
Administrator
ደቀ መዛሙርቱ ኮሌጁ ‹‹የትምህርት ሳይሆን የንግድ ማእከል ኾኗል›› አሉ
በመንፈሳዊ ኮሌጁ ትምህርት ተቋርጧል፤ ተማሪዎቹም ምግብ መመገብ አቁመዋል
የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርት÷ ለትምህርት ጥራት መሻሻልና ለደቀ መዛሙርቱ መብት መከበር ከመቆም ይልቅ ገንዘብ ለመሰብሰብና የግል ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ቅድሚያ ይሰጣሉ ያሏቸው ሁለት የአስተዳደር ሓላፊዎች ከሥልጣን እንዲወገዱ ያቀረቡት ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ባለማግኘቱ ትምህርት ማቆማቸውንና ምግብ ከመብላት መከልከላቸውን አስታወቁ፡፡ በጥያቄያቸው ያመለከቷቸው በርካታ የኮሌጁ ችግሮች ላለፉት ዐሥራ አራት ዓመታት ሲንከባለሉ የቆዩ መኾናቸውን የገለጹት ደቀ መዛሙርቱ÷ የመምህራኑ አቅም ማነስና የትምህርት ጥራት መውደቅ፣ የምግብ መበከልና የአስተዳደሩ በጥቅም ትስስርና በሙስና መዘፈቅ ሊታገሡት ከሚችሉት በላይ በመኾኑ ፓትርያሪኩና የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤቱ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጧቸው መጠየቃቸውን ገልጸዋል፡፡
ይኹንና ፓትርያሪኩን በአካል አግኝቶ ለማነጋገር አልያም የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ሓላፊዎችን ለማግኘት በተደጋጋሚ ያደረጉት ጥረት ከኮሌጁ ሓላፊዎች ጋራ በጥቅም ተሳስረዋል ያሏቸው አካላት እንደፈጠሩት በሚያምኑት መሰናክል አለመሳካቱን አስታውቀዋል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ከኮሌጁ አስተዳደር ጋራ የገቡበት ውዝግብ ከተቀሰቀሰ ሁለተኛ ሳምንቱን የያዘ ሲኾን ትምህርት መቋረጡም ተዘግቧል፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ እንደሚሰጥ የገለጸው አስተዳደሩ÷ ደቀ መዛሙርቱ ካለፈው ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ ያቋረጡትን ትምህርት እስከ ረቡዕ ቀትር ድረስ በአስቸኳይ እንዲቀጥሉ አሳስቧል፡፡ ደቀ መዛሙርት ወደ ትምህርታቸው የማይመለሱ ከኾነ ደግሞ በዚያው ዕለት ንብረትና መታወቂያ እያስረከቡ ኮሌጁን ለቀው እንዲወጡ አስተዳደሩ አስጠንቅቋል፡፡
‹‹ለሁለት ሰዎች ሲባል ሁለት መቶ ተማሪ አይባረርም፤ ብቃት የሌላቸውና ኮሌጁን እንደ ርስት በዘመድ ይዘው የጥቅም ማግበስበሻ ያደረጉት አካዳሚክ ዲኑና የቀን መርሐ ግብር አስተባባሪው ከሓላፊነታቸው ይነሡልን፤›› የሚሉት ደቀ መዛሙርቱ በበኩላቸው÷ ችግሮቻቸው በመሠረቱ ደረጃ በደረጃ መፈታት እንደሚገባቸው ቢቀበሉም ወደ ትምህርት ገበታቸው የሚመለሱት ግን የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲንና የቀን መርሐ ግብር አስተባባሪው ከሓላፊነታቸው ሲነሡ ብቻ ነው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ እንደሚያስረዱት÷ በተጠቀሱት የኮሌጁ አስተዳደር ሓላፊዎች ደረጃ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ ምእመኑ ‹‹የገንዘብ ምንጭ ብቻ ኾኗል፤ አገልጋይ ጠፍቷል፡፡›› ደቀ መዛሙርቱ÷ ኮሌጁን እንደ ግለሰብ ቤትና እንደ ዘመድ ርስት ይቆጥራሉ በሚሏቸው ጥቂት ሓላፊዎች መካከል አለ የሚሉት የጥቅም ትስስር በትምህርት ጥራትና በመብታቸው ላይ የፈጠረውን ተጽዕኖ የሚገልጹት ‹‹ኮሌጁ የትምህርት ሳይሆን የንግድ ማእከል ኾኗል፤›› በሚል ነው፡፡
ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የደቀ መዛሙርቱ መማክርት አባላት እንዳስረዱት÷ የተለያዩ ገባሬ ሠናይ ድርጅቶች ለኮሌጁ የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋሉ፤ ከእነርሱም በላይ በዋናነት ሁሉም አህጉረ ስብከት ከጠቅላላ ገቢያቸው አምስት ከመቶ ፈሰስ ያደርጋሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኮሌጁ ሕንጻውን በማከራየትና የመማሪያ ክፍሎቹን ለተለያዩ ኮሌጆች በመፍቀድ ከፍተኛ ገቢ ይሰበስባል፡፡ ይኹንና ደቀ መዛሙርቱ በሜዳ ላይ የሚማሩበት አጋጣሚ አለ፡፡ በየመርሐ ግብሩ ከተዘረጉት ኮርሶች ብዛት ጋራ የሚመጣጠኑ መምህራንን መቅጠር እየተቻለ የመምህራን ምደባው አራትና አምስት ኮርሶችን በሚይዙ ጥቂት መምህራን መካከል የተወሰነ ነው፡፡ የመምህራኑ ዕውቀት ‹‹ሙሉዕ በኩለሄ›› እስካልኾነና መምህራኑ ከተጨማሪ ሓላፊነቶች ጋራ ከሚያጋጥማቸው የዝግጅት ማነስ የተነሣ ምደባው የትምህርት ጥራቱን የሚጎዳው ይኾናል፡፡ ይህም በትምህርት አሰጣጡና በምዘናው ላይ በሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ የተነሣ አቤቱታ የሚያቀርቡ ደቀ መዛሙርትን የሚያሸማቅቁ፣ ከዚህም አልፎ በመማሪያ ክፍሎችና በቤተ መጻሕፍት ውስጥ ሳይቀር የሚደበድቡ መምህራን መኖራቸውን ነው ደቀ መዛሙርቱ ለአዲስ አድማስ የተናገሩት፡፡
በተማሪዎች አቀባበል ወቅት ኮሌጁ የሙሉ ጤንነት ምርመራ እንደሚያደርግላቸው የገለጹት ደቀ መዛሙርቱ በሂደት ግን በካፊቴሪያው ጥንቃቄ የጎደለው የምግብ ዝግጅት የተነሣ ጤንነታቸው የተጎዳና በቂ ሕክምና የማያገኙ ደቀ መዛሙርት ቁጥር ጥቂት እንዳልኾነ ደቀ መዛሙርቱ ለዝግጅት ክፍሉ ገልጸዋል፡፡ በቤተ መጻሕፍት አገልግሎትና በመረጃ ቴክኖሎጂ ረገድ የሚሰጠው አገልግሎትም አንፋውን ኮሌጅ የሚመጠን እንዳልኾነ ነው ደቀ መዛሙርቱ የሚናገሩት፡፡ ‹‹የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከተቀሩት ሁለት የቤተ ክርስቲያኒቱ ኮሌጆች ጋራ ሲነጻጸር አንጋፋ ቢኾንም ዛሬ ከአስተዳደሩ ድክመት የተነሣ የሚገኝበት ደረጃ ከዘመናዊነት የራቀ ነው፤›› ይላሉ ደቀ መዛሙርቱ፡፡ ይህ የኮሌጁ ኹኔታ የሚያሳስባቸውና በጉዳዩ ላይ ከደቀ መዛሙርቱ ጋራ የሚመክሩ መምህራን ማስጠንቀቂያ እንደሚሰጣቸውና ስለላ እንደሚካሄድባው ተመልክቷል፡፡
በኮሌጁ ሰፍኗል የሚሉትን ሙስናና የአሠራር ብልሽት የሚቃወሙት የአገርንና የሕዝብን ሀብት ከማዳን አንጻርም በመኾኑ መንግሥትም ሊያግዘን ይገባል፤ ‹‹ችግራችንን የማይፈቱልን ከኾነ ችግር ባይፈጥሩብን›› በማለትም በግል እየጠሩ ያስፈራሩናል፤ ይዝቱብናል ያሏቸውን የፖሊስ አባላት ይጠይቃሉ ደቀ መዛሙርቱ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ በአድራሻ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የጻፉትን ጥያቄዎቻቸውን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ለሰብአዊ መብት ኮሚሽንና ለፌዴራል ፖሊስ በግልባጭ ማሳወቃቸውን የገለጹ ሲኾን ለጥያቄዎቻቸው በቂ ምላሽ እስኪያስገኙ ድረስ ውርጩን፣ ረኀቡንና እንግልቱን ተቋቁመው ለመቆየት መወሰናቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡ በደቀ መዛሙርቱ ጥያቄዎችና ተቃውሞዎች ላይ የኮሌጁን ሓላፊዎች አስተያየትና ምላሽ ለማግኘት የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲንን በስልክ ለማነጋገር የሞከረን ቢኾንም ዲኑ በአካል ካልቀረባችኹ በስልክ ምላሽ አልሰጥም ብለውናል፡፡ የዝግጅት ክፍሉ በነበረበት የጊዜ እጥረት ዲኑን በአካል አግኝቶ ሊያነጋግራቸው አልቻለም፡፡
በኤርትራ የሰለጠኑ ታጣቂዎች በሱዳኖች ትብብር ተያዙ
ኤርትራ ውስጥ ሰልጥነው በጋምቤላ ክልል ድንበር አቋርጠው ጥቃት ሊፈፅሙ የነበሩ ታጣቂዎች በሰሜንና ደቡብ ሱዳን መንግስታት ትብብር ለኢትዮጵያ መንግስት ተላልፈው መሠጠታቸውን ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ ስልጠና ካገኙበት ከኤርትራ ተነስተው ሰሜን ሱዳንና ደቡብ ሱዳንን አልፈው ወደ ኢትዮጵያ ድንበር ሊያቋርጡ ሲሉ በሶስቱ አገሮች መሀል ባለው የፀጥታ የትብብር ስምምነት መሠረት ለክልሉና ለፌዴራል መንግስት የፀጥታ ሀይሎች ተላልፈው ተሠጥዋል፡፡
ታጣቂዎቹ በሰላም እጃቸውን እንዲሠጡ የቀረበላቸውን ጥያቄ ባለመቀበላቸው በተከፈተ የተኩስ ልውውጥ ህይወታቸውን ያጡ እንዳሉም የጠቆሙት ምንጮቹ በክልሉ በተፈፀሙ የተለያዩ የሽብር ተግባሮች እጁ እንዳለበት የሚጠረጠረውና በአስመራ ለረጅም ጊዜ የኖረው ኦማን ካውንዳን ጨምሮ አስራ አንድ ታጣቂዎች በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ባለፈው አመት በጋምቤላ ክልል የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ ላይ ይጓዙ የነበሩ ተማሪዎች ላይ እና በክልሉ በኢንቨስትመንት በተሰማሩ ፓኪስታንያውያን እንዲሁም በክልሉ ፖሊሶች ላይ ጉዳት አድርሷል በሚል በመንግስት ይፈለግ የነበረው አሜሪካዊ ዜግነት ያለው ኡሞድ ኡዶል ወደ ደቡብ ሱዳን ሄዶ እንደነበር ይታወቃል፡፡
አብረውት ከነበሩ ታጣቂዎች የተወሰኑት ተገድለው አብዛኛዎቹ ተይዘው ጉዳያቸው በፍርድ ሲታይ እሱ ተሠውሮ ሲፈለግ ከቆየ በኋላ በቅርቡ በፌደራል መንግስት ፀረ ሽብር ግብረ ሀይልና የፀጥታ አካላት ጋር በተደረገ የተኩስ ልውውጥ መገደሉንና የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ማረጋገጡ ይታወቃል፡፡
አርቲስቶችን እናክብራቸው፤ ቤተሰብ አላቸው
ባለፈው ሳምንት የአዲስ አድማስ ጋዜጣ እትም ላይ በአርቲስት ሠራዊት ፍቅሬ ዙሪያ የቀረበውን አጭር ዜና ስመለከት ብዙ ሃሳቦች መጡብኝ፡፡ በእርግጥ ሠራዊት ፍቅሬ የተወራበት ነገር አሉባልታ እንደሆነ መግለፁ በዜናው ተዘግቧል፡፡ ነገር ግን ሁለት ቅሬታዎች አሉኝ፡፡ አንደኛው ቅሬታዬ በዜና አዘጋገቡ ላይ ነው፡፡ ሁለተኛው ቅሬታዬ ግን በዜና ዘገባው ላይ ሳይሆን፣ በጊዜው በአርቲስቶች ላይ በሚናፈሱ ወሬዎች ላይ ነው፡፡ የመጀመሪያ ቅሬታዬን ላስቀድም፡፡ በአዲስ አድማስ የቀረበውን አጭር ዜና፣ በሙያ መመዘኛ እንየው ከተባለ ተቃራኒ ገፅታዎች ይስተዋሉበታል፡፡ ብልሃትና ጥንቃቄ የተሞላበት ዘገባ ነው፡፡
“ብልጠትም ያለበት ይመስላል” ብዬ ስሜታዊ ድምዳሜ ላይ መድረስ አልፈልግም፡፡ ጠንቃቃ ዜና መሆኑን ግን ያለ ጥርጥር መናገር ይቻላል፡፡ በተቃራኒው ደግሞ በዜናው አንዳንድ ገፅታዎች ላይ ግልፅ ጉድለቶች አሉበት፡፡ ለምሳሌ ዜናው ብዙ መረጃዎችን የሚሰጥ ይመስላል፡፡ ይህም የጥንቃቄ ውጤት ሳይሆን አይቀርም፡፡ ነገር ግን ዜናው ከሚሰጠን መረጃ ይልቅ በርካታ መልስ የሌላቸው ጥያቄዎችን የሚፈጥርብን መሆኑ ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ ሌላኛው ጉድለት፣ በዜናው ርእስ ላይ ጭምር የሚታይ ነው፡፡
ለዜናው መነሻ የሆነው ወሬ በዜናው ውስጥ ተጠቅሷል፡፡ አንዲት ሴት፣ አርቲስቱ ሊስመኝና ሊደባብሰኝ ሞክሯል ብላለች የሚል ወሬ ነው መነሻው፡፡ እንግዲህ ከዚህ ልንገነዘብ የምንችለው ወሬው ስለ ወሲብ ትንኮሳ እንጂ ስለ መድፈር ሙከራ አለመሆኑን ነው፡፡ ደግሞም ወሬው አሉባልታ መሆኑንም አርቲስቱ ገልጿል፡፡ በሌላ አነጋገር፤ ወሲባዊ ትንኮሳ እንደፈፀመ ተደርጐ ሲናፈስ የቆው ወሬ አሉባልታ እንደሆነ አርቲስቱ ተናግሯል፡፡ የዜናው ርእስ ግን “የወሲብ ትንኮሳ” የሚል አገላለፅን ሳይሆን፣ “የመድፈር ሙከራ” የሚል ሀረግ ተጠቅሟል፡፡ ይሄ ጉድለት ነው፡፡
ቺንዋ አቼቤ አረፈ
ከአፍሪካ ታላቅ ደራሲዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው ናይጄርያዊው ቺንዋ አቼቤ በ82 ዓመቱ ትናንት በአሜሪካዋ ማሳቹሴትስ ከተማ በድንገተኛ ህመም ከዚህ አለም በሞት ተለየ፡፡ አልበርት ቺኒዋ ሉሞጉ አቼቤ ከልቦለድ ስራዎቹ ባሻገር በገጣሚነትና በሃያሲነቱ የሚታወቅ ፕሮፌሰር ነበር፡፡
በ1960ዎቹ ስላለፈበት የቢያፍራ ጦርነት ትውስታዎችና የህይወት መታሰቢያ ታሪኩን “There Was a Country: A Personal History of Biafra” በሚል ርእስ ለመጨረሻ ጊዜ አምና ለንባብ አብቅቷል፡፡ ታዋቂው የእንግሊዝ አሳታሚ ኩባንያ ፔንጊውንስ ሞቱን ተከትሎ ባወጣው መግለጫ፣ ደራሲውን “እጅግ ምርጥ ችሎታ ያለው ፀሃፊ እና የአፍሪካ ታላቅ የስነፅሁፍ ሰብእና” ሲል አሞካሽቶታል፡፡ በአገሩ በናይጄርያና በአለማቀፍ ደረጃ በርካታ ሽልማቶችን ያገኘው አቼቤ በልቦለድ ስራዎቹ በአፍሪካዊነት፤ በብሄርተኝነት፤ በፀረ ቅኝ ግዛት ጭብጦች ዙሪያ በመፃፍ ይታወቅ በነበር፡፡
ቺንዋ አቼቤ ስነፅሁፍ በመላው አህጉሪቱ እንዲስፋፋ፣ በተማሪዎች ዘንድ የልቦለድ ባህል እንዲፈጠርና ከፍተኛ የስነፅሁፍ እድገት እንዲቀጣጠል በተጫወተው ፈርቀዳጅ ሚና ጎልቶ ይጠቀሳል፡፡ በአሜሪካ ኮሌጆች ሲያስተምር ቆይቶ እኤአ በ1958 በፃፈው ‹ቲንግስ ፎል አፓርት› በተባለ የልቦለድ መፅሃፉ ከፍተኛ ዓለማቀፍ ዝና አትርፍዋል፡፡ መጽሐፉ በመላው ዓለም በ50 የተለያዩ ቋንቋዎች ተተርጉሞ 12 ሚሊዮን ቅጂዎች ተሽጥዋል፡፡
የልቦለድ መፅሃፉ በበርካታ የአፍሪካ ከፍተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፤ ኮሌጆች እና ዩኒቨርስቲዎች እንደ መማርያ መፅሃፍ ሊያገለግልም በቅቷል፡፡ አቼቤ የናይጄርያ የመንግስታትንና የባለስልጣናትን ድክመት በመተቸት እንዲሁም ሙስናን በይፋ በማጋለጥ፤ እንዲሁም በተለያዩ የህትመት ውጤቶች መጣጥፎችን በማቅረብ ይታወቅ ነበር፡፡ አቼቤ ከ20 በላይ መፅሃፍትን ለንባብ ያበቃ ሲሆን ከፃፋቸው ልቦለዶች መካከል ‹ኖ ሎንገር አት ኢዝ›፤ ‹አሮው ኦፍ ጎድ›፤ ‹ኤማን ኦፍ ዘ ፒፕል›፤ እና ‹አንትሂልስ ኦፍ ሳቫና› የተባሉት ይጠቀሳሉ፡፡
‹‹አርሾ›› የሕክምና ላብራቶሪ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ተሰጠው
‹‹አርሾ›› የተሰኘው የግል የሕክምና ላቦራቶሪ አገልግሎት ሰጪ ድርጅት በዓለም አቀፍ ደረጃ የተለያዩ ድርጅቶችንና አገልግሎቶችን ጥራትን ማዕከል በማድረግ እያወዳደረ ዕውቅና በመስጠት ከሚታወቀው “Business Initiative Directives” ከሚባለው ዓለም አቀፍ ድርጅት “Century International Quality ERA Award in Gold Category” በሚለው የሽልማት ዘርፍ እ.ኤ.አ. በመጋቢት 10 ቀን 2013 ዓ.ም በአዉሮፓ የተባበሩት መንግስታት ጉባኤ ማዕከል በኾነው በስዊዘርላንድ ጄኔቫ ኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በተካሄደው ሥነ-ሥርዓት የወርቅ ዋንጫና የዕውቅና ሰርቲፍኬት ተሰጠው፡፡
የላብራቶሪው ዳይሬክተር አቶ ግዛቸው ቀዲዳ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፤ከ173 አገራት በተለያየ የግል የሥራ ዘርፍ ጥራትና ብቃት ያለው አገልግሎት በመስጠት በአየር መንገድ፣ በኢንጂነሪንግ፣ በሕትመት ሥራ፣ በፖሊስ አገልግሎት፣ በሕክምና እና በተለያዩ ሥራዎች ዘርፍ ተሰማርተው ሲሠሩ የነበሩ የተመረጡ ድርጅቶች በፕላቲኒየም፣ በወቅርና በብር ምድብ የተለያየ ሽልማት በተቀበሉበት መድረክ ላይ ‹‹አርሾ›› ተካፋይ ሆኖ በመሸለሙ እጅግ መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡
አክለውም “ሽልማቱ አሁን ከምንሰጠው ብቃት ያለው ሥራ የበለጠ እንድንተጋ ያደርገናል” ብለዋል፡፡ ኤርቫቢር ቲርዚያ በተባሉ አርመናዊ ፋርማሲስት በአነስተኛ ደረጃ ተመስርቶ ሥራ ከጀመረበት ከ1963 ዓ.ም. ጀምሮ በተለይ ቀደም ሲል ምንም የግል የሕክምና አገልግሎት ባልተስፋፋበትና አንድም የግል ላቦራቶሪ አገልግሎት ባልነበረበት ጊዜያት ከኢትዮጵያ ጤናና ስነምግብ ኢንስቲትዩት ቀጥሎ ለሁሉም የመንግሥት፤ የድርጅቶችና የግል የጤና ተቋሞች አስተማማኝ የላቦራቶሪ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቶአል፡፡ራሱን በማሳደርግም የዘመኑን ቴክኖሎጂ በመከተል እየሰጠ ባለው አገልግሎት ለዚህ ሽልማት የበቃው ‹‹አርሾ የሕክምና ላቦራቶሪ በአሁኑ ሰአት በአዲስ አበባ ስድስት ቅርንጫፎችን በመክፈት አየሠራ ይገኛል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም አዲስ የ3ጂ ፈጣን ኢንተርኔት አገልግሎት መስጠት ጀመረ
ኢትዮ ቴሌኮም ከሲ.ዲኤም.ኤ እና ከኢ.ቪ.ዲኦ ቀጣይ የሆነውን ሦስተኛ ትውልድ ፈጣን የ3ጂ ኢንተርኔት ጥቅል አገልግሎት መስጠት መጀመሩን አስታወቀ፡፡የ3ጂ ፈጣን ኢንተርኔት ጥቅል አገልግሎት የቀረበው ለሦስት የአገልግሎት ዐይነት ተጠቃሚዎች ሲሆን ለ1GB ከተጨማሪ 150 ሜጋ ቢት ልዩ ጥቅም ጋር በ400 ብር፣ ለ2GB ከተጨማሪ 200 ሜጋ ቢት ልዩ ጥቅም ጋር በ600 ብር እንዲሁም 4GB ከተጨማሪ 350 ሜጋ ቢት ልዩ ጥቅም ጋር በ800 ብር ወርሃዊ ክፍያ ጥቅም ላይ እንደሚውል ኢትዮ ቴሌኮም በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
አገልግሎቱ ከመጋቢት 12 ቀን 2005 ጀምሮ መሰጠት መጀመሩን የገለፀው ድርጅቱ በቅድመና በድህረ ክፍያ መጠቀም ለሚፈልጉም አገልግሎቱ በምርጫ ቀርቧል፡፡ደንበኞች ከመጋቢት 12 እስከ ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ባለው የአንድ ወር የማስተዋወቂያ ጊዜ አገልግሎቱን መጠቀም ከጀመሩ ለማስጀመሪያ ከተቀመጠው የመቶ ብር ክፍያ ነፃ ሆነው መጠቀም እንደሚችሉም አስታውቋል፡፡ ባለ ከፍተኛ ፍጥነት እንደሆነ የተነገረለት አዲስ የ3ጂ ኢንተርኔት ጥቅል አገልግሎቱን በድህረ ክፍያ ለማግኘት ለሚፈልጉ ደንበኞች የአገልግሎቱ ክፍያ የሚፈፀመው በወር መጨረሻ ላይ ሲሆን ከተመደበው የጥቅል አገልግሎት በተጨማሪ አገልግሎቱን የሚጠቀሙ ደንበኞች በተጠቀሙት የፍጆታ መጠን በመደበኛው የአገልግሎት ክፍያ መሰረት በሜጋ ቢት 46 ሳንቲም የሚከፍሉ መሆኑን መግለጫው አብራርቷል፡፡
የ3ጂ ዳታ ወይም ኢንተርኔት አገልግሎት ክፍያ በ3ጂ ዶንግል ከሆነ 799 ብር እንዲሁም በዋይፋይ ራውተር ከሆነ 1529 ብር የሚጠይቅ መሆኑም ተገልጿል፡፡ በቅድመ ክፍያ ጥቅል አገልግሎቱን መጠቀም ለሚፈልጉ ደንበኞች የማስደወያ ካርድን በመጠቀም ሂሳቡን መሙላት የሚኖርባቸው ሲሆን በጥቅም ላይ ያልዋለ የቅድመ ክፍያም ሆነ የድህረ ክፍያ የጥቅል ኢንተርኔት ወይም ዳታ አገልግሎት ወደሚቀጥለው ወር የማይተላለፍ መሆኑን ኢትዮ ቴሌኮም በመግለጫው አስገንዝቧል፡፡ በኢትዮ ቴሌኮም የኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን ኦፊሰር አቶ አብዱራሂም፤ አዲሱ 3ጂ አገልግሎት ከነባሩ የሚለየው ቀድሞ ሥራ ላይ የነበረው 3ጂ ሲም ካርድ የዳታና የድምፅ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን አዲሱ 3ጂ ግን የሚሰጠው የዳታ አገልግሎት ብቻ ነው፡፡ አዲሱ የኢንተርኔት አገልግሎት አቅሙ ከፍተኛ ከመሆኑም በመሆኑ ከኢ.ቪ.ዲኦ ጋር የፍጥነት ልዩነት እንዳለው ተናግረዋል፡፡
የሞባይል ኢንተርኔትና ሲ.ዲኤም.ኤ ኔትወርክ በማይሠሩበት፣ የ3ጂ ሲምካርድ እና ኢ.ቪዲኦ በኔትወርክ መንቀራፈፍ ደንበኞች በኢትዮ ቴሌኮም ላይ በሚማረሩበት ወቅት አዲስ አገልግሎት የመጀመሩ ፋይዳ ምንድነው? የችግሩስ መንስኤ ምንድን ነው? በሚል የተጠየቁት አቶ አብዱራሂም፤ ለኔትወርክ መቋረጥና ዘገምተኝነት የኀይል መቆራረጥና የፋይበር ኦፕቲክ ኬብል መቆራረጥን በዋነኛ መንስኤነት አስቀምጠዋል፡፡ የኀይል መቆራረጥ ከመሥሪያ ቤቱ አቅም በላይ ቢሆንም በኮንስትራክሽን ሥራና በሕገወጦች የሚቆራረጠው የፋይበር ኬብል ሌላው ለኔትወርክ መቆራረጥ ዋነኛ ምከንያት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ “ከኬብልና ከኀይል መቆራረጥ የሚመጣ የኢንተርኔት ኔትወርክ መጓተት እንጂ በአገልግሎቱ ላይ ችግር የለም” ብለዋል፡፡
ለሕዳሴ ግድብ የሥነፅሁፍ ምሽት ይቀርባል
በአባይ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለውን የሕዳሴ ግድብ አስመልክቶ የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ረቡዕ በ11 ሰዓት በብሄራዊ ትያትር የሥነፅሁፍ ምሽት ሊያቀርብ ነው፡፡ የማህበሩ ፕሬዚደንት ደራሲና ሃያሲ ጌታቸው በለጠ እንደገለፁት፤ አንጋፋ ደራስያን በአባይ ዙሪያ የገጠሟቸው ግጥሞች በምሽቱ ይዳሰሳሉ፡፡ ከዚህም በተማሪ ጥንታዊ የቆሎ ተማሪዎችና አባይ ያላቸውን መስተጋብር የሚቃኝ ዝግጅትም ተካትቷል፡፡ በተመሳሳይ ዜና የኢትዮጵያ ሰዓሊያን ማህበር በሕዳሴ ግድብ ዙሪያ የሥዕል አውደርእይ በቅርቡ ያዘጋጃል ተብሏል፡፡
“ዲያሪ” የቤተሰብ ፊልም ሰኞ ይመረቃል
ሪች ፊልም ፕሮዳክሽን የሰራው “ዲያሪ” የተሰኘ የቤተሰብ ፊልም ሰኞ እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ በአለም ተካ እና በአዲስ ጋዲሳ ተደርሶ አቤል ረጋሳ ያዘጋጀውን የ90 ደቂቃ ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት ተኩል ፈጅቷል፡፡ በፊልሙ እሱባለው ተስፋዬ፣ አለባቸው መኮንን፣ እሌኒ ተስፋዬ፣ አማኑዔል ታምራት፣ ብርሃኔ ገብሩ እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ውይይት ይደረጋል
ከታዋቂ የታሪክ ምሁራን መካከል አንዱ የሆኑት ፕ/ር ባህሩ ዘውዴ፣ “የኢትዮጵያ ታሪክ ከ1847 እስከ 1983” በሚል ርዕስ ባቀረቡት መፅሃፍ ላይ ሚዩዚክ ሜይዴይ ነገ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት፣ አምስት ኪሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመዘክር አዳራሽ የሚደረገውን የሦስት ሰዓት ውይይት፣ የመነሻ ሀሳብ በማቅረብ የሚመሩት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ድህረ ምረቃ ትምህርት ቤት ተማሪ የሆኑት አቶ ታምራት ኃይሌ ናቸው፡፡
ኮፍያው
ነገሩ የተጀመረው በኮፍያ ነው - ለምሳ ቤት መጥቶ ሲወጣ፣ በሩ አካባቢ ባገኘው ኮፍያ - ጥልፍልፍ የቴኒስ መጫወቻ (የራኬት) ምስል በላዩ ላይ ያለበት ኮፍያ፡፡ ኮፍያውን አንስቶ መኪናው ውስጥ ከተተውና ወጣ፡፡ ወደ ቢሮው ከገባ በኋላ የኮፍያውን ነገር ሊረሳው አልቻለም፡፡ “የማን ኮፍያ ነው?” የሚል ጥያቄ በአእምሮው ውስጥ አንቃጨለ፡፡ “አንድ ወንድ ጥሎት የሄደው ነው” … የሚል ምላሽ ከአእምሮው ስርቻ መልሶ አስተጋባ፡፡ ሀሳቡን ለማባረር ራሱን በሥራ ለመጥመድ ሞከረና አቃተው፡፡ ሥራ መሥራት ሲያቅተው ወደ ሚስቱ ደወለ፡፡ ሚስቱ፣ ቤት ነው የምትውለው፡፡ ከተጋቡ ገና አራት ወራቸው ነው፡፡ ስሟ ሶፊ ቢሆንም “ምጥን!” ይላታል፤ ሲያቆላምጣት - በዚህ አጠራሩ እሷ ባትስማማም፡፡ ምጥን ያለች ናት፤ አይኗ የተመጠነ፣ እጆቿ የተመጠኑ ውበቷ የተመጠነ፡፡ ትርፍ የሚባል ነገር የላትም፡፡ ጥርሷ ያምራል ግን ትንሽ አፍንጫዋ … የሚሏት አይነት አይደለችም፡፡ ሁሉ ነገሯ ያምራል፡፡
ስልኩን አነሳች፡፡ ትንሽ አወሩ፡፡ “ዛሬ፣ ቤት ማን መጥቶ ነበር?” አላት ባለቤቷ አበራ - እንደዘበት፡፡ ለአፍታ ዝም አለች፡፡ “ዛሬ … ዛሬ … ማንም አልመጣም … እኔ ምልህ …” ብላ ወደ ሌላ ወሬ አመራች፡፡ “ኮፍያው የማን ነው?” ሊላት ፈለገ፤ ግን ቃላቱ ከአንደበቱ ሊወጡለት አልቻሉም፡፡ እየዋሸችኝ ነው? ለምን ትዋሸኛለች? ሰውነቱን አንዳች ነገር ሲወረው ተሰማው፡፡ ትንሽ አውርተው ስልኩ ተዘጋ፡፡ ቢሮው ውስጥ እንዳለ ፈዞ ቆመ፡፡ እሱና እሷ ብቻ በሚኖሩበት ቤት ውስጥ አንድ ኮፍያ እንዴት ሊገኝ ይችላል? ኮፍያ መቼም እግር የለው፣ የሰው ግቢ ውስጥ ዘሎ የሚገባው! የአንድ ሰው … የአንድ ወንድ ጭንቅላት ላይ ሆኖ መግባት አለበት ወደ ግቢው፡፡ ያንን ኮፍያ ያደረገው ጭንቅላት የማነው? የብዙ ሰዎች ምክር በአእምሮው መጣ፡፡
ለምን አታገባም? በልጅነትህ እናትህ አንተን እና አባትህ ጥላችሁ ስለሔደች ነው? እናትህ ምን አይነት ጨካኝ ብትሆን ነው በገዛ ጓደኛው አባትህን ከድታው የሄደችው? አባትህ ግን ምን አይነት ሞኝ ቢሆን ነው? እድሜ ዘመኑን ሲሰማው የነበረ ንግግር፣ ምክር እና ጥያቄ፡፡ በመጨረሻ ሶፊን ሲያገኝ የሴት ጥላቻው እንደጉም በኖ፣ ትዳር መያዙን የሰሙ ሁሉ ማመን አልቻሉም ነበር፡፡ “ምን አስነክታው ነው?!” ብለው ነበር ያዳነቁት፡፡ ከሶፊ ጋር በትዳር ሲኖሩ ለጥርጣሬ የሚያበቃ አንዳችም ድርጊት አይቶባት አያውቅም፡፡ ሁሌም ግን እንደሰለላት ነው፡፡ … ሁሌም አይኖቹ ለጥርጣሬ የሚሆን ነገር ለማግኘት በንቃት ይቃብዛሉ፡፡ ሶፊ ላይ ግን ምንም ነገር አግኝቶ አያውቅም - ኮፍያውን ግቢው ውስጥ ወድቆ እስኪያገኝ ድረስ፡፡ ኮፍያውን ካገኘ በኋላ ነው ስጋት እንደደራሽ ያዋከበው - የፈራው ደርሶ በነፍሰ ስጋው እየተጫወተች እንዳይሆን ሰጋ፡፡ ምን ነበር አባቱ የሚለው? “አጥንት ቢሰበር ወጌሻ ይጠግነዋል፡፡ የተሰበረን ልብ ግን ከሞት በቀር የሚያድነው የለም! በተለይ በሴት የተሰበረ ልብ …” ነበር የሚለው፡፡
ልቡ በሴት እንዳይሰበር ስንት አመት ነበር የተጠነቀቀው? እናቱ ከውሽማዋ ጋር ስትሔድ የአባቱ ብቻ ሳይሆን የእሱም ልብ ነበር የታመመው፡፡ ስቃዩን ያውቀዋል! እና ሶፊ … ከቢሮው ተስፈንጥሮ ወጣና ሲበር ወደ መኪናው ሔዶ ኮፍያውን አወጣው፡፡ የማን ኮፍያ ነው!? ወደ አፍንጫው አስጠጋው፡፡ የወዝ ሽታ አፍንጫውን ሰነፈጠው፡፡ አሽቀንጥሮ ከጋቢናው ወንበር ላይ ጣለው፡፡ “ጎረምሳ ይሆናል፣ ወይ ደግሞ መላጣ! መላጣ ነው በዚህ የሙቀት ወር ኮፍያ የሚያደርገው - መላጣውን ለመሸፈን፡፡ ለዚህ ነው የኮፍያው አስቀያሚ የወዝ ሽታ ያልጠፋው፡፡ ከኔ ግን በምን አባቱ በልጦባት ነው?”… የኮፍያውን ባለቤት አሰበው፡፡ መላጣ … ምናልባትም ቴኒስ ተጫዋች፡፡ “ወይኔ!” ብሎ የመኪናውን ኮፈን በቡጢ ነረተው፡፡
“ቀደም ብዬ ለምሳ ቤት በመሔዴ ደርሼባቸው ያ መላጣ ተደናግጦ ይሆናል ኮፍያውን ጥሎ የፈረጠጠው፡፡ ይኼ መላጣ!” አለ በንዴት፡፡ “ግን ለምን መላጣ መረጠች? ስንት ባለጎፈሬ ሞልቶላት! ምናልባትም እኮ መላጣነቱን ይሆናል የወደደችው!” በሆዱ ወፈ ሰማይ ጥያቄ ፈለፈለ፡፡ ለሶስት ቀን እያደባ፣ ሰአት እየቀያየረ ባለኮፍያውን በአሳቻ ሰአት ሊያጠምደው ሞከረ፤ አልቻለም! ሌሊት እየተነሳ ከቤቱ ጓሮ ዞሮ አካባቢውን መረመረ፡፡ መላጣው ሰውዬ አጥር እየዘለለ ሊሆን ይችላል የሚገባው፡፡ የአጥር ጥግ ሁሉ አሰሰ - አንድም ዱካ የለም፡፡ “መላጣ ሰው እንዴት እንደምጠላ!” … ሰው መሰላችሁ!?” ይል ጀመር ለጓደኞቹ፡፡ ጓደኞቹ የጋራ አለቃቸውን በሾርኒ እያማው ስለሚመስላቸው ይስቃሉ፡፡ አለቃቸው መላጣ ነው፡፡ “ከአስር መላጣ አንድ ሾጣጣ!” አለ አንድ ቀን አፉ እንዳመጣለት፡፡ መላጣና ሾጣጣ ምን እንደሚያገናኛቸው ጓደኞቹ አልጠየቁትም - ዝም ብለው ሳቁ የጋራ አለቃቸውን እያሰቡ፡፡
በነጋታው አለቃው ጉዳዩን ሰምቶ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ ሰጠው፡፡ መላጦችን የሚጠላበት አንድ ተጨማሪ ምክንያት አገኘ፡፡ ከሶስት ቀን በኋላ ሚስቱ በእንቅልፍ ልቧ ስትዘባርቅ ሊሰማት ወስኖ ለተከታታይ ሁለት ቀናት አጠገቧ ተገትሮ አደረ፡፡ በሁለተኛው ቀን አጠገቧ እንደቆመ ነቃች፡፡ “ምነው!” አለችው በእጁ የያዘውን አውራ ጣቷን እያየች፡፡ ደንግጦ ለቀቃት፡፡ “አውራ ጣቱን የተያዘ ሰው፣ ሲያዝ ቀን የሰራው ይዘከዝካል” ብለው ሰዎች እንደመከሩት አልነገራትም፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በአምስተኛው ቀን፡ ከአምስት ቀን በኋላ ለምሳ መጥቶ ማዕድ ቀርቦ እየበሉ ሳለ ጥያቄ አነሳላት፡፡ “ስለ መላጣ ሰው ምን አስተያየት አለሽ?” አላት እንደዘበት፡፡ ጥያቄው ግራ ያጋባት ይመስል አይኗን እያስለመለመች አየችው፡፡ “ስለመላጣ ነው ስለሰላጣ?” … ጠየቀችው ለምሳ የቀረበውን ሰላጣ እያየች፡፡ “ስለ መ.ላ.ጣ?... ማለቴ እኔ አሁን መላጣ ሰዎችን እጠላለሁ…” አላት ሳቀች፡፡ “እኔ ደሞ መላጣ ሰው እወዳለሁ! አባቴ እኮ መላጣ ነበር፡፡ አንተም ቶሎ ብትመለጥ ደስ ይለኛል፡፡ የመላጣው ሰውዬ ባለቤት ብባል ደስ ይለኛል … ኸኸኸኸኸኸኸኸኸኸኸ” አስረዝማ ሳቀች ሶፊ፡፡ “እና አባትሽን እንዲያስታውስልሽ ነው መላጣ የጠበስሽው?” በሆዱ አጎረምርሞ ዝም አለ፡፡ ያ መላጣ እዚሁ ሰፈር ውስጥ ይሆናል እኮ የሚኖረው! ጎረቤቶቹን አሰባቸው፡፡ መላጣ ከመካከላቸው አለ እንዴ? ከቤታቸው ፊት ለፊት ያሉትን ሰውዬ አሰባቸው፡፡ እሳተ ጎመራ እንደቦደሰው ተራራ፣ መሀል አናታቸው ላይ ብቻ ነው ጸጉር የሌለው፡፡
እሳቸው ደሞ ኮፍያ አያደርጉም! ሌሎቹ ጎረቤቶቹ ደሞ አርቴፊሻል ፀጉር ካልተጠቀሙ በስተቀር ከመከም ጎፈሬ ናቸው፡፡ ቴኒስ የሚጫወት ከመካከላቸው አሰበ፤ ማንም ሊመጣለት አልቻለም፡፡ ጎረቤቶቹ ከሜዳ ቴኒስ ይልቅ ለፈረስ ጉግስ የቀረቡ ናቸው፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በስድስተኛው ቀን፡ ፀጉር ቤት ሔዶ “አንድ ዘመድ ሞቶብኛል!” ብሎ ፀጉሩን ተላጨ፡፡ መላጣ ሆኖ የዛን ቀን ወደቤት ቢገባም ሚስቱ ሶፊ ግን የተለየ ስሜት አልሰጣትም፡፡ “እሷ የምትወደው የተፈጥሮውን ራሰ በራ ይሆናል!” ብሎ ተናዶ ራቱን ሳይበላ ተኛ፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በሰባተኛው ቀን፡ ጓደኛውን ማትያስን ደውሎ ጠራው፡፡ ከሶፊ ጋር ሲጋቡ አንደኛ ሚዜው ነበር፡፡ ራሰ በራ ባይሆንም በቅርቡ ራሰ በረሀ የመሆን እድል አለው ሲል አሰበ፡፡ ራሰ በራ በሆነ ሰው ብቻ ሳይሆን በእጩ ራሰ-በራዎች መቅናት ጀምሯል፡፡ “ማቲያስ እንቢ የማትለኝ አንድ ነገር እንድታደርግልኝ እፈልጋለሁ!” ብሎ እግሩ ስር ወደቀ፡፡
ማቲያስን በግድ እሺ ካሰኘ በኋላ ከእግሩ ስር ተነሳ፡፡ “ሚስቴን ላምናት አልቻልኩም፡፡ በኔ ላይ የደረበችብኝ ይመስለኛል፡፡ ለዚህ ደግሞ ፍንጭ አግኝቻለሁ፡፡ ሰውዬው መላጣ ይመስለኛል…” ብሎ ስለኮፍያው ነገረው፡፡ “እና አንተ ሌላ ፍላጐት እንዳለው ሰው ሆነህ ቅረባት፡፡ ማለቴ… በቃ ልታወጣት እንደምትፈልግ…” አለው ማትያስን በመለማመጥ፡፡ ማትያስ በንዴት ጥሎት ሄደ! ኮፍያውን ባገኘ በስምንተኛው ቀን፡ ማትያስን አፈላልጐ አገኘው፡፡ እንባ አውጥቶ ለመነው፡፡ “የአባቴን ቁስል እያወክ!” በግድ…በግድ አሳመነው፡፡ እቅድ ነደፉ፡፡ እሱ ለመስክ ሥራ እወጣለሁ ብሎ ሊሄድ፤ ማትያስ ደሞ የእሱን መውጣት ተከትሎ እሷን ሊፈታተን፡፡
ኮፍያውን ባገኘ በሃያኛው ቀን፡ ማትያስ “ዝም ብለህ ነው! ሚስትህ ንፁህ ናት! ይኸው ሁለት ሳምንት ለሚጠጋ ጊዜ እቤታችሁ እያመሸሁ ተፈታተንኳት፡፡ እሷ ግን እንዴት ክብሯን የምትጠብቅ መሰለችህ?” አበራ፤ “አይምሰልህ ሴቶችን አንተ ስለማታውቃቸው ነው፡፡ ውጪ ራት ጋብዛት፡፡ ለኔ እንዳትነግረኝ አደራ ብለህ ንገራት!” ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ስድስተኛው ቀን፡ ሶፊ ስልክ ደውላ “አቤ…ቆየህ እኮ በጣም… ዛሬ ጓደኛህ ማትያስ ራት እንብላ አለኝ፡፡ እኔ ግን ደስ አላለኝም፡፡ አበራ ልቡ እየመታ “ሶፊ ደሞ ምን ማለትሽ ነው? ማትያስ ማለት እኔ ማለት ነው እያልኩሽ፡፡ እራት በልታችሁ መመለስ ነው፡፡
ምን ችግር አለው?…” ነዘነዛት፡፡ ተስማማች፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ሰባተኛው ቀን፡ ማትያስ፣ “አበራ ሚስትህ በጣም ታማኝ ናት! አንተ በሰጠኸኝ ገንዘብ እራት ጋብዣት እስከ ስምንት ሰአት ድረስ አብረን አመሸን፡፡ ግን… እኔንጃ በህይወቷ ሙሉ እንዳንተ የምትወደው ሰው እንደሌለ አረጋግጫሁ!” አበራ ንድድ አለው፡፡ በቃ የሴቶችን ልብ ማግኘት ከባድ ነው ማለት ነው? አባቱም እናቱን ታማኝ ናት ብሎ በደመደመበት ሰአት ነበር ጥላው የጠፋችው፡፡ አእምሮው የእናቱን ድርጊት እንደፊልም ማጠንጠን ጀመረ፡፡ ሶፊማ በፍፁም ልታታልለኝ አትችልም! “እና ካሁን በኋላ ተልእኮዬን ጨርሻለሁ?” አለ ማትያስ፡፡ “አንድ የመጨረሻ እድል ማቲ…” ለመነው ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ስምንተኛው ቀን፡ ማትያስ ሶፊ ቤት ሲጫወት አመሸ - የሰአቱ መንጐድ እንዳልተገነዘበ መስሎ፡፡ እኩለ ሌሊት ተጠጋ፡፡
በቤቱ ወስጥ እሱና ሶፊ ብቻ ናቸው ያሉት፡፡ በጣም መምሸቱን ሲያረጋግጥ “በጣም ስለመሸ እዚሁ ባድር…” የሚል ሰበብ አቀረበ፡፡ ኮፍያውን ባገኘ ሃያ ዘጠነኛው ቀን፡ አበራ ራሱ ለማትያስ ደወለ፡፡ “እሺ?” አለ አበራ “ምን እሺ አለ?” ማትያስ ቀዝቀዝ አለ፡፡ የሆነ ነገር ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡ አበራ ልቡ መታ፡፡ በአንድ በኩል ሚስቱ ስታታልለው ስለያዛት ደስታ፣ በሌላ በኩል ክህደቷ እንደወላፈን ገረፈው፡፡ “እኔ እኮ ነግሬሃለሁ! ሴቶች ከሀዲ ናቸው! ያ መላጣን ማውጣቷ ሳያንስ አንተንም! የማላውቃቸውን ስንት ወንዶች… ስንት ወንዶች…” የአበራ ድምፅ በለቅሶ ሻከረ፡፡ “ባክህ ዝም በል! ምንም የሆነ ነገር የለም! ትላንትና ማታ ሚስትህ ባለጌ ብሆንባትም አክብራ ሶፋ ላይ አስተኝታ፣ መኝታ ቤቷን ቆልፋ ነው የተኛችው!” ማትያስ ስልኩን ጆሮው ላይ ዘጋው፡፡
አበራ እልህ በልቡ ተንተከተከ፡፡ ከማትያስ ጋር እንደተመሳጠሩ ወይ ጠርጥራ በነፍሰ ስጋው እየተጫወተች ነው እንጂ… አእምሮው ውስጥ ያሉ ድምፆች አስተጋቡ - “የሴቶችን ልብ ማመን አትችልም! ልባቸውን ወንድ ያኘዋል ማለት ዘበት!” ሲፈራ ሲቸር ማቲያስ ጋር ደወለ፡፡ ያሳለፈውን ህይወት እየተረከ ማትያስ እንዳያዝንለት አደረገ፡፡ ማትያስ በጣም ተጨነቀ፡፡ “እሺ አሁን ምን አድርግ ነው የምትለኝ?” “ሚስቴን ማመን እፈልጋለሁ! ያን ለማድረግ የመጨረሻ! የመጨረሻ! አንድ ነገር ብቻ ተባበረኝ! ከዛ በኋላ አላስቸግርህም ማትያስ አማራጭ አልነበረውም “የተቆለፈ ልብ በአልኮል ይከፈታል! ያኔ የተደበቀ ማንነት ይወጣል!” አለ አበራ ኮፍያውን ባገኘ በሰላሳኛው ቀን፡ ማትያስ ሁለት ሰአት ላይ ወደ ሶፊ መጣ፡፡ ራት በልተው ሲጨርሱ ይዞ የመጣውን ሻምፓኝ ከፈተ፡፡ ሶፊ አልጠጣም አሻፈረኝ አለች፡፡ ማትያስ ለአበራ ደውሎ ነገረው፡፡ አበራ ለሶፊ መልሶ ደወለ “ሶፊዬ ማትያስ ማለት እኔ ማለት ነው፡፡ እሱ እኮ ብቸኝነት እንዳይሰማሽ ነው፡፡ ለኔ ስትይ እሺ በይው…” ለመናት፡፡
ሶፊ አንደኛውን የሻምፓኝ ብርጭቆ ተቀብላ ተጐነጨች… ደገመች… ኮፍያውን ባገኘ ሰላሳ አንደኛው ቀን ጠዋት፡ አበራ ጠዋት ወደ ቤቱ መጣ፡፡ በሩን ከፍቶ ሊገባ ሲል የግቢውን ቆሻሻ የሚደፋው ልጅ ከበሩ መግቢያ ላይ አገኘው፡፡ እድሜው ከዘጠኝ አመት አይበልጥም፡፡ “ጋሼ፤ ቆሻሻ አለ?” “የለም!” ብሎት አልፎት ሊገባ ሲል፣ ልጁ እየተቅለሰለሰ ጠጋ አለው፡፡” “ጋሼ ይቅርታ! ባለፈው ቆሻሻ ልወስድ ስገባ ያቺን ኬፕ… ማለቴ ኮፍያ ግቢ ውስጥ ረስቻት ወጣሁ፡፡ ባለፈው መኪና ውስጥ አይቻት ልጠይቅዎት ስል ሄዱ፡፡ በኋላ ፊልድ ሄደዋል አሉኝ…” አበራ አናቱን በዱላ የተመታ ያህል ደነገጠ፡፡
“ያንተ ነው?” አለ ልጁ ላይ እያፈጠጠ፡፡ ልጁ በድንጋጤ እንደተዋጠ ጭንቅላቱን ላይ ታች ወዘወዘ፡፡ “እና መላጣ ምናምን ስል የበረው በራሴ ፈጥሬ ነው?” አለ አበራ ሳይታወቀው እየጮኸ “ምናሉኝ ጋሼ?” ልጁ ግራ ተጋብቶ ጠየቀው፡፡ ልጁን ችላ ብሎ ወደ ግቢው ሲገባ ማትያስ አይኑ እንደቀላ ወደ በሩ ሲመጣ አየው፡፡ ቆሞ ጠበቀው፡፡ “ያው ደስ ይበልህ! ያሰብከው ሁሉ ሆነልህ! በመጠጥ አደንዝዘህ የምትፈልገውን ፈፅመናል!...” ማትያስ በንዴት ባሩድ የተቃጠሉ ቃላቶቹን እንደጥይት ተኮሳቸው፡፡ “ከሌላ ወንድ ጋር እስክታያት መቼም ቢሆን አርፈህ እንደማትቀመጥ እርግጠኛ ነበርኩ! ሚስት ያገባነው ለበቀል ነበር!” ብሎት ሄደ፡፡ ሚስቱን እጅ ከፍንጅ በመያዙ እርካታን ጠብቆ ነበር፡፡ እርካታ የለም! ፈፅሞ እርካታ ውስጡ የለም! ንፁህነቷ እየጐላ የእሱ መሰሪነት እየገዘፈ መጣበት፡፡
ቤት ሲገባ የሶፊ ሻንጣ ለጉዞ ተዘጋጅቶ ተቀምጧል፡፡ አንገቷን ደፍታ ከሶፋው ላይ ተቀምጣለች፡፡ ቀጭን እንባ በፊቷ ላይ ይወርዳል፡፡ በቆመበት ቁልቁል አያት! መግቢያ ቀዳዳ አጥታ ስትሽቆጠቆጥ በእርካታ ተሞልቶ እንደሚያስተውላት ነበር ያሰበው፡፡ መሳሳቱ ወለል ብሎ ታየው! እንደ አልማዝ የጠነከረ ታማኝነቷን እሳት ሆኖ ማቅለጥ ቢያቅተው፤ በውሃ ሸርሽሮ በድን አካሏ ቃል ኪዳን እንዲሰብር ማድረጉ መልሶ አንገበገበው…