
Administrator
“B787” የከፋ ችግር የለውም ተባለ
የቦይንግ ኩባንያ ዘመናዊ ምርት የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ድሪም ላይነር አውሮፕላን (“B787”) ባለፈው አርብ ለንደን ደርሶ ካረፈ በኋላ ጭራው አካባቢ እሳት ተነስቶበት መለብለቡ የሚታወስ ሲሆን፤ የቃጠሎው መነሻ ከሬዲዮ መገናኛ አንቴና ጋር የተያያዘ እንደሆነ በምርመራ ተረጋገጠ፡፡ የእንግሊዝ የአየር አደጋ ምርመራ ክፍል ትናንት ባወጣው ሪፖርት፤ ከአውሮፕላኑ ጭራ አካባቢ የተተከለው አንቴና በመደበኛ በረራ ላይ አገልግሎት የማይሰጥ መጠባበቂያ አንቴና መሆኑን ገልጿል፡፡ የራሱ አነስተኛ ባትሪ ጋር የተገጠሙ አንቴና ላይ በሽቦዎች መጠላለፍ አልያም ባትሪው ላይ በተፈጠረ አንዳች እክል እሳት እንደተፈጠረ የምርመራ ክፍሉ ገልፆ፤ በተጨማሪ ምርመራ ትክክለኛው መንስኤ ከነመፍትሔው እስኪታወቅ ድረስ፣ መጠባበቂያውን አንቴና ለጊዜው በማላቀቅ አውሮፕላኖች ያለ ስጋት መብረር ይችላሉ ብሏል፡፡
አዲሱና ዘመናዊው ድሪም ላይነር (“B787”) ከወራት በፊት በዋናው የባትሪ ማስቀመጫ ቦታ እሳት በመነሳቱ፣ በመላው አለም ሁሉም “B787” አውሮፕላኖች ከበረራ ታግደው መቆየታቸው ይታወሳል፡፡ ባትሪው ላይ የዲዛይን ማሻሻያ ተደርጐ አውሮፕላኖቹ ወደ በረራ ከተመለሱ በኋላ እንደገና ተጨማሪ ችግር መፈጠሩ የቦይንግ ኩባንያን እና እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ የ (“B787”) ቀዳሚ ተጠቃሚ ደንበኞች በእጅጉ አሳስቧቸው ነበር፡፡ ባለፈው አርብ የተፈጠረው ችግር ለክፉ የሚሰጥ እንዳልሆነ በምርመራ ተረጋግጦ ትናንት በይፋ ከተነገረ ወዲህ፣ የቦይንግ የአክሲዮን ዋጋ ወዲያውኑ እንዳንሰራራ ተገልጿል፡፡
ለዓለም ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ዝግጅት ግልፅ አይደለም
ከወር በኋላ በራሽያዋ መዲና ሞስኮ ለሚካሄደው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ምርጫ እና ዝግጅት በተመለከተ በግልፅ የታወቀ ነገር የለም፡፡ ኬንያ ተሳታፊ ቡድኗ ለመምረጥ ባዘጋጀችው ብሄራዊ ሻምፒዮና ላይ ሰሞኑን ከፍተኛ ትኩረት አድርጋ ቆይታለች፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን በዓለም ሻምፒዮናው በስንት የውድድር መደቦች እንደሚሳተፍ እና ስንት አትሌቶችን እንደሚልክ አለማሳወቁየሚኖረውን ዝግጅት እንዳያስተጓጉል ተሰግቷል፡፡ ከወር በፊት በአሜሪካ ዩጂን በተደረገው የፕሮፈንታይኔ ክላሲክስ ውድድር በ10ሺ ሜትር በሁለቱም ፆታዎች ለዓለም ሻምፒዮናው የሚመረጡ አትሌቶችን ለመለየት ፌደሬሽኑ ተጠቅሞበታል፡፡ ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ከሚጠይቀው ሚኒማ ባሻገር በየውድድር መደቡ ለሁሉቱም ፆታዎች ለእያንዳንዳቸው ሶስት ምርጥ አትሌቶችን ለመመልመል ስለሚከተለው አሰራር ግልፅ መረጃ አለመኖሩ ግን የሚያሳስብ ይሆናል፡፡
በዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ውጤታማ የሆኑ አትሌቶች በዓለም ሻምፒዮናው የዝግጅት ወቅት ካለባቸው የውድድር መደራረብ አንፃር ብቃታቸው የወደ እንዳይሆን ያሰጋል፡፡ በትልልቅ የዓለም ማራቶን ውድድሮች ያሸነፉ በርካታ ማራቶኒስቶች መኖራቸውም ለምርጫ ማስቸገሩ አይቀርም፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮናው በምታሳትፈው ቡድን ምርጫ ላይ ውስብስብ ችግሮች እንደሚኖሩም ይገመታል፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ኬንያ የዓለም ሻምፒዮና ተሳታፊ ቡድኗን የምትመርጥበት አይነት ተመሳሳይ ብሄራዊ ሻምፒዮናን በአሰላ ከተማ በሚገኘው አረንጓዴ ስታድዬም ማካሄዱ አይዘነጋም፡፡ ከ35 በላይ የክልል፤የከተማ መስተዳድሮችን፤ የክለብ እና የብሄራዊ ቡድን ውክልና ያላቸው 1070 አትሌቶችን ያሳተፈው ብሄራዊ ውድድር በጋራድ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ አብይ ስፖንሰርነት 42ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በሚል ስያሜ የተዘጋጀ ነበር፡፡ የመከላከያ አትሌቲክስ ቡድን አጠቃላይ አሸናፊ በሆነበት ብሄራዊ ሻምፒዮናው በ5 የስፖርት አይነቶች ብሄራዊ ሪከርዶች ከመሻሻላቸውም በላይከ1 በላይ የወርቅ ሜዳልያ የተጎናፀፉ 5 አትሌቶችም ተገኝተውበታል፡፡
ይሁንና ይህ ብሄራዊ ሻምፒዮና በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያን ስለሚወክለው ቡድን ምንም የሰጠው ፍንጭ አልነበረም፡፡ በተያያዘ ግን የኬንያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የሚሳተፉ አትሌቶችን ለመመልመል ዓመታዊ ብሄራዊ ሻምፒዮናውን ዛሬ በናይሮቢ ከተማ በሚገኘው ናያዮ ስታድዬም ያካሂዳል፡፡ ብሄራዊ ሻምፒዮናው ምርጥ እና ልምድ ያላቸው ፤ወጣት እና አዳዲስ አትሌቶችን በዓለም ሻምፒዮናው ቡድን ለማካተት የተዘጋጀ እንደሆነ ሲታወቅ በኬንያ ከፍተኛ ተመልካች የሚያገኝ የአትሌቲክስ ውድድር እንደሆነና ሳፍሪኮም በተባለ የቴሌኮም ኩባንያ በ23ሺ ዶላር የስፖንሰርሺፕ ድጋፍ እንደተዘጋጀ ተገልጿል፡፡ በዚሁ ሻምፒዮና በ10 የአትሌቲክስ ስፖርቶች መሳተፍ እንዲችሉ አስፈላጊውን ሚኒማ ያሟሉ፤ ከሁለት ዓመት በፊት የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆኑ 192 አትሌቶች (132 ወንድ እና 60 ሴት) ጥሪ የቀረበላቸው ሲሆን በየውድድር አይነቱ አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ማግኘት የሚችሉት በቀጥታ ለዓለም ሻምፒዮናው ቡድን የመመረጥ እድል እንዳላቸው ታውቋል፡፡ በብሄራዊ ሻምፒዮናው 3ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች አስቀድሞ በነበራቸው ውጤት ግምገማ ተደርጎ የመመረጥ እድል ይኖራቸዋል ተብሏል፡፡ በብሄራዊ ሻምፒዮናው የተመረጡ አትሌቶች ከአንድ ሳምንት በኋላ በካሳራኒ በሚገኘው የመኖርያ እና የልምምድ ካምፕ በመግባት የመጨረሻ ዝግጅታቸውን ያደርጋሉ፡፡
ኬንያ ለዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በመካከለኛ ርቀት፤ በ5ሺ ሜትርና በ10ሺ ሜትር ውድድሮች እና በማራቶን ከፍተኛ ውጤት ለማስመዝገብ የሚበቃ የቡድን ስብስብ እንደሚኖራት ትጠብቃለች፡፡ አይኤኤኤፍ ሰሞኑን እንዳስታወቀው ከ200 አገራት የተወከሉ 2000 አትሌቶች የሚሳተፉበት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በመላው ዓለም በሚኖረው የቀጥታ ቴሌቭዥን ስርጭት በሪከርድነት የሚመዘገብ ተመልካች ያገኛል፡፡ በርካታ የዓለም ክፍሎችን በቴሌቭዥን ስርጭት ለማዳረስ ስምምነቶች መደረጋቸውን የገለፀው ዓለም አቀፉ የአትሌቲክሰ ፌደሬሽኖች ማህበር ለ9 ቀናት የሚካሄደው የዓለም ሻምፒዮናው በ200 አገራት ሽፋን እንደሚኖረውና የሚያገኘው ድምር ተመልካች እስከ 5 ቢሊዮን እንደሚገመት አስታውቋል፡፡ ከ2 አመት በፊት በደቡብ ኮርያ ዳጉ ተደርጎ በነበረው 13ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኬንያ 47 አትሌቶችን በማሳተፍ በ17 ሜዳልያዎች (7 የወርቅ፤ 6 የብርና 4 የነሐስ) ከዓለም ሶስተኛ ከአፍሪካ 1ኛ ደረጃ አግኝታ እንደነበር ሲታወስ፤ ኢትዮጵያ በ34 አትሌቶች ተካፍላ 5 ሜዳልያዎችን (1 የወርቅና 4 የነሐስ) በማግኘት ከዓለም ዘጠነኛ ከአፍሪካ ሁለተኛ ነበረች፡፡ ባላፉት 13 የዓለም ሻምፒዮናዎች ደግሞ ኬንያ በተሳትፎ ታሪኳ በሰበሰበቻቸው 100 ሜዳልያዎች (38 የወርቅ፤ 33 የብርና 29 የነሐስ) ከዓለም በሶስተኛ ደረጃ ላይ ስትመዘገብ፤ ኢትዮጵያ በ54 ሜዳልያዎች(19 የወርቅ፤ 16 የብርና 19 የነሐስ) 7ኛ ላይ ናት፡፡
“መልክዐ ስብሀት” ሰኞ ይመረቃል
በደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ አርታኢነት ሰላሳ ፀሐፍት ገጣሚያንና ሰዓሊያን በስብሐት ገብረእግዚብሔር ህይወትና ሥራ ላይ ያቀረቧቸው ፅሁፎች የተካተቱበት “መልክዐ ስብሀት” የተሰኘ መጽሐፍ የፊታችን ሰኞ በ11 ሰዓት በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ መፅሐፉ በደራሲ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር ሥራና ህይወት ላይ የሚያተኩር እንደሆነ ታውቋል፡፡
ፅሁፎቻቸው በመፅሐፉ ከተካተቱ ፀሐፍት መካከል ሃያሲ አስፋው ዳምጤ፣ ቴዎድሮስ ገብሬ፣ ሌሊሳ ግርማ፣ አዳም ረታ፣ ኢዮብ ካሣ፣ ሚካኤል ሽፈራው፣ ነቢይ መኮንን፣ አልአዛር ኬ፣ አውግቸው ተረፈ የሚገኙበት ሲሆን ከሰዓሊያን ደግሞ በቀለ መኮንን፣ ፍፁም ውብሸት፣ ቴዲማን ተካትተዋል፡፡
መፅሐፉ ሲመረቅ ነቢይ መኮንን፣ ታገል ሰይፉ፣ በቀለ መኮንን፣ ተፈሪ አለሙ እና ሌሎችም ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡
“መልክዐ” በሚል ቅድመ ግንድ ተከታታይ መፅሐፍት ለመታተም መታቀዱንና “መልክዐ ፀጋዬ ገብረመድህን” በዝግጅት ላይ መሆኑን የገለፀው አርታኢው፤ ስለ ስብሃት የታተመው “መልክዐ ስብሐት” መድበል ሚዛናዊነቱን የጠበቀ እንዲሆን ጥረት መደረጉን ተናግሯል፡፡
ፈንዲቃ የባህል ቡድን በሞንታና ፎልክ ፌስቲቫል ይሳተፋል
ትናንት በተከፈተው የሞንታና ፎልክ ፌስቲቫል ፈንዲቃ የባህል ቡድን ኢትዮጵያን በመወከል እንደሚሳተፍ ተገለፀ፡፡ ከ200 አገራት የተውጣጡ የሙዚቃ ቡድኖችና የፋሽን ባለሙያዎች የሚሳተፉበት ዓለም አቀፉ የሙዚቃ ፌስቲቫል እስከ 31 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የንግድ ስራዎች የሚንቀሳቀስበትና ከ16ሺ በላይ ጎብኝዎች የሚገኙበት ነው፡፡ ፈንዲቃ የኢትዮጵያ አዝማሪ ባንድ እና የባህል ውዝዋዜ ቡድን ሲሆን ስድስት ሙዚቀኞች፤ ሁለት ተወዛወዦች እና አንድ ድምፃዊን በማቀፍ በሞንታና ፎልክ የሙዚቃ ፌስቲቫል በመሳተፍ የአገር ባህልን በማስተዋወቅ ከፍተኛ ትኩረት ያገኛል ተብሏል፡፡ ፈንዲቃ የባህል ቡድን ከአምስት ዓመት በፊት በተወዛዋዥነቱና በባህል አምባሳደርነቱ በሚታወቀው አርቲስት መላኩ በላይ እንደተመሰረተ ይታወቃል፡፡
“ከልጆች ዓለም” ስብስብ ተረቶች ለገበያ ቀረበ
አዳዲስና ነባር የልጆች ተረቶች የተካተቱበት “የልጆች ዓለም” መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ ዝግጅትና ቅንብሩ በመብራቱ ካሳ የተሰራው መጽሐፍ በሥዕሎች የታጀበ ሆኖ 85 ገፆች አሉት፡፡ በነጭ ሳር ማተሚያ ድርጅት የታተመው “ከልጆች ዓለም” በ25 ብር ከ30 ለገበያ ቀርቧል፡፡
“ስኬታማ የጊዜ አጠቃቀም” እና “ራስን ማወቅ” እየተሸጡ ነው
በአለን ሌከን ተፅፎ አባተ መንግሥቱ የተረጐመው “ስኬታማ የጊዜ አጠቃቀም” እየተሸጠ ነው፡፡ በውጤታማ የጊዜ አጠቃቀም ዙርያ የተፃፈው መፅሐፍ ኤችኬ ፐብሊሺንግ የታተመ ሲሆን ዋጋው 25 ብር ከ35 ነው፡፡የመጽሐፉን የአርትኦት ስራ ደራሲና ሃያሲ መስፍን ሃብተማርያም ነው የሰራው፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሮቢን ሻርማ “The Monk Who Sold His Ferrari” በብርሃኑ በላቸው “ራስን ማወቅ” በሚል ርዕስ ተተርጉሞ ለገበያ የበቃ ሲሆን በ35 ብርም እየተሸጠ ነው፡፡ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመው መፅሐፉ፤ 176 ገፆች አሉት፡፡ መፅሐፉን መገናኛ አካባቢ የሚገኘው ዩኒቲ መፃህፍት መደብር እንሚያከፋፍል ታውቋል፡፡
“እኔና ቄስ ገንዘቤ” እና “የሸገር ወጐች” ለንባብ በቁ
በወይንሸት መርከቡ የተደረሱ አምስት አጫጭር ልቦለዶች የተካተቱበት “እኔና ቄስ ገንዘቤ” የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ለንባብ በቃ፡፡ በመፅሐፉ “እኔና ቄስ ገንዘቤ” ባለ አራት ክፍል አጭር ልቦለድ እንዲሁም “ማትሪክ”፣ “አቢይ እና አባይ”፣ “ኮሌጅ” እና “ይድረስ ለፈጣሪ” የተሰኙ ሌሎች አጫጭር ልቦለዶች ተካተውበታል፡፡ 118 ገፅ ያለው መፅሐፉ ባናዊ ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን ዋጋው ለሀገር ውስጥ 25 ብር፣ ለውጭ ሀገራት 10 ዶላር ነው፡፡ በሰሎሞን ታደሰ የተደረሱ ወጐችና እውነተኛ ታሪኮች የተካተቱበት “የሸገር ወጐች እና እውነተኛ ታሪኮች” መፅሐፍ እንዲሁ ለንባብ በቅቷል፡፡ በመፅሐፉ “የሸገር ወጐች”፣ “መጣንላችሁ ማሳጆች”፣ “የጨለሙ ታሪኮች በዱባይ” እና ሌሎች ታሪኮች ተካተዋል፡፡ ደራሲው ካሁን በፊት “ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ አብቅቷል፡፡ “የሸገር ወጐች” በ39.50 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
የማይክል ጃክሰን አሟሟትና የፍርድ ሂደቱ ተወሳስቧል
በሙዚቃው ንጉስ ማይክል ጃክሰን አሟሟት ላይ በተመሰረተ ክስ የተጀመረው የፍርድ ሂደት 10ኛ ሳምንቱን ሲይዝ ሁኔታዎች እየተወሳሰቡ መምጣታቸውን ዘገባዎች አመለከቱ፡፡ ታዋቂው የኮንሰርት አዘጋጅ ኤኢጂ ላይቭ ለአሟሟቱ ተጠያቂ መሆን አለበት በሚል የማይክል ካትሪን ጃክሰን እና ቤተሰባቸው ክስ እንደመሰረቱ ሲታወቅ፤ በክሱ የ40 ቢሊዮን ዶላር ካሳ የከፈለን በሚል እየተሟገቱ ናቸው፡፡ ማይክል ጃክሰን ከአምስት ዓመት በፊት ከመጠኑ ያለፈ መድሃኒት በመውሰድ ለድንገተኛ ሞት መብቃቱ የሚታወስ ሲሆን የተጠየቀው ካሳ አርቲስቱ በ50 ዓመቱ እድሜው ህይወቱ ባያልፍ ኖሮ በኮንሰርት ስራዎች እና በአልበም ሽያጭ ሊያገኝ የሚችለው ገቢን በማስላት የተተመነ ነው፡፡ የግሉ ሃኪም የነበሩት ዶክተር ኮናርድ ሙራይ ለሞቱ መንስኤ የሆነ መድሃኒት ያለጥንቃቄ ሰጥተዋል በሚል ክስ ተጠያቂ መደረጋቸው ይታወቃል፡፡ አሁን በተጀመረው የፍርድ ክርክር ደግሞ የኮንሰርት አዘጋጁ ኤኢጂ ላይቭ ታላቁን ሙዚቀኛ አላግባብ ትኩረት በመንፈግ ከሞት አደጋው ሳይታደጉ ቀርተዋል በሚል ተከስሰዋል፡፡ የኤኢጂ ጠበቃዎች ማይክል ጃክሰን ለሞት የተዳረገው ራሱ በቀጠረው እና በወር እስከ 150ሺ ዶላር በሚከፍለው የግሉ ሃኪም ስህተት እንጂ ከሚያቀርበው ዓለም አቀፍ ኮንሰርት በተያያዘ አለመሆኑን በመግለፅ የክስ መከላከያቸውን አቅርበዋል፡፡
ኤኢጂ ላይቭ የማይክል የግል ሀኪም የነበሩትን ዶክተር ኮናርድ ሙራይ አልቀጠርኩም ብሎ ከመካዱም በላይ ለሞቱ ምን ሃላፊነት የለብኝም ይላል፡፡የማይክል ቤተሰብ በጉዳዩ ላይ 97 ምስክሮችን እንዲሁም ኤኢጂ ላይቭ ደግሞ 113 ምስክሮችን ለክስ መከላከያው በማቅረብ ለወራት በጉዳዩ ላይ በመሟገት ይቀጥላሉ፡፡ በሌላ ዜና ማይክል ጃክሰን በሞቱ ማግስት በ500 ሚሊዮን ዶላር እዳ ተይዞ እንደነበር ያስታወሰው ሴሌብሪቲኔይዎርዝ ከዚህ እዳው ሙሉለሙሉ ነፃ መውጣቱን አስታውቋል፡፡ የማይክል ጃክሰን ሃብት ንብረትን ለመሰብሰብ ቤተሰቡ ለጠበቆች እስከ 13.6 ሚሊዮን ዶላር መክፈላቸውን ያወሳው ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ የሃብት መጠኑ 600 ሚሊዮን ዶላር እንደሚደርስ አመልክቷል፡፡ ማይክል ጃክሰን በኑዛዜው ከሃብት ንብረቱ 40 በመቶውን ለልጆቹ፤ 40 በመቶውን ለእናቱ እና ቀሪውን 20 በመቶ ለበጎ አድራጎት መለገሱ ሲታወቅ እናቱ ካተሪን ጃክሰን ከመየርሳቸውን ድርሻ ልጆቹ እንዲወርሱ መናዘዙን ለማወቅ ተችሏል፡፡
50 ሴንት አምስት ዓመት በሚያሳስር ጥፋት ተከሰሰ
ታዋቂው ራፐር 50 ሴንት በቀድሞ ፍቅረኛው ላይ አድርሷል በተባለ ጥቃት ሊከሰስ ነው፡፡ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ የአምስት አመት እስርና የ46ሺ ዶላር ካሳ እንዲከፍል እንደሚወሰንበት የቢልቦርድ ዘገባ አመልክቷል፡፡ 50 ሴንት ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ ቀድሞ ፍቅረኛው የኮንዶሚኒዬም መኖርያ በመሄድ ጥቃት ማድረሱ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ከፈፀመው ፆታዊ ጥቃት ጋር በትችት መወጠሩ ሳያንሰው ራፐሩ በስልክና በፅሁፍ መልዕክት የ16 ዓመት ልጁን በማስፈራራቱም እየተብጠለጠለ ነው፡፡ ራፐሩ ከታዳጊ ልጁ ጋር በስልክ ባደረገው ንግግር “የእናትህ ልጅ እንጂ የእኔ አይደለህም፡፡ ገና የደም ምርመራ ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እንደ እናትህ እና እንደ ቤተሰብህ ከእኔ የምትፈልገው ስጦታ ብቻ ነው፡፡ ከእንግዲህ ግን ምንም እንዳትጠብቅ፡፡ ስልኬን ሰርዘው፡፡ ሁለተኛም እንዳትደውልልኝ” ብሎታል፡፡
ቢልቦርድ መፅሄት እንደዘገበው፤ ራፐሩ በቀድሞ ፍቅረኛው እና በልጁ ላይ የፈፀማቸው ተግባራት ገፅታውን እያበላሸበት ነው፡፡ በሌላ በኩል ፊፍቲ ሴንት ከሙዚቃው ባሻገር በተሰማራበት ንግድ እጅግ ትርፋማ እየሆነ መምጣቱን ያመለከተው ሂፖፕ ኒውስ፤ በ260 ሚሊዮን ዶላር ከአምስቱ የዓለም ሃብታም ራፐሮች አንዱ ሊሆን እንደበቃ ጠቁሟል፡፡ ለ50 ሴንት ሃብት ማደግ በዋናነት “ቪታሚን ዎተር” በተባለው የውሃ ምርት አምራች ኩባንያ ያዋለው ኢንቨስትመንት ትርፋማነት መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ ‹ጂ ዩኒት› በተባለው የፋሽንና የሙዚቃ ኩባንያው እንዲሁም በፊልም ስቱድዮው እና በተለያዩ የማስታወቂያ ስራዎችም የተወጣለት ነጋዴ መሆኑን አብራርቷል፡፡
‹‹...የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ለእድሜልክ...››
• እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ከሆኑ ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ • ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ይበልጥ የሚመረጠው እናቶቹ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተለሰለፍ ለመታደግ ሲባል የአለምአቀፉ የጤና ድርጅትን ጨምሮ በየአህጉሩ ያሉ ብሔራዊ ተቋማት እና ሌሎች አለምአቀፋዊ ድርጅቶችን ጨምሮ የተለያዩ ጥረቶች መደረግ ከጀመረ ሰንበትበት ብሎአል፡፡ የሚወለዱ ሕጻናት ከእናቶ ቻቸው የኤችአይቪ ቫይረስን እንዳይወስዱ ለማድረግ የሚያስችሉ ግኝ ቶች እና አሰራሮች በመዘርጋታቸው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ሕጻናትን ማዋለድ ተችሎአል፡፡ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት በእርግዝና ፣በምጥ ፣በመው ለድ ወይንም ጡት በማጥባት ሲሆን ስርጭቱም ከ25-45 % የሰፋ ነው፡፡
የኤችአይቪ ቫይረስን ስርጭት ለመግታት አስቸኩዋይ እቅድ የማወጣት ፕሮግራም ወይንም ደግሞ pepfar (ፔፕፋር) ተብሎ የሚጠራው ሰፊ ፕሮግራም ባወጣው መረጃ መሰረት የዛሬ አራት አመት ገደማ በአለም ላይ ወደ 390,000- (ሶስት መቶ ዘጠና ሺህ) የሚጠጉ ህጻናት ከቫይረሱ ጋር ተወል ደዋል፡፡ ከእነዚህ ህጻናት ውስጥ 90 % የሚ ሆኑት ከሰሃራ በታች ያሉ ሀገራትን ጨምሮ በ22/ ሀገሮች ውስጥ የተወለዱ ናቸው፡፡ ባደጉት ሀገሮች ውስጥ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት ሙሉ ለሙሉ ተገትቶአል ማለት የሚያስችለው የ pepfar ጥናት በእርግዝና ጊዜ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒትን ትክለኛ የሆነ አጠቃቀምና ከወሊድ በሁዋላ ጡት ባለማጥባት ቀጥተኛ የሆነውን የቫይረሱን ስርጭት እስከ 5 % ድረስ መቀነስ ይቻላል ብሎአል፡፡ pepfar የዛሬ ሶስት አመት ባደረገው ዘመቻ መሰረት 9.8/ ሚሊዮን የሚሆኑ እር ጉዝ ሴቶች የኤችአይቪ ምርመራ እንዲያደርጉ ከእነዚያ ውስጥ 660,000/ያህሉ ቫይረሱ በደማ ቸው ተገኝቶ ነበር፡፡ እነዚህ እናቶች ቫይረሱን ወደልጆቻቸው እንዳያስተላልፉ ሲባል ART የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት እንዲወስዱ ተደርጎአል፡፡
ይህ በመሆኑ ከ200,000/ (ሁለት መቶ ሺህ .. በላይ የሆኑ ሕጻናት ከኤችአይቪ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ እድሉ ተፈጥሮአል፡፡ ከእናታቸው በቀጥታ ቫይረሱን የተቀበሉ ሕጻናት በሕይወት የሚቆዩት ቢበዛ እስከ ሁለት አመት እድሜያቸው ድረስ ነው፡፡ ከኤድስ ነጻ የሆነ ትውልድን ለማፍራት የሚደረገው እርብርብ አ.ኤ.አ በ2015/ ለታቀደው የሚሊኒየም ግብ 90% የሚሆነውን ከእናት ወደልጅ የሚተላለፈውን የቫይረሱን ስርጭት ይገታል የሚል ተስፋ አለ፡፡ ሕጻናት የኤችአይቪ ቫይረስን ከእናታቸው እንዳይወርሱ ከሚያስችለው አለምአቀ ፋዊ ጥረት መካከል እርጉዝ የሆኑ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኘ በቀጥታ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን እንዲወስዱ ማድረግ ይገኝበታል፡፡ ይህም በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በተግባር ላይ እንዲውል የሚያስችል አሰራር የተዘረጋ ሲሆን ይህንን በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጡን የጋበዝነው ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ ናቸው፡፡ ዶ/ር ታደሰ እንደሚገልጹት በኢትዮጵያ ላለፉት አስር አመታት በላይ ኤችአይቪ ከእናቶች ወደ ልጆች እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚያስችል አሰራር በተግባር ውሎአል፡፡ አሰራሩን አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለመለወጥና ከኤችአይቪ ነጻ የሆነ ትውልድ ለማፍራት እንዲያስችል የተለየ አገልግሎት በየጤና ተቋማቱ እንዲሰጥ በመደረግ ላይ ነው፡፡ ይህ አገልግሎትም ከአሁን ቀደም ቫይረሱ ያለባቸውን እርጉዝ ሴቶች በመለየት ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ጸረኤችአይቪ መድሀኒት ይሰጥ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ግን የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ለእድሜልክ እንዲሆን ተወስኖአል፡፡
የዚህ አላማም ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ከማድረግ ባሻገር እናት ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ሌሎች ሕመሞችን እንዳትታመም እና የእራስዋን ጤንነት ለመጠበቅ እንዲያስችላት ነው፡፡ስለዚህም እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ፖዘቲቭ የሆኑት ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ እርጉዝ ሴቶችም ሆኑ ሌሎች ሰዎች በደማቸው ኤችአይቪ ቫይረስ የሚገኝ ከሆነ የሰውነታቸው የመከላል አቅም እና በሰዎቹ ላይ የተከሰተውን የተለያየ ሕመም መሰረት በማድረግ ቫይረሱ ያለበት ደረጃ ከታየ በሁዋላ ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት መውሰድ የሚገባቸውንና የማይገባቸውን በመለየት መድሀኒቱ ይሰጥ እንደነበር ይታወሳል፡፡ አሁን ግን እናቶቹ የሰውነት የመከላከል አቅማቸው ያለበት ደረጃ በምርመራ እንዲታወቅ የሚደረግ ሲሆን ያ የሚደረገው ግን ፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን ለመጀመር ሳይሆን የጤንነታቸው ሁኔታ ያለበትን ደረጃ ለማወቅ እና ክትትሉን ለማድረግ እንዲያስችል ሲባል ነው፡፡ ፀረ ኤችአ ይቪ መድሀኒትን ቀድሞ መጀመር ከኤችአይቪ ጋር ተያይዘው የሚመጡ የተለያዩ በሽታዎችን እንዳይኖሩ ከማድረግ በተጨማሪ እናቶቹ ለረጅም ጊዜ ጤንነታቸው ተጠብቆ እንዲኖሩ ፣የሚወልዱዋቸው ሕጻናትም ከቫይረሱ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ ይረዳቸዋል፡፡ ዶ/ር ታደሰ ከተማ እንደገለጹት እናቶች የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርገው አሰራር ኤችአይቪን በተመለከተ ልዩ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል በተባሉ 22/ ሀገራት ተሞክሮ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን በተለይም ማላዊ የተሳካ ልምድ ያገኘችበት ነው፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ለእናቶች ጤና ተገቢው እና ትክክለኛው ነው በሚል እንዲተገበር ብዙ አገራትን እያማከረ እና አቅጣጫን እያስያዘ ያለበት አሰራር በመሆኑ በኢትዮጵያም ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚሰጠው አገልግሎት በደረጃ ሊከፋፈል የሚችል ነው፡፡ •በእርግዝና ወቅት እናቶች የእርግዝና ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ •የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት መስጠት፣ •እናቶች በጤና ተቋማት እንዲወልዱ ማድረግ፣ •ከኤችአይቪ ፖዘቲቭ እናቶች የተወለዱት ሕጻናት ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ እናቶች የእርግዝና ክትትል የማድረጋቸው ሁኔታ ቀደም ካሉት ጊዜያት የተሸሻለ ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ወደ 20 % የነበረው የእር ግዝና ክትትል ዛሬ ወደ 80% ደርሶአል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ከ35 -45 % የማያንሱ እናቶች የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት ያገኛሉ፡፡ በአገሪቱ በአጠቃላይ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብሎ ከሚገመቱት ወደ 34000/ እናቶች ውስጥ 42 % የሚሆኑት ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡
ከተወለዱት ልጆችም የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው የሚገኙ የመኖራቸውን ያህል በተለይም ቤተሰቦች ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ የሚያቋርጡ በመሆኑ እንደ አንድ ችግር የሚታይ ነው፡፡ አንዳንድ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ የሆኑ እናቶችም የህክምና ክትትላቸውን በትክክል ሳያቋርጡ የማይከታተሉ በመሆኑ በዚህ ረገድ ገና ብዙ መሰራት የሚጠበቅበት ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ምንም እንኩዋን ከነበረበት ሁኔታ የተሸሻለ ነገር ይታያል ቢባልም በአጠቃላይ አላማው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ልጆችን ማዋለድ ሲሆን ይህንን ግን በትክክል ለማወቅ የሚያስችል አካሄድ እስከአሁን ማግኘት አልተቻለም፡፡ እ.ኤ.አ በ2011/ የተሰራ አገር አቀፍ ጥናት እንደሚጠቁመው በኢትዮጵያ ውስጥ ቀደም ሲል የነበረው የቫይረስ ስርጭት እየቀነሰ መምጣቱን ያመላክታል፡፡
በዚህም ጥናት መሰረት ቀደም ሲል ወደ 3% የነበረው አሁን 1.5% በሚል ሊጠቀስ እንደሚችል ጥናቱ ያሳያል፡፡ ቀደም ሲል ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብለው የሚገመቱ እናቶች ቁጥር ወደ 80,000/ እና 90,000/ ገደማ የነበረ ሲሆን በዚህ ጥናት የታየው ግን ከ34,000 ብዙም የማይበልጡ እናቶች ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ የሚል ግምት አለው፡፡ ይህም የግንዛቤ ማስጨበጥን ስራ እና በተለያዩ ተቋማት የሚሰሩ ስራዎችን ውጤታማ አካሄድ የሚያ ሳይ ሲሆን እነዚህ አካላት ወደፊትም ብዙ እንዲሰሩ የሚጠበቅበት ሁኔታ መኖሩ ግልጽ ነው ብለዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ፡፡ በእርግዝና ክትትል ወቅት ኤችአይቪ በደማቸወ ውስጥ የተገኘባቸው እናቶች ቁጥር እና ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒትን ተጠቃሚ የሆኑት ቁጥር በፊት ከነበረበት 25% አሁን ወደ 42% ደርሶአል፡፡ ስለዚህ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኝ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ይሁኑ ሲባል ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይ ተላለፍ እና እናቶችም ጤንነታቸው በተጠበቀ ሁኔታ ሕይወታቸውን እንዲቀጥሉ ለማስቻል መሆኑን ሁሉም ሊረዳው ይገባል፡፡
ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት ሶስት አመታት ውስጥ ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ወይም መተላለፉን ለማጥፋት እቅድ ይዘው እየሰሩ ካሉ አገሮች ውስጥ አንዱዋ ነች፡፡ ስለዚህም ይህንን አለማ እውን ከማድረግ አንጻር ይህ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒት ለሁሉም ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ለሆኑ እርጉዝ ሴቶች በዘለቄታዊ መንገድ መስጠት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ እንዳብራሩት፡፡