Administrator

Administrator

ካለፈው አመት ጀምሮ መቅረብ የጀመረው “ግጥምን በማሲንቆ” ባለፈው ሳምንት በጎንደር ተካሄደ፡፡ ለሁለተኛ ጊዜ ጐንደር ከተማ በሚገኘው አፄ በካፋ ሆቴል አዳራሽ የተካሄደው ፕሮግራሙ፣  በየአመቱ በወርሃ ጥር በጥምቀት መዳረሻ ላይ እንደሚካሄድ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ገጣሚ ትዕግስት ሲሳይ ተናግራለች፡፡ በዝግጅቱ ላይ ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ጌትነት እንየው፣ ገጣሚና ጋዜጠኛ ባንቻየሁ አለሙና በርካታ ወጣት  ገጣሚያን ስራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ ግጥምና ማሲንቆ አንዳቸው ያለ አንዳቸው መኖር አይችሉም ያለችው አዘጋጇ፣ፕሮግራሙን የማስፋፋት አላማ እንዳላት ተናግራለች፡፡

አንዳንድ ዕውነተኛ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ የሚከተለው ትርክት እንዲያ ያለ ጠባይ አለው:-
ሰውየው እሥረኛ ነበሩ አሉ፡፡ በጥንት ዘመን፡፡ ዚቀኛ ናቸው - ነገር አዋቂ፡፡
እሥረኞች “የሻማ” የሚሉት ፈሊጥ አላቸው፡፡ የኢኮኖሚ እርዳታ ነው አንዱ፡፡ የመዝናኛ ጥያቄ ነው ሁለተኛው፡፡
ጠያቂው እሥረኛ - በምን ታሠሩ? አላቸው፡፡
አዲሱ እሥረኛ - አለቃዬ ጠፍቶ
ጠያቂው እሥረኛ - ለምን ጠፋ?
አዲሱ እሥረኛ - ለሠራዊት የመጣ የዩኒፎርም ጨርቅ ወደ መርካቶ አሻግሮ
ጠያቂው እሥረኛ - ታዲያ እርሶ ምን አገባዎት?
አዲሱ እሥረኛ - እሱ እስኪመጣ እዚህ ተቀመጥ ተብዬ ነው
ጠያቂው እሥረኛ - እሺ አሁን እርሶ ምንድነዎት ታዲያ ?
አዲሱ እሥረኛ - ቀብድ ነኛ!
ሁሉንም አሳቋቸው፡፡
እሥረኛው ዋሉ አደሩና ለምርመራ ተጠሩ፡፡
ሄደው ሲመለሱ ፊታቸው ቀልቷል፡፡ ንዴትና እልህ እየተናነቃቸው ነው! የሚቀርባቸው እሥረኛ ጠጋ ብሎ አነጋገራቸው፡፡
“ምነው ከፍቶዎታል?” አላቸው
“መርማሪው አበሳጨኝ!”
“ለምን?”
“ቀበሌህን ተናገር አለኝ - አላውቅም አልኩት”
“ምን ነካዎት አድራሻ መደበቅማ አይቻልም፡፡ መናገር ነበረብዎት!”
“እኔ እምቢ አልኩት - ስለማላምንበትም ነው፡፡ ጣጣው ብዙ ነው”
“እንዴት ነው የማያምኑበት”
“ቆይ ላጫውትህ… አንድ ልጅ ቄስ ት/ቤት ይማራል አሉ፡፡ አንድ ቀን ተገርፎ ወደቤቱ እያለቀሰ ይመጣል፡፡
እናቱ - “ምን ሆንክ ልጄ” ስትል ትጠይቀዋለች፡፡
ልጁም እየተነፋረቀ፤ “እኚህ የኔታ መቱኝ” ይላታል፡፡
“ምን አድርገሃቸው መቱህ?”
“ሀ በል ሲሉኝ ጊዜ እምቢ አልኳቸው”
“አንተ የሞትክ! ሀ ማለት አቅቶህ ትገረፋለህ?”
“አይ እማዬ የኔታን አታውቂያቸውም፡፡የየኔታ ጉዳቸው መች ያልቃል? - ሀ ስትይ ሁ በይ ይሉሻል። ሁ ስትይ ሂ በይ ይሉሻል…እንዲህ እያሉ እስከ “ፐ” ያለፉሻል!...”
*    *    *
ጣጣው የማያልቅ ችግር ለትውልድ ይተርፋል፡፡ በትምህርት ከሀ እስከ ፐ መጓዝ የማይናቅ መሆኑ ባይካድም፤ ውጣ - ውረዱ፣ መከራው ሰቆቃው አይጣል ነው፡፡ ችግርን ከምንጩ መንቀል ብልህነት ነው። ከፊደልም ከህይወትም መማር ሙሉ ያደርገናል፡፡ ለለውጥ ዝግጁ የምንሆነው አንድም ዕውቀታችን ወደ ጥበብ ሲበስል፤ አንድም ለአዲስ ነገር አዕምሮአችን ክፍት ሲሆን፤እንዲሁም ከስህተታችን ለመማር እንችል ዘንድ ግትርነትን ስናስወግድ ነው፡፡
በሀገራችን የታሪክ ሂደት፤ ትግል፣ ድርድር፣ ዕርቅና ስምምነት፣ ጠቅልሎ ገብቶ ከመንግሥት ጋር መሥራት፣ መጣላትና መክዳት አዘውትረው የታዩ ክስተቶች ናቸው፡፡
በተለይ መከዳዳት እጅግ ተደጋግሞ የታየ ነው፡፡
“ወዳጅን አንዴ መክዳት ይቻላል ሁለት ጊዜ ግን አይቻልም” ceasy to rat but not to re – rat) ይላሉ ዊንስተን ቸርችል፡፡ ትግል ሲከር፣ ዘመን ሲከዳ፣ አቋም ሲሟሽሽ፣ ተስፋ ሲጠፋ፣ በተለይም ወኔ ሲከዳ፤ አሊያም አቋም ሲለወጥ፤ እናት - ክፍልን ትቶ ወደሌላ ሠፈር ይገባል፡፡
መደራደር፣ ዕርቅና መስማማት ከጦርነት እኩል ሜዳ ላይ ናቸው ይባላል፡፡ ጂኬ ቴስተርተን እንደሚለን “መደራደርና መስማማት ማለት ግማሽ ዳቦ ማግኘት ከምንም ይሻላል ነበር፡፡ አሁን ግን በዘመናዊ መንግሥታት ዘንድ ግማሽ ዳቦ ከሙሉ ዳቦ ይሻላል በሚል ተለውጧል”፡፡ ተደራድሮ አንድ ነገር ማግኘት ታላቅ ነገር ነው፡፡ ሆኖም መደራደርን እጅ ከመስጠትና ከክዳት ለይቶ ማየት ያሻል፡፡ ከማጐብደድ መለየት የስፈልጋል፡፡
ደራሲና ፀሐፌ - ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን “በምኒልክ” ተውኔቱ ያለውን አለመርሳት ደግ ነው። “ሸዋም ያው ያባት ልምዱን፣ የባህል ግብሩን፣ በጐበና ሹመት ላይ አጉተመተመ፡፡ አጉረመረመ፡፡ ያኑ የሆድ ክፋት ቅርሱን፣ ምሱን፣ የምቀኛ ተውሳኩን፣ ውስጥ ውስጡን አቀረሸ፡፡ “ማናቸውን ንጉሥ እንበል?!” እያለ፤ ይሄ አዲሱ ጐበና፣ የልቼው ሳይሆን፣ ራሱን እንደንጉሥ ላስጠራ ባይ ተቆናኝ ሆኗል፤ መሾሙንስ ምኒልክ ሾመው፣ መሻሩንስ ማን ይሽርለት ይሆን? እያለ…”
ወገን ሳይኖር፣ አጋር ሳይኖር፣ በዙሪያ ደግ - አሳቢ ሳይኖር፤ ሹመት የዛፍ ላይ እንቅልፍ ነው! በእርግጥ አያሌ ከእናት ፓርቲያቸው የተለያዩ የጥንት የጧት ሰዎች እናውቃለን፡፡ ምናልባትም እነሱም የራሳቸው ምክንያት ይኖራቸው ይሆናል፡፡ ለአንድ የእንግሊዝ ፓርላማ ቀዳማዊት ኤልሣቤጥ አደረጉት የሚባል ንግግር ላይ “እንደኔ ከሆነ፤ ለምን መኖርን መውደድ እንዳለብኝ ወይም ለምን መሞትን መፍራት እንዳለብኝ አንዳችም ምክንያት የለኝም፡፡ የዚህችን ዐለም በቂ ልምድ አግኝቻለሁ፡፡ ዜጋ መሆንም፤ መሪ መሆንም ምን ማለት እንደሆነ አውቄያለሁ፡፡ መጥፎም ጥሩም ጐረቤት ኖሮኝ ያውቃል፡፡ ስለዚህ በራሴ ዕምነት መክዳት ጥሩ እንደሆን ተገንዝቤአለሁ፤ ብለዋል፡፡ ደግና ክፉ መለየት ያለበት ራሱ ባለቤቱ ነው።
የዱሮም ይሁን የአሁን ወዳጅ፣ ከጊዜ በኋላ፤ አቋም ለውጠው ሲገናኙ እንዴት እንደሚገናኙ፣  እንዴት እንደሚወያዩ፤ ግራ ሊገባቸው ይችላል፡፡ ሆድ ለሆድ ተግባብተው? ተቂያቂመው? ወይስ ይቅር ለእግዚሃር ተባብለው፤ ስለአገር ጉዳይ ተስማምተን እንሥራ ተባብለው?
በየትኛውም የሹመት ደረጃ ብንሆን፤ አገርን የሚጐዳ ከሆነ ሥልጣን በቃኝ ማለት መክዳት አይደለም የእንግሊዝ ተወላጁ የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዴ ሀይለኛ ግምገማ ተደርጐ አይምሬ የሆነ ግልጽ ሂስ ሲካሄድባቸው፤ “እኔምኮ ዶሮ እስኪጮህ ነበር የምጠብቀው ሥልጣኔን ለመልቀቅ” አሉ፤ አሉ፡፡ የፖለቲካ ሥልጣንን፤ ተዋግተንም እናምጣው፣ በሰላማዊ ድርድር፤ አሊያም ደጅ ጠንተን፤ ዳገት ቁልቁለት የሌለበት፣ በወርቅ አልጋ፣ በእርግብ ላባ ላይ መተኛት ነው ብሎ ማሰብ፤ ቢያንስ የዋኅነት ነው። “ሳያሽ የጐረሠ ዝንጀሮ በሳል ይመታል” ማለት ይሄው ነው፡፡

የቻይና አምባሳደር ሞባይላቸውን ስለመሰረቃቸው ምን ይላሉ ?  
በጥምቀት በዓል በስርቆት ላይ ከተሰማሩት መካከል 26ቱ ተይዘዋል
 የጽዳት ችግር እንዳለ አምነዋል፣ “ከተማዋን  ጽዱ ለማድረግ እየሰራን ነው”
በየአዝማሪው ቤት በህፃናት ማስታወቂያ የሚያሰሩ ቢራ ፋብሪካዎችን ወቅሰዋል   

አቶ ጌትነት አማረ ይባላሉ፡፡ የጐንደር ከተማ ከንቲባ ናቸው፡፡ ባለፈው ዓመት በምርጫ ተወዳድረው ከንቲባ ከመሆናቸው በፊት ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ  በምክትል ከንቲባነትና በተቀዳሚ ምክትል ከንቲባነት አገልግለዋል፡፡ በቢዝነስ አድሚንስትሬሽንና በዴቨሎፕመንት ማኔጅመንት ሁለት ዲግሪዎች ያገኙት ከንቲባው በኧርባን ማኔጅመንት ደግሞ የማስተርስ ድግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት ለጥምቀት በዓል ወደ ጎንደር የሄደችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ የከተማዋን ከንቲባ አቶ ጌትነት አማረን በቢሮቸው አግኝታ በተለያዩ የከተማዋ ጉዳዮች ላይ አነጋግራቸዋለች፡፡  

ጐንደር  ባሏት ታሪካዊ  ቅርሶች የተነሳ በአለም አቀፍና በአገር ውስጥ ቱሪስቶች በየጊዜው የምትጎበኝ ከተማ ናት፡፡  ከተማዋና ህዝቧ ከቱሪዝም ምን ያህል ተጠቃሚ ሆነዋል ይላሉ?
እንዳልሽው በየጊዜው በቅርሶቿ ከመጐብኘቷም ባሻገር በወርሀ ጥር፣ ጥምቀት በድምቀት የሚከበርባት ከተማ ናት፡፡ በመሆኑም ህዝቡን የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ከማድረግና የከተማዋን ገጽታ ከመገንባት ባለፈ የአገር ውስጥና የውጭው አለም ጐበኚዎችን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም በማሰብ፣ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ የባህል ፌስቲቫል እያዘጋጀን ቆይተናል፡፡ በነዚህ ፌስቲቫሎች አገራችንን በደንብ ማስተዋወቅና የቱሪስቶችን ቁጥርም መጨመር ተችሏል፡፡ የቱሪስቶች የቆይታ ጊዜያቸውም አንፃራዊ በሆነ መልኩ እየጨመረ መጥቷል፡፡ ሰሞኑን አይተሽ ከሆነ----አዳዲስ ሆቴሎች፣ ሎጆች፣ የባህል ምሽት ቤቶች እየተገነቡና እየተከፈቱ ቢሆንም አሁንም በቂ አይደለም፣ አሁን ባለው ሁኔታ አልጋ በቀላሉ ማግኘት አይቻልም፡፡ የቱሪስት ቁጥር መጨመር፣ የቆይታ ጊዜው መራዘምና መሰል ነገሮች ለከተማዋም ሆነ ለነዋሪዎቿ ተጠቃሚነት መጨመር ጉልህ ሚና አላቸው፡፡ ለምሳሌ የታክሲና የባጃጅ ሹፌሮች ሰፊ ስራ ያገኛሉ፣ ባለሆቴሎች በምግብና በመኝታ በኩል ተጠቃሚ ናቸው፤ የባህል ቡና የሚያፈሉት፣ አዝማሪ ቤቶች፣ ሊስትሮ ሳይቀር-- የገቢ መጠኑ ይጨምራል። የስጦታ እቃ ሻጮች፣ ባህላዊ አልባሳትና ቁሳቁስ አምራቾችም እንዲሁ ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ ባለሀብቱ ሎጅና ትልልቅ ሆቴል ለመገንባት ፍላጐት እያሳየ በመሆኑ ለነዋሪው የስራ እድል በመፍጠርም ሚናው የጐላ ነው፡፡
ሰሞኑን በከተማዋ ሶስት በዓላት (ዝግጅቶች) ነበሩ፡፡ አንዱ አመታዊው “አገር አቀፍ” የባህል ፌስቲቫል ሲሆን ሁለተኛው “ኢትዮጵያን በጐንደር” የተሰኘ አመታዊ ካርኒቫል ነው ሶስተኛው ጥምቀት፡፡ በዓላት እንዲህ ሲደራረቡ ለጐብኚዎች የሚደረገውን መስተንግዶ ጥራት አይቀንሰውም ?
አንደኛው በዓል በቅንጅት የተከበረ ነው፡፡ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ በብሔራዊ የባህል ማዕከልና በጐንደር ከተማ አስተዳደርና ባህል ቱሪዝም መምሪያ ማለት ነው፡፡ እኛ ይህንን በዓል ስናከብር አንደኛ የባህል ፌስቲቫሉ ሲከበር ነበር። እኛ ከዚያ ቀደም ብለን “ኢትዮጵያን በጐንደርን” ስናከብር ቆይተናል፡፡ ዘንድሮ ለየት የሚያደርገው አንድ አይነት አላማ የያዘ በመሆኑና ከቀድሞው ትንሽ የእንግዳ ቁጥር መጨመሩ ነው፡፡ ሌላው ልዩነት ዘንድሮ ከዘጠኙ ክልል እና ከሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ሰዎች መጥተው የእንግዳውን ቁጥር በተወሰነ መጠን ጨምረውት ነበር፣ እግዚቢሽንም ነበር፣ ከዚያ በፊትም ባዛር ነበረ፡፡ ባዛሩ “አዘዞ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት” ለመገንባት የተዘጋጀ ነበር፡፡ እንዳልሽው በዓሉ ተደራራቢ ነው፤ አዎ ይሄ እርግጥ ነው፡፡ ነገር ግን የባህል ማዕከሉና የእኛ ከተማ አስተዳደር ያዘጋጀው በዓል በአብዛኛው ተመሳሳይ ነው፡፡ ቀጥሎ ጥምቀቱ ነው፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ፍላጐት ምንድነው--- የቱሪስቱ ቁጥርም ሆነ የከተማ አስተዳደሩ ቁጥር እንደሚጨምር ነው፡፡ በሌላው ዓለም ለምሳሌ ብራዚልን ብትወስጂ--- በሚዲያ እንደምንሰማው በዓመት አንዴ ለሳምንታት የሚያከብሩት ፌስቲቫል በዓመት ውስጥ የማይሰበስቡትን ገቢ ያገኙበታል፡፡ አላማውም ይሄው ነው፡፡
ሌላው አለም ምናልባትም በቂና የተደራጀ  የመስተንግዶ አገልግሎት የተሟላ ስለሚሆን በርካታ እንግዳ ቢጠራም  ተደራራቢ በዓላት ቢያዘጋጅም ችግር ላይገጥመው ይችላል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አዳጊ አገራት ግን የምንገነባውን ገጽታ እንዳናፈርሰው የሚያሰጋ ይመስለኛል ----
የሆስፒታሊቲውን ሁኔታ በተመለከተ አንዱና ዋነኛው ነገር፣ በባህልና ቱሪዝም በኩል አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በስልጠና ማገዝ፣ ሁለተኛ ሰርቪሱን መጨመር ከተቻለ ለጐንደር ከዚህም በላይ እንግዳ መጥራት ይቻላል፡፡ ጀማሪ ከመሆናቸው አኳያ በግንዛቤ እጥረትና በልምድ ማነስ የተነሳ መስተንግዷቸው አርኪ ላይሆን ይችላል እንጂ እንግዳው ስለበዛ፣ በዓል ስለተደራረበ ሆስፒታሊቲ መጥፎ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ግንዛቤና ልምድ ከሌለ ጥቂት እንግዳ መጥቶ መስተንግዶውና ሁኔታው ላይመቸውና ቆይታውንም ላያራዝም ይችላል፡፡ ስለዚህ ቀስ በቀስ በልምድና በስልጠና በሆስፒታሊቲ ዘርፍ የተሰማሩ ተቋማትን ማስተካከል ይቻላል፡፡ ለምሳሌ በ2003 ዓ.ም በተደረገው አጠቃላይ የመስተንግዶ ግምገማ፣ 2004 ዓ.ም እና 2005 ዓ.ም ላይ የተሻሉ የመስተንግዶ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ ከባለፈው ዓመት የዘንድሮው የተሻለ እንደሆነ አምናለሁ፣ ስለዚህ በዓላት መደራረባቸው ሳይሆን የግንዛቤው ጉዳይ ነው  ሆስፒታሊቲው ላይ ችግር የሚፈጥረው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዓላት ተደራርበውም ግን  ያን ያህል ጐንደር በእንግዳ ተጥለቀለቀች ለማለት ያስቸግረኛል፡፡ ቀደም ብዬ እንደተናገርኩት፣በበዓላቱ መደራረብ ከወትሮው የእንግዳ ቁጥር ትንሽ ጨምሯል፡፡ በሌላው ዓለም እኮ በአንድና በሁለት ቀን የሚገባው ቱሪስት መጠን የሚያስደነግጥ ነው፡፡
እርስዎ የሚያውቁት ቱሪስት የሚጎርፍበት የአለም ከተማ አለ?
እኔ በቅርቡ እስራኤል አገር ሄጄ ነበር፡፡ እየሩሳሌም ኦልድ ሲቲ የሚባል ቦታ አለ፡፡ በአንድ ቀን የሚገባው ቱሪስት አካባቢውን የሚያጨናንቅ ነው፡፡ ታሪካዊ ቦታዎችን ለማየት ወረፋው በጣም በጣም የሚያታክት ነው፡፡  ያንን ያየ ሰው፣ጐንደር እንግዳ ያጨናነቃት፣ አስተናጋጆች መውጫ መግቢያ አጥተው የሚዋከቡባት ናት ሊል አይችልም፡፡ ነገር ግን አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በተፈለገው ደረጃ ተገንብተው፣ በጥራት ደረጃቸውም ልቀው ሄደዋል ለማለት አንችልም፡፡ ይሄ ቀስ በቀስ ከልምድም ከኢኮኖሚ አቅምም ጋር ተያይዞ የሚስተካከል ነው፡፡
ህዝቡ ከቱሪዝሙ ተጠቃሚ ሆኗል ብለውኛል፡፡ ቱሪስቱ የሚመጣው ቅርሶች ስላሉ ነው፡፡ ነገር ግን ህዝቡ ለቅርሶቹ ያን ያህል ጥንቃቄና ጥበቃ ያደርጋል የሚል እምነት አላደረብኝም፡፡ አንዳንድ ታሪካዊ ቅርሶች በጥንቃቄ ጉድለት ጉዳት ደርሶባቸው ይስተዋላል፡፡ የአስተዳደሩ  ጽ/ቤት  ህዝቡ በቅርስ አጠባበቅ ላይ ግንዛቤ እንዲኖረው ምን ያህል ጥረት አድርጓል?
ትክክል! አንደኛ በባለቤትነት የጐንደር ከተማ ባህልና ቱሪዝም አለበት፡፡ ከእኛ ጽ/ቤት ጋር በትብብር የሚሰሩም አሉ፡፡ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ቅርሱ እንዲጠገንም እንሰራለን፡፡ ሁለተኛ ቅርሱን ለመንከባከብ፣ ጥፋት እንዳይደርስበት የምንሰራቸው ስራዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ በፊት የሰርግ ስነስርዓት ሲኖር፣ በፋሲል አብያተ መንግስታት ጭፈራና የሞንታርቦ ጩኸት ይደረግበት ነበር፡፡ ድምፁና ጭፈራው ቅርሱን እንዳይጐዳው ያንን ማስቀረት ችለናል፡፡ እዛው አካባቢ ባዛርም ይካሄድ ነበር፡፡ መስቀል አደባባይ ላይ ሁከቱና  ባዛሩ ቅርሱን እንዳይጐዳው እሱንም አስቀርተናል፡፡ የፓርኪንግ ስራም ነበረው፡፡ አሁን በአካባቢው ምንም ስራ አይሰራም፡፡ በከተማ አስተዳደሩ በኩል የጐደሉ ነገሮችን ማስተካከሉ እንዳለ ሆኖ ቅርሶችን የመንከባከብ ስራ እየሰራን ነው፡፡ ከግንዛቤም አኳያ አጠቃላይ ለህዝቡ ግንዛቤ ፈጥረናል ብለን አናስብም፣ ግን በዘርፉ እየተሰሩ ያሉና የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ የአመቱን እቅዳችንን ለፈፃሚ አካላት በምናስተዋውቅበት ጊዜና በተለያዩ ዎርክሾፖች ላይም ቅርሱን መታደግ የከተማ አስተዳደሩና የተወሰኑ አካላት ብቻ ሳይሆን የህዝቡም እንደሆነ ግንዛቤ ለማስጨበጥ የጀመርናቸው እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ በአጠቃላይ ግን የተሟላ ግንዛቤ ህዝቡ ልብ ውስጥ አኑረናል የሚል እምነት የለንም፡፡ በቀጣይ ከፍተኛ ስራን መስራት ይጠይቃል ማለቴ ነው፡፡
የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት /UNESCO/ አንድ ቅርስ የአለም ቅርስ ነው ብሎ ሲመዘግብ የቅርሱን ዙሪያና አጠቃላይ ድባብ /Buffer Zone/ ብሎ ይከልላል። በፋሲል አብያተ መንግስታት ዙሪያውን ያሉ የድሮ ክብክብ ድንጋይ ቤቶች በባፈር ዞኑ የተከለሉ ይመስለኛል፡፡ እዛ አካባቢ ግን ስጋቶች አሉ?
ምን አይነት ስጋቶች ናቸው?
ሰሞኑን በእንኮዬ በር በኩል እነ እመት አበቅየለሽ መንደር ሄጄ ነበር፡፡ እዛ አካባቢ ያሉ የድንጋይ ክብክብ ጥንታዊ ቤቶች ሲፈርሱ ነበር፡፡ የህንጻ ግንባታ ሊካሄድ ነው የሚል ስጋትም አለ፡፡ ይሄ ከዩኔስኮ ጋር አያጋጫችሁም?
ጥሩ! አንደኛ በጐንደር ከተማ ላይ እየሰራን ያለነው ስራ ምንድነው---ህንጻ በአካባቢው ሲገነባ ከፍታው አልፎ አልፎ ችግር ነበረው፡፡ ይህ የሆነው ከግንዛቤ ማነስ ነው፡፡ የፋሲልን አጠቃላይ እይታ የሚከልሉ ፎቆች ተሰርተው ነበር፡፡ ነገር ግን ባለፉት አመታት የባህል ፌስቲቫሎቹን ስናከብር እግረ መንገዱን ልዩ ልዩ የፓናል ውይይቶች ይካሄድ ነበር፡፡ እዚያ ላይ ትኩረት ሰጥተን ያየነው ነገር ምንድነው--- በግንቡ ዙሪያ እይታውን የሚከልሉ ፎቆች በተሰሩ ቁጥር፣ ግንቡ ቱሪስትን የመሳብ አቅሙ ይቀንሳል፡፡ በተጨማሪም ዩኔስኮ ከዝርዝር ውስጥ ያወጣዋል የሚለውን ጉዳይ ተመልክተናል፡፡ ከዚያም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከመጡ ምሁራን ጋር በመተባበር በተደረገ ውይይት፣ ከግንቡ በተወሰነ ሬዲየስ ላይ የሚገነቡ ፎቆች ከፍታ መጠን እንዲወሰን የሚያደርግ ሥራ ተሰርቷል፡፡ ሌላው ቅድም ያልኳቸው እንኮዬ መስክ አካባቢ ያሉ ቤቶች እንዳይፈርሱ ጥብቅ ክትትል እናደርጋለን። ሌላው ቀርቶ ፊት ለፊት ቅድም ያየሻቸው ቤቶች በመኖራቸው፣ የጐንደር ዋና ዋና መንገድ አይተሽው ከሆነ ድሮ በጣሊያን የተቀየሰ ነው፡፡ በዚያ ምክንያት ትንሽ የትራፊክ መጨናነቅ አለ፡፡ አሁን የእግረኛ መንገድ እየሰራን ነው፡፡ መንገዱን ስንሰራ እነዚህን የድንጋይ ክብክብ ቤቶችን አገኘን፡፡ እነዚህን ቤቶች ማፍረስ በቅርሱ ላይ የሚያደርሰውን ጥፋት ስለምናውቅ እንዳይነካ አድርገናል፡፡ እንኮዬ መስክ ላይ ያሉ ተመሳሳይ ቤቶችንም እንዲሁ የምንነካበት ምክንያት አይኖርም፡፡ ሁለተኛ የኮር ዞንና በፈር ዞን የሚለውን በተመለከተ  ከፌዴራልም ከክልሉም ጋር እየተነጋገርንበት ነው፡፡ ባለሙያዎችም ያጠኑት ነገር አለ፡፡ በፈር ዞኑ እስከየት ድረስ ነው? የሚለውን ጉዳይ ማለት ነው፡፡ የት የት ድረስ መከለል አለበት የሚለውንም ያጠኑት ባለሙያዎች ለከተማው ባህልና ቱሪዝም ገልፀዋል፡፡ በቅርቡም ለከንቲባ ኮሚቴ ቀርቦ መልክ የምናስይዘው ይሆናል፡፡
ቀደም ሲል የመፍረስ ስጋት ብቻ ሳይሆን ይፍረሱ የሚል ትዕዛዝ ተሰጥቶ ላለፉት ስድስት አመታት ክርክር ላይ ያሉ ባለ ይዞታዎችን አግኝተናል፡፡ “እነዚህ ደብር ያላቸውና ከግንቡ ጋር ልዩ ታሪክ ያላቸው በመሆኑ ሊፈርሱ አይገባም፣ ሲፈርሱም ከ300 ሰዎች በላይ ይፈናቀላሉ” ሲሉ ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ ይህን ያውቃሉ?
የምትይውን ቦታ በትክክል አላወቅኩትም ነገር ግን ዩኔስኮ እንዲጠበቁ በበፈር ዞን የያዛቸው ቤቶች እንደማይሆኑ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ሌላው ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ እዛ አካባቢ ፎቅ ይገንባ ቢባል እንኳን የከፍታው ሁኔታ የተመጠነና የግንቡን ሁኔታ በማይከልል ሁኔታ ነው፡፡ ይፈርሳል የሚባሉ ቤቶች  ካሉም ዝም ብሎ በግለሰቦች የተያዙ ነገር ግን ከተማዋ ደረጃዋን የጠበቀች እንድትሆን የመልስ ማልማት ስራ የሚካሄድባቸው ይሆናሉ እንጂ እነዚህ ዩኒስኮ ጥብቅ ያደረጋቸው “ጅጌ” የተባሉት ክብ የድንጋይ ቤቶች አይነኩም፡፡ የቀበሌ ቤቶች ይኖራሉ- በግለሰብም የተያዙ ሆነው ጐስቋላ ቤቶች፡፡ እነሱ ለመልሶ ማልማት ሊፈርሱ ይችላሉ፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ አበባም ሆነ ሌላ የትኛውም ከተማ ላይ የሚካሄድ ነው፡፡
ሌላው የአካባቢው ነዋሪዎች ያነሱት ቅሬታ “እዛው መንደር ውስጥ እመት አበቅየለሽ ጠጅ ቤት ፊት ለፊት አቢሲኒያ ባንክ ያለበት ህንፃ የተገነባው ሌሎች ጥንታዊ ቤቶች ፈርሰው ነው፡፡ የህንፃው ሶስት አራተኛ ክፍል ግን አልተከራየም፡፡ ሰው ከቦታው የተፈናቀለው በከንቱ ነው” የሚል ነው፡፡ በዚህ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
ያልሽው ህንፃ ከተገነባ ቆይቷል፡፡ ያን ጊዜ እኔም አልነበርኩም፡፡ ግን ህንፃው ሲገነባ የምትያቸው ጥንታዊና መፍረስ የሌለባቸው ቤቶች እንደፈረሱ የሚያሳይ ሪፖርት የለም፡፡ በየሶስት ወሩ ህዝቡን በሲኒማ አዳራሽ እያገኘን እንወያያለን፡፡ ሆኖም እንዲህ ዓይነት ቤቶች ፈረሱ የሚል ቅሬታ ሳይሆን ቅድም ከቅርስ ጥበቃ ጋር ያነሳሽው አይነት ሃሳብ ያቀርባሉ፡፡ ይህ ማለት እንዴት ቅርሶች ከጉዳት ይጠበቁ፣ ህዝቡ እንዴት የባለቤትነት ስሜት ይሰማው በሚልና በመሰል ጉዳዮች ህዝቡ ሃሳቦችን እያነሳ እንወያያለን፡፡ አሁንም አቢሲኒያ ባንክ ያለበትን ህንፃ በተመለከተ በፋሲል ግንብ ፊት ለፊት እንደመሆኑ ከG+1 በላይ እንዳይገነባ በወቅቱ የነበረው አመራር መከልከል ነበረበት፡፡
ግን እኮ ህንፃው ባለሶስት ፎቅ ነው?
ትክክል ነው፣ ሶስት ፎቅ ነው፡፡ ይህንን እንደ ስህተት ነው የምንወስደው፣ አሁንም የማረጋግጥልሽ ለቅርስ ተብለው የተያዙ ቤቶች አይፈርሱም። ከዚያ ውጭ ያሉ የግል ጐስቋላ የቀበሌ ቤቶች በመልሶ ማልማት ግን ይፈርሳሉ፡፡
ከተማዋ የአለም አቀፍ ቱሪስቶች መዳረሻ ከመሆኗ አንፃር  ጽዳት ይጐድላታል፣ የሚሸቱ ቱቦዎች አሉ፣ ይሄ ደግሞ ቱሪስቶችን ያሸሻል፡፡ ይሄን ለማሻሻል ምን አስባችኋል?
ትክክል ነው፣ የጽዳት ችግር አለ፣ ግን ጽዱ ለማድረግ እየሰራን ነው፡፡
ለምሳሌ ምን አይነት ስራዎች?
ለምሳሌ አንዱ ያደረግነው ነገር ምንድነው--- የደረቅ ቆሻሻ ማኔጅመንቱ በፊት በማዘጋጃ ቤቱ ነበር የሚካሄደው፡፡ ነገር ግን ውጤታማ ባለመሆኑ፣ እንዲህ አይነት ስራዎችን በሌላ አካል (አውት ሶርስ) በማሰራት የስራ እድል መፍጠርና ህዝቡንም ማሳተፍ ይቻላል በሚል ከባለፈው አመት ጀምሮ በምክር ቤታችን አጽድቀን እየተሰራበት ነው፡፡ እዚህ ላይ ያጋጠመን ችግር ማህበራቱ የጠነከሩ አለመሆናቸው  ነው፡፡ አንደኛ ተሽከርካሪ የላቸውም፣ ተከራይተው ነው የሚሰሩት፡፡ ሁለተኛ የልምድም ማነስ ችግሩን ሙሉ በሙሉ ለመቅረፍ እንቅፋት ሆኗል፡፡ አሁን የትኛውን አማራጭ እንጠቀም የሚለውን እያጠናን ነው፡፡
ሁለተኛ ከፍሳሽ ቱቦዎች መሽተት ጋር ያነሳሽው ችግር፣ ብዙዎቹ በተለምዶ ፒያሳ በሚባለው አካባቢ ያሉት ድሮ በጣልያን ጊዜ የተሰሩ ፍሳሽ ማስወገጃዎች በመሆናቸው የመጣ ችግር ነው። ከባለፈው አመት ጀምሮ የእግረኛ መንገድም የፍሳሽ ማስወገጃ ቦይዎችም እየሰራን ነው፡፡ እሱን ስንሰራ ሴፕቲክ ታንካቸው በቀጥታ ከድሬኔጅ ጋር የተገናኘ ሆኖ ነው ያገኘነው፡፡ እነዚህ ችግሮች በአብዛኛው ያለባቸው ቤቶችና አካባቢዎች የኪራይ ቤቶች ይዞታ ናቸው፡፡ አሁን ሳያልቅ ስለመጣችሁ ነው እንጂ እሱን የማስተካከል ስራ ጀምረናል፡፡ ሴፕቲክታንክ እንዲቆፈር፣ ከድሬኔጅ ጋር የተያያዙ ስዌሬጆች እንዲላቀቁ የማድረግ ስራ ተጀምሯል፡፡ አንቺ እንዳልሽው የተወሰኑ ቅሬታዎች ይደርሱናል፣ ነገር ግን ኪራይ ቤቶች በቅርቡ እልባት ይሰጠዋል ብለን እናምናለን፡፡ በአጠቃላይ ያለውን የከተማ ጽዳት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ፣ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የፍሳሽ ማስወገጃ መኪኖችን ገዝቶ በቅናሽ ዋጋ ለማህበረሰቡ መስጠት ጀምሯል። ያየሽውና የጠየቅሽው ትክክል ነው፡፡ ጐንደር ከተማ በተፈለገው ደረጃ አልፀዳችም፡፡ ግን ይህንን ለማስተካከል እየተሰራ ነው፡፡  
ሌላው እጅግ አሳሳቢው ነገር የቢራ ፋብሪካዎች የፉክክር ትንቅንቅ ነው፡፡ በየምሽት ቤቱ ቢራዎችን እየጠጡ የሚያስተዋውቁት 18 አመት ያልሞላቸው ታዳጊዎች ናቸው፡፡ በሁሉም ቢራ በሚሸጥባቸው  ምሽት ቤቶች ቢራ ስፖንሰር ያደርጉና “ይሄ የእከሌ ቢራ ቤት ነው ይሄኛው ራስ ምታትና ሀንግኦቨር አለው” እያሉ ህፃናቱ ሲናገሩ አንገት ያስደፋል። ይህን ጉዳይ የእርስዎ ጽ/ቤት ያውቀዋል? ይሄ ትውልዱን ወዴት ይወስደዋል?
ይሄ ጉዳይ ከማስታወቂያ አለጣጠፉ ጀምሮ ቅድም ያልሽውን ነገር ያመጣል፡፡ አሳሳቢም ነው። ሰሞኑን ከበዓሉ ጋር ተያይዞ በየኮርነሩ ያለው ማስታወቂያ ይገርማል፡፡ የነፃ ገበያ አስተሳሰብና ግንዛቤ ልክ እንዳልሆነ እየገባን ነው፡፡ በቀደም ዕለትም በጨረፍታም ቢሆን አሁን አንቺ ያልሽኝን ነገር ሰምቼዋለሁ፡፡ አንድ የቢራ ኩባንያም ሆነ ሌላ ባለምርት ምርቱን ማስተዋወቅ ያለበት ተጽእኖ በማሳደር አይደለም፡፡ ለምሳሌ ዳሽን ምርቱን ለማስተዋወቅ የራሱ ጋርደኖች አሉት፡፡ አሁን በየምሽት ቤቱ ህፃናቱን እያሰማሩ እንዲህ አይነት ስራ ስለማሰራታቸው በጨረፍታ ሰምቻለሁ፡፡ ስህተቱ ግን የወጣቶቹ ነው የሚል እምነት የለኝም። ይህ ችግር የቢራ ኩባንያዎቹ ነው፡፡ የቅስቀሳውም ሁኔታ ትክክል አይደለም፡፡
በአንድ የአዝማሪ ምሽት ቤት “ይሄን ቢራ አትጠጡ ራስ ምታት አለው” እያሉ ህፃናት ልጆች ሲናገሩና የሚያስተዋውቁትን ቢራ እየጠጡ ሲጨፍሩ እዚያው ሆኜ በዓይኔ አይቼአለሁ---
ለዚህ ችግር በአስቸኳይ  እልባት መስጠት ይኖርብናል፣ ካልሆነ ችግሩ የከፋ ይሆናል፡፡ የትኛውም ቢራ ሲያስተዋውቅ አግባብ በሆነ መንገድ እንጂ ሌላውን እያጥላላና ተጽእኖ እየፈጠረ መሆን የለበትም፡፡ አንዱን እየጠጡ፣ ሌላውን  ይፈልጥሃል  ይቆርጥሃል፣ ማለት ተገቢ አይደለም፡፡ ይሄ የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡ ዳሽን ብቻ የሚሸጥበት ወይም ሜታ ብቻ የሚሸጥበት ሆቴል የለም፡፡  ሁሉም ቢራ ይሸጣል፡፡ ሰው የሚፈልገውን መርጦ ይጠጣል ወይም የራሳቸው ቢር ጋርደን ሊኖራቸው ይገባል። በእርግጠኝነት የምነግርሽ ግን የእኛ ንግድ መምሪያ አለ፡፡  
በመምሪያው በኩል አቅጣጫ እናስቀምጣለን። በሌላ በኩል የኩባንያዎቹን ተወካዮች ጠርተን ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ እንሰጣለን፡፡  ጉዳዩ ችላ የሚባል አይደለም፡፡ ጥቆማውና መረጃው ግን በጣም ይጠቅመናል፡፡ ይሄ ጉዳይ አይቀጥልም፡፡ በቅርቡ  ህጋዊ እርምጃዎችን እንወስዳለን፡፡
የጥምቀት እለት የቻይናውን አምባሳደር ጨምሮ በርካታ እንግዶች ሞባይል፣ ካሜራ፣ ፓስፖርትና ሌሎች ንብረቶች ተሰርቆባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የፀጥታና ደህንነት ስራው ላይ ክፍተት እንዳለ የሚጠቁም ነው፡፡ በበዓሉ ላይ ምን ያህል ንብረት እንደተሰረቀ መረጃው አለዎት? በዕለቱ የሶስት የካሜራ ጋዜጠኞች ሞባይል መጥፋቱንም አውቃለሁ፡፡ ይሄ የጎንደርን ገፅታ አያበላሽም?
ይህን በዓል ስናስብ በተለይ የፀጥታ አካሉ እና የአስተዳደር ፀጥታ፣ እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ከፍተኛ ዝግጅት አድርገዋል፡፡ በበዓሉ ብቻ ሳይሆን ቱሪስቶች በየጊዜው ስለሚገቡና ስለሚወጡ አመቱን ሙሉ ከፍተኛ ጥንቃቄ ይደረጋል፡፡ እሱ እንደተጠበቀ ሆኖ ቀደም ሲል የጠቀስሻቸው ችግሮች ተከስተዋል፡፡ ይህም የተከሰተው ጥምቀተ ባህሩ ላይ የሚገባው ህዝብ ከመጠን በላይ የተጨናነቀ ስለነበረ ነው። እዛ ላይ የሞባይል እና የመሳሰሉ እቃዎች ንጥቂያ ተፈጽሟል፡፡ የሚገርምሽ ከሰዓት በኋላ ብዙዎቹ እጅ ከፍንጅ ተይዘዋል፡፡
ስንት ይሆናሉ እጅ ከፍንጅ የተያዙት?
27 ናቸው፡፡ የሚገርምሽ ይህን በዓል በማሰብ ከሌላ ክልል ተደራጅተው መጥተው ነው የያዝናቸው፡፡ 13 ያህል ተንቀሳቃሽ ስልክ እጅ ከፍንጅ ተይዞ ለባለቤቶቹ ተመልሷል፡፡ ፓስፖርትና መንጃ ፍቃድ ተመልሷል፡፡ ከ27ቱ ውስጥ  የዚህ ከተማ ነዋሪ ሆኖ ያገኘነው አንድ ሰው ብቻ ነው፡፡ ከ26ቱ ደግሞ 11ዱ ከአንድ ክልል የመጡ ናቸው፡፡
እኔ ጐንደር ከመጣሁ ዛሬ ዘጠነኛ ቀኔ ነው፡፡ እስካሁን መብራት ጠፍቶ አያውቅም፣ ውሃም ሄዶ አላየሁም፣ የኢንተርኔት አገልግሎቱም ግሩም ነበር፣ ነገር ግን አንዳንድ ነዋሪዎች በከተማዋ  የውሃ ችግር እንዳለና በየተራ ውሃ እንደሚያገኙ፣ መብራት እንደሚቆራረጥ የሚናገሩ አሉ፡፡ ለበዓሉ እና ለእንግዶች ሲባል በውሃና መብራት ላይ ጥንቃቄ ተደርጐ ነው? ወይስ--
Thank you! ጐንደር ላይ አንዱ ቅሬታ የውሃና የመብራት መቆራረጥ ችግር ነበር፡፡ የችግሩ መንስኤ የውሃም ሆነ የመብራት አለመጠገን ነበር። የሚገርመው ከባለፈው አመት ሚያዚያ በፊት በሳምንት በአማካይ ሶስትና አራት ጊዜ መብራት ይጠፋ ነበር፡፡ ይህንን ለማስቀረት ከሰሜን ምዕራብ ሪጂን መብራት ሃይል ጥገና ክፍል ጋር በመነጋገር ከፍተኛ ስራ ሰርተናል፡፡ በፊት መቆራረጥ ብቻ ሳይሆን  ሃይል የለውም፡፡ በተለይ ትልልቅ ሆቴሎች ላይ ደብዛዛ ሆኖ ነበር የሚበራው፡፡ በዚህ ምክንያት ለተከታታይ ሶስት ወራት ጥገና ተካሄደ፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላ ጐንደር ላይ መብራት አይጠፋም፡፡ በውሃም በኩል ከአንገረብ ወንዝ ውሃው የሚገፋው በኤሌክትሪክ ፓምፕ ስለነበር መብራት ሲቋረጥ ውሃም ይቋረጥ ነበር፡፡ ከባለፈው ሰኔ ወር ጀምሮ ግን የውሃም የመብራት መቋረጥም በእጅጉ ቀንሷል፡፡


ከሰው ቤት ተገኝቶ ምንድነው ቅልውጡ፣
ግብፆች ለሀበሻ ደግሰው ላይሰጡ፡፡
ይህ ቅኔ የተነገረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን በግብጽ ቤተክርስቲያን ሥር በምትመራበትና፣ ዻዻሳት ከግብጽ ታስመጣ በነበረበት ዘመን ነው፡፡
ኢትዮጵያውያን ከራሳቸው የሃይማኖት አባት እንይሾሙ የተጣለባቸው ገደብ ትክክል አይደለም፣ በሚል ውሣኔው ይሻርና ይታረም ዘንድ ጥያቄ ላነሱ ኢትዮጵያዊን ክብር ይግባቸው፡፡ ከሰላሣ ዓመት በላይ የወሰደው ሙግትና ድርድር ለፍሬ በቅቶ ኢትዮጵያዊያን ከራሳቸው የሃይማኖት አባቶቻቸውን ለመሾም በቁ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከ1600 ዓመታት በኋላ ለእኩልነትና ለነጻነት በቃች፡፡ አገሪቱ ለዚህ ማዕረግ እንድትበቃ ላደረጉት ለንጉሱ አጼ ኃይለ ስላሴና ረዳቶቻቸው ነፍስ ይማር ልባዊ ጸሎቴ ነው፡፡
እስከማውቀው ድረስ እስልምና እንደ ካቶሊኮችና ኦርቶዶክሶች አንድ ማዕከል የለውም። ይህ በመሆኑም ወደ ግብጽና ወደ ሌሎች አገራት ተጉዘው ተምረው  የመጡ  ሙስሊም ወንድሞቻችን የግብጽን ወይም የሌላ አገር ተጽዕኖ አላመጡምና  እድለኞች ነን፡፡
ከግብጽ ተጽዕኖ ነጻ የመውጣት ሁለተኛው የትግል ምዕራፍ ደግሞ ታላቁ የኢትዮጵያ የሕዳሴ ግድብ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ግብፆች “በአባይ ወንዝ ላይ ምንም አይነት ኘሮግራም ይኑራችሁ መጀመሪያ የእኛን ፈቃድ ወይም ይሁንታ ማግኘት አለባችሁ፣ ይህን ታደርጉ ዘንድም አስገዳጅ አለም አቀፍ ስምምነት አለ፡፡ ለአባይ ወንዝ ታሪካዊ ባለመብቶች ነን” ይሉናል፡፡ ኢትዮጵያ የምታውቀው፣ የፈረመችውና የሚያስገድዳት ውል ባለመኖሩ የግብጽ ይሁንታ አትፈልግም በማለት የሕዳሴውን ግድብ በራሷ ጊዜ ጀምራለች፡፡ ይሄንንም በተግባር እንዲገነዘቡት አድርጋለች፡፡
አፈሩን ገለባ ያድርግላቸውና ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ፤ የሕዳሴውን ግድብ የመሠረት ድንጋይ ባስቀመጡበት ጊዜ፣ “ግድቡ ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ግብጽንም፣ሱዳንንም ስለሚጠቅም መሠራት የነበረበት በሶስቱም አገሮች ገንዘብ ነበር” የሚል መንፈስ ያለው ንግግር ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ ግብፆች የግድቡን ትክክለኛ ባህሪ ከመረዳት ይልቅ እንደ አንድ የመቅሰፍት ኃይል በማየት ወደ  ማጥላላት ዞሩ እንጂ፡፡
የግድቡ መሠራት ለሱዳንም ሆነ ለግብጽ ቋሚና የተመጣጠነ የውሃ ፍሰት እንደሚያስገኝ፣ አደጋ ሳይሆን ጥቅም መኖሩን ኢትዮጵያ አጠንክራ ለማስረዳት ብትጥርም፣ በተለይ ግብፆች የሚሰማ ጆሮ፣ የሚያገናዝብ አእምሮ ያገኙ አይመስልም፡፡
መረዳት የተቸገረው አእምሮአቸው ግን ጥያቄ በመጫር ሰነፍ ስላልነበረ የግድቡ ዝርዝር ጥናት ተሰጥቶን በራሳችን ባለሙያዎች እናስፈትሸው የሚል ጥያቄ አነሱ፡፡ ይህን ጤነኛ ያልሆነ ጥያቄ፣ ትክክለኛ አላማና ፍላጐት የተረዳው የኢትዮጵያ መንግስት “ ሲያምራችሁ ይቅር” የሚል ቁርጥ ያለ መልስ በመስጠት ምራቃችው አፋቸው ውስጥ እንዲደርቅ አደረጋቸው፡፡
ምን እየሠራች እንደሆነ የምታውቀው ኢትዮጵያ፣ ያለባቸውን ስጋት ማጥፋት ካልሆነም መቀነስ ይችሉ ዘንድ አንድ የባለሙያዎች ቡድን ተቋቁሞ ስለታላቁ የሕዳሴ ግድብ እንዲያጠና ፈቃደኛነቷን  አሳየች። እያንዳንዱ አገር ከየራሱ ሁለት ሁለት ሰው እንዲያቀርብ፣ በሶስቱም አገራት ተቀባይነት ያገኙ ሌሎት አራት ሰዎች በቡድን ውስጥ እንዲካተቱ ተደረገ፡፡ ኢትዮጵያ በዚህ አቋሟ በድምጽ የሚተላለፍ ውሣኔ ቢኖር የበላይነቱን እንደምትይዝ ልብ ይሏል፡፡ ይህም ሆኖ ኢትዮጵያ በውሣኔዋ ገፍታ አለም አቀፍ የሙያተኞች  ቡድን ወደ ሥራ እንዲገባ ተደረገ፡፡ ቡድኑ ሥራውን እስኪያጠናቅቅ ለመጠበቅ ትዕግስት ያጡት ግብፆች፤ ኢትዮጵያን መረጃ እየደበቀች ነው በማለት ከሰሱ፡፡ ከአንድ ጊዜም ሶስት ጊዜ ግድቡ በሚሠራበት ቦታ በመገኘትና ሂደቱን ለመከታተል የቻለው አለም አቀፉ የባለሙያዎች ቡድን፤ ሥራውን አጠናቆ ለሶስቱም መንግስታት ሪፖርቱን አስረከበ፡፡ ሱዳንና ኢትዮጵያ ለሪፖርቱ ቀና አስተያየት ሲሰጡ፣ ግብጽ ብቃት ይጐለዋል በማለት አጣጣለችው፡፡
አለም አቀፉ የሙያተኞች  ቡድን፤ ሪፖርቱን ለየሀገራቱ መስጠት እየተዘጋጀ ባለበት ጊዜ፣ የግድቡ ሥራ ከአንድ ደረጃ ላይ እየደረሰ ስለነበር፣ አባይ ድሮ ይፈስበት ከነበረው ወጥቶ አዲስ በተሠራለት መስመር እንዲፈስ ተደረገ፡፡ ግብፆች በዚህም ተናደዱ። በግብጽ የወቅቱ ኘሬዚዳንት መሐመድ ሙርሲ የሚመሩት የእስላም ወንድማማች ፓርቲ ከሌሎች ተቃዋሚዎች ጋር ስብሰባ ተቀምጦ ስብሰባውም በቀጥታ የቴሌቪዥን ሥርጭት እንዲተላለፍ ተደረገ። በዚህ ስብሰባ ላይም  በአሁኑ ወቅት ከስልጣን ተወግደው በእሥር ላይ የሚገኙት መሐመድ ሙርሲ ነገሩን በድርድር ለመጨረስ እንደሚፈልጉ ጠቁመው “አስፈላጊ ከሆነ ግን እያንዳንዷን የአባይ ጠብታ ውሃ በደም ጭምር እናስከብራለን” ሲሉ ተናገሩ፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በዲኘሎማሲያዊ ቋንቋ ተገቢ እርምጃ ከመውሰዱ በላይ፣ ባልሳሳት ተወካዮች ምክር ቤት ደርሶ እየተንከባለለ የነበረው የናይል ተፋስስ አባል አገሮች የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሕግ ሆኖ እንዲጸድቅ አደረገ፡፡ ስምምነቱ የመጨረሻ ጉዞውንም ጀመረ፡፡ አሁን ኡጋንዳም አጽድቃለች፡፡ ሌሎች እየተጠበቁ ናቸው፡፡
የባለሙያዎች ቡድን ያደረገውን ጥናት ወደ ተግባር ለማሸጋገር የሶስቱ አገሮች የጋራ ስብሰባ ከብዙ  መጓተት በኋላ ካርቱም ላይ ሲጀመር፣ ግብፆች አሁንም የተለመደውን ፈቃደኝነት የማጣት  ባህሪያቸውን ይዘው ቀረቡ፡፡ የትናንት አጋራቸው ሱዳን ወደ ኢትዮጵያ አቋም በማዘንበሏ፣ እንደ ከዳተኛ ቆጥረው ከመዝለፋቸውም በላይ፣ (የጠቅላይ ሚኒስትር መለስን ንግግር አስበው ሊሆን ይችላል)፣  በግድቡ ሥራ በቀጥታ ለመሣተፍ እንደሚፈልጉ ገለጡ፡፡ ይህንንም ተከትሎ ግድቡ የሚይዘው የውሃ መጠን እንዲቀንስ፣ የሚያመነጨው የኃይል መጠንም በዚያው መጠን እንዲያቀዘቅዝ ጥያቄ አቀረቡ፡፡ ይኸኛውም ፍላጐታቸው ተቀባይነት ሳያገኝ ቀረ፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት፤ ግብፆች ቢሰሙትም ባይሰሙትም  የሕዳሴው ግድብ ግንባታ ለአንድ ሴኮንድ እንኳ እንደማይቆም በተደጋጋሚ ተናገረ፡፡
ግብፆች ግን አልተዋጠላዋውም፡፡ የግድቡ ግንባታ በ30% ተጠናቋል የሚለውን የመንግስት መግለጫ “ውሸት” ነው ማለት ያዙ፡፡ ሕዝቡ ድሀ ስለሆነ መንግስትም የገንዘብ አቅም ስለሌለው ግንባታው መቆሙ አይቀርም ሲሉም ተነበዩ፡፡ መንግስት ቀድሞ ነገሩን “የጠላት ወሬ ነው” አለው እንጂ እኔ የሚኖረኝ መልስ “ልክ ናችሁ እንዲያውም ከመሬት አልተነቃነቀም” የሚል በሆነ ነበር፡፡ በአገራችን “ሽል ከሆነ ይገፋል ቂጣ ከሆነ ይጠፋል” የሚል ምሣሌ አለና ጊዜ ለሚመሰክርው ጉዳይ የማንም ራስ ሊታመም አይገባውም ማለቴ ነው፡፡ ለዚህኛውም የግብፆች ቧልት የኢትዮጵያ መንግስት የሰጠው መልስ፣ “በድጋሚ ቁርጣችሁን እወቁ” የሚል ዓይነት ነበር፡፡ “በሚቀጥለው ዓመት ግድቡ የመጀመሪያውን የኤሌክትሪክ ሃይል ያመነጫል” የሚል መግለጫ መስጠት   ትርጉሙ ይሄው ነው። እስከአሁን ላነሷቸው ጥያቄዎችና ፍላጐቶች በኢትዮጵያ በኩል ተቀባይነት ያጡት ግብፆች፤ “ማንም ከማድረግ አያድንም” ወዳሉት እርምጃ ገብተዋል፡፡  
አዲስ ባረቀቁትና 98% የሕዝብ ይሁንታ አግኝቷል በተባለው ሕገ መንግስታቸው ውስጥ ለአባይ (ናይል)  አንድ አንቀጽ በመስጠት፤ “መንግስት የአባይን (ናይልን) ወንዝ ደህንነት ይጠብቃል፤ ግብጽ በወንዙ ላይ ያላትን ታሪካዊ መብት ከማስከበሩም በላይ እስከመጨረሻው ድረስ ተጠቃሚ ያደርጋታል….” የሚል ሃሣብ እንዲካተት አድርገዋል፡፡ ይህ ቃል እንደ ከዚህ ቀደሞቹ የግብጽ ባለሥልጣናት መግለጫዎች ተራና ዋጋ ቢስ ቃል አይደለም፡፡ በዚህ ህገ-መንግስት መሠረት የሚቋቋመው የግብፅ መንግስትና የመከላከያ ኃይሉ በአጠቃላይ የግብጽ ሕዝብና መንግስቱ የሚለፉለት ጉዳይ ነው፡፡ ግብጽና ኢትዮጵያ ቀጥተኛ የሆነ የድንበር መዋሰን ባይኖራቸውም፣ እንዲህ በቀላሉ ወታደራዊ ወረራ ያካሂዳሉ ተብሎ ባይታሰብም፣ ብዙ ደባ ለመጠንሰስ ግን የሚያገለግል መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡
በተለያዩ የሀገሪቱ የውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ በመግባት እንዲሁም የአለም አቀፍ ግንኙነቷን በማደናቀፍ፣ ይህን ሁሉ የምናደርገው በሕገ መንግስታችን ተደነገገውንና ግብጽ በአባይ ላይ ያላትን ጥቅም ለማስጠበቅ ነው ሊሉን ይችላሉ። አሁንም የጀመሩት ስለሆነ ወደ ኋላ ይመለሳሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡
ይህ የግብፆች “አዲስ የምስራች”፤ ለኢትዮጵያ መንግስትና ሕዝብ አዲስ ነገር ይዞ አልመጣም፡፡ የቀድሞውንና ያለውን እውነት ነው ያጐላው፡፡ አዲሱ ህገ መንግስት፤ ኢትዮጵያ ከግብጽ ጋር ተደራድራ፣ የግብጽን አቋም ለመለወጥ  የምታደርገው ጥረት ብዙም ለውጥ እንደማያመጣ ያሳያል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ ሌሎች የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ፈራሚ አገሮች፣ ይህን የግብጽ ሕገ መንግስት እንደ ተራ ጉዳይ ሊያዩት የሚገባ አይመስለኝም፡፡ ጉዳዩን በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ መድረኮች ላይ በማቅረብ መወያያና መከራከሪያ ሊያደርጉት፣ ያረገዘውን ደባም ሊያጋልጡ ይገባል፡፡ ይሄ ህገ መንግስት ነገ የሚያመጣውን መዘዝ አለም እንዲያውቅ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡


                 ባለፈው ሳምንት፣ “ወደ ፍቅር ጉዞ” በተሰኘው የሙዚቃ ኮንሰርቶች ዝግጅት ላይ በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ከድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ጋር ያደረግነውን ቃለምልልስ ያቀረብን ሲሆን፤ ስላለፈው ዘመን ታሪክና ስለአዲሱ ትውልድ ፍላጎት ያለውን አስተሳሰብ መግለፁ ይታወሳል። ሁለተኛውን ክፍል እነሆ፡-
የአገሪቱን የሩቅና የቅርብ ጊዜ ታሪክ እየጠቀስክ፣ ታሪካዊ ሰዎችንም እያነሳህ የሰራሃቸው ዘፈኖች፣ ኢትዮጵያውያንን በፍቅር የሚያቀራርቡ ናቸው ብለህ ታምን ይሆናል። ነገር ግን፤ ብዙውን ጊዜ የምናየው ከዚህ የተለየ ነው። የተለያዩ ወገኖች ጎራ ለይተው፣ ታሪክን እየጠቀሱ ሲወዛገቡ ነው የምናየው። እንደማጥቂያ መሳሪያ ይጠቀሙበታል። የውዝግብ ማራገቢያ ከሚሆን፣ ቢቀር አይሻልም?    
ታሪክን የፖለቲካ መጠቀሚያ ማድረግ ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን ታሪክ ጥቅም የለውም ማለትም አይደለም፡፡ ከታሪክ ውስጥ በአድናቆት አክብረን የምንወስደውና የምናሳድገው ነገር እንዳለ ሁሉ፣ ከታሪክ ውስጥ እንዳይደገም አድርገን የምናስተካክለውና የምናሻሽለው ነገር ይኖራል፡፡ ዛሬ በህይወት የሌሉ ሰዎች በጊዜያቸው ካሰቡት፤ ከተናገሩት፣ ከሰሩትና ከፈፀሙት ነገር የምንወርሰውና የምንማረው ብዙ ነገር አለ። ነገር ግን፤ ሁሉንም ነገር መውረስ የለብንም። ከሞቱ ሰዎች ላይ፣ ህይወት ያለው መልካም ስራቸውን መውሰድ እንጂ፤ ከነሱ ጋር አብሯቸው የሞተ መጥፎ ነገርን ማውጣትና ማግዘፍ ምን ይጠቅመናል? በጎ በጎውን እንጂ፣ ክፉ ክፉውን ማጉላት ጥቅም የለውም።
በጨላለመው አቅጣጫ ላይ ካተኮርክና ከተጓዝክ ጨለማ ይውጥሃል፡፡ ወደ ብርሃናማው አቅጣጫ አተኩረህ ስትንቀሳቀስ ደግሞ፣ ትንሿ ጭላንጭ እንኳ እየፈካች እየሰፋች ትመጣለች፡፡ የወደድከው ነገር ወዳንተ ይመጣል የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ አንተ ስትቅርበው ወዳንተ ይመጣል፡፡
ታሪክ አበላሽቷል ብለን የምናስበውንና ከብዙ አመታት በፊት የሞተውን ሰው እያነሳን፤ አፈር የተጫነው አፅሙ ላይ ክፉኛ እንጨክናለን። የሞተ ሰው ላይ እንዲያ ከጨከንን፣ በሕይወት ባሉ ሰዎች ላይ ጭካኔያችን ምን ሊሆን እንደሚችል ስታስበው ያስፈራል፡፡ ይሄ ጥሩ አይደለም፡፡
ከምንም በላይ፣ ለሚቀጥለው ትውልድ፣ ለሚቀጥሉት ልጆች ማሰብ ያስፈለጋል፡፡ ሲሆን ሲሆን፣ ታላላቆቻችን የድሮ ቅሬታና አስወግደው፣ ‘አዲሱ ትውልድ የራሱን ታሪክ እንዲሰራ መልካም ነገር እናውርሰው’ ብለው ሲያስቡልን ብናይ እንወዳለን፡፡ ታላላቆቻችን ይህ ካልሆነላቸው፣ ቢያንስ ቢያንስ ብሩህ ዘመን እንዲፈጠር መመኘት አለባቸው ብዬ አስባለሁ፡፡
ፈጣሪ ፍቅር ነው ስለሆነም ከፍቅር ማምለጥ አንችልም። የእለት ተእለት ኑሮ ላይ የማያግባቡን ጥቃቅን ነገሮች ይኖራሉ። ግን የጥላቻ አጥር አናድርጋቸው። ከፈጣሪ ጋር እንግባባለን የምንል ከሆነ፤ ፈጣሪ ሁሉንም የሚያቅፍ ስለሆነ፤ ሁላችንንም የሚያግባባ ፍቅር አለን ማለት ነው፡፡
ሰው መሆንን አሳንሰን፣ ታሪክንም አሳንሰን፣ ፈጣሪንም እንዲሁ ወደ እለታዊ ስሜት አውርደን፣ ወደ ፖለቲካ ንትርክ ደረጃ አጥብበን ማየታችንን ማቆም አለብን። የትኛው ሃይማኖት ነው ፍቅርን የማይሰብከው? የትኛው ሃይማኖት ነው እርቅን የማይደግፈው?
የገብረክርስቶስ ግጥም ላይ አንዲት ጥንቸል አለች፡፡ ጥንቸሏ ከመሬት ጋር የተዋዋለችው ብድር ነበረ፡፡ መሬት የተጠየቀችውን ሰጠች፡፡ ጥንቸሏ አቅም ስላላገኘች ይሁን ፍላጐት ስላጣች አይታወቅም፡፡ ቃሏን አላከበረችም፡፡ እና ለማምለጥ ትሮጣለች፡፡ አሁንም ትሮጣለች፡፡ ከመኖሪያዋ ከመሬት ነው ለማምለጥ የምትሮጠው፡፡ እኛስ እንዴት ነው ከፈጣሪ ፍቅር ለማምለጥ የምንሮጠው? ማን በዘረጋው መሬት ማን ባሰፋው ሰማይ ነው፤ ቂም እያወረስን አሳዳጅና ባለዕዳ ለመሆን የምንሞክረው? በታላላቆቻችን አለመግባባት ምክንያት የመጣ አውድ መሃል የተፈጠረ ትውልድ ሆነን፣ በፍቅርና በመግባባት መቀጠል ስንፈልግ እንዴት በክፉ ይታያል? እንዴት ታናናሾች ይህንን ለታላላቆች ይነግራሉ? እንዴት ታናናሾች ታላላቆችን ይሸከማሉ? ይሄ ከባድ ጥያቄ አለብን፡፡ በየአጋጣሚውና በሰበቡ በሚፈጠር ንትርክ ላይ ሳይሆን፤ ያንን ከባድ ጥያቄ ለመፍታት ነው መነጋገር ያለብን፡፡ ታላላቆቻችንን፤ አለመግባባት እንዲወገድና ፍቅር እንዲሆን፣ አዲሱ ትውልድ በተስፋ አይን፣ አይናቸውን እየተመለከተ ይጠይቃቸዋል፡፡
እስቲ ተዋደዱ ይያያዝ እጃችሁ
አለበለዚያማ በምን ያስታውቃል እኛን መውደዳችሁ?
ቂምን ተሸክሞ አለመግባባትን የሙጢኝ ማለት ውጤቱ ምን እንደሆነ አብረን እያየነው፤ ለምን ወደሚቀጥሉት ልጆች እንዲሸጋገር እናደርጋለን? አንዳንዴ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ቀና ትውልድ የድርሻውን እንዳይሞክር ማወክ፣ የፍቅር ሃሳቡንም ማፍረስ የለብንም፡፡ መድሃኒት አይገፊም፡፡ ፍቅር መድሃኒት ነው፤ ረዥም ጊዜ ከተማመንበት በሽታ የሚያድነን፤ ፈውስ ነው፡፡
የድሮ ሰዎችን ትልቅ ታሪክና ጀግንነት እየጠቀስን የምንኮራ ከሆነ፤ በስህተታቸው ማፈርና የጥፋታቸው ባለዕዳ መሆን የግድ ነው፡፡ ሁለት ወዶ ይሆናል? ከወላጆቼና ከታላላቆቼ ያኛውን ትቼ ይህኛውን ብቻ ልውረስ ማለት ያስኬዳል?
በፍቅር ተገናኝተው ልጆችን ለማፍራት የበቁ ወላጆች፣ የአያቶችን አለመግባባትና ቂም አስታውሰው ሲለያዩ፤ ለልጆቻቸው የሚያወርሱትን አስበው፡፡
የቅርብ ጊዜ ታሪካችን ላይ’ኮ አይተናል፡፡ ለዚህም አይደለም እንዴ፤ ዳህላክ ላይ ያለው ሰውዬ፤ ለተለያትና ለተለየችው ባለቤቱ፤ አለመግባባትና ፀብ በኛ ላይ ያቁም፤ ቅሬታን ለልጃችን አናውርሰው፤ ጥላቻንና ቂምን አናስተምረው የሚላት፡፡ ፍቅርንና መግባባትን ብናስተምረውና መልካም ችግኝ ብናደርገው፤ እኛን መልሶ የሚያቀራርብና የሚያስታርቅ ታላቅ ሰው ይሆናል ይላታል፡፡ አለመግባባት ሊያጋጥማቸው አይገባም ነበር በለን ታላላቆችን ሁሉ መውቀስ ስህተት የመሆኑን ያህል፤ አለመግባባትን ማውረስ ስህተት ነው፡፡ አለበለዚያማ፤ መሻሻልና ማደግ አይኖርም፡፡ እንደ ዳህላኩ ሰውዬ ታላላቆች ለአዲሱ ትውልድ መልካም ሲጨነቁ፣ ከወረሱት ቂም ይልቅ የሚያወርሱት ፍቅር እንደሚበልጥ አስበው መልካም ነገር ሲያስተምሩ፤ የታናናሾች እና የልጆች ስሜት ብሩህ፤ የአገሬው መልክና መንፈስ ያማረ ይሆናል፡፡ የአገር ታሪክ፣ ፖለቲካና መንግስትም ደግሞ፣ የአገሬውን ሕዝብ መምሰሉ የማይቀር ነው፡፡ በቅንነት የወደድከው ሳይመጣ አይቀርም፡፡ አዲሱ ትውልድ ቅን ስለሆነ፤ መልካም ዘመን፣ ድንቅ ታሪክ እየመጣ ነው፤ እድል እንስጠው፡፡
ወደ ፍቅር ጉዞ አይቆምም ብለሃል። ኮንሰርቶቹ ይዘጋጃሉ ማለት ነው?
የትውልድ ድምጽ፤ የትውልድ ራዕይ ነው። ራዕይ ደግሞ አስቀድሞ የተፈፀመ ነገር ግን አሁን የሚገለጥ ነው፡፡ ፍቅር እጅግ ሃያል ስለሆነም ጉዞውን ይቀጥላል፡፡ አገራችን በታሪክም በህዝብም ሰፊ ነች፡፡ አለመግባባት አይፈጠርም ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ ሰው፤ እንደተገነዘበውና እንዳወቀው መጠን፤ እንደመጣበትና እንደመረጠው መንገድ፤ በመሰለውና በኮረኮረው መጠን ያስባል፡፡ ይሄ ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ፍቅር ይህንን ሰፊ ተፈጥሮ ስለሚያቅፍ፣ በየአጋጣሚው የሚያደነቃቅፍ ነገር ያጋጥመዋል ግን ይጓዛል፡፡
ወደ ፍቅር ጉዞ ተጀምሯል ትላለህ። ግን፣ ዙሪያችንን ስናየው፤ ብዙም ለውጥ የለም። በየምክንያቱ ግጭት፣ በየሰበቡ ውዝግብ ነው፤ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ...። ጉዞው ቢጀመር እንኳ ስንዝር መራመድ የሚችል አይመስልም።
ወደ ፍቅር የምትጓዘው መንገዱ ተመቻችቶ ሲዘጋጅ ብቻ አይደለም፡፡ መንገድ ከጠበበ እያሰፋህ መንገዱ ካልተመቸ እያስተካከልክ ነው የምትጓዘው። በአለም ደረጃም ልታስበው ትችላለህ፡፡ ከባድ አለም ውስጥ ነው የምንኖረው፡፡ በየአገሩ ለጦር መሳሪያ የሚውለው ሃብት፣ ለጦርነት የሚወጣው የገንዘብ ሲታይ፣ ሰላምን ማጣጣም ወይም መፍትሔ ማግኘት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ይነግርሃል። ፍቅር ያሸንፋል ሲባል፤ ክብደት የለውም ብሎ ለማቃለል አይደለም፡፡ ብዙ ነገር የመሸከም ሃይል ስላለው ነው። “ቀላል ይሆናል” የሚለው ዘፈንም’ኮ የተራራው ጫፍ እያለ ከባድነቱን ያሳያል፡፡
ደቂቀ ተስፋን ካየናት አርቀን
ነገ ሌላ ይሆናል ጥሩ ቀን
የተስፋ ጭላንጭሏ ማነስ፣ የተራራው አናት ርቀት፣ የመንገዱ አለመደላደልና አስቸጋሪነት ባይካድም፤ በብርሃን የተሞላው መስክና የተራራው ጫፍ ላይ ለመድረስ መጓዝ አለበት፡፡ ለምን ብትል፤ “ፍቅር ያሸንፋል” ካልን፤ “ለፍቅር እንሸነፋለን” ማለት ነው፡፡ ወደ ወደድከው ነገር ትጓዛለህ፡፡ ለፍቅር ብለህ፡፡
ሁላችንም አሸናፊ ለመሆን እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን አሸናፊነት ማለት የመጨረሻው ውጤት ብቻ አይደለም፡፡ ጉዞውም ጭምር ነው፡፡ “ገዳዩ፣ ገዳዩ” የሚሉ ብዙ ዘፈኖች አሉን፡፡ አሸናፊነን ለመግለጽ ነው፡፡ ግን መተውም ቢሆን የሚያሸንፉ አሉ፡፡ ኢየሱስ ይህንን ያስተማረን ይመስለኛል፡፡ ጥላቻን በይቅር ባይነት ድል በሚያደርግ ቀና የፍቅር መንገድ መጓዝ አሸናፊነት ነው፡፡ “ፍቅር ያሸንፋል” እና “ፍቅር አሸንፏል” ብሎ መናገር ልዩነት የለውም፡፡ ገና ከጅምሩ ጉዞው ውስጥ አሸናፊነት አለ፡፡
አንድ በጣም ስሜትን የሚነካ ታሪክ ላስታውስህ። በእስራኤልና በፍልስጥኤም መካከል ለዘመናት ያላበራው ግጭት፣ ጥፋት እና ሃዘን አሁንም ከየእለቱ ዜና ጠፍቶ አያውቅም፡፡ ነገሩ፤ የሙስሊሞች በዓል የሚከበርበት ቀን ላይ ያጋጠመ ነው፡፡ የታሪካቸው ቅርበት ያህል የብዙዎቹ ኑሮም ቅርብ ለቅርብ ነው፡፡ ከመንገዱ ወዲህ ፍልስጤኤማውያን፣ ከመንገዱ ወዲያ ደግሞ እስራኤላዊያን ይኖራሉ፡፡ ጥዋትም ከሰዓትም በኋላም ማዶ ለማዶ ይተያያሉ። ፋታ የሌለው ጥርጣሬ ግን በሰላም እንዲተያዩ አላደረጋቸውም፡፡
እና በዚያ የበዓል ቀን፤ አባት ለልጁ አዲስ ልብስ ገዝቶለታል፤ አዲስ መጫወቻም አምጥቶለታል፡ በተገዛለት መጫወቻ የተደሰተው ህፃን፣ አዲስ ልብሱን እንዳደረገ ከቤት ውጭ ይጫወታል፡፡ ቦታው ትንሽ ከፍ የለ ነው፡፡ ወደ ታች ብዙም ሳይርቅ የእስራኤላዊያን መንደር አለ፡፡
ከመሃል ባለው መንገድ ላይ ለጥበቃ የተመደቡ የእስራኤል ወታደሮች አካባቢውን ይቃኛሉ። እና ከወታደሮቹ አንዱ፣ ከጉብታው አካባቢ የሰው እንቅስቃሴ ሲመለከት፤ አደጋ ተሰማው፡፡ የተነጣጠረ መሳሪያ ታየው፡፡ ሳይቀድመኝ ልቅደም ብሎ ይተኩሳል፡፡
አባቱ የገዙለትን ውሃ የሚረጭ ሽጉጥ ይዞ ሲጫወት የነበረው ህፃን በጥይት ተመታ፡፡ አባት የተኩስ ድምጽ ሰምቶ በድንጋጤ ከቤት ወጥቶ ይመጣል፡፡ ልጁ ወድቋል፡፡
የእስራኤል ወታደሮችም ተጠግተው አይተዋል፡፡ የተነጣጠረ መሣሪያ የመሰላቸው ነገር ውሃ የሚረጭ ሽጉጥ መሆኑን ሲያዩ ደነገጡ፡፡ ህፃን መጉዳታቸውን ሲያዩ አዘኑ፡፡
በአስቸኳይ ሄሊኮፕተር ተጠርቶ ልጁ ወደ ሆስፒታል እንዲወሰድ አደረጉ፡፡ ነገር ግን ወደ ሆስፒታል የተወሰደውን ህፃን ለማዳን ሃኪሞች ቢጣጣሩም አልተሳካላቸውም፤ ህይወቱ አለፈ፡፡ ይሄ አባት፣ ከዚያች ቅጽበት በኋላ ምን አይነት ሰው እንደሚሆን አስበው፡፡
በሀዘን የተመታው አባት፤ ሃኪሞቹን ጠየቃቸው። “የልጄ ልብ ንፁህ ነው ወይ” አላቸው፡፡ ያልጠበቁት ጥያቄ ነው፡፡ “አዎ ጤናማ ነው” አሉት፡፡
“እንግዲያውስ፣ በልብ ህመም ለሚሰቃዩ እስራኤላዊ ሕፃን አስተላልፉለት” አላቸው፡፡ ያልተለመደ በጣም አስገራሚ ታሪክ ነው፡፡ ሁሉም ሰው ውስጥ ይበዛም ይነስ በጐ ነገር አለ፡፡ አደገኛነት ብቻ ሳይሆን ታላቅነትም የሚወለደው እንዲህ ካለ ጥልቅ ጉዳት ውስጥ ነው፤ ምክንያቱም ፍቅር ሳይሰቃይ አያሸንፍምና፡፡

መንግስት፤ ተቋሙ የተቃዋሚዎች የፕሮፖጋንዳ ማስፈፀሚያ ነው
“በኢትዮጵያ የነፃ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ ነው”
“በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሳት ነውር ሆኗል” ብሏል

የኢትዮጵያ መንግስት የዜጐችን  ሰብአዊ መብት በስፋት ይጥሳል በማለት ተደጋጋሚ ወቀሳና ስሞታ የሚያቀርበው ሂውማን ራይትስ ዎች የተሰኘው አለማቀፍ የመብት ተቋም፤  ሰሞኑን ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ፣ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ነፃነት ይበልጥ መጥበቡንና የነጻ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ መውደቁን ገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ የተቋሙን ሪፖርት ያጣጥላል፡፡ በአገሪቱ ውስጥ የፖለቲካ ነፃነትና የፖለቲካ እንቅስቃሴ የማካሄድ እድል (የፖለቲካ ምህዳር) እየጠበበ የመጣው ከምርጫ 97 በኋላ መሆኑን የገለፀው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከዚያ ወዲህ በመንግስት የፀደቁትን የፀረ - ሽብር እና የበጐ አድራጐት ማህበራት አዋጆችን በምሳሌነት ጠቅሷል፡፡ በፀረ - ሽብር አዋጁ መነሻነት ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ሽብርተኛ ተብለው እንደታሠሩና እንደተፈረደባቸው የተቋሙ ሪፖርት ጠቅሶ፣ በህጋዊና ሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በፍርሃት እንዲሸበቡ ተደርገዋል ብሏል፡፡
ጋዜጠኞች የፀረ-ሽብር አዋጁን በመፍራት የሙያ ተግባራቸውን እንዳያከናውኑ መታፈናቸውን ሲገልጽም፤ የአዋጁ አንቀፅ እየተጠቀሰ እሥራት የተፈረደባቸው ጋዜጠኞች መኖራቸውንም አውስቷል፡፡
በኢትዮጵያ ጐልተው የሚታዩት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የፖለቲካ ምህዳር መጥበብና የኘሬሶች አፈና ቢሆኑም፤ ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችም መሻሻል አላሣዩም ብሏል ሪፖርቱ፡፡
በማረሚያ ቤት ያሉ እሥረኞች በገለልተኛ አካላት እንዳይጐበኙ መከልከል፣ ያልተፈረደባቸው ግለሰቦችን አስሮ ማቆየትና ለፍርድ ቤት አቤቱታ እንዳይቀርቡ ማገድ፤ ያልተፈረደባቸውን ሰዎች በብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ በሚሠራጩ ፕሮግራሞች ላይ እንደ ወንጀለኛ መፈረጅ… በአገሪቱ ከሚታዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ውስጥ የሚካተቱ መሆናቸውን ሪፖርቱ ዘርዝሯል፡፡  
ሠላማዊ ሠልፍ የማካሄድ፣ የመብት ጥያቄ የማቅረብና ተቃውሞን የማሰማት መብቶችንም ፈትሼያለሁ የሚለው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ጥያቄ ባቀረቡና ሰላማዊ ሰልፍ ባካሄዱ ሙስሊሞች ላይ እንግልት፣ ድብደባና እሥር ተፈጽሟል ብሏል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች የተጠሩ ሠላማዊ ሠልፎችም  በአፈና ውስጥ የተካሄዱ መሆናቸው በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የመብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል ከተባሉት አገራት መካከል ኤርትራ በቀዳሚዎቹ ተርታ ውስጥ እንደምትመደብ ተቋሙ ገልፆ፤ ጋዜጠኞች ለእሥራት እና ለእንግልት፤ ብዙ ዜጐችም ለስደት መዳረጋቸውን ዘርዝሯል፡፡
በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሣት ነውር ሆኗል ያለው ይሄው ሪፖርት፤ የኤርትራ ሁኔታ ከሁሉም የአፍሪካ ሀገራት እጅግ በጣም አሣሣቢ ነው ብሏል፡፡
ሃሣብን በነጻነት መግለጽ፣ መደራጀትና የፈለጉትን አቋም መያዝ ለኤርትራውያን እንደማይፈቀድ በመጥቀስም፤ ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውጪ ሰዎች እየተያዙ ይታሠራሉ፤ እስር ቤት የታጐሩ  ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞችና ሌሎች ዜጐች  ያለምንም ፍርድ ከ10 ዓመት በላይ ሆኗቸዋል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ሙሉ ለሙሉ እንደማይቀበል በተደጋጋሚ ያስታወቀ ሲሆን፤ ተቋሙ ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት የሚሠራ ነው፤  የተቃዋሚ ሃይሎች የኘሮፖጋንዳ ማስፈጸሚያ ነው ሲል ይከሳል፡፡
ሰሞኑን የተሰራጨውን አመታዊ ሪፖርት በተመለከተ የጠየቅናቸው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ “ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣው ሪፖርት ተአማኒነት የሌለውና ገጽታን ለማጠልሸት ያለመ ነው” ብለዋል፡፡
ተቋሙ ሀገር ውስጥ ሣይገኝ ወይም መርማሪዎቹን ሣይልክ፣ ኬንያናና ሌላ ሀገር ተቀምጦ ከተቃዋሚዎች በሚቃርመው ያልተጣራ ተባራሪ ወሬ ላይ ተመስርቶ፣ ከመንግስት ምላሽ ሳይጠይቅ የሚያወጣው መናኛ ሪፖርት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ፈጽሞ አይገልጽም ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው፡፡
ተቋሙ የኢትዮጵያን መንግስት ለማጥላላት  አቅዶ የሚሠራ ነው ያሉት አቶ ሽመልስ፤ የተቋሙ የምስራቅ አፍሪካ ወኪል አቶ ዳንኤል በቀለ፣ ህገ-መንግስቱን የማፍረስ ነውጥ በማስነሳት የተከሰሱና የተፈረደባቸው፣ ይቅርታ ጠይቀው ቢለቀቁም በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ቂም የቋጠሩ በመሆናቸው ሪፖርታቸው ገለልተኛ ሊሆን አይችልም ብለዋል። ይህ ሲባል ግን ሀገራችን ታዳጊ ሀገር እንደመሆኗ ችግሮች አይኖሩም ማለት አይደለም ያሉት ኃላፊው፤ የኘሬስ ነጻነትና የጋዜጠኞች መብት ሙሉ ለሙሉ ተጠብቆ ኘሬሱ እንዲጠናከርና  እንዲስፋፋ እየተደረገ ነው፣ ከባለሙያዎች ጋርም እየተመካከርን በጋራ እየሠራን ነው ብለዋል፡፡

ዋና አዘጋጁ በ5ሺህ ብር ዋስ ተለቋል

 “ሰንደቅ” ጋዜጣ ስለ ጉዲፈቻ በሰራው ሰፊ ዘገባ ላይ የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር  በስም ማጥፋት አቤቱታ እንዳቀረበበት የገለፀው ዋና አዘጋጁ ፍሬው አበበ፤ ባለፈው ሀሙስ ጠዋት ማዕከላዊ ምርመራ ቀርቦ ቃሉን ከሰጠ በኋላ በ5ሺህ ብር ዋስ መለቀቁን ተናገረ፡፡
ጋዜጣው ታህሣሥ 23 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም ‹‹የጉዲፈቻ ዘመቻ በተጠያቂነት መጀመር አለበት›› ርዕስ አንቀጽና በሕግ አምዱ ላይ ‹‹ጉዲፈቻና የሕጎቻችን ክፍተቶች›› በሚል ዘገባ ማውጣቱን ዋና አዘጋጁ ተናግራል፡፡ የሴቶች፣ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር በጋዜጣው የአገርን ገፅታ የሚያበላሽ፣ የፍትህ ስርዓቱን ተዓማኒነት የሚያሳጣና የሚኒስትሯን ክብር የሚያዋርድ ዘገባ አውጥቷል ሲል ለፓሊስ አቤቱታ ማቅረቡን የተናገረው ዋና አዘጋጁ፤ ከትላንት በስቲያ በፌደራል ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ቀርቦ ቃሉን ከሰጠ በኋላ፣ በ5ሺህ ብር ዋስ መለቀቁን ገልጿል፡፡
በጉዲፈቻ ዙሪያ ባወጡት ዘገባ ስም በማጥፋት በመንጀላቸው እንዳሳዘነው የገለጸው ዋና አዘጋጁ ፍሬው፤ “የተፈለገው ሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነትን እንዳናጋልጥ ቢሆንም ፈርተን ወደ ኋላ አንልም፤ ሞያው የሚጠይቀውን  መስዋዕትነት ሁሉ እንከፍላለን” ብሏል፡፡ 

አደራዳሪው አምባሳደር ስዩም የተኩስ አቁም ስምምነቱን ይቆጣጠራሉ
በመንግስት የታሰሩ ተቃዋሚዎች ይለቀቃሉ ተብሏል


የደቡብ ሱዳንን ገዢ ፓርቲ ለሁለት በመሰንጠቅ፣ አንጋፋ መሪዎች በሁለት ጐራ የሚያካሂዱትን ጦርነት ለመሸምገል በአካባቢው አገራት ይሁንታ የተመደቡት አምባሳደር ስዩም መስፍን፣ ሁለቱ ባላንጣዎች ተኩስ እንዲያቆሙ በማስማማት ሐሙስ ማታ አፈራረሙ፡፡
በፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ከስልጣን የተባረሩት የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንት ሬክ ማቻር የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ካካሄዱ በኋላ፣ መንግስት አፈንጋጭ የገዢው ፓርቲ አመራሮችንና ባለስልጣናትን ያሰረ ሲሆን አፈንጋጮቹ በበኩላቸው፤ በወታደራዊ ጥቃት በርካታ ከተሞችና የነዳጅ ማውጫ ቦታዎች ላይ መዝመታቸው ይታወቃል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ የኢጋድ አባል አገራት፣ አምባሳደር ስዩም መስፍንን ከቻይና በመጥራትና ሁለት ተጨማሪ ልዑካንን በማከል ተቀናቃኝ የደቡብ ሱዳን ባላንጦችን እንዲሸመግሉ ቢመድብም፣ ተቀናቃኞቹ ያቀረቡት የድርድር ቅድመ ሁኔታ ፈታኝ ሆኖባቸው እንደቆየ ተነግሯል። ድርድሩ ያለ ውጤት ሊራዘም ይችላል ተብሎ ቢገመትም ፤ መንግስት ለሰላም ድርድር ሲል ተቃዋሚዎችን ከእስር እንዲለቅ፤ ተቃዋሚዎች ደግሞ በሃይል ስልጣን ለመያዝ ከመሞከር እንዲቆጠቡ በማሳመን ሐሙስ እለት የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲፈራረሙ ተደርጓል፡፡
ተቀናቃኞቹ ወገኖች ከወታደራዊ ጥቃትና ከፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ለመቆጠብ የተፈራረሙትን ስምምነት ማክበራቸውን ለመቆጣጠር አምባሳደር ስዩም እና ሁለቱ ተጨማሪ የኢጋድ ልዑኮች ሃላፊነት ተሰጥቷቸዋል፡፡
ከዚህ አስቸጋሪ ሃላፊነት በተጨማሪ፤ ተቀናቃኞቹ ዘላቂ መፍትሔ ላይ ለመድረስ የሚያካሂዱት የሰላም ድርድር ብዙ ፈተናዎች ስለሚጠብቁት፤ የደቡብ ሱዳን ጉዳይ አሳሳቢ እንደሆነ ይቆያል ተብሏል፡፡
በሚቀጥለው ሣምንት በአዲስ አበባ የሚካሄደው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤም በግብርናና በምግብ ዋስትና ዙሪያ እንዲያተኩር ታስቦ የነበረ ቢሆንም፤ የጉባኤው ትኩረት ወደ ደቡብ ሱዳንና ወደ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ የፀጥታ አደጋዎች ይዞራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከሃይማኖት ጋር የተነካካው የማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ቀውስ እና የእርስ በርስ ግጭት ሰሞኑን ረገብ ያለ ቢመስልም አገሪቱ አሁንም ከቀውስ አልወጣችም፡፡ የዋና ከተማዋ የባንጉዊይ ከንቲባ የአገሪቱ ኘሬዚዳንት እንዲሆኑ ተመርጠው ስልጣን ቢረከቡም የፀጥታ ሁኔታው አሁንም እንዳልተረጋጋና አፋጣኝ ሁነኛ መፍትሄ ካልተገኘ ግጭቱ ወደ እርስ በርስ እልቂት ሊያመራ እንደሚችል ከአገሪቱ የሚወጡ መረጃዎች እየጠቆሙ ነው፡፡
ከመሪዎቹ ጉባኤ አስቀድሞ የአፍሪካ የሚኒስትሮች ጉባኤ በባህርዳር ከተማ እየተካሄደ ሲሆን፤ በሠላምና መረጋጋት ችግሮች ላይ ተወያይቶ የውሳኔ ሃሣቦችን ለመሪዎቹ ጉባኤ ያቀርባል፡፡
በህብረቱ ጉባኤ ላይም ሆነ ጣና ላይ እየተካሄደ ባለው የሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ ግብጽ አትሳተፍም። የመሀመድ ሙርሲን መንግስት ተክቶ ያለው ወታደራዊ መንግስት ስልጣኑን በህዝብ ለተመረጠው መንግስት እስኪያስረክብ ድረስ ግብጽ በአፍሪካ ህብረት እንዳትሳተፍ ማዕቀብ ተጥሎባታል፡፡

አንድ ታዋቂ ደራሲ የእርሳሱ ታሪክ በሚል የጻፈው የአጭር አጭር መጣጥፍ እጅግ አስተማሪ ነውና ዛሬ ከትበነዋል፡፡ አንድ ልጅ፤ ሴት አያቱ ደብዳቤ ሲጽፉ አተኩሮ ይመለከታቸዋል፡፡ ብዙ ካያቸው በኋላ፤ “ስለ እኛ ታሪክ ነው የሚጽፉት? ስለኔ ነው?” አለና ጠየቃቸው፡፡ አያትየው፤ ደብዳቤ መጻፋቸውን አቆሙና ለልጅ ልጃቸው እንዲህ አሉት፡- “እርግጥ ነው ልጄ ስለ አንተ ነው የምጽፈው፡፡ ሆኖም ከጻፍኳቸው ቃላት ይልቅ ስለ እርሳሱ ማወቅ ያለብህ ነገር ነው እሚበልጠው፡፡ አንድ ቀን አንተም አድገህ እንደዚህ እንደምገለገልበት እርሳስ እንደምትሆን ተስፋ አደርጋለሁ” በነገሩ እጅግ ተነክቶ፤ ልጁ እርሳሱን ትኩር ብሎ ተመለከተው፡፡ ሆኖም፤ ከሚያውቀው እርሳስ የተለየ ሆኖ አላገኘውም፡፡ “ይሄ ዱሮም የማውቀው እርሳስ አይደለም እንዴ? ምን የተለየ ተዓምር አለው? ሲል ጠየቃቸው። አያትየውም፤ “አየህ ልጄ፤ እሱ አንተ ነገሮችን የምታይበት ዓይን ጉዳይ ነው፡፡ እርሳስ አምስት ዓይነት ልዩ ጠባያት፤ አሉት፡፡ እነዚህን ልብ ካልክ፣ ምን ጊዜም በዓለም ላይ ሰላም ያለው ልጅ ትሆናለህ፡፡ “የመጀመሪያ ልዩ ጠባዩ፤ ትላልቅ ነገሮችን የመሥራት ክህሎት መኖሩ ነው፤ ሆኖም ምንም ዓይነት ልዩ ክህሎትና ችሎታ ቢኖርህ መንገድህን የሚመራ እጅ መኖሩን አትርሳ፡፡ ያን እጅ አምላክ እንለዋለን፡፡

እሱ ሁልጊዜ እንደ ፈቃዱ የሚመራን ነው፡፡ ሁለተኛው ልዩ ጠባዩ፤ በምጽፍ ጊዜ አሁንም አሁንም መጻፌን አቁሜ ልቀርፀው ይገባኛል፡፡ ያም እርሳሱ ትንሽ እንዲያመው ያደርገዋል፡፡ ሆኖም ከታመመ በኋላ የበለጠ የሰላ ይሆናል፡፡ ስለዚህ አንተም ህመምህንና ሀዘንህን እየተሸከምክ፣ እየቻልክ መኖርን ከተማርክ የተሻለ ሰው ትሆናለህ፡፡ ሦስተኛው ልዩ ጠባዩ፤ ድንገት የተሳሳተ ነገር ብንፅፍ በላዺስ ተጠቅመን ማጥፋት እንችላለን፡፡ ይሄ የሚያመለክተን አንድ የሠራነው ነገር ስህተት ሆኖ ሲገኝ ማረም መጥፎ አለመሆኑን ነው፡፡ ወደ ትክክሉ፣ ወደፍትሐዊው መንገድ ተቃንተን እንድንጓዝ ይረዳናልና! አራተኛው ልዩ ጠባዩ፤ የእርሳሱ የላይኛው የእንጨት ልባሱ ወይም ቅርፊቱ ሳይሆን ዋናው ከውስጡ ያለው ግራፋይት /እርሳሱ/ ነው ቁም ነገሩ፡፡ ይህ ራስህ ውስጥ ምን እየተከናወነ እንደሆነ ልብ ማለት እንዳለብህ ትምህርት ይሰጥሃል፡፡ ዋናው የውስጣችን፣ የመሠረታችን ጉዳይ፤ ማለት ነው፡፡ አምስተኛውና የመጨረሻው ልዩ ነገር፤ እርሳስ ባለፈበት ሥፍራ ሁሉ ምልክት ወይም አሻራ ይተዋል፡፡ ልክ እንደ እርሳሱ ራስህን ቆጥረህ ብታስበው፤ እያንዳንዱ በህይወትህ እየሠራህ የምታልፈው ነገር ሁሉ ምልክት ይተዋል፡፡ ስለዚህ ያለፍክ ያገደምክባትን የሕይወት መንገድ ሁሉ አስተውል፡፡

                                                             * * *

ከአያት ከቅድመ አያት የወረስናቸውን ትምህርቶች በአግባቡና በቅጡ ሥራ ላይ ካዋልናቸው ከመሠረታዊ የኑሮ ግልጋሎታቸው ባሻገር አገርን ለማሻሻል የለውጥ አንጓ ይፈጥሩልናል፡፡ የራሳችንን ሰላም የምንፈጥረው ራሳችን ነን፡፡ የሚመራን እጅ/አምላክ እንዳለ ማሰብ ያለብን ራሳችን ነን፡፡ ህይወታችንን ማለትም እራሳችንን በየጊዜው መቅረጽ ይኖርብናል፡፡ ይህንን ስናደርግም የየጊዜውን ህመም ተቋቁመን መሆን አለበት፡፡ ስህተትን አርሞ ወደ ፍትሐዊው መንገድ መጓዝ ሌላው ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ ህይወት ከላይ ከላይ ስትታይ ብልጭልጯ ብዙ ነው፡፡ ብልጭልጯ ግን እንደእርሳሱ የተቀባ የእንጨት ቅርፊት ነው፡፡ ዋናው ውስጧ ነው፡፡ ቡጧ ነው፡፡ ውስጣችንን እናንብብ። አገራችንን እንወቅ፡፡ በውስጥ የሚከናወነውን እናጢን፤ እናውጠንጥን፡፡ ንፁህ ዜጋ በውስጡ የሚካሄደውን ክንዋኔ ሲያውቅ ራሱን ያውቃል፡፡ ቀጣይ መንገዱ ያውቃል፡፡ ለሀገሩ የሚበጀውን ያደርጋል፡፡ በእያንዳንዱ ቀን ላይ የምንተወውን አሻራ ብናውቅ የአመት የአምስት ዓመቱን፣ የዘለቄታውንም አሻራ እናስተውላለን፡፡ አሻራችንን ጠንቅቀን እንወቅ፡፡ ያም ሆኖ አንዳንዶች የሁሉን ተግባር አልፋና ኦሜጋ ራሳቸውን አድርገው ይፎክራሉ፡፡ “ሁሉ ያማረ በእኔ ነው፡፡ ሁሉን እምሠራ እኔ ነኝ፡፡ ከማንም የተሻልኩ ንፁሕ ነኝ፤ አልተሳሳትኩም፤” በማለት ይፎክራሉ፡፡ ይሄ በተራ ግንዛቤ እንኳ ሲታይ “የሚሠራ ይሳሳታልን” መርሳት ነው፡፡

“ክንፍ አለኝ፣ መልዐክ ነኝ ብለህ አትፎክር ትንኝም ክንፍ አላት፣ ባየር ለመብረር…” ይሉናል ብርሃኑ ድንቄ፡፡ የአደጉና አዳጊ፣ ትላልቅና ትናንሽ አገሮች አንዱ አንዱን የሚያይበት ዐይኑ መለያየቱ እንጂ እንከን አልባ ብሎ አገር የለም፡፡ የዓለም ገዢ ነን የሚሉት ኃያላንም ቢሆኑ፡፡ “ዓለም አቀፍ ዴሞክራቲክ ካፒታሊዝምም ቢሆን እንደዓለም አካላይ ኮሙኒዝም፤ አስተማማኝ ሥርዓት አለመሆኑን ልብ በሉ”፤ ይለናል ጆን ግሬይ፡፡ ዕምነት እምንጥልባቸውን ታላላቅ አገሮች በዲፕሎማሲያዊ ጥንቃቄ እንያዛቸው፡፡ እነሱም ለጥቅማቸው፣ እኛም ለጥቅማችን፤ እንበል። ሲያመሰግኑን “ሊበሏት የፈለጓትን አሞራ ጅግራ ይሏታል”ን “እንዲህ እያልሽ ውቴልሺን ሽጪ” ማለትን እንልመድ፤ ቢያንስ በሆዳችን፡፡ ያለጥቅም እጅ የማይዘረጋበት ዘመን ነው፡፡ በተለይ ዕምነተ ካፒታሊዝማችን ያለዕውቀትና ከልኩ ያለፈ ሲሆን “የባለጌ ሃይማኖት ከጅማት ይጠናል” ነው እሚሆነው፡፡ ፓውሎ ኮሄሎ የተባለ ፀሐፊ፤ “አንዳንድ ታላላቅ መንግሥታት በሽብርተኝነት ላይ የሚካሄድ ጦርነት ባሉት ላይ፣ የዓለም አቀፍ የፖሊስ መንግሥት መፍጠሪያ ዘዴ አድርገው ይጠቀሙበታል” ሲል ይሟገታል፡፡

“እቺ ጠጋ ጠጋ ሣር ፍለጋ ሳትሆን ዱባ ለመስረቅ ነች” እንደሚባለው ነው፤ ማለቱ ነው፡፡ “አንዱ ሲያለማ፣ ሌላው ያደለማ” በሆነበት የአገራችን ሁኔታ ውስጥ፤ ምሥጡን ከመዥገሩ፣ መወቴን ከአለሌ፣ ጨውን ከአሞሌ፣ ቱሪስትን ከፒስኮር፣ ህንዱን ከሳኒያን፣ ዶፉን ከወጨፎ፣ ጐረቤትን ከጐረቤት፣ ኔትዎርክን ከኖ-ወርክ…ለይተን ካልተጓዝን፣ የትም አንደርስም፡፡ እንወቅበት። ዛሬ “ከልጄ ለቅሶ፣ የጌታዬ ደቦ ይበልጣል” የሚል አድርባይ የበዛበት ጊዜ ነው፡፡ ለጥቅም የማይነቀል ባህር ዛፍ የለም፡፡ ባለጊዜን ማወደስ በየሥርዓቱ የሚታይ ክስተት ቢሆንም የከፋ ጊዜ ሲመጣ ባልሠራው የሚሞገስ፣ ባልፀዳበት ንፁህ የሚባል እየበዛ መሄዱ አንድም የአወዳሹን የፈጠጠ ደጅ ጠኒ አዕምሮ፣ አንድም የተወዳሹን ግብዝነት ያሳያል፡፡ ይሄ ደግሞ በምንም መለኪያ አገር ገንቢ ነው ሊባል አይችልም፡፡ ገና ሥራው ሳይሰራ በመፈክርና ይሄን ላደርግ ይህን ልፈጥር አቅጃለሁ በሚል ከፍ - ከፍ አርጉኝ ማለት፤ “ተዋጊ፤ ወደ ጦር ሜዳ ሲሄድ ሳይሆን፣ ሲመለስ ነው የሚወደሰው” የሚባለውን ተረት መዘንጋት ይሆናል!

ዶ/ር ነጋሶ የአቶ ሌንጮ መመለስ በበጐ የሚታይ ነው ብለዋል

</p በኢትዮጵያ መንግስት “ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመው የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር /ኦነግ/ ከፍተኛ አመራር የነበሩት አቶ ሌንጮ ለታ፣ አዲስ ያቋቋሙትን ፓርቲ ይዘው በሰላማዊ መንገድ ለመታገል አዲስ አበባ መግባታቸውን ምንጮች ገለፁ፡፡ ኢህአዴግ የደርግ ስርዓትን አስወግዶ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር ከአቶ መለስ ዜናዊ ጋር ለፕሬዝዳንትነት እንዲወዳደሩ ተጠቁመው አልፈልግም ማለታቸው የሚነገርላቸው አቶ ሌንጮ፤ ወደ ሰላማዊ ትግል መግባታቸውን በተመለከተ ብዙዎች አምነው እንዳልተቀበሏቸው የገለፁ ሲሆን ከሶስት ቀናት በፊት አዲስ አበባ መግባታቸው ታውቋል፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ኢትዮጵያ መግባታቸውን አስመልክቶ የቀድሞ ድርጅታቸው ኦነግ ስላለው አቋም ከውጭ ሚዲያዎች የተጠየቁት አቶ ሌንጮ፤ “እሱን ኦነግ ነው የሚያውቀው” ሲሉ መልሰዋል፡፡ የአቶ ሌንጮ ለታን ወደ ሀገር ቤት መመለስ አስመልክቶ አስተያየት የተጠየቁት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፤ ቀደም ሲል ኦነግ በሁለት አመለካከቶች መሃል ሲዋልል የነበረ ፓርቲ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ አንደኛው፤ ኦሮሚያ ሙሉ ለሙሉ መገንጠል አለባት የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ትገንጠልም አትንገንጠልም በሚለው አመለካከት መሃል የሚዋልል ነበር ይላሉ፡፡

አሁን የእነ አቶ ሌንጮ ወደ ሠላማዊ ትግል መመለስ፣ በኢትዮጵያ አንድነት እምነት የነበረው አካል ተለይቶ መውጣቱን ያመለክታል ብለዋል፡፡ ይህም በበጐ የሚታይ ነው ያሉት ዶ/ር ነጋሶ፤ ለኢትዮጵያ ህዝብና ለኦሮሞ ህዝብ ትግል መልካም መንገድ እንደሚከፍትም ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ቀደም ሲል በኦነግ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ማለፋቸውን “ዳንዲ፣ የነጋሶ መንገድ” በሚለው መጽሃፋቸው ጠቁመዋታል፡፡ ከኦነግ ዋና ዋና መሪዎች አንዱ የነበሩት ሌንጮ ለታ “ወደ ሰላማዊ ትግል ተመልሻለሁ” ማለታቸውን መንግስት ያውቀው እንደሆነ የተጠየቁት የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ በበኩላቸው፤ በግለሰብ ደረጃ የተሟላ መረጃ እንደሌላቸው ጠቁመው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሰየመ ድርጅት ወደ ሰላማዊ ትግል መመለሱ የሚረጋገጥለትና ስያሜው የሚነሳለት ግን በራሱ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው ብለዋል፡፡ አቶ ሌንጮ ለታን በአካል አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡