Administrator
ዋልያዎቹ ለወሳኙ ፍልሚያ 1 ሳምንት ቀራቸው ከብራዛቪል ወደ ብራዚል
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የዛሬ ሳምንት በኮንጎ ብራዛቪል ከሴንተራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር የሚያደርገው ወሳኝ ጨዋታ እንደዘበት ደረሰ፡፡ ዋልያዎቹ በዚሁ ወሳኝ ፍልሚያ አድራጊነት ብቸኛው አማራጫቸው ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በበቂ የዝግጅት ግዜ እና የተጨዋቾች ስብስብ ሳይሰራ መቆየቱና የወዳጅነት ጨዋታ አለማድረጉ ያለውን እድል አስጨናቂ አድርጎታል፡፡ ዋልያዎቹ በኮንጎ ብራዛቪል መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን ካሸነፉ ብራዚል በ2014 እኤአ ላይ ለምታዘጋጀው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በአፍሪካ ዞን ለሚደረገው የ10 ብሄራዊ ቡድኖች የመጨረሻ ጥሎ ማለፍ ማጣርያ ይበቃሉ፡፡ በምድብ 1 ሌላ ጨዋታ በደርባን በሚገኘው የሞሰስ ማዲባ ስታድዬም ደቡበ አፍሪካ ቦትስዋናን ታስተናግዳለች፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ከምድባቸው የማለፍ እድል የሚኖራቸው ኢትዮጵያ ከተሸነፈች ብቻ ነው፡፡ በምድቡ ሁለተኛ ደረጃ ይዛ የምትገኘው ደቡብ አፍሪካ የማለፍ እድል የሚኖራት ቦትስዋናን ካሸነፈች በኋላ ኢትዮጵያ ከሴንተራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር አቻ ከወጣች ወይንም ከተሸነፈች ብቻ ይሆናል፡፡ በምድቡ በሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ቦትስዋና በበኩሏ ማለፍ የምትችለው ደቡብ አፍሪካን ማሸነፍ ከቻለች እና ኢትዮጵያ በሴንተራል አፍሪካ ከተረታች ይሆናል፡፡
የቦትስዋናው ጋዜጣ ሜሜጌ በድረገፁ እንደፃፈው ዜብራዎቹ በደቡብ አፍሪካ በሚኖራቸው ጨዋታ በቀላሉ 3 ነጥብ እንደማይጥሉ እና እጅ እንደማይሰጡ አትቷል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ለወሳኙ ጨዋታ በጣም ጠንካራ የቡድን ስብስብ ለማዋቀር ደፋ ቀና ስትል መሰንበቷን ሲያወሳም፤ ከ23 የባፋና ባፋና አባላት ከ8 በላይ በአውሮፓ ፕሮፌሽናል ደረጃ የሚጫወቱ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡ ቦትስዋና ለሳምንቱ ጨዋታ በአብሳ ፕሪሚዬር ሊግ የሚጫወቱ ተጨዋቾችን እንዳሰባሰበች የሚገልፀው ጋዜጣው እነዚህ ልጆች በደቡብ አፍሪካ ሊግ ባላቸው ከፍተኛ ልምድ ጨዋታው የካይዘር ቺፍ እና የኦርላንዶ ፓይሬትስ ደርቢ ይመስላል ብሏል፡፡የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እያደረገ ባለው ዝግጅት አንድም የወዳጅነት ጨዋታ አለማሳቡ የሳምንቱን ግጥሚያ አቋሙን ሳይፈትሽ የሚደርስበት ሆኗል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በተለያዩ አገራት ለፕሮፌሽናል ቅጥራቸው የተሰማሩ ምርጥ ተጨዋቾችን በቶሎ ማሰባሰብ ባይችሉም፤ 32 ተጨዋቾችን በመጥራት እየተዘጋጁ ነው፡፡ በብሄራዊ ቡድኑ ስብስብ በደቡብ አፍሪካ ሊግ የሚጫወተው ጌታነህ ከበደ፤ በሱዳን ሊግ ያለው አዲስ ህንፃ፤ በእስራኤል ያለው አስራት መገርሳ እንዲሁም በስዊድን ያለው ሳላዲን ሰኢድ በቶሎ አለመካተታቸው በቡድኑ መቀናጀት የተወሰነ ተፅእኖ ሊፈጥር ይችላል፡፡ በዝግጅት ቡድኑ ጊዮርጊስ 11፤ ኢትዮጵያ ቡና 4፤ ደደቢት 3፤ መከላከያ 2 ፤ መብራት ሃይል 2 ተጨዋቾች ሲያስመለምሉ በ2006 የውድድር ዘመን ፕሪሚዬር ሊጉን የሚቀላቀለው የዳሸን ቢራ ክለብ 3 ተጨዋቾች በማስመረጥ ብሄራዊ ቡድኑን ማጠናከሩ አስደንቋል፡፡ከደቡብ አፍሪካ ጋር ተደርጎ በነበረ ጨዋታ እያንዳንዳቸው ሁለተኛ የቢጫ ካርዳቸውን ያዩት የኋላው ደጀን አይናለም ሃይሉና ግብጠባቂው ጀማል ጣሰው በሳምንቱ ጨዋታ በቅጣት አይሰለፉም፡፡
“የጃንሆይ ወርቅ መዘዝ” ለንባብ በቃ
ጆን ማን “The On’s Share” በሚል ርዕስ የፃፈው መፅሃፍ “የጃንሆይ ወርቅ መዘዝ” በሚል ርዕስ በሙሉቀን ታሪኩ ተተርጉሞ ለንባብ በቃ፡፡
መፅሃፉ የአገሪቱ የቀድሞ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማርያም፣ ከምዕራባውያን በተለይ ከአሜሪካ ድጋፍ በማግኘት የተራቡ ወገኖችን ለማበራከት የነደፉት እቅድ ባለመሳካቱ ወደ ሩሲያ መዞራቸውን፣ ከአንድ ባንክ የተበደሩትን 200 ሚሊዮን ዶላር ከሩሲያ የጦር መሳሪያ ለመግዛት ማዋላቸውንና ሌሎች ጉዳዮችን ይገልፃል፡፡ በኤችዋይ ኢንተርናሽናል አታሚዎች የታተመው ባለ 173 ገፅ መፅሃፍ፣ በ40.50 ብር እየተሸጠ ነው።
ኮሌጆች ተማሪዎች ያስመርቃሉ
ኩኑዝ ኮሌጅ ከደረጃ ሁለት እስከ አራት በአካውንቲንግ ያስተማራቸውን 81 ተማሪዎችና ሁለት መፅሃፍት ዛሬ ከጠዋቱ 3 ሰዓት በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ትያትርና ባህል አዳራሽ እንዲያስመርቅ አስታወቀ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ረዳት ፕሮፌሰር በድሉ ዋቅጅራ በክብር እንግድነት ይገኙበታል ተብሎ በሚጠበቀው የምረቃ ሥነስርዓት ላይ “የኢትዮጵያ የትምህርት ችግሮች ያስከተለው ኪሳራና መፍትሄዎች” የሚለውና “ወርቃማ ቁልፍ” የተሰኘ የእንግሊዘኛ ማስተማሪያ መፅሃፍ ይመረቃሉ ተብሏል፡፡ መፅሃፎቹን ያዘጋጁት የኩኑዝ ኮሌጅ እና የሜሪት የቋንቋ ትምህት ቤት ባለቤትና ፕሬዝዳንት አቶ ተስፋዬ ለጋ ናቸው፡፡
በተያያዘ ዜና ቅድስት ልደታ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ በነርሲንግ፣በፋርማሲና በህክምና ላብራቶሪ የሰለጠኑ 169 ተማሪዎችን ነገ ከጠዋቱ 2 ሰአት፣ አምስት ኪሎ በሚገኘው የጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ ያስመርቃል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በሌላም በኩል ኒው ጄኔሬሽን ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 250 ተማሪዎች ዛሬ ያስመርቃል። ተማሪዎቹ የሚመረቁት ሜክሲኮ አደባባይ በሚገኘው የአፍሪካ ህብረት አዳራሽ ነው፡፡
“መሰረታዊ የፊልም ድርሰት አፃፃፍ ዘዴ” ነገ ይመረቃል
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የትያትር ጥበባት መምህር የሆኑት አቶ ኤፍሬም ለማ ያዘጋጁት “መሰረታዊ የፊልም ድርሰት አፃፃፍ ዘዴ” መፅሃፍ ነገ ይመረቃል፡፡ መፅሃፉ በቀኑ 8ሰዓት የሚመረቀው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ስድስት ኪሎ ግቢ፣ ኔልሰን ማንዴላ አዳራሽ ነው፡፡
ብሄራዊ ትያትር ከያንያንን ዛሬ ይዘክራል
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ትያትር በኢትዮጵያ ኪነጥበብ ጉልህ ድርሻ ያላቸውን ከያንያን ዛሬ እንደሚዘክር አስታወቀ፡፡ የትያትር ቤቱ ባልደረቦች “የኢትዮጵያ ብሄራዊ ትያትርን በአዲስ ራዕይ” በሚል መርህ በሚያቀርቡት ዝግጅት ላይ በትያትር ቤቱ የሰሩ እና ሌሎች አንጋፋ ባለሙያዎች ልምዳቸውን የሚያካፍሉ ሲሆን የቀይ ምንጣፍ አቀባበልና የምሳ ግብዣ እንደሚደረግላቸው ትያትር ቤቱ ጨምሮ ገልጿል፡፡
ላ-ቦረና ሰኞ ይመረቃል
በኢንጂል አይስ ፊልም ፕሮዳክሽን የተዘጋጀውና በደራሲ ዮናታን ወርቁ የተደረሰው ላ-ቦረና ፊልም፣ የፊታችን ሰኞ በ11 ሰዓት በብሄራዊ ትያትር ቤት ይመረቃል፡፡ በላይ ጌታነህ ዳሬክት ያደረገው ፊልሙ፣ በአንዲት ፈረንሳዊት አንትሮፖሎጂስት ጥናት ላይ ያተኮረ ሲሆን የቦረናን ባህልና ወግ ያንፀባርቃል ተብሏል፡፡ በፊልሙ ላይ አለም ሰገድ ተስፋዬ፣ ማርያኔ ቤለርሰን፣ አንተነህ ተስፋዬና ሌሎችም ተውነውበታል፡፡ ፊልሙ የ1፡40 ርዝማኔ እንዳለውም ተገልጿል፡፡
“ነገር ለጫሪዋ ትተርፋለች ረግረግ የረገጣትን ታሰጥማለች
(ነገር ንአጓዲኣ ትልክም፣ ታኼላ ንኣታዊኣ ተስጥም)
ከእለታት አንድ የክረምት ቀን፣ አንዳች አውሎ ንፋስ በመጣ ሰዓት፤ ፈረስ፣ በሬ እና ውሻ አንዱን የሰው ልጅ እንዲያስጠልላቸውና እንዲያሳድራቸው ለመኑት፡፡ ሰውዬው መልካም ፈቃዱ ሆነ፡፡ የክረምቱ ብርድ በርዷቸዋልና ይሞቃቸው ዘንድ እሳት አነደደላቸው፡፡ የሚተኙበት ምቹ ስፍራም ሰጣቸው፡፡ ይበሉት እንዳይቸገሩም ለፈረሱ ገብስ ሰጠው፡፡ ለበሬው ጭድ ሰጠው፡፡ ለውሻውም ከራሱ ራት ከተረፈው ፍርፋሪ አቀረበለት፡፡
በነጋታው ነፋሱ ካቆመ በኋላ ሲለያዩ ምሥጋናቸውን ለሰውዬው ለማቅረብ አሰቡ፡፡
“እንዴት አድርገን እናመስግነው?” አለ ፈረስ፡፡
“የሰውን ልጅ እድሜ እናስላና፤ በየፊናችን ተካፍለን፣ ያለንን ጥሩ ጠባይ ብንሰጥስ?” አለ ውሻ፡፡
“እንዴት ማለትህ ነው?” ሲል ጠየቀ በሬ፡፡
ውሻም፤
“እያንዳንዳችን ልዩ ችሎታ አለን አይደል? ያንን የው ልጅ እድሜ፣ ከእድሜው ጋር በሚሄደው ፀባዩ አንፃር እናጤነዋለን” አለ፡፡
ፈረስ፤
“አሁንም ልትል የፈለግኸው በደንብ አልገባኝም”
ውሻ፤
“ልዘረዝርልህ እኮ ነው፡፡ ለምሳሌ በመጀመሪያ የህይወቱ ክፍል፣ የሰው ልጅ ወጣት ነው፡፡ ለዚህ የሚሆን ጠባይ ማን ይስጠው?” ሲል ጠየቀ፡፡
ፈረስ፤
“እኔ እሰጠዋለሁ” አለና ሰጠ፡፡ በዚህ ረገድ ወጣቶች ሁሉ ትእግስት-የለሽና ጉልበተኛ እንዲሆኑ ሆኑ፡፡
ውሻ ቀጠለና፣
“ቀጥሎ፣ ሁለተኛው የህይወቱ ክፍል የመካከኛ እድሜ ጐልማሳነቱ ነው - ለዚህስ የሚሆን ፀባይ ማን ይስጠው?” አለ፡፡
በሬ፤
“እኔ እሰጠዋለሁ፡፡ የእኔን ጠባይ ይውሰድ” አለ፡፡ እውነትም የሰው ልጅ በመካከለኛ እድሜው በሚሰራው፣ ሥራ ዘላቂ ምን ጊዜም ደከመኝ የማይል፣ ምንጊዜም ታታሪ የሆነ ባህሪ ኖረው፡፡
በመጨረሻም ውሻ፤
“የሽምግልና ጊዜ ጠባይን እኔ እለግሰዋለሁ” አለ፡፡ በዚህም መሰረት የሰው ልጅ በእርጅናው ጊዜ ነጭናጫና በትንሹ የሚያኮርፍ፣ “ውሻ በበላበት ይጮሃል” እንደሚባለው ምግብ ላበላውና ምቾት ለሀጠው የሚያደላና፤ ፀጉረ - ልውጥ ሰው ላይ ግን የሚጮህና የሚናከስ ሆነ፡፡
***
ትእግስት-የለሽና ጉልበተኛ ወጣቶች ለአደጋ ይጋለጣሉ፡፡ ዘላቂና ታታሪ ዜጐች ለሀገር ህልውና ዋና ቁምነገር ናቸው፡፡ የሽማግሌዎች መርጋትና መሰብሰብ፤ ለሀገር የረጋ ህይወት መሰረት ነው፡፡ በአንፃሩ ሽማግሌው ነገር ፈላጊ፣ ጉልቤ ልሁን ባይ፣ የማያረጋጋ ከሆነ የአገር አደጋ ነው፡፡ የፈረሱም፣ የበሬውም፣ የውሻውም ባህሪ በሰው ልጆች ህይወት ውስጥ ወሳኝነት ያላቸው ጉዳዮች እንደመሆናቸው፤ ህብረተሰባችንን ለመመርመር ያግዙናለ፡፡ በየሥራ ምድቡና በየሀብት መደቡ፣ እንዲሁም በአገር አመራር ደረጃ ባሉ ዜጐች ላይም ይንፀባረቃሉና፡፡
የሀገር መሪዎች ወደ አመራሩ ቡድን ፊታቸውን ሲያዞሩ፤ ለህዝቡ ጀርባቸውን መስጠታቸው አይቀሬ ነው ይላሉ የፖለቲካ ፀሐፍት፡፡ ”ከጭምብሉ በስተጀርባ” በተባው መፅሐፍ ደራሲው ባድዊን፤
“ኦርኬስትራውን ለመምራት የሚፈልገው ኅብረ-ዜማ - አቀናጅ (Conductor) ጀርባውን ለተመልካቹ ህዝብ ይሰጣል” ይለናል፡፡
ኦርኬስትራው መስመር ከያዘ በኋላ ግን ወደ ህዝቡ መዞር ያስፈልጋል፡፡ ኦርኬስትራውም የሚያነጣጥረው ተመልካቹ ላይ ነው፡፡ የኅብረ-ዜማውን ቃና ማጣጣም ያለበት ህዝቡ ነው፡፡ ኦርኬስትራውም ሆነ መሪው ኅብረ-ዜማው ለኅሩያን ኅዳጣን (ለጥቂቶች ምርጦች እንዲሉ) ብቻ እንዲሰማ ከሆነ የታቀደው፤ አዲዮስ ዲሞክራሲ!
በሀገራችን እንደተመላላሽ በሽተኛና አልጋ ያዥ በሽተኛ ተብለው ሊከፈሉ የሚችሉ አያሌ ችግሮች አሉ፡፡ አንድኞቹ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሳይገባ በፊት ሲነገሩ፣ ሲመከሩ የሚሰሙ ዜጐች “እሺ፤” ጐርፍ ከመጣም ሲደርስ እናቋርጠዋለን” የሚሉ የሚፈጥሩት ነው፡፡ ሁለተኞቹ ጐርፍ እሚባል ከነጭራሹም ሊመጣ አይችልም፤ የሚሉቱ የሚፈጥሩን ችግር ነው፡፡ ሦስተኞቹ ሀሳቡን ወይም መረጃውን ያመጡትን ክፍሎች “በሬ ወለደ ባዮች” ብለው የሚፈርጁ በመሆናቸው የሚፈጠር፡፡ አራተኞቹ ግን በጣም ጥቂቶቹ ምክር ተቀብለው፤ ድምፅ የላቸውም እንጂ፣ እንጠንቀቅ እያሉ ጥሩ ደወል ቢያሰሙም የመደማመጥ ችግር ነው፡፡ ደጋግመን በከበደ ሚካኤል ልሳን እንደተናገርነው፡- ዛሬም “…አሁን የት ይገኛል ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈልግ የባሰ ደንቆሮ”
እንላለን፡፡
እንሰማማ፡፡ ችግሮች ይግቡን፡፡ ቀድመን ሁኔታዎችን እንይ! የቅድመ-አደጋ ጥሪ ማዳመጥን ትተን፤ ጐርፉ ሲመጣ አንጩህ፡፡ ጉዞ እሚሰምረው ነገር ማጣጣም ሲኖር ነው፡፡ ጉዞ ይሳካል እሚባለው ቅድመ-እንቅፋትን ማየት ሲቻል ነው፡፡
እንቀሰቅሳለን ያልነው መንገድ ውሎ ሲያድር ምን እሳት ይዞ እንደሚመጣ እናስተውል፡፡ “እዚያም ቤት እሳት አለ!” ጨዋታ ንግገር አይደለም፡፡ ቀድሞ ማስላት ጉዳት የለውም፡፡ የቀደሙ ስህተቶችንም አውቆ ማረም ነውር አይደለም፡፡ እሳቱ ሲለኮስ ማገዶ ሲጫር ያልነቃ ልቦና፤ ብዙ ጊዜ አደጋ ያስተናግዳል፤ ይባላል፡፡
የተዳፈነ እሳትን ለማንቃት መሞከር አላግባብ ድካም ነው፡፡ ያ እሳት ከተንቀለቀለ ደግሞ ራስንም ጭምር ያነዳል፡፡ ይሄ ማለት ደግሞ፤ እንደትግሪኛው ተረት፤ “ነገር ለጫሪዋ ትተርፋለች፣ ረግረግ የረገጣትን ታሰጥማለች” ማለት ነው፡፡
አቢሲኒያ ባንክ ከ351 ሚ.ብር በላይ አተረፍኩ አለ
አቢሲኒያ ባንክ ዘንድሮ 351.2 ሚሊዮን ብር አጠቃላይ ትርፍ ማግኘቱንና ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ12.2 በመቶ ብልጫ እንዳለው ገለፀ፡፡ ባንኩ በላከው መግለጫ ላይ እንዳስታወቀው፤ የባንኩ አጠቃላይ ገቢ 895 ሚሊዮን ብር መድረሱንና ካለፈው ዓመት በ126 ሚሊዮን ብር ብልጫ ያለው መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ለተለያዩ የንግድና አገልግሎት ዘርፎች በአጠቃላይ 4.7 ቢሊዮን ብር ብድር የሰጠ መሆኑን የገለፀው ባንኩ፤ አጠቃላይ ተቀማጭ ሂሣቡ 8.5 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቋል፡፡ አቢሲኒያ ባንክ 371ሺ 420 የሚሆኑ የገንዘብ አስቀማጭ ደንበኞች እንዳሉት መግለጫው ጠቅሶ፤ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞችና ክልሎች 82 የሚደርሱ ቅርንጫፎችን ከፍቶ ለደንበኞቹ አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
አገሬ፣ እኔ እናሻማ!
መሸ
ቤቴ ገባሁ፡፡
ያው ደሞ እንዳመሉ
እንደባህሉ ሁሉ …መብራቱ ጨልሟል፡፡
እና ሻማ ገዛሁ
በሻማው ብርሃን፣ ልፀዳበት አሰብሁ፡፡
እና ሻማ ገዛሁ…ሁሉንም ባይሆንም
አንድ ሁለት አበራሁ
በሻማው ብርሃን …መንፈሴን አፀዳሁ
እንደ አያቴ መስቀል
እንደሼኪው ሙሰባህ
እንደ አበው መቁጠሪያ
እንደአገሬ ማተብ …እንዳገሬ ክታብ
አምኜ ጀመርኩኝ፣ ማስታወሻ መፃፍ
ህይወት ባገኝ ብዬ፣ ከጨለማው ደጃፍ፡፡
ከሐምሌ ጨለማ
ከጨረቃዋ ሥር፣ ጉም ከተናነቃት
ክረምቱ ዘንቦባት
ብርድ እንደዛር - ውላጅ፣ እያንቀጠቀጣት፤
አገሬ ጨልማ፤
በእንግድነት ቤቴ፣ መጥታ ልትጠይቀኝ
“መብራቴን ሸጫለሁ፣ ሻማ ለኩስልኝ”
ብላ ለመነችኝ፡፡
“የሸጥሽበት ገንዘብ፣ የት ደረሰ?” አልኳትኝ፡፡
(ይሄኔ ነጋዴ ኖሮ ቢሆን ኖሮ፤ “አትርፋለች?” ባለኝ፡፡
ይሄኔ አንድ ምሁር፣ ኖሮ ቢሆን ኖሮ
ማን ፈቅዶ ነው ይሄ፣ ምን ‘ማንዴት’ አላቸው?
ጉድ መጣ ዘንድሮ፤
ኖሮ ቢሆን ኖሮ፣ የጋዜጣ አንባቢ፤
“ህዝብ ያቃል ይሄንን?
ደባ ሲሰሩ ነው!” ባለ ነበር ምሩን
ሁሉን አስባበት፣ ሻማዊ ሳቅ ሳቀች
ሁሉን አስቤበት፤ ሻማዊ ሳቅ ሳኩኝ፡፡
ከነልብሴ ተኛሁ፣ ብርድ ልብስም የለኝ፡፡
እሷም ሌጣዋን ነች፤ ጐኔ ገለል አለች፡፡
ልክ ዐይኔን ስከድን፣ ቀና አለች ወደኔ
“ሻማውን አጥፋ እንጂ፤ ለነገ አታስብም?
የቁጠባ ባህል፣ ዛሬም አልገባህም?!”
ስትል ገሰፀችኝ፡፡
ሻማው ሰማ ይሄንን፣ ጣልቃ ገባ እንዲህ ሲል
“መብራት ከሄደበት፣ እስኪመለስ ድረስ
ዓመት ፍቃድ ላይ ነኝ፣ ይሁን ልሥራ ለነብስ
የበራሁ መስዬ፣ ተዉኝ ትንሽ ላልቅስ!
ብቻ ወዳጆቼ፤
እንሰነባበት፣ እንሳሳም በቃ፤
ስለማይታወቅ፣ ነግ ማን እንደሚከስም
ነግ ማ እንደሚነቃ!!”
(የነገን ማን ያውቃል ለሚሉ)
ከግንቦት 2004-2005 ዓ.ም
“ሆራይዘን ቡዩቲፉል ፊልም ውዝግብ አሰነሳ” ለሚለው ዘገባ “ከብሉናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ” የተሰጠ መልስ
“ሆራይዘን ቢዩቲፉል ፊልም ውዝግብ አስነሳ” በሚለው ዘገባ ”ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚን የሚመለከት ዘገባ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ ይሁን እና የቀረበው አጭር ዘገባ የተዛቡ መረጃዎችና ስህተቶችን የያዘ በመሆኑ እንደሚከተለው እንዲታረም እንጠይቃለን፡፡
ለመነሻ ያህል ሆራይዘን ቢዩቲፉል በብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚና ቴል ፊልም በተባለ የስዊዘርላንድ ድርጅት የተሰራ የትምህርታዊ ፕሮጀክት ፊልም ሲሆን፣ ትምህርት ቤቱ በፊልሙ ስራ የተሳተፈበት አላማም ተማሪዎቹ ልምድ ካላቸው የውጭ የፊልም ባለሞያዎች ጋር ጐን ለጐን የሚሰሩበትን ተግባራዊ ልምምድ በማመቻቸት፣ የፊልም ስራ ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ ማስቻል ነው፡፡
ተማሪዎች በትምህርታዊ ፕሮጀክቱ ላይ የሳተፉት ገንዘብ እንደሚከፈላቸው ተነግሯቸው ሳይሆን ከፕሮጀክቱ ለመማር እና ራሳቸውን የተሻለ የፊልም ባለሞያ ለማድረግ በሙሉ ፈቃደኝነትም ጭምር ነው፡፡ በፊልም ስራው ላይ ከተለያዩ የትምህርት ዘመን የተውጣጡ ከ35 በላይ የትምህርት ቤቱ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን፣ በፕሮዳክሽኑ መጨረሻ ከተማሪዎቻችን ጋር በተደረገው ግምገማ እና ውይይትም ትምህርታዊ ፕሮጀክቱ እጅግ ውጤታማ እና ተማሪዎቹ በርካታ ጠቃሚ እውቀት እና ልማዶችን ያካበቱበት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
የጋዜጠኛዋ ዘገባ፣ በፊልሙ ላይ የተሳተፉ ተማሪዎች አካዳሚው የሚገባንን ክፍያ እንዲሁም አንድ አመት የተማርንበትን ሰርተፊኬት ከልክሎናል እንዳሉ ያትታል፡፡ “ሆራይዘን ቢዩቲፉል” ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ ቀደም ሲል ያስመረቃቸው እንዲሁም በወቅቱ በትምህርት ላይ የነበሩ ከ35 በላይ ተማሪዎች የተሳተፉበት ፊልም ነው፡፡ ጋዜጠኛዋ ክፍያ እና ሰርተፊኬት ተከልክለናል ያሉትን ግለሰቦች ስም ለመጥቀስ አልፈለችም፡፡ ከትምህርት ቤቱ ምክትል ስራ አስኪያጅ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ሁሉንም ተማሪዎች እንደምታነጋግር ቃል የገባች ሲሆን ትምህርት ቤቱም በፊልሙ ላይ የተሳተፉትን ተማሪዎች ስም ዝርዝር እና ስልክ ቁጥር ሰጥቷት ነበር፡፡ ጋዜጠኛዋ በወቅቱ እንደገለፀችው “ከተማሪዎቹ አንዳቸውም እንኳን ከላይ ክፍያ እና ሰርተፊኬት ተከልክለናል በሚለው ባይስማሙ በዘገባው ላይ ይህ ጥያቄ የተማሪዎቹ ጥያቄ እንደሆነ አድርጐ ማውጣት አግባብ አይደለም” ብላለች፡፡ ይሁን እና ሁሉንም ተማሪዎች ይቅርና የተማሪዎቹን ድምጽ ለመወከል የሚበቃ ቁጥር ያላቸውን ሳታናግር ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ ከመላው ተማሪዎቹ ጋር ተቃርኖ ውስጥ የገባ በማስመሰል ለማቅረብ ሞክራለች፡፡ የጥቂት ግለሰቦች አጀንዳ የሆነን ጉዳይ ግለሰቦቹን በማንነታቸው ከማቅረብ ይልቅ “ተማሪዎች” ከሚል መከለያ ጀርባ በመደበቅ ለማራመድ መሞከር ተገቢ የጋዜጠኝነት ስነ ምግባር አይመስለንም፡፡
“ተማሪዎቹ ተከለከልን አሉ” ስለተባለው ሰርተፊኬት ጉዳይም ለጋዜጠኛዋ የሰጠነው መልስ “…ያላሟሉት ነገር ቢኖር ነው” የሚል የመላምት መልስ ሳይሆን የሚከተለውን ነው፡፡ በፊልሙ ላይ የተሳተፉት ከተለያየ አመት የተውጣጡ ተማሪዎች እንደመሆናቸው መጠን፣ ከፊሎቹ ትምህርታቸውን አጠናቀው ፊልሙ ከመጀመሩ በፊት ሰርተፊኬታቸውን የወሰዱ ሲሆን ቀሪዎቹ ደግሞ በወቅቱ በትምህርት ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ ከእነዚህም መሀከል ከትምህርት ገበታ አለመቅረትን፣ የልምምድ እና የመመረቂያ ፕሮጀክት መስራትን እንዲሁም ስነ ምግባርን ጨምሮ በትምህርት ቤቱ መመሪያ መሰረት ማሟላት ያለባቸውን ቅድመ ሁኔታ ያሟሉ ተማሪዎች የመመረቂያ ሰርተፊኬት የወሰዱ ሲሆን ይህን ላላጠናቀቁ ተማሪዎች ሰርተፍኬት መስጠት ግን የትምህርት ቤቱ ደንብ አይፈቅድም፡፡
3. ዘገባው ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ ከቴል ፊልም ስዊዘርላንድ ጋር በመተባበር የሰራው ፊልም ወደፊት ትርፍ ከተገኘበት ለፀሐፊዎቹ 10% ይከፈላል እንዳለ ይገልጻል፡፡ ለጋዜጠኛዋ በሁለቱ ድርጅቶች መሀከል የተፈረመውን የፕሮዳክሽን ስምምነት ከነአማርኛ ትርጉሙ የሰጠናት ከመሆኑም በላይ በቃለ መጠየቁ ወቅት ቃል በቃል እያነበብን እንዳስረዳነው፣ ከፊልሙ ከሚገኝ ማናቸውም ገቢ የተጣራ ትርፍ ላይ ቴል ፊልም የተባለው የስዊዘርላንድ ድርጅት ለፊልሙ ዋና ፀሐፊ ለሆነው የውጭ ዜጋ 10 በመቶ የሚከፍል ሲሆን፤ ይህም በአራቱ ፀሐፊዎች መሀከል እኩል የሚከፋፈል ይሆናል፡፡ ብሉ ናይል ለፀሐፊዎች የ10 በመቶ ክፍያ ይከፍላል የሚል መረጃ አልሰጠንም፤ በፕሮዳክሽን ስምምነቱም ውስጥ የተገለፀው ይህን አይደግፍም፡፡
4. ዘገባው የፊልሙ ክፍያን በተመለከተ በተነሳው ውዝግብ ፊልሙ ለእይታ እንዳልበቃ ጠቅሷል፡፡ ይህ ዘገባ ስህተት ሲሆን ትምህርት ቤቱ እስከሚያውቀው ድረስ ፊልሙ ለእይታ ያልበቃው የፖስት ፕሮዳክሽን ስራው ተጠናቆ ባለማለቁ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ይህ ተጠናቆ ፊልሙ በተለያዩ የውጭ አገር ፌስቲቫሎች ላይ በመታየት ላይ መሆኑን ከፊልሙ የፌስ ቡክ ገጽ መረዳት ይቻላል፡፡ ፊልሙ በአገር ውስጥ ለመታየት ያልቻለውም እንደተባለው በክፍያ ውዝግብ ሳይሆን በፊልሙ ላይ ምንም መብት የሌለው እና የቀድሞ የትምህርት ቤቱ ተማሪ የነበረ ግለሰብ፣ ከትምህርት በቱ ፈቃድ ውጭ ፊልሙን ለማሳየት በዝግጅት ላይ መሆኑን ትምህርት ቤቱ በመረዳቱ እና ይህን ለማስቆም ለሚመለከታቸው አካላት ባቀረበው አቤቱታ መሰረት፤ ትምህርት ቤቱ የፊልም ባለቤትነቱን በማረጋገጥ ሂደት ላይ በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ከተጠናቀቀ በኋላ ለእይታ የሚቀርብ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጭ ፊልሙ በሌሎች ወገኖች ለእይታ ቢቀርብ ግን ትምህርት ቤቱ ህጋዊ እርምጃ የሚወስድ ይሆናል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ጋዜጠኛዋ ያቀረበችው መረጃ የአንድ ወገን እይታን ብቻ ያንፀባረቀ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡
ዘገባው ተማሪዎቹን እና ጸሀፊዎቹን ለያይቶ ለማቅረብ ያልቻለ ቢሆንም የፊልሙ ጸሀፊዎች የፊልሙን ጽሁፍ በሚያዘጋጁበት ጊዜ እያንዳንዳቸዉ 2500 ብር ብቻ እንደተከፈላቸዉ እና ለትራንስፖርት እና ሌሎች ወጪዎች ከኪሳቸዉ ሲያወጡ እንደነበረ ይገልጻል፡፡ አሁንም የጸሀፈዎቹን ስም ለመግለጸ እንዳልተፈለገ ልብ ይሏል፡፡ በቃለ መጠይቁ ወቅት ጋዜጠኛዋ ጸሀፊዎቹ ምንም አይነት ክፍያ እልተሰጠንም እንዳሏት ገልጻ፣ ይህ ለምን እንደሆነ ጠይቃለች፡፡ በምላሹም ይህ ስህተት እንደሆነ እና ምንም እንኳን ፊልሙ ትምህርታዊ ፕሮጀክት ቢሆንም ጸሀፊዎቹ በስራ ወቅት ለሚያወጡት ወጪ እና ከሌላ ስራ ያገኙት የነበረዉን ገቢ በጥቂቱም ቢሆን ለማካካስ በየወሩ 2500 ብር ሲከፈላቸዉ እንደነበረ፣ ለትራንስፖርት እና ሌሎች ወጪዎችም ባቀረቡት ደረሰኝ መሰረት እንደተከፈላቸዉ ገልጻ ለዚህም በእጃችን የነበረዉን ማስረጃ አሳይተናል፡፡ ይሁን እና ጋዜጠኛዋ የእኛን መልስ እና ማስረጃ ወደጎን በመተዉ ይልቁንም ያቀረብነዉን ማስረጃ እነዚህ ግለሰቦች የሰጡትን የተሳሳተ ማስረጃ “የተከፈለን 2500 ብር ብቻ ነዉ” ወደሚል ማስተካከያ ለመቀየር ተጠቅማበታለች፡፡ አንድ ጋዜጠኛ የተሰጠዉ መረጃ ስህተት አንደነበረ የሚያረጋግጥ መረጃ ሲደርሰዉ ይህን እንዳላዩ ማለፍ እና ይበልጡንም የሀሰት ማስረጃ የሰጡትን ግሰቦች ቃል ለማስተካከል መጠቀሙ ወገንተኝነትን የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ የጋዜጠኛዉን ሀቀኝነት እና ተአማኒነት ጥያቄ ዉስጥ የሚጥል ነዉ፡፡
በዘገባዉ የቀረበዉ የገንዘብ መጠንም እንዲሁ ገንዘቡ ወደብር ሲለወጥ በፊልሙ ዝግጅት ወቅት ከአንድ አመት ከሰባት ወር በፊት ባለው የምንዛሪ ሂሳብ ሳይሆን ዛሬ ባለዉ በመሆኑ ስህተት ነዉ፡፡ በዚህም መሰረት የገንዘብ መጠኑ እንደተባለዉ 360,400 ብር ሳይሆን 252,000 ብር ነው፡፡
ከላይ የተገለጻዉን ገንዘብ አጠቃቀም በተመለከተም ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ ከተቋቋመበት አላማም ሆነ “ከሆራይዘን ቢዩቲፉል” ትምህርታዊ የፊልም ፕሮጀክት አላማ አኳያ፤ ትምህርት ቤቱ ገንዘቡን በደሞዝ መልክ ማከፋፈል ሳይሆን ተጨማሪ ትምህርታዊ የፊልም ፕሮጀክቶችን በመስራት ነባር እና መጪ ተማሪዎች ክህሎታቸዉን እንዲያዳብሩ የማድረግ አቋም ያለዉ መሆኑን እንገልጻለን፡፡
ከሰላምታ ጋር
ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ