Administrator

Administrator

- የመፈንቅለ መንግስት ሴራ ተሸርቦብኛል፤ እስከመጨረሻው እታገላለሁ ብለዋል
በተለያዩ ውንጀላዎች የመከሰሳቸውና በስልጣን የመቆየታቸው ቀጣይ እጣ፣ ነገ በሚከናወን የምክር ቤቶች የድምጽ አሰጣጥ ስነ-ስርዓት የሚወሰንባቸው የብራዚል ፕሬዚዳንት ዲላማ ሩሴፍ፣ ከተጠያቂነት ነጻ ለመሆንና መንበራቸውን ላለማስነጠቅ እስከ መጨረሻዋ ደቂቃ ድረስ ተግተው እንደሚታገሉ ማስታወቃቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የአገሪቱን ኢኮኖሚ የተሻለ ደረጃ ላይ ያደረሱ በማስመሰል ሃሰተኛ መረጃ አውጥተዋል፣ በሙስና ተዘፍቀዋል፣ በስልጣን ላይ ለመቆየት ሲሉ የበጀት ህጎችን ጥሰዋል  በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠማቸው ፕሬዚዳንቷ፤ ድርጊቱን አለመፈጸማቸውን በመግለጽ፣ ተቀናቃኞቼ መፈንቅለ መንግስት በማድረግ ያለ አግባብ ስልጣኔን ለመቀማት የሸረቡብኝ ሴራ ነው፤ ድምጽ አሰጣጡ አግባብ ባለመሆኑ እስከመጨረሻው እታገለዋለሁ ሲሉ መናገራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
65 አባላት ያለው የአገሪቱ የኮንግረስ ኮሚቴ ሰኞ ዕለት በአብላጫ ድምጽ ባሳለፈው ውሳኔ በስልጣን ቆይታቸው ላይ ድምጽ እንዲሰጥበት የተወሰነባቸው ፕሬዚዳንት ዲላማ ሩሴፍ፣ የመፈንቅለ መንግስት ሴራ ሸርበውብኛል ብለው ከጠቀሷቸው ፖለቲከኞች መካከል ምክትል ፕሬዚዳንቱ ሚሼል ቴምር እንደሚገኙበት ታውቋል፡፡
ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠማቸው ዲላማ ሩሴፍ ከሚመሩት ጥምር መንግስት ውስጥ ራሳቸውን ማግለላቸውን ማክሰኞ እለት ያስታወቁ ሁለት ፓርቲዎች፣ ነገ በሚደረገው ድምጽ አሰጣጥ ላይ ሴትዮዋ ስልጣን ይልቀቁ በሚል ድምጻቸውን እንደሚሰጡ መግለጻቸውንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
ፕሬዚዳንቷ ከስልጣን እንዲለቁ የሚፈልጉ በሺዎች የሚቆጠሩ ብራዚላውያን ውሳኔውን በደስታ መቀበላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በአንጻሩ የፕሬዚዳንቷ ደጋፊዎች የሆኑ በርካቶችም ጉዳዩን የፖለቲካ ጠላቶች የፈጸሙት ህገወጥ የስልጣን ቅሚያ ነው በማለት አውግዘውታል ብሏል፡፡
በአመት 2015 ነዳጅን ጨምሮ የተለያዩ የአገሪቱ ሸቀጦች ዋጋ መቀነሱን ተከትሎ፣ የብራዚል ኢኮኖሚ ባለፉት ከ30 በላይ አመታት ታሪኩ በከፋ ቀውስ መመታቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ የዋጋ ግሽበት ባለፉት 12 አመታት ከፍተኛው ደረጃ ላይ መድረሱንና የስራ አጥነት በ9 በመቶ ማደጉን፣ ይህም የፕሪዚዳንቷን አስተዳደር ክፉኛ ማስተቸቱን ገልጧል፡፡
ነገ አመሻሽ ላይ ይፋ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው በአገሪቱ ምክር ቤቶች በየደረጃው የሚከናወኑ ድምጽ አሰጣጦች አጠቃላይ ውጤት፣ የፕሬዚዳንቷን ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ይወስነዋል ተብሏል፡፡

 የአለማችን ረጅሙ ህንጻ የሆነውና 828 ሜትር ቁመት ያለው ቡርጂ ከሊፋ መገኛ የሆነቺው ዱባይ፣ በቁመቱ አዲስ የአለም ክብረወሰን እንደሚያስመዘግብ የተነገረለትን አዲስ ሰማይ ጠቀስ ህንጻ በ1 ቢሊዮን ዶላር ወጪ ለመገንባት ማቀዷን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ እጅግ ያማረ የስነ-ህንጻ ጥበብ የተገለጠበት ነው የተባለውን የዚህን ሰማይ ጠቀስ ህንጻ ግንባታ ፕሮጀክት የያዘው “ኢማር ፕሮፐርቲስ” የተባለው ተቋራጭ ኩባንያ ስለሚገነባው አዲስ ህንጻ ቁመት ባይገልጽም፣ ግንባታው በአራት አመት ጊዜ ውስጥ ተጠናቅቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር አስታውቋል፡፡
20 የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ወለሎች፣ ሬስቶራንቶች፣ የመኖሪያ ክፍሎች፣ ሆቴልና ሌሎችን ይይዛል የተባለውንና የዱባይን ገጽታ ሙሉ ለሙሉ ሊያሳይ የሚችል ማማ ያለውን ይህን ህንጻ ዲዛይን ያደረገው ስፔናዊው የኪነ-ህንፃ ባለሙያ ካልትራቫ ቫልስ ሲሆን፣ የሚገነባውም በዱባይ መካከለኛ ስፍራ ላይ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡
በቁመቱ እርዝማኔ የአለማችንን ክብረወሰን ይዞ የሚገኘው የዱባዩ ሰማይ ጠቀስ ህንጻ ቡርጂ ከሊፋ፣ ለግንባታው 1.5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ እንደተደረገበትና በ2010 መጀመሪያ ላይ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 - የ8 አመት ህጻንን ለአጥፍቶ መጥፋት አሰማርቷል

     በምዕራብ አፍሪካ አገራት የሽብር ተግባራት መፈጸሙን አጠናክሮ የቀጠለው ጽንፈኛው ቡድን ቦኮ ሃራም፤ በተለያዩ አካባቢዎች ለአጥፍቶ መጥፋት ተግባር የሚያሰማራቸው ህጻናት ቁጥር ባለፈው አመት በ11 እጥፍ እንዳደገ ዩኒሴፍ መግለፁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ዩኒሴፍ ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው ሪፖርቱ እንዳለው፣ ቦኮ ሃራም ባለፉት ሁለት አመታት በናይጀሪያ፣ በካሜሩንና በቻድ በፈጸማቸው የሽብር ጥቃቶች ላይ ካሰማራቸው አጥፍቶ ጠፊዎች መካከል 20 በመቶ የሚሆኑት ህጻናት ሲሆኑ አብዛኞቹም ሴቶች ናቸው፡፡ ቦኮ ሃራም ለሽብር ተግባሩ የሚመለምላቸውና ለጥቃት የሚያሰማራቸው ህጻናት ቁጥር እየጨመረ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ በ2014 አራት ህጻናትን በአጥፍቶ መጥፋት ጥቃት ላይ ያሰማራው ቡድኑ፣ ድርጊቱን በማጠናከር ባለፈው አመት 44 ህጻናትን ለጥቃት ማሰማራቱን አስታውቋል፡፡ ቡድኑ በአጥፍቶ መጥፋት ጥቃት ካሰማራው ህጻናት መካከል ዝቅተኛውን ዕድሜ የያዘው የ8 አመት ህጻን እንደሆነ ዩኒሴፍ ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ ቡድኑ በናይጀሪያ፣ ካሜሩን፣ ቻድ እና ኒጀር በፈጸማቸው የሽብር ጥቃቶች ሳቢያ 1.3 ሚሊዮን ህጻናት ከመኖሪያ ቤታቸው መፈናቀላቸውንና 670 ሺህ ያህሉም ትምህርታቸውን ማቋረጣቸውን አመልክቷል፡፡

 - የአውሮፓ ታላላቅ ባንኮች የከፋ ችግር ውስጥ ገብተዋል
     - የእንግሊዝ ከህብረቱ አባልነት መውጣት፣ በአህጉሪቱ ቀውስ ሊፈጥር ይችላል ተብሏል

    አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ የአውሮፓ አህጉር በገንዘብ ቀውስ ልትመታ እንደምትችል ሰሞኑን ባወጣው የግማሽ አመት አለማቀፍ የገንዘብ ሁኔታ ሪፖርት፣ ማስጠንቀቁንና በአለማቀፉ የገንዘብ መረጋጋት ላይ የተጋረጡ አደጋዎች ተባብሰዋል ማለቱን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡ በአውሮፓ አገራት ከሚገኙ ባንኮች አንድ ሶስተኛ የሚሆኑት ትርፋማ ሆነው እንዳይቀጥሉ በሚያግዷቸው የከፉ ችግሮች መተብተባቸውን ያስታወቀው ተቋሙ፣ በአገራቱ ባንኮች ላይ የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታት አፋጣኝ እርምጃዎች መወሰድ እንዳለበት አሳስቧል፡፡
ባለፈው የካቲት ወር ላይ በአህጉሪቱ በተከሰቱ የባንክ ቀውሶች ክፉኛ ከተጎዱት መካከል፣ የግሪክ፣ የጣሊያንና የፖርቹጋል ባንኮች እንደሚገኙባቸው ያስታወሰው ተቋሙ፣ እየተባባሰ የቀጠለው የገንዘብ ቀውሱ በመላ አህጉሪቱ የሚገኙ ባንኮችን ተጠቂ ሊያደርግ እንደሚችልም አስጠንቅቋል፡፡ ቢቢሲ በበኩሉ አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም ባወጣው አለማቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ትንበያ ሪፖርት፣ ለረጅም ጊዚያት አዝጋሚ ሆኖ የዘለቀው የአለማችን ኢኮኖሚ እድገት ዘንድሮም 3.2 በመቶ ብቻ ሊያድግ እንደሚችል በመጥቀስ፣ የአለም ኢኮኖሚ ለአደጋ የበለጠ ተጋላጭ ሆኗል ማለቱን ዘግቧል፡፡
በዘንድሮው አመት ከአለማችን አገራት የኢኮኖሚ እድገቷ በከፍተኛ ሁኔታ ይቀንሳል ተብሎ የምትጠበቀው ናይጀሪያ ናት ያለው ዘገባው፤ ብራዚል፣ ሩስያና ሌሎች በርካታ የአለማችን አገራትም ዘንድሮ ያስመዘግቡታል ተብሎ ከተገመተው የኢኮኖሚ እድገት ያነሰ እድገት እንደሚያስመዘግቡ ይጠበቃል መባሉንም ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜናም እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት አባልነት መውጣቷ በአካባቢው አገራትና በአለማቀፍ ደረጃ የከፋ አደጋ ሊያስከትል ይችላል ሲል አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይ ኤም ኤፍ ማስጠንቀቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ የእንግሊዝ ከህብረቱ አባልነት መውጣት ለረጅም ጊዜ የዘለቁ የንግድ ግንኙነቶችን ከማቃወሱ በተጨማሪ ለእንግሊዝም ሆነ ለተቀሩት የአውሮፓ አገራት ፈታኝ ሁኔታዎችን ይፈጥራል ያለው ተቋሙ፣ በጉዳዩ ዙሪያ የተካሄደው ህዝበ ውሳኔ በኢንቨስተሮች ዘንድ ያለመተማመን ስሜት መፍጠሩንም ገልጧል፡፡

Saturday, 16 April 2016 11:09

የቢዝነስ ጥግ

 (ስለ ደንበኞች)
የቢዝነስ ዓላማ ደንበኞችን የሚፈጥር ደንበኛ መፍጠር ነው፡፡
ፒተር ድራከር
ትክክልም ይሁን ስህተት፣ ሁልጊዜም ደንበኛ  ትክክል ነው፡፡
ማርሻል ፊልድ
ደሞዝ የሚከፍለው ቀጣሪው አይደለም። ቀጣሪዎች የሚያደርጉት ገንዘቡን ማስተዳደር ብቻ ነው፡፡ ደሞዝ የሚከፍለው ደንበኛው ነው፡፡
ሔነሪ ፎርድ
ደንበኞች ፍፁም እንድትሆን አይጠብቁህም። እነሱ የሚጠብቁት ነገሮች ሲበላሹ እንድታቀናቸው ነው፡፡
ዶናልድ ፖርተር
ደንበኛህን የታሪክህ ጀግና አድርገው፡፡
አን ሃንድሌይ
አንድ አለቃ ብቻ ነው ያለው፡፡ ደንበኛችን። ገንዘቡን ሌላ ቦታ በማጥፋት ብቻ በኩባንያው ውስጥ ያሉትን ሠራተኞች በሙሉ ከዋና ሥራ አስፈፃሚው እስከ ዝቅተኛው ተቀጣሪ ድረስ ከሥራ ሊያባርር ይችላል፡፡
ሳም ዋልተን
ደንበኞችህን ካልተንከባከብካቸው ሌላው ይንከባከባቸዋል፡፡
ያልታወቀ ሰው
ሁሉም ነገር ከደንበኛ ይጀምራል፡፡
ሎዩ ገርስትነር
ትህትና የተመላበት አያያዝ ደንበኛውን ተጓዥ ማስታወቂያ ያደርገዋል፡፡
ጄ.ሲ.ፔኒ
የደንበኛ አገልግሎት አንድ ዲፓርትመንት አይደለም፡፡ አመለካከት ነው፡፡
ያልታወቀ ሰው
አንድን ደንበኛ ለማግኘት ወራት ይፈጃል፤ ለማጣት ግን ሰኮንዶች ይበቃሉ፡፡
ክላንትጌሪችዜይድ
የደንበኛ አገልግሎት ብቸኛ ዓላማው ስሜትን መለወጥ ነው፡፡
ሴዝ ጐኮን    

Saturday, 16 April 2016 11:02

የፀሃፍት ጥግ

(ስለ ትርጉም)
ፀሃፍት በቋንቋቸው አገር አቀፍ ሥነ ፅሁፍፉን ይፈጥራሉ፤ የዓለም ሥነ ፅሁፍ የሚፃፈው ግን በተርጓሚዎች ነው፡፡
ጆሴ ሳራማጎ
ትርጉም ባይኖር በአገሬ ድንበር ተወስኜ እቀር ነበር፡፡ ተርጓሚ በጣም አስፈላጊ አጋሬ ነው፡፡ ለዓለም ያስተዋውቀኛል፡፡
ኢታሎ ካልቪኖ
ተርጓሚ እንደሚተረጉመው ደራሲ መሆን አለበት፤ ከደራሲው መላቅ የእሱ ስራ አይደለም፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
ትርጉም የውድቀት ጥበብ ነው፡፡
ዩምቤርቶ ኢኮ
ትርጉም የዓለም ሥነ ፅሁፍ የዝውውር ሥርዓት ነው፡፡
ሱሳን ሶንታግ
ትርጉም የቃላት ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ አንድን ሙሉ ባህል አንባቢው እንዲረዳው የማድረግ ጉዳይም ጭምር ነው፡፡
አንቶኒ በርጌስ
የትርጉም ጥበብ፤ ታሪክንና የሰው ልጅ አዕምሮን የመመልከቺያ መስኮት ይከፍታል፡፡
“ፋውንድ ኢን ትራንስሌሽን”
ተርጓሚዎች እንደ ወይን ጠጅ ናቸው፤ አሪፍ ለመሆን ጊዜ ይፈልጋሉ፤ ከእርካሾቹ የምታተርፉት ራስ ምታት ብቻ ነው፡፡
ትርጉም ባይኖር ኖሮ በዝምታ በተከለሉ ግዛቶች ነበር የምንኖረው፡፡
ጆርጅ ስቴይነር
ትርጉም እንደ ሴት ነው፡፡ ውብ ከሆነ ታማኝ አይደለም፡፡ ታማኝ ከሆነ በእርግጠኝነት ውብ አይደለም፡፡
ይቭጌኒ ይቭቱሼንኮ
ትርጉም ለእኔ እንደዘበት የምሰራው ነገር ነው፤ ምክንያቱም በልጅነቴ ከጀርመንኛ ወደ እንግሊዝኛ ተተርጉሜአለሁ፡፡
ማይክል ሃምቡርገር

Saturday, 16 April 2016 10:59

የዘላለም ጥግ

(ስለ ዕውቀት)
• እውቀት ምን እንደሚናገሩ ማወቅ ሲሆን
ጥበብ መቼ እንደሚናገሩ ማወቅ ነው፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
• ግሩም ውሳኔ በዕውቀት ላይ እንጂ በቁጥር
ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ብሬይኒ
• በዕውቀት ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት
እጅግ የላቀውን ወለድ ያስከፍላል፡፡
ቤንጃሚን ፍራንክሊን
• ለዕውቀት ባለህ ጥማት በመረጃዎች
አለመስመጥህን እርግጠኛ ሁን፡፡
አንቶኒ ጄ.ዲ አንጄሎ
• ሳይንስ የተደራጀ ዕውቀት ነው፡፡ ጥበብ
የተደራጀ ህይወት ነው፡፡
አማኑኤል ካንት
• በመረጃ ውስጥ እየሰጠምን ነው፡፡ ነገር ግን
ዕውቀትን ተርበናል፡፡
Quotesaday.com
• መረጃ ዕውቀት አይደለም፤ ዕውቀት ጥበብ
አይደለም፤ ጥበብ እውነት አይደለም፤
እውነት ውበት አይደለም፤ ውበት ፍቅር
አይደለም፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
• እውቀት ከመማር ይመጣል፡፡ ብልህነት ከኑሮ
ይገኛል፡፡
አንቶኒ ዳግላስ ዊሊያምስ
• የእውቀት ብቸኛ ምንጭ የህይወት ልምድ
ነው፡፡
አልበርት አንስታይን
• ከሃሰተኛ ዕውቀት ተጠንቀቅ፤ ከድንቁርና
የበለጠ አደገኛ ነው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው
• ጥርጣሬ የዕውቀት ቁልፉ ነው፡፡
ምሳሌያዊ አባባል
• እውቀት ለብልህ ሰው ሃብቱ ነው፡፡
ዊሊያም ፔን
• እውቀት መሳሪያ ነው፡፡ ጦርነት ከመጀመርህ
በፊት ራስህን በቅጡ አስታጥቅ፡፡
ጆርጅ አር. አር. ማርቲን
• መማር ዕውቀት የመሰብሰብ ጉዳይ ነው፤
ጠቢብነት ያንን ዕውቀት መጠቀም ነው፡፡
ሩፕሊን


Saturday, 16 April 2016 10:52

ማራኪ አንቀጽ

    ባለብዙ ቀለምዋ ሕይወት ብዙ ጠብታዎች አሏት - እንደ ሻማ ቀልጠው ብርሃናቸው ካበቃ በኋላ በዘመን ሰም ተወልውለው የሚቀመጡ። … ብርሃን የአንድ ጊዜ ፍንደቃ፣ ጨለማም የአንድ ጊዜ ድብርት ይሁን እንጂ በሰው ልጅ ልብ ውስጥ የመቆየትና እየተፍለቀለቁ ወይም እየሰቀቁ የመኖር ዐቅማቸው ብዙ ነው። ሕይወት በአንድ ትከሻ ጎመን የነሰነሰ ጎጆ፣ በሌላው ደግሞ ጮማ የተንተራሰ ቪላ አዝላ ስትሄድ በዚያ መንገዳገድ ውስጥ  ለሚያልፈው አዳም በልቡ  የምትጽፋቸው ውሎች አሉ። … ውበትና ፉንጋነት!
እኔም በልጅ ልብ የሚኖሩ … በወጣትነት ዘመን እንደ እሳተ ገሞራ እየተንፈቀፈቁ የሚወጡ ግንፍል ስሜቶች የሚታፈኑበትን፣ ማኅበረ-ፖለቲካዊ፣ … ማኅበረ-ባህላዊና ማኅበረ-ታሪካዊ ቀውሶች የነበሩበትን ትውልድና ምጡን፣ ደመና የዋጠው ድምፁንና ሣቁን፣ ደረቅ ሳሉንና አልደርቅ ያለ እንባውን ለማሰብና ለማስታወስ ነፍሴ ግድ ብላኛለች። ምናልባትም ታላቁ አሜሪካዊ ደራሲ፣መምህርና ሃያሲ ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን -በእግሮቻችን እንሄዳለን፤በእጆቻችን እንሰራለን፤የአእምሯችንን እንናገራለን” እንደሚል ውስጤ ያለውን ማውጣት ግድ ብሎኛል፡፡  
… ከፊል ዘመነኞቼን ያሰብኩበት ብሔራዊ ውትድርናና የብላቴውን የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎችን ሕይወትና የሀገሪቱን ምስቅልቅል፣ … በሌላ በኩል ደግሞ የቀዳሚዎቹን ዘመነኞች ጡንቻማ ፍልሚያ ወላፈን ከሕፃናት ሕይወት ጋር እጅ ለእጅ ለማጨባበጥና ለማስታወስ ፈዛዛ ምስሎች በትንሷ ኪሴ ወሽቄያለሁ። የማላውቀውን ዘመን ነፋስ ስሜት በሩቁ እንጂ እጄን በመስደድ እልፍኙን አልደፈርኩም።
… ግን ደግሞ የክብር ዘውድ ሊደፋባቸው የሚገባ ጭንቅላቶች ላይ የተጎነጎነውን የሾህ አክሊል አለማሰብ አልተቻለኝምና ጥላሸት በለበሰው የትዝታ ፋኖሴ ትንሽ ጭላንጭል ለኩሻለሁ።
ከሁሉ  ይልቅ አበባነት ውስጥ ያሉ ትንንሽ የሕይወት እንጎቻዎች በትንሷ ምጣድ ላይ ተጋግረው፣ በመዓዛቸው ድንበር ዐልፈው እንዲመጡ፣ አጥር ዘልለው እንዲያፏጩ … ቅጥሩን ዝቅ አድርጌላቸዋለሁ ብዬ አምናለሁ። … በዚህም በጾታዊ ፍቅር የሚንከባለሉ ከረሜላ ልቦች … ሰማይ የሚቧጭሩ ሀገራዊ ምኞቶች … ክንፍ ሳያወጡ በእንቁላልነታቸው እቅፍ ሥር ለባከኑ ሕልሞች … እንባ ያነቃቸው ሣቆች በታሪኩ ተራራ ላይ እንደ ሰንደቅ  ተተክለዋል።
(ከደረጀ በላይነህ “የደመና ሳቆች” የተሰኘ አዲስ ረዥም ልብወለድ መግቢያ ላይ የተቀነጨበ)

     በኩዌት በቤት ሰራተኛነት ተቀጥራ የምትሰራ ስሟ ያልተጠቀሰ ኢትዮጵያዊት፣ የአሰሪዎቿን  ቤተሰቦች የሰው ስጋ ይበላሉ ስትል መክሰሷን ገልፍ ዲጂታል ኒውስ የተባለው ድረገጽ ዘገበ፡፡ሳላዋ በተባለው የአገሪቱ አውራጃ በቤት ሰራተኛነት ተቀጥራ የምትሰራው ኢትዮጵያዊቷ፣ በአሰሪዎቿ   መኖሪያ ቤት ውስጥ የሰው ራስ ቅል ተደብቆ ማየቷን በመጥቀስ ለፖሊስ አቤቱታዋን ያቀረበች ሲሆን፣ የአካባቢው ፖሊስም ጉዳዩን ለማጣራት ወደ አሰሪዎቹ በሄደበት ወቅት፣ የቤቱን በር የሚከፍትለት ሰው ማጣቱን ዘገባው ገልጧል፡፡ ፖሊስ ጉዳዩን በመመርመር ላይ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ የምርመራ ቡድኑ ምናልባትም ኢትዮጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ ከአሰሪዎቿ የደረሰባትን በደል ለመበቀል ያደረገቺው ድርጊት ሊሆን ይችላል፣ አልያም የአእምሮ ጤንነቷ የተዛባ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት መያዙን አስታውቋል፡፡

ይድረስ ለኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር
ሰሞኑን ሥርጭቱን በጀመረው “ቃና ቲቪ” ይዘት እና አሰራር ላይ ለመወያየት በደብዳቤ
ባሳወቅናችሁ መሰረት ተወካያችሁን መላካችሁ ይታወቃል፡፡  የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበር ተወካዮቹ (የእናንተም ባሉበት) በተጠቀሰው ጉዳይ ለሁለት የተለያዩ  ቀናት የጋራ ውይይት አካሂደው የጋራ የአቋም መግለጫ ማውጣታቸው ይታወቃል፡፡ ይህ የጋራ  አቋም በፅሁፍና በንባብ ለሚዲያ ከመቅረቡ በፊት የእናንተ ሁለት ተወካዮችን ጨምሮ የሁሉም   የሞያ ማኅበር ተወካዮች መስመር በመስመር በጥንቃቄ ተመልክተው ማሻሻያና ማረሚያ ካደረጉ  በኋላ በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫው የተሰጠ መሆኑ አይዘነጋም፡፡ መግለጫ ከመሰጠቱ አንድ ቀን ቀደም  ብሎ (በ20/07/2008) የደራስያን ማኅበር ልሳን በሆነውና ዘወትር ማክሰኞ ምሽት በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 በሚቀርበው ፕሮግራም ላይ የመግለጫውን ፍሬ ሃሳብ ለህዝብ በመግለፅ ሚዲያዎች እንዲገኙ መረጃ ስታደርሱ እንደነበርም ይታወቃል፡፡ይህ ጥሬ ሀቅ ባለበት ሁኔታ ባለፈው ቅዳሜ ሚያዚያ 1 ቀን 2003 ዓ.ም በወጣው የአዲስ አድማስ  ጋዜጣ ላይ የደራስያን ማኅበር ፕሬዝደንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ የሰጡት ከእውነት የራቀና የተዛባ  መግለጫ እጅግ የሚያሳፍርና የሚያሳዝን ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ የመላው የደራስያን ማኅበር አመራርና አባላት እምነት እንዳልሆነም እናምናለን፡፡ የእሳቸው ማኅበር ተወካይና ሌሎች የጥበብ ማኅበራት በጋራ ተወያይተው ያወጡትን መግለጫ በምን ምክንያትና መነሳሳት ለመካድ እንዳነሳሳቸው ለጊዜው ያወቅነው ነገር የለም፡፡ በሂደቱ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ሲሳተፍ የነበረውን የማኅበራቸውን ተወካይ፤ “መግለጫውን ለመከታተል የተገኘ ነው” በማለት ከደራሲያን ማኅበር ተወካይነት ወደ ሚዲያ ተወካይነት ለውጠው፣ ለጋዜጣው ለመግለፅ ለምን እንደተገደዱም አልተረዳንም፡፡ ከዚህም በላይ ማህበራቱ የቴሌቪዥን ጣቢያውን በሚመለከት እያቀረቡት ካለው አመክንዮና ለህዝብ ከገለፁት አቋም ፈፅሞ የራቀና የማናውቀውን ጉዳይ በመናገር አንባቢን ግራ ከማጋባታቸውም በላይ የማኅበራቱን ጥያቄ ያልተገባ ለማስመሰል መሞከራቸው ከምን በመነጨ አስተሳሰብና ዓላማ እንደሆነ ለጊዜው አልደረስንበትም፡፡ በእሳቸውና በመላው የጋዜጣዊ መግለጫው ተሳታፊ በነበሩ የሚዲያ አካላት እጅ በሚገኘው ባለ አምስት ገፁ የሞያ ማኅበራቱ የአቋም መግለጫ በየትኛው አንቀፅ ላይ ይሆን የሳንሱር ጉዳይ የተነሳው!? የኢትዮጵያ ደራስያንን እወክላለሁ የሚል
የማኅበር ፕሬዚደንት የተፃፈን ፅሑፍ አንብቦ መረዳት ተሳነው ቢባልስ ማን ያምን ይሆን!? የሆነስ
ሆነና “እነ በዓሉ ግርማን የመሳሰሉ ፀሐፍት በሳንሱር ምክንያት የሕይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል”
ማለታቸውስ የደራስያን ጉዳይ ጉዳዬ ነው ብሎ የፕሬዚደንትነት ሥልጣን ከተቆናጠጠ ግለሰብ ይጠበቃል ወይ!? ሌላው ቢቀር የደራስያን ማኅበር የአመራር አባል በነበረው ደራሲ እንዳለጌታ  ከበደ ጥልቅ ጥናትና ምርምር የታተሙትን “ማዕቀብ” እና “የበዓሉ ግርማ ሕይወትና ሥራዎች” የተሰኙ በብዙዎች የተነበቡ መፃሕፍትን ቢያነቡ ኖሮ በዓሉ ግርማን ጨምሮ በኢትዮጵያ ውስጥ በሳንሱር ምክንያት የሕይወት መስዋዕትነት የከፈለ (የተገደለ) አንድም ደራሲ እንደሌለ በተረዱ ነበር፡፡ እንደሚታወቀው የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበራቱ በመግለጫቸው ያሉት ዋና ፍሬ ሀሳብ ዶ/ር ሙሴ በስህተት አልያም በችኮላ ተረድተው እንዳሉት ሳይሆን “ቃና” ቴሌቪዥን ለውጭ ሀገር ፕሮግራሞች የሰጠው (70%) ተገቢ አይደለም የሚል ነው፡፡ ይህ ሀሳብ የሳንሱር ሳይሆን በሀገር ውስጥ፣ በሀገር አቅም በሚሰሩ ፊልሞች ላይ ጫና ፈጥሮ ፍትሀዊ ተወዳዳሪነት እንዳይኖር በማድረግ፣ ዳዴ በማለት ላይ ያለውንና የብዙ ዓይነት ጥበቦችና ባለሙያዎች ውህደት ውጤት የሆነውን የኢትዮጵያ ሲኒማ አቀጭጮ ያጠፋል፣ አዲስ ለሚከፈቱ ጣቢያዎች በቀላሉና በውስን ሰዎች ሳይለፉ ገንዘብ እንደሚሰራ በማሳየት በመስኩ የተሰማሩ የኢትዮጵያ ዜጎች በሀገራቸው ስለ ሀገራቸው ጉዳይ የሚተርክ ፊልም በመስራት እንዳይጠቀሙና ሞያውን እንዳያሳድጉ እንቅፋት ይሆናል፣ ህዝብን የሚያረካ ሥራን የሰሩና ይሁንታን በማግኘት የተደነቁ ባለሙያዎችም ዝናቸውን በመጠቀም የደሀ
ህዝባቸውን ችግር ለመቅረፍ በሚደረጉ የማኅበራዊ አገልግሎቶች ላይ የሚያደርጉትን በጎ እንቅስቃሴና ቅስቀሳ ተፅዕኖ አልባ በማድረግ ያዳፍነዋል የሚል ነው፡፡ በእግረ መንገድም ፊልሞቹ በአብዛኛው ከምዕራባውያን የሚመጡ እንደመሆናቸውና የሚተላለፈው ለቤተሰብ ቅርብ በሆነው የቴሌቪዥን ሚዲያ በኩል ከመሆኑ አንፃር አጉል ባህል በቀላሉ ታዳጊ ህፃናትና ልጆች ላይ እንዳይሰርፅ ሥጋታችንን የገለፅንበት ነው፡፡ የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበራቱ በጋራ ባካሄዱት ውይይት ዶ/ር ሙሴ የእሳቸውን ማኅበር በመወከል በተገኘው ግለሰብ እምነት ከሌላቸው፣ ከቢሮአቸው በአራት እርምጃ ከሚርቀው የጋራ ማኅበራቱ
መሰብሰቢያ ቢሮ በመምጣት ጉዳዩን ማጣራት ይችሉ ነበር፡፡ አልያም በአሁን ሰዓት የደራስያን አመራር አባል የሆኑት የሥራ ባልደረባቸው በዚሁ ጋዜጣ ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፃፉትን ጥልቅና ለብዙዎች ስለ ጉዳዩ የበለጠ ግንዛቤ ያስጨበጠ ፅሑፍ ቢቻል አንብበው ካልሆነም ካነበበ ሰምተው አስተያየታቸውን ቢሰጡ ኖሮ ትዝብት ላይ የሚጥል ስህተት ባልሰሩ፣ መልካም ሥም የነበረውን ማኅበራቸውንም ባላቀለሉ ነበር እንላለን፡፡
(ተፃፈ፡- ከ “የኢትዮጵያ  የኪነ ጥበብ ማኅበራት
ጊዜያዊ አስተባባሪ”)