Administrator

Administrator

“ድብቆቹ ህገ-ደንቦች! የጽዮናውያን አለሙን የመቆጣጠር እቅድ ሰነድ” የተሰኘውና በግደይ ገ/ኪዳን የተዘጋጀው መጽሃፍ ሁለተኛ ጥራዝ ለገበያ ቀረበ፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም 24 ህገ ደንቦች የያዘውን የመጽሃፉን የመጀመሪያ ክፍል ለአንባቢያን ያቀረበ ሲሆን በዚህኛው የመጽሃፉ ክፍል ስለ ህገ-ደንቦች ታሪካዊ አመጣጥ እንዲሁም ህገ-ደንቦች እውነተኛ ናቸው፣ ወይንስ የግምት የሚሉ መከራከሪያ ሃሣቦች እንደተካተቱ ተጠቁሟል፡፡ ደራሲው ከዚህ ሌላ “ጥንታዊ ውጊያ”፣ “ህልም አጨናጋፊዎቹ”፣ “የአሜሪካ የሚስጥር ተቋም” በሚሉ ሥራዎቹም ይታወቃል፡፡

ማነው ተጠያቂ ጋዜጠኞች፤ አሰልጣኙ፤ ተጨዋቾች፤ ፌደሬሽኑ? በደቡብ አፍሪካ አዘጋጅነት ሲካሄድ የቆየው 3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ከኢትዮጵያ ጋር በአንድ ምድብ የነበሩት ጋና እና ሊቢያ በሚያደርጉት የዋንጫ ጨዋታ ዛሬ ሊፈፀም ነው። በምድብ 3 የነበረው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሊቢያ 1ለ0 እንዲሁም በጋና 2ለ0 መሸነፉ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ምድብ እርስ በራስ በተገናኙበት ጊዜ ጋና እና ሊቢያ 1 እኩል አቻ ተለያይተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን ያለበት ምድብ በደቡብ አፍሪካ በተደረገ አህጉራዊ ሻምፒዮና ለዋንጫ ጨዋታ የደረሱ ሁለት ቡድኖችን ሲያስገኝ የቻን የዋንጫ ጨዋታ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ ከዓመት በፊት እዚያው ደቡብ አፍሪካ በተስተናገደው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ቡድን በምድብ 3 ከናይጄርያ፤ ቡርኪናፋሶ እና ዛምቢያ ጋር ተደልድሎ ነበር። በምድብ ጨዋታዎች ዋልያዎቹን ናይጄርያዎች 2ለ0 እንዲሁም ቡርኪናፋሶ 4ለ0 አሸንፈው እርስ በራስ ተገናኝተው 0ለ0 አቻ ከተለያዩ በኋላ በፍፃሜ ጨዋታ ናይጄርያ 1ለ0 ቡርኪናፋሶን በማሸነፍ ዋንጫውን ወስዳለች፡፡ ሊቢያ እና ጋና ለቻን የዋንጫ ያለፉት ተጋጣሚዎቻቸውን በመለያ ምቶች አሸንፈው ነው፡፡ ጋና ናይጄርያን 4ለ1 ስታሸንፍ ሊቢያ ደግሞ ዚምባቡዌን 5ለ4 በመርታት ለፍፃሜው ደርሰዋል።

የሊቢያው አሰልጣኝ ሃቪዬር ክሌሜንቴ በወጣቶች ስብስብ የተጠናከረው ቡድናቸው ለዋንጫ ጨዋታ የደረሰበትን አስደናቂ ጥረት እንደሚከሩበት የተናገሩ ሲሆን፤ የጋና አሰልጣኝ ማክሲም ኒኮዲ በበኩላቸው በቻን ውድድር ምርጥ ብቃት ያሳዩ ወጣት ጋናውያን ዋንጫውን በመውሰድ ለጥቋቁሮቹ ክዋክብቶች የዓለም ዋንጫ እድል መነቃቃት እንዲፈጥሩ ተስፋ አድርገዋል፡፡ ሊቢያ በአህጉራዊ ውድድር ለዋንጫ ጨዋታ ስትደርስ ከ1982 እኤአ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን በ2009 እኤአ ላይ በኮትዲቯር በተካሄደው 1ኛው ቻን ላይ በዋንጫ ጨዋታ በዲሪ ኮንጎ 2ለ0 ተሸንፋ ዋንጫውን ያጣችው ጋና ክብሩን መልሶ ለማግኘት አጋጣሚ ተፈጥሮላታል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለቻን ውድድር ባዘጋቸው 3.2 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ መሰረት ሻምፒዮን ቡድን 700 ሺ ዶላር፤ ለሁለተኛ ደረጃ 400ሺ ዶላር፤ ለደረጃ የሚጫወቱ ሁለት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 250ሺ ዶላር፤ በሩብ ፍፃሜ የወደቁ አራት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 175ሺ ዶላር፤ በምድባቸው 3ኛ ደረጃ ያገኙ 125ሺ ዶላር እንዲሁም በየምድባቸው አራተኛ ደረጃ ይዘው የጨረሱ ቡድኖች እያንዳንዳቸው 100ሺ ዶላር እንደሚከፈላቸው ታውቋል። 3ኛው የአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮና ቻን ውድድር ዛሬ በዋንጫ ጨዋታ ኬፕታውን በሚገኘው የኬፕታውን ስታድዬም ሲደረግ የፊፋው ፕሬዝዳንት ሴፕ ብላተር በክብር እንግድነት የሚገኙ ሲሆን በታዋቂ የደቡብ አፍሪካ ሙዚቀኞች እና ዳንሰኞች ልዩ የመዝጊያ ስነስርዓት እንደሚደረግም ታውቋል፡፡ ከዋንጫ እና የደረጃ ጨዋታዎች በፊይት በቻን ውድድር በተደረጉ 28 ጨዋታዎች 72 ጎሎች የተመዘገቡ ሲሆን ይህም በአንድ የቻን ጨዋታ 2.6 ጎል በአማካይ የሚቆጠርበት ሆኗል፡፡

በደቡብ አፍሪካ መስተንግዶ የቻን ውድድር ለ3ኛ ጊዜ በስኬት እንደተከናወነ እየተገለፀ ሲሆን፤ በውድድሩ የሚመዘገብ ውጤት በወዳጅነት ጨዋታ ደረጃ ለፊፋ ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ ነጥብ የሚያሰጥ ሊሆን መብቃቱ አዲስ የለውጥ ምእራፍ ነው ተብሏል። በቻን ውድድር ተሳታፊ በሆኑ 16 ብሄራዊ ቡድኖች ለአፍሪካ እግር ኳስ ተተኪ የሚሆኑ ታዳጊ ተጨዋቾች በብዛት መታየታቸው፤ ተመጣጣኝ ፉክክሮች መደረጋቸውም ተደንቋል፡፡ በሌላ በኩል የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በ2015 ለሚደረጉ ውድድሮች የማጣርያ ጨዋታዎች ድልድን ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል፡፡ በ2015 እኤአ ላይ ሞሮኮ ለምታስተናግደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተዘጋጀው የማጣርያ ፕሮግራም ላይ 51 አገራት ተሳታፊ ሲሆኑ ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ዓመታት በአህጉራዊ ውድድሮች ባስመዘገበችው ውጤት ለምድብ ማጣርያ በቀጥታ ካለፉት 21 አገራት አንዷ ሆናለች፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ29 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና በዋና ውድድር በነበረው ተሳትፎው 4 ነጥብ፤ በ2012 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ተሳትፎው 1 ነጥብ፤ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የማጣርያ ጨዋታዎች በ7 ነጥብ አስመዝግቦ በአጠቃላይ 12 ነጥብ ለምድብ ማጣርያ ካለፉት 21 አገራት መካከል 16ኛ ደረጃ አግኝቷል፡፡ በተያያዘ ካፍ በ2015 በሀ20 እና በሀ17 ብሄራዊ ቡድኖች ለሚደረጉ የቅድመ ማጣርያ ውድድሮች የጨዋታ ድልድል አሳውቋል። ኢትዮጵያ በ2015 ሴኔጋል በምታዘጋጀው የሀ20 ሻምፒዮና በቅድመ ማጣርያ ከሲሸልስ ጋር የትገናኝ ሲሆን በደርሶ መልስ ጥላ ለማለፍ ከበቃች በሁለተኛ ዙር ማጣርያ ተጋጣሚዋ ደቡብ አፍሪካ ነች፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ2015 በሀ17 ኒጀር ለሚደረገው የታዳጊዎች አህጉራዊ ሻምፒዮና የቅድም ማጣርያ እንድትሳተፍ የቀረበውን ግብዣ ሳትቀበል ቀርታለች፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኃላፊዎች ዛሬ በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ከጋዜጠኞች እና ከባለድርሻ አካላት ጋር የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በሚመለከት የግምገማ መድረክ ሊያወያይ እንደሆነ ታወቀ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ፤ ተጨዋቾች እና ፌደሬሽን ከናይጄርያ ጋር በካላባር ከተደረገው የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ጨዋታ በኋላ በተለያዩ አወዛጋቢ አጀንዳዎች ከስፖርት ጋዜጠኞች የጀመሩት ንትርክ ሰሞኑን ተባብሷል፡፡ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኃላፊዎች ከ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን ጨምሮ በቻን ውድድር ላይ የነበሩ ተጨዋቾች እና ከቡድኑን አባላት በኢንተርኮንቲነታል ሆቴል ስብስባ ያደረጉ ሲሆን በዚሁ መድረክ አንዳንድ ተጨዋቾች በቻን ተሳትፎ ውጤቱ የጠፋው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች የሚሰጡት አስተያየት አዕምሯችንን በመረበሹ እና በመበጥበጡ በማለት አቤቱታ ማሰማታቸው ተነግሯል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በቻን ውድድር ያሳየው ደካማ እንቅስቃሴ እና ውጤቱ ከምን የመጣ ነው? በሚል ርዕስ በተካሄደው ስብሰባ ተጨዋቾቹ አስተያየት ሲሰጡ ከመጀመሪያው ቀን ሽንፈት በኃላ በነበሩት ሁለት ጨዋታዎች ሜዳ ውስጥ እንዴት መጫወት እንዳለብን እስክንዘነጋ ድረስ የጋዜጠኞቹ ትችት ተፅእኖ ነበረው ብለው አማርረዋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዋቂ ነኝ ባይ ሰው ወደገበያ ቦታ ይሄድና “ዕጣ - ፈንታችሁን እነግራችኋለሁና ማወቅ

የምትፈልጉ ተሰብሰቡ” ይላል፡፡
ሰው ባንድ ጊዜ ይሰበሰባል፡፡ ለመጀመሪያው ሰውዬ፤ “ምን እንድረዳህ ትፈልጋለህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ይህ ሰውዬ

አለባበሱ ለየት ያለ ነው፡፡ በጣም ደማቅ አረንጔዴ ካፖርትና አረንጓዴ ቆብ አድርጓል፡፡ አረንጔዴ ጫማም ተጫምቷል፡፡
ሰውዬውም፤ “እዚህ አገር ያልሞከርኩት ሥራ የለም፡፡ ሆኖም ሊያልፍልኝ አልቻለም፡፡ አሁን ተስፋ ወደመቁረጡ ነኝ፡፡

የመጨረሻ ዕድሌን አንተ በምትሰጠኝ ምክር እሞክራለሁና ምክርህን ለግሰኝ” አለው።
አዋቂውም፤ “ዕጣ ፈንታህ ይታየኛል፡፡ የሚያልፍልህ የተጠራቀመ ሀብት አለና እሱን ካለበት ቦታ ቆፍረህ በማውጣት

ነው፡፡ ያ ሀብት ባለቤቱ በቀላሉ ሳይወጣ ሳይወርድ፣ ሳይደክም ያገኘው በመሆኑ አይጠቀምበትም፡፡ ውድ ውድ የቤት

ዕቃዎች፣ የቅርሳቅርስ ጌጦች፣ አልማዝና ወርቆች እንዲሁም የከበረ ድንጋይ አለው፡፡ አሁን የአንተ አንድ ትልቅ ሥራ

የዚያ ሰው ቤት የት እንዳለ ማወቅ ብቻ ነው፡፡ እንደምንም ቤቱን ካገኘኸው፤ እሱ ብዙ ጊዜውን ውጪ ስለሚያሳልፍ

ልትወስድበት ትችላለህ” አለው፡፡
ሰውዬው ተደስቶ በስንት ጊዜ ካጠራቀመው ገንዘብ አውጥቶ ለአዋቂው ዋጋውን ከፈለው፡፡ አዋቂው በጣም አመስግኖት

“እንግዲህ በደማቅ አረንጔዴ ካፖርትህ፣ በጫማህና በባርሜጣህ አስታውስሃለሁ” አለው፡፡ ባለአረንጓዴ ካፖርቱ ሰው

መንገዱን ቀጠለ፡፡
አዋቂውም ሌሎች ተረኛ ሰዎችን እያነጋገረ፤ ዕጣ ፈንታቸውን መንገሩን ቀጠለ፡፡ አንዷን “ምቀኞች አሉብሽና ሰፈርሽን

ለቀሽ ሌላ ቦታ ኑሪ” ይላታል፡፡ አመስግናው ገንዘብ ከፍላ ትሄዳለች፡፡ አንዱን ደግሞ “አለቃህን ደጅ ካልጠናህ በስተቀር

አይሳካልህም፡፡ ስታየው ላንተ ደግ ይመስልሃል፤ ግን ዕድገትህን ቆልፎ ይዞብሃል” አለው፡፡ አመስግኖና ገንዘብ ከፍሎት

ይሄዳል፡፡ ሌላውን “አዲስ ሸሪክ ያዝ፡፡ እስካሁን አብሮህ ይሠራ የነበረው ሰው ምቀኛህ ነው!” ይለዋል፡፡ ይሄም ገንዘብ

ሰጥቶት አመስግኖት ይሄዳል፡፡ በዚህ ዓይነት ለብዙ ሰዓታት የዕጣ - ፈንታ ትንቢት ሲነግር ይቆያል፡፡
በድንገት አንድ ሰው ወደ አዋቂው እየሮጠ ይመጣል፡፡
“ምነው ምን ሆነህ እንዲህ እያለከለክህ መጣህ?” ሲል አዋቂው ይጠይቃል፡፡
ሲሮጥ የመጣውም ሰውዬ፤
“አዋቂ ሆይ! እኔ የሰፈርህ ሰው ነኝ፡፡ የሰፈራችን ሰዎች ሁሉ ተሰብስበው “ያን አዋቂ ከወዴት እናግኘው?” ሲባባሉ

ሰማሁ፡፡ “ለምን ፈለጋችሁት ብዬ ብጠይቅ፤ “ሌባ ቤቱ ገብቶ ያለ የሌለ ንብረቱን ጥርግርግ አድርጐ ወስዶበት ሄደ”

አሉኝ፡፡ እኔም የሰፈር ሰው ሆኜ ሳልነግርህ ብቀር ጥሩ አይሆንም!” ብዬ ስሮጥ መጣሁ አለው”
አዋቂው እጅግ ተደናግጦ ተነስቶ ወደሠፈሩ በረረ፡፡ ሰዎች ተሰብስበው አገኘ፡፡
“ምን ዓይነት ሰው ነው የሰረቀኝ? አይታችሁታል ወይ?” ሲል ጠየቀ፡፡
ሁሉም ዝም ዝም አሉ፡፡ አንድ ትንሽ ልጅ ግን፤
“እኔ አይቸዋለሁ” አለ፡፡
“ምን መሳይ ነው?” ሲል ጠየቀ አዋቂው፡፡
ልጁም፤
“አረንጌዴ ካፖርት፣ አረንጔዴ ባርሜጣ፣ አረንጔዴ ጫማ ያረገ ነው!” አለው፡፡
“አዬ ጉድ! በገዛ ጥይቴ ነዋ የተመታሁት!” ብሎ እያዘነ ወደቤቱ ገባ፡፡
*    *    *
አበሻ “ጠንቋይ ለራሱ አያውቅ!” ይላል፡፡ የሌሎችን እጣ - ፈንታ እየተናገረ የራሱን ዕጣ ፈንታ አያውቅም ለማለት ነው፡፡

አብዛኞች የታዳጊ አገር መንግሥታት የራሳቸው ቤት እየተዘረፈ ስለሌሎች አገሮች ሙስና ሲያወጉ ያመሻሉ፡፡
የብሪቲሽ ጠቅላይ ሚኒስቴር ጂም ካላግሃን ለፓርላማው ባረጉት ንግግር “ውሸት የዓለምን ግማሽ አዳርሶ ሲጨርስ፤

ዕውነት ገና ቦት - ጫማውን እያጠለቀ ነው!” ያለው ወዶ አደለም፡፡ ቀጣፊው ቢበዛበት ነው፡፡
የምንናገረው የምናወጣው መመሪያ የምንመራበት መራሄ - ፅድቅ፣ የምናቅደው እቅድ፤ የምንነድፈው ስትራቴጂ፤

መሠረታቸው ዕውነት እንጂ ባዶ ተስፋ መሆን የለበትም፡፡ ዕውነት ላይ ስንመረኮዝ አዕምሮአችንም ልቡናችንም ከፍሬ

ጉዳያችን ጋር የተቆራኘ ይሆናል፡፡ የምናፈራው ፍሬ የዚህ ውጤት ነው፡፡
ለመንገዶቻችን ሁሉ አማራጭ እናብጅላቸው፡፡ በህይወት ውስጥ አንድና ቀጥ ያለ መንገድ አይገኝም። በርካታ መንገዶች

ናቸው የመሻሻል አማራጭ የሚሰጡን፡፡
ብልጧን አይጥ ተመልከት፡፡ ኑሮዋን ለአንድ ጉድጓድ ብቻ አትሰጥም” ይላሉ ጣሊያኖች፡፡ አንድም በገዢው ፓርቲ ትይዩ

በተፃራሪ የቆሙ፣ አንድም ወግነው ያሉ ሁለት ቁምነገሮችን ማሰብ አለባቸው፡፡
አሿፊው እረኛ፤ “ተኩላ ተኩላ!” እያለ ሲቀልድ ከርሞ ዕውነተኛው ተኩላ መጥቶ በጐቹን ሲበላ ማን ያግዘው? ዋዛ ፈዛዛ

ልብ አያስገዛ! ሆነ!!”
በአንፃሩ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤
“እሳት! እሳት” ስትል “ቀጣፊ ነሽ” ሲሏት
ሰፈሩ ነደደ፣ በዐይናቸው እያዩት!”
የሚለውንም አንርሳ፡፡ የሀገር ጉዳይ የዋዛ ፈዛዛ አይደለም፡፡ የሚሉንን እንስማ፡፡ እሳት ከነደደ በኋላ፣ ቤት ፈርሶ ካበቃ

በኋላ አይደለም ህዝባችን አደገ ማለት ያለብን፡፡ ከህዝብ እንመካከር፡፡
ለማሰብ ከሰነፍን፣ መጥፎ ሥራ እንኳ ለመሥራት ከንቱ ከሆን፣ ያንን ለመቀበልም ከፈራን፤ ጥበብና ብስለት የሚባል

በሠፈራችን አይደርስም፡፡
ወጣቶችን በመልካም ስብዕና መቅረፅ የሁሌም ግዴታችን መሆን አለበት፡፡ “አጓጉል ትውልድ ያባቱን መቃብር ይንድ”

ነውና ታሪክን፣ ባህልን፣ ብሔረተኝነትን፣ ጀግንነትን ይዞ ያላደገ ትውልድ የማንነት ድቀት ወይም ቀውስ (Identity

crisis) ውስጥ እንደሚገባ የዓለም ታሪክ በስፋት አሳይቶናል፡፡ የወላጅ የመምህርና የመንግሥት ሦስትዮሽ ድጋፍ

ያስፈልገዋል፡፡
አንድም በግብረ - ገብነት፣ አንድም በትምህርት፣ አንድም በፖለቲካ ስብዕና ብቃት እንዲጠናና እንዲጐለብት ማድረግ

በተለይ ዛሬ ዋና ጉዳይ ነው!
ሽማግሌዎቹ ወጣቶቹን ከእናንተ እንበልጣለን ሲሉ፤ ወጣቶቹ ይሄ ምን ዓይነት የጅል አስተሳሰብ ነው እያሉ

እስከሚመራመሩና እስኪያሰላስሉ፤ ሲያረጁ፤
መላው ቀለጠ፡፡ አገር ከሰረ፡፡
“ሲዋሽ ልክ እንደምሥክር ነው” ይላሉ ሩሲያኖች፡፡ የምንዋሸው ነገር የትውልድ መዳከም ነው፡፡ ዛሬም እናስብበት!
“የምዋሸው ዕውነቴን ለመቆጠብ ብዬ ነው” አለ አሉ አያ ዋሾ፡፡ የረቀቀ ውሸት መዋሸት ካልቻልን በስተቀር ዕውነት

መናገርን መመሪያ ማድረግ ምርጥ ነገር ነው!!

          የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩትና በአሁኑ ሰዓት የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት የተከበሩ አቶ ኡመድ ኡባንግ፤ ከአገር መኮብለላቸውን ምንጮቻችን ገለፁ፡፡ አቶ ኡመድ ኡባንግ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ከሃገር መውጣታቸውን የጠቆሙት ምንጮች፤ ወደ ኢትዮጵያ እንደማይመለሱ ለሚቀርቧቸው ሰዎች መናገራቸውን አመልክተዋል። የሚኒስትር ዴኤታውን መኮብለል በተመለከተ የጠየቅናቸው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም፤ አቶ ኡመድ በስራ ገበታቸው ላይ እንደሌሉ ማረጋገጣቸውን ገልፀው መስሪያ ቤታቸው ለተለየ ተልዕኮ እንዳላሰማራቸውና ፈቃድ ሳይጠይቁ ከስራ ገበታቸው እንደቀሩ ተናግረዋል፡፡ ሚ/ር መስሪያ ቤታቸው ጉዳዩን እያጣራ መሆኑንም አክለው ገልፀዋል፡፡ አቶ ኡመድ ከጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንትነት የተነሱት በክልል መንግስቱ የስራ አፈፃፀም ላይ ለአንድ ሳምንት ከዘለቀ ግምገማ በኋላ ሲሆን፤ ሌሎች የክልሉ ባለስልጣናትም በዚሁ ግምገማ ከኃላፊነታቸው መነሳታቸው ይታወሳል፡፡

         ገዳሙ ጨርሶ ሳይጠፋ ጉዳያቸው በሲኖዶሱ እንዲታይ መናንያኑ ጠይቀዋል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀ/ስብከት ሞረትና ጅሩ ወረዳ የሚገኘው የመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን የደብረ ብሥራት አቡነ ዜና ማርቆስ አንድነት ገዳም ተፈትቶ፣ መናንያኑና መነኰሳቱ መበተናቸውን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገለጹ፡፡ ጥንታዊውን ገዳም ለመፈታት፣ ማኅበረ መነኰሳቱንም ለመበተን ያበቃቸው በአካባቢ ተወላጅነት የገዳሙን መሬት በተለያዩ ጊዜያት ተቆጣጥረው ለግላቸው ይጠቀሙ ከነበሩ ግለሰቦች ጋር ተፈጥሮ የቆየውና በተለያዩ ምክንያቶች እየተካረረ የመጣው አለመግባባት መኾኑን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡ በኅዳር ወር 2006 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ገዳሙን ለቀው የወጡት በቁጥር ከ50 - 80 የሚገመቱ መነኰሳት፣ መነኰሳዪያትና መናንያን ከተለያዩ አህጉረ ስብከትና ክልሎች የተሰባሰቡ ሲኾኑ በሀገረ ስብከቱ ውሳኔ ከአስተዳዳሪነት የተነሡትን አበምኔቱን መ/ር አባ ተክለ ብርሃን ሰሎሞንን ጨምሮ ከፊሎቹ በአሁኑ ወቅት በደነባ በኣታ ለማርያም ገዳም ተጠልለው እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የወረዳው መንግሥታዊ አስተዳደር፣ ከእነዋሪና ደነባ የተውጣጡ የሀገር ሽማግሌዎች ገዳማውያኑንና ግለሰቦቹን በተለያየ ጊዜ በማገናኘት ለአለመግባባቱ የመፍትሔ ሐሳብ ሲሰጡና ውሳኔ ሲያሳልፉ እንደቆዩ ያስታወሱት መነኰሳቱ፤ ‹‹ተሰዳጅና መጤ›› ከሚል በቀር ግለሰቦቹ የሚያቀርቡባቸው ክሦች መሠረተ ቢስ እንደኾኑ ተረጋግጧል ብለዋል፡፡ የገዳሙን ሥርዐተ ማኅበር በመጣስ የመሬት ይዞታውን፣ ቅርሱንና የልማት ቦታውን ለመከፋፈል የሚሹ ግለሰቦች በሥነ ምግባር ጉድለት ርምጃ ከተወሰደባቸው የስም መናንያን ጋራ በማበር ያቀረቡትን አቤቱታ ብቻ በመቀበል በፓትርያርክ የሚሾሙት አበምኔት በሀ/ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤ ውሳኔ ከሓላፊነት መነሣታቸውን ያስረዱት ማኅበረ መነኰሳቱ፣ አንዳንድ የሀ/ስብከቱን ሓላፊዎች በስም በመጥቀስ ለችግሩ መባባስ ተጠያቂ አድርገዋቸዋል፡፡ የገዳሙን መሬት ይዘው ከገዳማውያኑ ጋራ ተቀላቅለው ይኖሩ የነበሩትን የአካባቢውን አርሶ አደሮች ትክ መሬት እንዲያገኙና ለንብረታቸውም ካሳ እንዲሰጣቸው በማድረግና ጣልቃ ገብነትን በመከላከል የገዳሙን ይዞታና ሥርዐተ ማኅበሩን ያስከበሩትን፤ በግብርናና በሽመና ሥራዎች፣ በሙዓለ ሕፃናት፣ በኪራይ ቤቶች ግንባታ የራስ አገዝ ልማትን በማስፋፋት ልመናን ያስቀሩትን አበምኔት አላግባብ ከሓላፊነት ማንሣት÷ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ኤፍሬም ስለ አበምኔቱ የአስተዳደርና ትምህርት ብቃት እንዲሁም ልማታዊነት ሲሰጡ የቆዩትን ምስክርነት የሚያስተባብልና የገዳሙን መተዳደርያ ደንብ የሚጥስ ከመኾኑም በላይ በሀ/ስብከቱ ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ላይ የተንሰራፋው የመልካም አስተዳደር ችግር አስከፊ መገለጫ ነው ብለዋል ማኅበረ መነኰሳቱ፡፡

ከገዳማቸው የተፈናቀሉት ማኅበረ መነኰሳቱ ሥርዐተ ማኅበራቸውን ጠብቀው በገዳሙ የጀመሩትን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ልማታዊ አገልግሎት ለመቀጠል እንዲችሉ፤ የገዳሙ ቅርሶች፣ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረቶች እንዲጠበቁ፣ በገዳሙ ያለጧሪ የቀሩት ድኩማን አረጋውያን ደኅንነትም እንዲጠበቅ ቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ውሳኔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡ የደብረ ብሥራት ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ ገዳም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዝሙር በኾኑት አቡነ ዜና ማርቆስ የተመሠረተ የዐሥራ ሁለተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ገዳም መኾኑን የገዳሙ ታሪክ ይገልጻል። ገዳምነቱን ሳይለቅ እስከ 8000 መናንያንን እያስተዳደረ በሥርዐተ ማኅበር በቆየው ገዳም፣ ሰበካ ጉባኤ በማቋቋም ወደ ደብርነት እንዲቀየርና በቃለ ዐዋዲ እንዲመራ ለማድረግ ተሞክሮ እንደነበር የገለጹት የዜናው ምንጮች÷ ሲኖዶሱ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የገዳማት አስተዳደር መምሪያና የቅርስ ጥበቃ የሚመለከታቸው አካላት ኹሉ ከጻድቁ የእጅና የመጾር መስቀሎች ጀምሮ በርካታ ቅርሶች የሚገኙበትን የመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሥርዐተ ምንኵስናና የትምህርት ማዕከል ጨርሶ ሳይጠፋ መታደግ እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል፡፡

በቅርቡ የተቋቋመው “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” ከትናንት በስቲያ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሂዶ የማህበሩን የመተዳደሪያ ደንብ ያፀደቀ ሲሆን አመራሮቹንና የስራ አስፈጻሚ አካላትንም መርጧል፡፡ ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ሊቀመንበር፣ ጋዜጠኛ ስለሺ ሃጐስ ምክትል ሊቀመንበር እንዲሁም ጋዜጠኛ ነብዩ ሃይሉ ዋና ፀሃፊ በመሆን የተመረጡ ሲሆን ጋዜጠኛ አያሌው አስረስ የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ አፈ-ጉባኤ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ምክትል አፈ-ጉባኤ እንዲሁም ጋዜጠኛ ብሩክ ከበደ የአፈ-ጉባኤ ፀሃፊ ሆነው እንደተመረጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲስ የተመረጡት አመራሮች በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ማህበሩ ሙያተኛውን ብቻ ማዕከል አድርጐ በመንቀሳቀስ የአባላቱን መብት እንደሚያስከብር፣የአባላቱን ሙያዊ ክህሎት በተለያዩ ስልጠናዎች እንደሚያዳብርና ሃሣብን በነጻነት የመግለጽ መብትን በተሟላ መልኩ ለማስከበር በትጋት እንደሚሰራ ጠቁመዋል፡፡ አዲሱን የጋዜጠኞች ማህበር ማቋቋም ያስፈለገው በአገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የጋዜጠኞች ማህበራት የሙያተኛውን መብት በቅጡ ማስከበር ባለመቻላቸው ነው መባሉ ይታወሳል፡፡

አንድ ኪሎ ጤፍ በአውሮፓ ከ200 ብር በላይ ይቸበቸባል
የአሜሪካ አውሮፓና፣ እስራኤል ገበሬዎች ጤፍ እያመረቱ ነው
ከጤፍ ተፈላጊነት የኢትዮጵያ ገበሬዎች መጠቀም አለባቸው ተባለ “ጤፍ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ሱስ ነው” ትላለች - የ”ዘ ጋርዲያን” ዘጋቢዋ ኤሊሳ ጆብሰን፤ ባለፈው ሳምንት ለንባብ ባበቃችው ዘገባ ላይ፡፡ በአገሪቱ ከ6 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች ጤፍ እንደሚያመርቱና ከአገሪቱ የእርሻ መሬት ከ20 በመቶ በላይ የሚሆነውም በጤፍ እንደሚሸፈን ትገልጻለች፡፡ በአገሪቱ ለምግብነት ከሚውሉ የሰብል አይነቶች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዝና እንጀራም ብሄራዊ ምግብ እስከመሆን መድረሱን በዘገባዋ ጠቁማለች፡፡ ጤፍ ለአገር ውስጥ ፍጆታ ከመዋል አልፎ በእንጀራ መልክ ባህር ተሻግሮ በተለይ በምዕራባውያን አገራት በሚገኙ ዲያስፖራዎች መበላት ከጀመረ አስርት አመታት እንዳለፈው የምታስታውሰው ዘጋቢዋ፤ አሁን አሁን ደግሞ የጤፍ ተፈላጊነት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ትናገራለች፡፡

የኢትዮጵያ ጤፍ በአለም ገበያ ቀጣዩ ተፈላጊ ሰብል ለመሆን እንደሚችል በመግለጽ፣ ነገ ከነገ ወዲያ ኢትዮጵያ ከቡና ቀጥሎ ለአለም የምታበረክተው ሁለተኛው ስጦታ ጤፍ መሆኑ እንደማይቀር ትናገራለች፡፡ በውስጡ ካልሺየም፣ አይረን፣ ፕሮቲንና ሌሎች ንጥረነገሮችን የያዘውና ለጤና ተስማሚ የሆነው ጤፍ፤ በአለማቀፍ ደረጃ ተፈላጊነቱ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መምጣቱን ነው ዘ ጋርዲያን ከሰሞኑ ያስነበበው ዘገባ የሚያስረዳው፡፡ “ጤፍ በውስጡ የያዘውን ንጥረ ነገር ባወቅሁ ጊዜ እጅግ ነበር የተገረምኩት፡፡ በህይወት ዘመኔ ሁሉ ስመገበው የኖርኩት ጤፍ፤ እንዲህ ያለ ጠቃሚ ነገር መሆኑን አላውቅም ነበር፤ የሚገርም ነገር ነው!” ያለችው ነዋሪነቷ በለንደን የሆነው ኢትዮጵዊቷ ሶፊ ከበደ ናት፡፡ ሶፊ በጤፍ ተገርማ አላበቃችም፡፡

የግርምት ብቻ ሳይሆን የገቢ ምንጭም መሆን እንደሚችል ገብቷታል፡፡ ለዚህ ነው ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ ለንደን የሆነ ‘ጦቢያ ጤፍ’ የተሰኘ የንግድ ኩባንያ ከባለቤቷ ጋር በማቋቋም፣ ጤፍን ከአምራች አገሮች እየገዛች ወደእንግሊዝ በማስመጣት መሸጥ የጀመረችው፡፡ የዘጋርዲያን ዘገባው እንደሚለው፣ ዛሬ “ፕላኔት ኦርጋኒክን” የመሳሰሉ የለንደን ታላላቅ መደብሮች ጤፍ አሽገው በመቸብቸብ ላይ ናቸው፡፡ በእነዚህ መደብሮች አንድ ኪሎ የጦቢያ ጤፍ ዱቄት 7 ፓውንድ (ከ200 ብር በላይ) ይሸጣል፡፡ በመደብሮቹ በጤፍ ዱቄት የተሰራና የተለያዩ ማጣፈጫዎች የታከሉበት ዳቦም ለገበያ ይቀርባል፡፡ ጤፍ አሁን የአገር ቤትና የአገር ልጅ ምግብ ብቻ አይደለም፡፡ የተለያዩ ምዕራባውያን አገራት ዜጎችም በጤፍ አምሮት መለከፍ ይዘዋል፡፡ ፍላጎቱም ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መጥቷል፡፡ “ማማ ፍሬሽ” የተባለው የንግድ ኩባንያ በአዲስ አበባ ለሚገኙ ሆቴሎችና ሬስቶራንቶች ለአመታት እንጀራ ሲያቀርብ መቆየቱንና በአሁኑ ወቅትም ወደ ፊLላንድ፣ ጀርመን፣ ስዊድንና አሜሪካ እየላከ እንደሚገኝ ዘገባው ያሳያል፡፡ ወደ አሜሪካ የሚልከውን ምርት በ2014 በእጥፍ የማሳደግ እቅድ ይዞ እየሰራ ያለው ኩባንያው፤ በቅርቡም የጤፍ ፒዛ፣ ዳቦና ብስኩት እያመረተ ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንደሚጀምር ዘገባው ያስረዳል፡፡

ዘጋቢዋ እንደምትለው፤ “ጥያቄው ኢትዮጵያ እና አርሶ አደሮቿ ከዚህ አለማቀፍ ገበያ ተጠቃሚ መሆን የሚችሉበትን ሁኔታ ማረጋገጥ የሚቻለው እንዴት ነው?” የሚለው ነው፡፡ ለመሰል የተወሰኑ አገራት ምርት ብቻ የሆኑ በንጥረነገር ለበለጸጉ የምግብ እህል ሰብሎች እያደገ የመጣው አለማቀፍ ፍላጎት፣ በድህነት የሚማቅቁ የአምራች አገራትን ማህበረሰቦች ጎጂ ሲሆኑ ይታያሉ ትላለች ዘጋቢዋ፡፡ ይህን እውነታ ለማስረዳት የቦሊቪያና የፔሩን ተሞክሮ በአብነት የምትጠቅሰው ዘጋቢዋ፣ በእነዚህ አገራት የሚመረተው “ኪየኑአ” የተሰኘ የሰብል አይነት በብዛት ወደ ውጭ አገራት መላኩ፣ በአገሪቱ የምግብ እጥረት ማስከተሉን እንዲሁም ሰብሉን አምርቶ በብዛት በመሸጥ የምዕራባውያኑን ፍላጎት ለማሟላት በሚል በአርሶአደሮች ዘንድ የመሬት ሽሚያና ግጭት መፈጠሩን ትገልጻለች፡፡ “በኢትዮጵያ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ለጤፍ ያላቸው ፍላጎት እያደገ ነው፡፡ በአገሪቱ የጤፍ ዋጋ ባለፉት አስርት አመታት እየጨመረ መምጣቱን ተከትሎም ድሃ ዜጎች ጤፍ መግዛት የማይችሉበት ደረጃ ላይ እየደረሱ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ አምራቾችም ምርታቸውን ወደ ከተማ እያወጡ በመሸጥ ላይ ናቸው፡፡” ያለችው ዘጋቢዋ፤ የመንግስትን መረጃ ጠቅሳ እንደጻፈችው፣ በከተማ የሚኖሩ ዜጎች በአመት በአማካይ 61 ኪሎግራም ጤፍ እንደሚመገቡ ይገመታል፡፡

በገጠር የሚኖሩት ደግሞ 20 ኪሎግራም፡፡ የአገሪቱ መንግስት አመታዊ የጤፍ ምርቱን በ2015 በእጥፍ የማሳደግ እቅድ አለው፡፡ ይህም የአገር ውስጥና የውጭ ገበያ አቅርቦቱን ለማሳደግ ያስችላል ተብሎ ይገመታል፡፡ የተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት፣ የንግድና ገበያ ዳይሬክተር ዴቪድ ሃላም እንደሚሉት፣ አገር በቀል የሰብል ምርቶችን ለአዳዲስ አለማቀፍ ገበያዎች በማቅረብ ጥሩ ገቢ ማግኘት መቻሉ እንዳለ ሆኖ፣ መንግስታት አነስተኛ ሰብል አምራቾች ከእነዚህ ገበያዎች የሚገባቸውን ጥቅም ማግኘት እንዲችሉ ድጋፍ ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባዮ ዳይቨርሲቲ ተቋም የቀድሞ ሃላፊ የነበሩት የግብርና ተመራማሪው አቶ ረጋሳ ፈይሳ በበኩላቸው፣ ጤፍን በከፍተኛ መጠን እያመረቱ ለውጭ ገበያ የማቅረቡ አካሄድ በአግባቡ ካልታቀደና ጥንቃቄ ካልተደረገበት አደጋ አለው ማለታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡ እሳቸው እንደሚሉት፤ ይህ አካሄድ፣ አርሶ አደሮች ለሌሎች ምርቶች ትኩረት እንዳይሰጡ ሊያደርግ ይችላል፡፡ በብዛት አምርቶ ለገበያ የማቅረቡ አካሄድ አነስተኛ ገበሬዎችን ተጠቃሚ በማያደርግ መልኩ ለጥቂት አትራፊዎች ሲሳይ ሊሆን ይችላል፡፡ በአለማቀፍ ገበያ ላይ የሚቀርበው የኢትዮጵያ ጤፍ አነስተኛ መሆኑን ተከትሎ የአሜሪካ ገበሬዎች ጤፍ ማምረት መጀመራቸውን የገለጸው ዘገባው፤ የአውሮፓ፣ የእስራኤልና የአውስትራሊያ ገበሬዎችም በሙከራ ደረጃ ጤፍ ወደማምረት መግባታቸውን ጠቁሟል፡፡

የ “ጦቢያ ጤፍ” ኩባንያ ባለቤት የሆነችው ሶፊ ከበደ፤ በለንደን ለገበያ የምታቀርበውን ጤፍ፣ ከአገር ቤት ሳይሆን ከደቡባዊ አውሮፓ አገራት ገበሬዎች እንደምትገዛ ገልጻለች፡፡ ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች የሚያመርቱትን ማኛ ጤፍ ለእንግሊዝ ገበያ የማቅረብ ፍላጎት እንዳላትና የአገሯ ገበሬዎች ምርታቸውን ለአለማቀፍ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን የማይችሉበት መንገድ እንደሌለም ለ “ዘጋርዲያን” ተናግራለች፡፡ እ.ኤ.አ በ2006 የኢትዮጵያ መንግስት ጤፍን በእንጀራ መልኩ ካልሆነ በቀር በቀጥታ ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚከለክል ህግ ማውጣቱን የወሳው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን እገዳው ዘላቂ እንደማይሆን ገልጿል፡፡ ምክንያቱም የመንግስት ስትራቴጂ ያስቀመጠው ግብ ለአገር ውስጥ ፍጆታና ለውጭ ገበያ የሚውል በቂ የጤፍ ምርት ማምረት ነውና፡፡

ከአስራ አራት ቀን በፊት “አድዋ ይከበር ይዘከር ለዘላለም” በሚል መሪ ቃል ከአዲስ አበባ ጣይቱ ሆቴል የእግር ጉዞ የጀመሩት የጉዞ አድዋ አባላት፤ የካቲት 23 ታሪካዊቷ አድዋ አምባ እንደሚደርሱ ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ ወደ አድዋ የሚያደርጉትን ታሪካዊ ጉዞ ከመጀመራቸው በፊት በዶ/ር አኧዘ ጣዕመ፣ ሙሉ የጤንነት ምርመራ የተደረገላቸው ሲሆን “ዘ አዘር ፌስ ኦፍ ኢትዮጵያ” ሙሉ ወጪያቸውን እንዲሁም አዲካ ለቀረጻ የሚያገለግላቸውን መኪና እንዳበረከተላቸው ከተጓዦቹ አንዱ የሆነው አርቲስት መሃመድ ካሣ ገልጿል፡፡

የጉዞው ዓላማ የአድዋ ጀግኖችን መዘከርና እነሱ የተጓዙበትን አስቸጋሪ መንገድ ማስታወስ ሲሆን አባላቱ የጉዞ መስመራቸውን ያደረጉትም አጼ ሚኒልክ ጦራቸውን ከአዲስ አበባ ይዘው በወጡበት መንገድ ነው ብሏል - አርቲስት መሃመድ፡፡ በዛሬው እለት ከአዲስ አበባ ከ400 ኪሎ ሜትር በላይ በምትርቀው ሀይቅ ከተማ የሚደርሱ ሲሆን የጉዞው ፍጻሜ የአድዋ በዓል ዕለት የካቲት 23 ቀን 2006 ዓ.ም ይሆናል፡፡ የጉዞው አባላት መሃመድ ካሳን ጨምሮ 5 ሲሆኑ የኢትዮፒካ ሊንክ ሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅ ብርሃኔ ንጉሴ እንዲሁም ኤርሚያስ አለሙ፣ ሙሉጌታ መገርሣ (አማሩ) እና አለም ዘውዱ ካሣሁን ይገኙበታል፡፡በጉዟቸው የጤና እክል እንዳላጋጠማቸው የገለጹት የጉዞው አባላት፤ በዶ/ር አኧዞ የቅርብ ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

በቶም ፊልም ኘሮዳክሽን የቀረበው “ፅኑ ቃል” ፊልም የካቲት 2 ቀን 2006 ዓ.ም በሁሉም የግል ሲኒማ ቤቶች እንዲሁም

የካቲት 3 በሸራተን አዲስ እና በመንግስት ሲኒማ ቤቶች ለእይታ ይቀርባል፡፡
የ1 ሰዓት ከ50 ደቂቃ ርዝማኔ ያለውን ይህን ፊልም ሠርቶ ለማጠናቀቅ ከአንድ ሚሊዮን ሶስት መቶ ሺህ ብር በላይ ወጪ

የፈጀ ሲሆን ዳንኤል በየነ ዳይሬክት አድርጐት፣ ቶማስ ጌታቸው በደራሲነትና ኘሮዱዩሰርነት ተሣትፎበታል፡፡
የሮማንስ ሰስፔንስ ዘውግ ባለው በዚህ ፊልም ላይ መሪ ተዋናዮቹን እነ ግሩም ኤርሚያስ፣ ማህደር አሰፋና ኤልያስ

ወሰንየለህን ጨምሮ ከ450 በላይ ባለሙያዎች ተሣትፈውበታል፡፡
ቶም ፊልም ኘሮዳክሽን ከአሁን ቀደም “ስርየት” እና “ፔንዱለም” የተባሉ ፊልሞችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡

የግጥም፣ የወግና የአጭር ልቦለድ ስብስቦች የተካተቱበት  ‹‹ታሽጓል››  መጽሐፍ፣ ባለፈው ሳምንት አርብ በጎንደር ከተማ ‹‹ሲኒማ አዳራሽ›› የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ ገዛኸኝ ፀጋው፣ በክብር እንግድነት በተገኙበት በይፋ መመረቁን በስፍራው የነበረው ሪፖርተራችን ዘግቧል፡፡  
 የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር የጎንደር ቅርንጫፍ ሰብሳቢ በሆኑት በአቶ ግርማይ ከበደ የተደረሰው ‹‹ታሽጓል›› መጽሐፍ፣ 123 ገጾች ሲኖሩት፣ በ30 ብር ለገበያ መቅረቡ ታውቋል፡፡