እንደሚገኝ የጠቆመው ተቋሙ፣ የምግብ ዋጋ መናር ቤተሰቦች ሳይመገቡ እንዲውሉና ንብረቶቻቸውን ሽጠው ምግብ እንዲገዙ እያስገደዳቸው ነው ብሏል፡፡መንግስታት ችግሩን ለመቋቋም የራሳቸውን ጥረት እያደረጉ ቢሆንም፣ በህጻናቱ ላይ የተከሰተው የከፋ የምግብ እጥረት አሳሳቢ ነው ተብሏል፡፡ሌሴቶ፣ ዚምባቡዌና አብዛኞቹ የደቡብ አፍሪካ አገራት ድርቁን ተከትሎ አስቸኳይ እርዳታ እንደሚፈልጉ ማስታወቃቸውን የዘገበው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ፣ በኢትዮጵያም የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ቁጥር በዚህ አመት ከ10 ሚሊዮን ወደ 18 ሚሊዮን ከፍ ይላል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡ማላዊ ባለፉት 9 አመታት የከፋ በተባለው የምግብ እጥረት እንደተጠቃች ያስታወሰው ዘገባው፣ 15 በመቶ ያህል ህዝቧ የርሃብና የከፋ የምግብ እጥረት ችግር እንዳንዣበበበት አክሎ ገልጧል፡፡

“ትራምፕ በምርጫው አሸንፎ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት አይሆንም!...” ባራክ ኦባማ
             “በአሜሪካ ታሪክ እጅግ ቀሽሙ ፕሬዚዳንት ኦባማ ነው!...” ዶናልድ ትራምፕ
    ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማና በመጪው የአሜሪካ ምርጫ ሪፐብሊካንን ወክለው ለመወዳደር በምርጫ ክርክር ተጠምደው የሰነበቱት አነጋጋሪው የሪልስቴት ከበርቴ ዶናልድ ትራምፕ የቃላት ጦርነት ውስጥ መግባታቸው ተዘገበ፡፡
ኦባማ ባለፈው ሰኞ ካሊፎርኒያ ውስጥ በተካሄደ ስብሰባ ላይ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ ትራምፕ በምርጫው አሸንፈው ቀጣዩ የአሜሪካ መሪ ሊሆኑ አይችሉም፤ ምክንያቱም አገርን መምራት ዕቃ ዕቃ ጨዋታ አይደለም! የአገሬ ህዝብ እንዲህ ያለ ሰው እንዲመራው እንደማይፈቅድ ስለማውቅ፣ ትራምፕ አሸንፎ ፕሬዚዳንት እንደማይሆን አምናለሁ ሲሉ መተቸታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡“የአሜሪካ ፕሬዚዳንት መሆን፣ የቶክ ሾው መምራት አይደለም!... በምርጫ ማሸነፍም፣ ሰፊ ማስታወቂያ የመስራትና የገበያ ጥናት የማድረግ ጉዳይ አይደለም፡፡ ከባድ ተልዕኮ ነው!...” ብለዋል ኦባማ የትራምፕን አካሄድ በመተቸት፡፡ኦባማ ይሄን ማለታቸውን ተከትሎም፣ በምርጫ ክርክር ተወጥረው የሰነበቱት ዶናልድ ትራምፕ፤ በነጋታው ረቡዕ ለኦባማ ትችት መረር ያለ የአጸፋ ምላሽ መስጠታቸውን ሲኤን ኤን ዘግቧል፡፡“በአሜሪካ ታሪክ እጅግ ቀሽሙ ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ ነው!... እሱ የሚሰራውን ነገር የማያውቅ፣ የአገር መሪ ነኝ የሚል ቀሽም ሰው ነው!... በ2012 ምርጫ በዕጩ ተወዳዳሪነት ብቀርብ ኖሮ፣ ኦባማን በቀላሉ ዘርሬ ስልጣኑን እይዝ እንደነበር ቅንጣት ታህል አልጠራጠርም!” ብለዋል ትራምፕ፡፡

ቫይረሱ በ39 አገራት ተሰራጭቷል
    የዓለም የጤና ድርጅት፤ ነፍሰጡሮችን በማጥቃት የጭንቅላት መጠናቸው አነስተኛና የአእምሮ እድገታቸው ውስን የሆኑ ህጻናት እንዲወለዱ የሚያደርገውን ዚካ ቫይረስ ለመዋጋት ለሚከናወኑ ስራዎች 56 ሚ ዶላር ያስፈልጋል ማለቱን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ገንዘቡ በተለይ በደቡብ አሜሪካ አገራት በመስፋፋት ላይ ለሚገኘው ዚካ ቫይረስ በአፋጣኝ ክትባት ለመፍጠር፣ በቫይረሱ የተጠቁትን ለመመርመርና በጉዳዩ ዙሪያ ዘላቂ መፍትሄ የሚያመነጩ ምርምሮችን ለማድረግ እንደሚውል የጠቆሙት የድርጅቱ ጄኔራል ዳይሬክተር ማርጋሬት ቻን፣ ቫይረሱ ወደ 39 የአለማችን አገራት በመስፋፋቱ በአፋጣኝ መፍትሄ መፈለግ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ድርጅቱ የሚፈለገውን ገንዘብ ከአባል አገራትና ከለጋሾች አገኛለሁ ብሎ እንደሚጠብቅ የገለጹት ቻን፣ ሰሞኑን ቫይረሱ ክፉኛ ወደተስፋፋባት ብራዚል አምርተው ድርጅቱ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት እያከናወነ የሚገኘውን ስራ እንደሚገመግሙና ከአገሪቱ የጤና ሚኒስትር ጋር በጉዳዩ ዙሪያ እንደሚወያዩም ተናግረዋል፡፡

    በኢትዮጵያ የህብረት ስራ ማህበራት ታሪክ 50 ዓመታትን ያስቆጠረ ቢሆንም ማህበራቱ በስርአት ተደራጅተው፤ በፖሊሲ ታቅፈው ሥራ ከጀመሩ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ አልሆናቸውም፡፡ በአሁኑ ሰዓት የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመርና ወደ ውጪ በመላክ ለአገሪቷ ገቢ ያስገባሉ፡፡ ምርጥ 10 ከሆኑት ቡና ላኪዎች ውስጥ አብዛኞቹ የህብረት ሥራ ማህበራት ናቸው፡፡ ነገር ግን የሚጠበቅባቸውን ያህል እየሰሩ አይደለም ይባላል፡፡ በሌላ በኩል ለማህበራቱ ተገቢው ትኩረት አልተሰጠም የሚል ቅሬታ ይሰነዘራል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ማህሌት ኪዳነወልድ፤ የፌደራል ህብረት ሥራ ማህበር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኡስማን ሱሩርን በማህበራቱ እንቅስቃሴ፣ችግሮችና የወደፊት ትልሞች ዙሪያ አነጋግራቸዋለች፡፡  
የማህበራቱ አላማ ምንድን ነው?
እንግዲህ ማህበራት ለአርሶ አደሩ፣ ለአርብቶ አደሩ፣ እንዲሁም ለዝቅተኛው ማህበረሰብ ትልቅ ጠቀሜታ አላቸው፡፡ የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር፣ አርሶ አደሩ ላመረተው ምርት ተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ፣ በገጠር የፋይናንስ ስርአት ቅርፅ እንዲይዝ… በአጠቃላይ የአንድ አገር ኢኮኖሚ እድገት ዘላቂ እንዲሆን ከተፈለገ፣ የማህበራቱ ሚና በተለይም በግብርናው ዘርፍ መተኪያ የለሽ ነው፡፡
አጠቃላይ እንቅስቃሴያችሁ ምን ይመስላል?
እንግዲህ በአጠቃላይ ማህበራቱ ከ15.8 ቢ. ብር በላይ ካፒታል አላቸው፡፡ ከ802ሺ በላይ ለሚሆኑ ዜጎችም የስራ እድል ፈጥረዋል፡፡ በተለይም የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመርና ወደ ውጪ በመላክ ለአገሪቷ ገቢ ያስገባሉ፡፡ በተለይ በቡናና ሰሊጥ ምርቶች፡፡ ምርጥ 10 ከሆኑት ቡና ላኪዎች ውስጥ አብዛኞቹ የህብረት ሥራ ማህበራት ናቸው፡፡
ከዚያም በላይ መንግስት ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን በመቅረፅ ሚናቸውን በማያሻማ መልኩ አስቀምጧል፡፡ እንግዲህ ይህን ያልኩት ጠቀሜታቸውን በአጭሩ ለማሳየት ነው፡፡ ሆኖም የሚጠበቅባቸውን ያህል እየሰሩ አይደለም፡፡ በርካታ ቀሪ ነገሮች አሉ፡፡ በፖሊሲው ላይ እንደተቀመጠው ከሆነ፣ አሁን የምናየው ውጤት በቂም ብቁም አይደለም፡፡ ትልቅ የአመለካከት ችግር አለ፡- በአመራሩ፣ በተደራጀው ክፍል፣ በአደራጁ… በሁሉም በኩል፡፡ አንዳንዱ ማህበራቱን የደርግ ሶሻሊስት ስርአት ማስፈፀሚያ አድርጎ የማሰብ፣ የደሃ መሰብሰቢያ እንዲሁም ከእድርና ከእቁብ የተለየ ተቋም አድርጎ ያለማየት ችግሮች አሉ፡፡ ይህ ችግር ማህበራቱ ማግኘት ያለባቸውን ድጋፍ እንዳያገኙ እያደረገ ነው፡፡ የመሰረተ ልማት አቅርቦት ችግር አለባቸው፡፡ መጋዘን የላቸውም፡፡ መስሪያ ቦታ፣ ቢሮ የለም፡፡ ይህንን ማቅረብ ያለበት አካልም የዝግጅት ችግር አለበት፡፡ ፖሊሲው አንድ ሆኖ፣ ከክልል ክልል አፈፃፀሙ ይለያያል፡፡ ወደ ዞንና ወረዳ ስትወርጂ ደግሞ ችግሩ እጅግ የከፋ ነው፡፡ ሌላው ነገር ብድር ነው፡፡ በቂ ብድር የለም፤ የብድር ጉዳይ ትልቅ ማነቆ ነው፡፡ ማህበራቱ ብድር የሚያገኙበት ማእቀፍ የለም፡፡ ስለሆነም ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ማበርከት ያለባቸውን አስተዋፅኦ አላበረከቱም፡፡ በተጨማሪም ብዙዎቹ ማህበራት በኮሚቴ እንጂ በባለሙያ አይመሩም፡፡ ምርቱ ተወዳዳሪ ቢያደርጋቸውም ወደ ተግባር የሚቀይር ባለሙያ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እንግዲህ ፖሊሲውን በማስፈፀም የመሰረተ ልማት ችግርን ለመፍታት እየሰራን ነው፡፡ ፋይናንስ አካባቢ ግን ገና መታየት አለበት፡፡ አማራጮች ሊቀመጡ ይገባል፡፡
መንግሥት ለዘርፉ ተገቢውን ትኩረት አልሰጠም እያሉኝ ነው?
መንግሥት በፖሊሲ ማእቀፍ ያስቀመጠው አቅጣጫ፣ የሰጠው ትኩረት አለ፡፡ ትኩረት ስንል ከፌደራል እስከ ክልል ነው፡፡ እንግዲህ መንግስት ስንል፤ ክልል፣ ዞን፣ ወረዳ፣ ቀበሌ እያለ ይወርዳል፡፡ ያው ትኩረት አሰጣጡ ከክልል ክልል ይለያያል፡፡ ትኩረቱ በእርግጥ በቂ አይደለም፡፡ እንደውም ወደ ታች ከክልል ወረዳ እያለ ሲወርድ… ጭራሽ የለም ማለት ይቻላል፡፡ አንዳንዱ ክልል የህብረት ስራ ጉዳይን የመጨረሻ አጀንዳው ያደርገዋል፡፡ እንግዲህ በGTP2 የተሻለ ነገር ለማየት ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ አስተዳደር ከማህበር አገልግሎትና ብዛት እንዲሁም ከተማዋ ዋና የገበያ ማእከል ከመሆኗ አንፃር፣ ለማህበራት የሰጠው ትኩረት እጅግ አናሳ ነው፡፡
ብዙ ጊዜ ማህበራቱ ከዘይትና ስኳር ስርጭት ጋር በተያያዘ በረጅም ሰልፍና አንዳንዴም የለም በማለት ነው የሚታወቁት …?
ህብረት ስራ ማህበራት በዋናነት የሚደራጁት ለዘይት፣ ስኳርና ዱቄት ብቻ አይደለም፡፡ በርካታ ምርቶችን ያቀርባሉ፤ በተለይ ግብርናው ላይ፡፡ ምንድነው --- መንግስት በድጎማ የሚያቀርባቸው እነዚህ ምርቶች ላይ የአቅርቦትና የፍላጎት ያለመጣጣም ችግር አለ፡፡ ስለሆነም አነስተኛ ገቢ ላለው ህብረተሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ በማህበራት በኩል ያቀርባል፡፡ በመዲናዋ ከ130 የሚበልጡ ማህበራት አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ከ30 በማያንሱት ላይ ኪራይ ሰብሳቢነት ሊታይ ይችላል፡፡ በጓሮ በር እያወጡ የሚሸጡ መኖራቸው አይካድም፤ተከታተለንም እርምጃ እየወሰድን ነው፡፡ ነገር ግን በጅምላ መጥላትና መንግስት ለራሱ ጥቅም ያደራጃቸው ተቋማት አድርጎ ማየቱ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህንን ነው እንግዲህ ቅድም የአመለካከት ችግር አለ ያልኩሽ፡፡ የማህበራቱ መልካም ስራ አብሮ መነሳት አለበት፡፡ ለምሳሌ አዲስ አበባ ፒያሳ፣ ማህበራቱ አንድ ኪሎ የቁርጥ ስጋን ከ80-90 ብር ይሸጣሉ፡፡ ሌላ ቦታ ከ180-200 ብር ሲሸጥ እያየን ነው፡፡ 1 ኪሎ ሽንኩርት ከ6-7 ብር ይሸጣሉ፡፡ በሌላው ገበያ 12 እና 14 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ ማህበራቱ ከ30 እስከ 120 በመቶ የዋጋ ልዩነት አላቸው፡፡
እንግዲህ ማህበራቱ ባለፈው ዓመት 4.5 ቢ. ብር ምርት ሸጠዋል፡፡ ከ30 እስከ 120 በመቶ የዋጋ ልዩነት አላቸው ካልን፣ በአማካይ ወስደን በ60 ብናበዛው እንኳን ብዙ ሚሊዮን ብሮች ተጠቃሚ ኪስ ገብቷል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሀብት ክፍፍሉን ፍትሃዊ ያደርገዋል፡፡
ወደተለያዩ የውጭ አገራት በመሄድ ተሞክሮ ወስዳችኋል፤ ተሞክሮው ምን ይመስላል?
እነ ጃፓን፣ ኦስትሪያ፣ ታይላንድ፣ ማሌዢያና አውሮፓ… ለህብረት ስራ ማህበራት የድጋፍ ማእቀፎች አሏቸው፡፡ የፋይናንስ ችግርን ለመፍታት የተለየ ባንክ ፣ የተለየ የፖሊሲ ማእቀፍ አላቸው፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ኮሪያ ሦስት አይነት ባንክ አላት፡- ንግድ ባንክ፣ ህብረት ስራ ባንክና ፖሊሲ ባንክ ናቸው፡፡ የትኛውም ማህበር የገንዘብ እጥረት ሲገጥመው ቢዝነስ ፕላን አቅርቦ ብድር ያገኛል፡፡ የሚሰራበት ቦታ ይሰጠዋል፡፡ ግብር ነፃ ነው፡፡ ሌላም ሌላም፡፡ በእኛ ሀገር አንዳንዱ አዋጁ ላይ አለ፤ ነገር ግን አተገባበር ላይ ችግር አለ፡፡ አንዳንድ አዋጆችም ማሻሻያ እንዲደረግባቸው እየጠየቅን ነው፡፡ ማህበራቱ የዜጎቻቸውን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆን አለባቸው፡፡ መንግስታት ሲቀያየሩ የኢኮኖሚ እድገትን የሚያስቀጥሉ ሊሆኑ ይገባል፡፡
ከ5 እና 6 ዓመታት በፊት አውሮፓና አሜሪካ የፋይናንስ ችግር ሲገጥማቸው ማህበራት ግን ሳይነኩ ወጥተዋል፡፡ ጃፓን ግብርናዋ የሚመራው በህብረት ስራ ነው፡፡ ሰሞኑን ያዘጋጀነው ኤግዚቢሽንና ባዛር ከነሱ በወሰድነው ተሞክሮ፣ የገበያ ትስስርን ለመፍጠር ያለመ ነው፡፡ በሌሎች አገራት ማህበራት በ50 እና 60ሺ ካሬ ላይ ያረፈ ትልልቅ የገበያ ማዕከላትም አሏቸው፡፡ እንግዲህ ቅድም 13.3 ሚ. ዜጎች የማህበራት አባል ናቸው ብዬሻለሁ፤ ይህንን ቁጥር በ5 ቤተሰብ እንኳን ብናበዛው እያወራን ያለነው ስለ 60ሚ. ህዝብ ነው፡፡ ስለዚህ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ከተፈለገ የአመለካከት ችግሮች ተቀይረው የሚገባቸውን ትኩረት ሊያገኙ ይገባል፡፡ በእርግጥ ማስተዋወቁ ላይ እኛ ዘንድም ክፍተት አለ፡፡ በቀጣይ የምንሰራበት ይሆናል፡፡
በአሁኑ ወቅት ስንት የህብረት ሥራ ማህበራት አሉ?
ከ71 ሺህ በላይ መሰረታዊ የህብረት ስራ ማህበራት፣ ከ353 ሺህ በላይ የህብረት ስራ ዩኒየኖች አሉ፡፡ በኢትዮጵያ ከ13.3 ሚ. በላይ ዜጎች የህብረት ስራ ማህበራት አባል ናቸው፡፡

    የተባበሩት የአረብ መንግሥታት ንብረት የሆነው ፍላይ ዱባይ አየር መንገዱ ከወር በፊት በተጠናቀቀው የፈረንጆች ዓመት ባደረገው እንቅስቃሴ ስኬታማ እንደነበር አስታወቀ፡፡
 አየር መንገዱ በዓመቱ ውስጥ 81,530 በረራዎችን በማድረግና 9.04 ሚሊዮን ተሳፋሪዎችን በማጓጓዝ፣ 27.4 ሚሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን የተጓዞቹ ብዛት ከ2014 ጋር ሲነፃፀር በ1.8 ሚሊዮን ሰዎች ብልጫ (25 በመቶ መጨመሩን) እንዳለውና ለ4ኛ ዓመት ትርፋማ መሆኑን ገልጿል፡፡
አጠቃላይ ገቢው 1.33 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን ከ2014 ጋር ሲነፃፀር የ11 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ በአንዳንድ መዳረሻ መስመሮች በሚፈጠሩ እገዳዎች ብዙ መስተጓጎሎች መፈጠራቸውንና ከአዳዲስ የበረራ መስመሮች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ግፊትና ጫና እንደነበረበትም አመልክቷል፡፡
የፍላይ ዱባይ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሚ/ር ጋኢዝ አል ጋኢዝ፤ አጠቃላይ የንግድ ሁኔታው ፈታኝ ቢሆንም የዕድገት ታሪካችንን በመጠበቅ ዓመቱን በስኬት አጠናቀናል ብለዋል፡፡ 

“ዘ ዊክንድ” በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀውና ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ አለማቀፍ ዝናን በማትረፍ ላይ የሚገኘው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፣ በሳምንቱ መጀመሪያ በተካሄደው የዘንድሮው የግራሚ ሽልማት ስነስርዓት በሁለት ዘርፎች ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በዘንድሮው የግራሚ ሽልማት በሰባት ዘርፎች ለሽልማት ታጭቶ የነበረው አቤል ተስፋዬ፤ ሎሳንጀለስ ውስጥ በተከናወነው 58ኛው የግራሚ ሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ “ቤስት ኧርባን ኮንቴምፖራሪ አልበም” እና “ቤስት አር ኤንድ ቢ ፐርፎርማንስ” በተሰኙት ሁለት ዘርፎች አሸናፊ በመሆን ሽልማቱን ተቀብሏል፡፡
“ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” የተሰኘው አልበሙ በ“ቤስት ኧርባን ኮንቴምፖራሪ አልበም”፣ “ኧርንድ ኢት” የተሰኘው ስራው ደግሞ  በ“ቤስት አር ኤንድ ቢ ፐርፎርማንስ” ዘርፎች ለሽልማት እንዳበቁት የተዘገበ ሲሆን፣ ባለፈው ሰኞ ምሽት በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓቱ ላይ የሙዚቃ ስራዎቹን ለተመልካቾች አቅርቧል፡፡
በዘንድሮው የግራሚ ሽልማት ካሸነፉት ድምጻውያን መካከል ቴለር ስዊፍት፣ ኬንድሪክ ላማር እና ኤሚ ዋይንሃውስ ይገኙበታል፡፡