Administrator

Administrator

በሊንኬጅ አርት ሪሶርስ ሴንተር አዘጋጅነት በየዓመቱ የሚካሄደው የፊልም ፌስቲቫልና የፊልም ውድድር ባለፈው ሳምንት

ተካሂዶ አሸናፊዎች ተሸለሙ፡፡
ድርጅቱ ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ ባካሄደው ዝግጅት ፊልሞችን በእስር ዘርፎች አወዳድሯል፡፡
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከኢትዮጵያ ባህልና ቱሪዝምና ከደራሲያን ማህበር የተውጣጡ አምስት የፊልም ባለሞያዎች፣

ፊልሞቹን በተለያዩ ሲኒማ ቤቶች በመመልከት ዳኝተዋል፡፡
ባለፈው ሰኞ በብሔራዊ ቲያትር በተከናወነው የመዝጊያና የሽልማት ስነስርዓት ላይ ይፋ እንደተደረገው “ኒሻን” ፊልም

በሶስት ዘርፎች አሸናፊ ለመሆን በቅቷል - በዓመቱ ምርጥ ፊልም፣ ምርጥ ዳይሬክተርና ምርጥ ሲኒማቶግራፊ፡፡



በወርሃ ታህሣሥ፣ 2001 ዓ.ም ነው … አንዲት ቀይ የቤት መኪና፣ ስድስት ኪሎ ከሚገኘው ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ

ዋናው ግቢ፣ በአንደኛ በር በኩል ወጥታ ቁልቁል ወደ አራት ኪሎ አቅጣጫ ከነፈች፡፡ የጣሊያኖችን የግፍ ጭፍጨፋ

ከሚዘክረው ሀውልት ጋ ሥትደርስ፣ ወደ ማርቆሥ ቤተክርሥቲያን ታጠፈችና አሁንም ቁልቁል ወደ አፍንጮ በር

ተተኮሰች፡፡ ሰዓቱ፣ 11፡45 አካባቢ እንደነበረ አሥታውሣለሁ፡፡ ቀዩዋ መኪና፣ የዩኒቨርሲቲው አንድ አንጋፋ መምህር

እያሽከረከሯት ወደ ፒያሳ አመራች፤ የመምህሩን አምስት የሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎች ብትጭንም፣ ከ12፡30 በፊት፣

አሊያንስ ኢትዮ-ፍራንሴዝ ግቢ የማድረስ ሀላፊነት ተጥሎባታል፡፡ ቀይዋ መኪና ከተቆረጠው ሰዓት በፊት ጥቂት

ደቂቃዎችን ቀድማ ከተባለው ቦታ አደረሠችን፡፡
የአሊያንስ ኢትዮ-ፍራንሴዝ ግቢ፣ ከያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት በወጡ ሙዚቀኞች እንደተቋቋመ በተነገረለት “ሃራ

ሳውንድ ባንድ” አማካኝነት፣ ሞቅ ደመቅ ብሎ ይታያል፡፡ በመሣሪያዎች ብቻ የተቀናበሩ ጣዕመ ዜማዎች ይንቆረቆራሉ፡፡

ውጭ ላይ የተሠናዳው መድረክ፣ በህዝበ አዳም ተሞሽሯል፡፡ አሁን ጨለማው ዐይን ያዝ ከማድረግ አልፏል፤ ትላልቅ

ፓውዛ መብራቶች መድረኩን በብርሃን አድምቀውታል፡፡ የሙዚቃ ቅንብሩ በስፋት መደመጥ ያዘ፡፡ አንድ ገጣሚ መድረኩ

ላይ ወጥቶ በመሣሪያ ቅንብር ከሚወጣው ጣዕመ ዜማ ጋር በወጉ ተለክቶ የተሠፋ የሚመሥል የሰውነት እንቅስቃሴ

ማሣየት ጀመረ፡፡ የውዝዋዜው ሥልት፣ ከሙዚቃው ምት ጋር በእርጋታ እየተዋሀደ ከለብታ ወደ ሞቅታ ሲዛወር፣

የገጣሚው አንደበት ተከፈተ፡፡
ከዚያ ሥልጡን አንደበት ውስጥ የሚወጡ የተመጠኑ የስንኝ ቋጠሮዎች፣ በተለያዩ የሙዚቃ መሣሪያዎች ምጣኔ ዜማ

ታጅበው ሲለቀቁ፣ በታላቅ ኪናዊ የመንፈስ ከፍታ ወደ ሰማየ ሰማያት የሚያርጉ ይመስሉ ነበረ፡፡ እኔ በበኩሌ ግጥም፣

ከዋሽንት ባለፈ በተለያዩ ዘመናዊ የሙዚቃ መሣሪያዎች ቅንብር ታጅቦ ሲቀርብ ሣይ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ በመድረኩ ላይ

የተለያዩ ወጣት ገጣሚያን፣ ከሙዚቃው ምት ጋር የስንኞቻቸውን ምት እያዋደዱ በውዝዋዜ ሞሽረው ታዳሚውን

ማስኮምኮም ቀጥለዋል፡፡ መሀከል ላይ ይመስለኛል፣ የቀዩዋ መኪና አሽከርካሪ፣ አንጋፋው የዩኒቨርሲቲ መምህርም

መድረኩን ተቆጣጠሩት፤ ገጣሚው ፕሮፌሰር፣ ከወጣቶቹ ባልተናነሰ፣ እንደውም ካንዳንዶቹ በተሻለ ቆሞ ሲያሥተምር

የዋለ ወገባቸውን ከሙዚቃው ሥልት ጋር አዋደው ማወዛወዝ ጀመሩ፡፡ ግጥማቸውንም ከሙዚቃው ሥልት ጋር እያዋሀዱ

አቀነቀኑት፡፡ ይህ ቀን፣ በኢትዮጵያ የሥነ ጽሁፍ ታሪክ፣ ሥርዓት ባለው መልኩ ግጥም በጃዝ የቀረበበት ዕለት ተብሎ

ሊመዘገብ ይችላል፡፡
የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ እንደማስታውሰው ከሆነ፣ በዕለቱ ግጥሙን በመሣሪያዎቹ ቅንብር ጣዕመ ዜማና በራሡ ሥልታዊ

ውዝዋዜ አጅቦ በማቅረብ መድረኩን የሟሸው ገጣሚ አበባው መላኩ ይመስለኛል፡፡ “ይመስለኛል”ን ያመጣሁት፣

የመጀመሪያው የመድረክ አሟሺ አበባው ነው ወይስ ደምሰው መርሻ? ባለ “አሻራ”ዋ ምሥራቅ ተረፈ ናት ወይስ ሰዓሊዋ

ምህረት ከበደ? ወይስ ደግሞ “ለግጥም ጥም ጠብታ” የበቃው ፍሬዘር አድማሱ? የሚለውን ቀዳሚ ሰው በውል ማስታወስ

ባለመቻሌ ነው፡፡ “እየሄድኩ አልሄድኩም” የሚሉት የቀዩዋ መኪና አሽከርካሪ ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ ግን መሀከል ላይ

ማቅረባቸው፣ ብዙ ጥርጣሬ አልፈጠረብኝም። ለማንኛውም ግን፣ ስድስቱ ገጣምያን የዕለቱ ባለ ታሪኮች እንደነበሩ

ለመጠቆም መፈለጌን ብታውቁልኝ አልጠላም፡፡
በርግጥ፣ ግጥም በጃዝ ሥርዓት ባለው ቡድናዊ አደረጃጀት ለመጀመሪያ ጊዜ የቀረበው በ2001 ዓ.ም ነው ቢባልም፣ ለዚህ

የቡድን ዝግጅት ከመብቃቱ በፊት ሌሎች ሙከራዎች እንደነበሩ አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እስከ አሁን በተገኙ

ማስረጃዎች መሰረት፣ በ2000 ዓ.ም በብሔራዊ ትያትር አበባው መላኩ “ቅናት” የተሠኘ ግጥሙን በሲዲ በቀረበ የሙዚቃ

ቅንብር አጃቢነት ለተመልካች ማቅረቡ ይታወቃል፡፡ በዚህ ዕለት ከታዳሚው ከፍተኛ አድናቆት እንደተቸረው ተነግሯል፡፡

አበባው፣ በብሔራዊ ትያትር መድረክ ግጥሙን ከተቀናበረ ሙዚቃ ጋር ያቀርብ ዘንድ ንቃትና ብርታት የሆነው “ደግ

አይበረክትም” የተሠኘው የግጥም ሲዲው ዝግጅት ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ፡፡
እንግዲህ፣ ግጥምን በጃዝ መድረክ የሚያቀርበው የቡድን አባላት በአሊያንሥ ኢትዮ-ፍራንሴዝ ዝግጅትና በኋላም

በተለያዩ መድረኮች ግጥም በጃዝ ማቅረቡን እየሠለጠነበት መጣ፡፡ ቡድኑ፣ ከታዋቂው የፒያኖ ተጫዋች ግርማ ይፍራሸዋ

ጋር በጣሊያን የባህል ማዕከል ያቀረበው ዝግጅት፣ የወደፊቱን የከፍታ ዘመን አመላካች ነበረ ማለት ይቻላል፡፡ በቦሌ

ሮክና በሸራተን አዲስ መድረኮች ላይም ኢትዮጵያዊ ግጥም በጃዝ ተሞሽሮ ይቀርብ ዘንድ የቡድኑ የላቀ ትጋትና ጥረት

ቀጠለ፡፡ በ2003 ዓ.ም፣ ወር በገባ የመጀመሪያው እሮብ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል መድረክ ላይ ከመለከት ባንድ ጋር በኋላም

ከአቢሲኒያ ባንድ ጋር በመተባበር ግጥም በጃዝ እየሸመኑ ማቅረብ ተወዳጅ ኪነት እየሆነ መጣ። የዋቢ ሸበሌው የአንድ

ዓመት የግጥም በጃዝ ጉዞ ሲስተናበር የነበረው በቸርነት ወልደ ገብርኤል፣ በደምሰው መርሻና በአበባው መላኩ እንደነበረ

ያሠባሠብኳቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በዚሁ ዓመት ወደ ኋላ ላይ ግሩም ዘነበና ሜሮን ጌትነት የቡድን አባላቱን

እንደተቀላቀሉ ሰምቻለሁ፡፡
አሁንም የግጥም በጃዝ መድረኮች፤ የታዳሚን ቀልብ እየገዙ፣ የኪነት ልክፍት ያለበትን እያፈዘዙ፣ የገነገኑ ሀገራዊ

ሰንከፎችን እየመዘዙ የስኬት ጉዟቸውን ተያያዙት፡፡ በ2004 ዓ.ም፣ ግጥም በጃዝ በራስ ሆቴል መድረኮች ላይ አብቦ

ይፈካ ዘንድ ጊዜው ፈቀደ፡፡ ወር በገባ የመጀመሪያው እሮብ የራስ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ፣ በታዳሚዎች መጣበብ ጀመረ።

የሆቴሉ ሰፊ ግቢ ሊሸከመውና ሊያስተናግደው ከሚችለው በላይ በሆኑ ረዣዥም ሰልፎች ይፈተን ዘንድ ግድ አለው፡፡

አዳራሹ፣ ከ800 በላይ የሚሆኑ ታዳሚዎች ጢም ብለው ሞልተው ይፈሡበታል፡፡ የሚገርመው ግን ይህ ሁሉ ታዳሚ

የሚርመሰመሰው ዝግጅቱ የሚቀርበው በነፃ ሥለሆነ እንዳይመሥልዎ! 50 ብር የመግቢያ ዋጋ ለመክፈል የተሠለፉ

የግጥም በጃዝ እድምተኞች፣ አዳራሹ እየሞላባቸው ሲመለሱ ማየት የየዕለቱ ክሥተት ሆኗል፡፡
የራስ ሆቴሉ ግጥምን በጃዝ መድረክ አሠናጂ የቡድን አባላት፣ ለግዜው “ጦቢያ ግጥም በጃዝ” በሚል ሥያሜ፣ ድርጅት

ከፍቶ የኢትዮጵያን ግጥም በጃዝ አፍክቶ ማቅረቡን ተያይዞታል፡፡ በራስ ሆቴል መድረክ ወር በገባ በመጀመሪያው ዕለተ

እሮብ፣ ለጥበብ ሱሰኞች ምሣቸውን እያደረሠ ይገኛል። የቡድኑ የጥበብ ጉዞ ሥርዓት ባለው መንገድ እየተጓዘ፣

ለተከታታይ 28 ወሮች በመድረክ ላይ ነግሷል፡፡ ቡድኑ፣ ዝግጅቱን በተከታታይ ማቅረብ የጀመረበትን ሁለተኛ ዓመትም

ለማክበር በቅቷል፤ በዚሁ በዓል ላይ፣ የተመረጡ ዝግጅቶች፣ “ጦቢያ ግጥም በጃዝ” (ቅጽ አንድ) በሚል ስያሜ በዲቪዲ

አሣትሞ በ50 ብር ዋጋ ለጥበብ ወዳጆች ማቅረቡ ይታወቃል፡፡ በነገራችን ላይ በራስ ሆቴል መድረክ በጃዝ የሙዚቃ

ቅንብር ተከሽነው የሚቀርቡት ግጥሞች ብቻ አይደሉም፤ ስሜት ኮርኳሪ፣ መሣጭና እውቀት አጋሪ የሆኑ ወጐችና

ዲስኩሮችም ሢቀርቡ አይቻለሁ፡፡ እንደውም፣ በጦቢያ ግጥምን በጃዝ ቢሮ ውስጥ በተገኘ መርሐ ግብር መሠረት፣

በየዕለት መድረኩ 5 ገጣምያን፣ 1 ወግ ተራኪ እና1 ዲስኩር አቅራቢ የኪነት ቤተኞች ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ

ይታወቃል፡፡
የዛሬ የጦቢያ ግጥም በጃዝ ቡድን ተጠሪዎች፤ አበባው መላኩ፣ ምሥራቅ ተፈራ፣ ደምሰው መርሻ፣ ምህረት ከበደ፣ ግሩም

ዘነበና ሜሮን ጌትነት ሲሆኑ፣ አብዛኞቹ፣ በዘመነኛ ትንታግ ገጣሚነታቸው ይታወቃሉ፤ በመካከላቸው በትወናም

የተጨበጨበላቸው ይገኛሉ፡፡ ከ1990ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ አብዛኞቹ የቡድን አባላት በተለያዩ መድረኮች በግጥም

ተናግረዋል፤ ለግጥም ተዋድቀዋል፤ ስለ ግጥም አንብተዋል፤ ስለ ግጥም ቆመዋል፤ ለግጥም ጦም አድረዋል፡፡ ዛሬ ግን

በግጥም እያሠቡ፣ በግጥም ትውልድ ይሞግታሉ፤ በግጥም ተከብረው፣ በግጥም በልተው አድረዋል፡፡
ዛሬ ይህ ቡድን፣ ከተለያዩ ኤምባሲዎችና ከተለያዩ ድርጅቶች የአብረን እንስራ ጥሪ ይቀርብለታል። በታወቁ ተቋማት

ስፖንሰርነት፣ የተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮችን ይወጣ ይዟል፡፡ ለምሣሌ በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም፣ ከያኒው ሰርክ

የሚጠበብበት ተፈጥሮ፣ ህልውናዋ አደጋ ላይ መውደቁን ለማጠየቅ፣ በብሔራዊ ትያትር መድረክ “ጥበብ ለተፈጥሮ”

በሚል ርዕስ የተደነቀ ዝግጅት አቅርቧል፤ በዕለቱ የቀረቡት ግጥሞች በ80 የፖሊስ የማርሽ ባንድ አባላት ታጅበው

እንደነበረ ይታወሣል፡፡
ዛሬ፣ “ጦቢያ ግጥም በጃዝ” የቡድን አባላት፣ የራስ ሆቴልን መድረክ በጥበብ አድምቀው የሚሞሸሩት፣ በራሣቸው

“የመንፈስ ከፍታ” ያህል ብቻ በመንጠቅ አይደለም፤ የተለያዩ ገጣሚዎችን፣ ወግ አራቂዎችን፣ ዲስኩር አቅራቢዎችን ወዘተ

በመጋበዝ አዳዲስ ጥበበ ቃላት እንዲከሸኑ ሥርዓት ዘርግተዋል እንጂ፡፡ ለዚህ ነው፣ ከእግረ ተከል የኪነት ባለሟሎች

እስከ ጉምቱ የጥበብ አያቶች ድረስ በመድረክ ላይ ሢዘምኑ የሚታየው፤ በእውነትና በእውቀት እየተመሙ፣ ኪናዊ ውበት

ሲያፈልቁ የሚገኘው፡፡
ዛሬ ግጥም በጃዝ መድረክ የሚደነቅና የሚወደድ ውበት ብቻ ሣይሆን የሚናፈቅ ሕይወትም እየሆነ ያለ ይመሥላል፡፡

ዛሬ፣ 50 ብር ከፍለው የሚታደሙ አድናቂዎች ብቻ አይደለም የሞሉት፤ የዓመታት ወጪ ሸፍነው የቡድኑ አባል ለመሆኑ

የሚታትሩ ጭምር ተመዝግበዋል እንጂ፡፡ ዛሬ ቡድኑ፣ ጥበብን የሚያቀርብበት የነፃ አዳራሽ መንግሥት ይፍቀድልኝ

አይልም፤ እንደውም በየወሩ ለመንግሥት በሺዎች የሚቆጠር ብር ይገብራል እንጂ፤ “ግብር አይደለም ዕዳ” እንዲል

የገቢዎች ሚኒስቴር፡፡
ምን አለፋዎት … ግጥም በጃዝ መድረክ ላይ በሃበሻ ግጥም፣ የሀበሻ እውነትና እውቀት በጥበባዊ ሥልት ተፈታትቶ

በምርጥ የቃላት ጡብ፣ ሢገጣጠም ያያሉ (እመኑኝ እያጋነንኩ አይደለም-በፍፁም)፡፡ ከሃበሻ የኑሮ ልማድ ውስጥ

እውነቱና እውቀቱ በብልሃት ይተነተናሉ-በግጥም፡፡ ከእውነቱና ከእውቀቱ የተጠነፈፈው ማንነቱ በቃላት ምታት መድረክ

ላይ ሢሠጣ፣ ታዳሚው እየሣቀ ይተክዛል፤ እያጨበጨበ ይቆዝማል፡፡ ግጥሞቹ፣ ወጉና ዲስኩሩ በሀበሻ የመንፈስ ክር

የተሣሠሩ ሽንፈቶቹን፣ ቁጭቶቹን፣ ህልሞቹን ይናገራሉ፤ ከሀገር እውቀቶቹና እውነቶቹ ጋር እየተጣቀሡም፣ የዘመን

መንፈስን እያሥጠቀሡ፣ ገዝፈውና በዝተው ይቀነቀናሉ፡፡ የአዳሚም የታዳሚም መንፈስ ከፍ ብሎ ይንሣፈፋል፤ ዝቅ

ብሎም ይነፍሣል … እኔ በበኩሌ በዩኒቨርሲቲ ውስጥ በመምህርነትም በተማሪነትም ያጣሁትን የመንፈሥ ልዕልና በዚያ

አዳራሽ ውስጥ የተጐናፀፍኩ አይነት ነው የሚሠማኝ፡፡ የሀበሻ ግጥም፣ ወግና ዲስኩር በተቀናበረ ሙዚቃ ታጅበው

እውነት፣ እውቀትና ውበት በሚያፈልቁበት በዚህ አዳራሽ፣ የሰዓታት ሰላም ያገኘሁ ይመሥለኛል፡፡
እስኪ በራሥ ሆቴል አዳራሸ ከሚቀርቡ ዝግጅቶች መካከል የቅርቡን (ህዳር 4 ቀን 2006 ዓ.ም) የጥበብ ድግሥ

በጨረፍታ ልጠቁማችሁ። እንደተለመደው ትልቁ አዳራሽ ከአፍ እስከ ገደፉ ጢም ብሏል፡፡ የውጭ ሀገር የመገናኛ

ብዙኃን ባልደረቦች ትላልቅ መቅረፀ ምሥል ካሜራዎችን ተሸክመው ዝግጅቱን ለመቅረጽ ከወዲያ ወዲህ ሽር ጉድ

ይላሉ፡፡ “ነፃ አውጪ ባንድ” በመሣሪያ የተቀነባበሩ ጣዕመ ዜማዎችን ያሠማሉ፡፡ የመድረክ አጋፋሪው፣ ዝነኛው ተዋናይ

ግሩም ዘነበ ወደ መድረኩ ጐራ እያለ በአስገምጋሚ ድምፁ መርሐግብሩን ያሥተዋውቃል፡፡
በዚህ ዕለት፣ የሸገር ሬዲዮ ባልደረባው ስመ ጥሩ የመድረክ ሰው ተፈሪ ዓለሙ፣ የሁለት ትውልዶችን ብጭቅጫቂ ኑሮ በ

“ስውር-ስፌት” እየጠቀመ ያለው (“ጠ” ጠብቃ ትነበብ) የአዲስ አድማሱ ዋና አዘጋጅ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ ሢያሻው

በግጥም መናገር የሚችለው ታዋቂው ሰዓሊና ቀራፂ በቀለ መኮንን፣ የዕለቱን መድረክ “የመንፈስ ከፍታ” አግዝፎ የናኘው

ገጣሚ በረከት በላይነህ፣ ለግጥም ወይም ስለ ግጥም ሕይወተን እየከፈለ ያለ የሚመሥለኝ ገጣሚ ደምሰው መርሻ፣ መሪር

ሰዋዊ ግዙፍ ጥያቄዎች በተራኪ ግጥም እንዴት በብልሃት ሊቀርብ እንደሚችል በገቢር ያሣየው ገጣሚ ፈቃዱ ጌታቸው፣

ይህ ትውልድ ከሃገሩ አልፎ ዓለምን የመሞገት ብቃት እንዳለው በአንድ የወግ ጽሁፉ ማሣመን የቻለው የ“ፋክት”

መጽሔቱ አምደኛ ሚካኤል ዲኖ እና በተለያዩ መድረኮች ዝናን ያተረፉት የ“ፋቡላ ኪነጥበብ” አባላት የራስ ሆቴልን

አዳራሽ በሀበሻ የጥበብ አየር ሞልተውት አምሽተዋል፡፡ የታዳሚውን ስሜትና የመንፈሥ እርካታ እንዲህ ነው ማለት

ይከብደኛል፤ የአጋነንኩ ይመስልብኛልና! እራስዎት ጠይቀው ቢያረጋግጡ ይሻላል፡፡ አዘጋጆቹ፣ የ“ጦቢያ ግጥም በጃዝ”

ቡድን አባላት ብራቮ!

Saturday, 07 December 2013 13:01

እንኳን ለዓመት ጉድ አበቃን!

ዘንድሮም ልክ በዓመቱ፣ እንደአምናና እንደ ሃቻምና
የሐምሌ ጐርፍ ሞላና፣ ይኸው ለዓመት ጉድ
በቃና …
አደጋ ባሕል ከሆነን፣ እስቲ እግዚአብሔር ይመስገና፣ …
ዝግጁው ማዘጋጃ ቤት፣ ዜና መግለጫ ለማውጋት
እንደጥምቀተ ባሕር ወግ፣ የዓመቱን ጐርፍ ለማውሣት
ደረሰ ፍል ውሃ ሜዳ፣ በጋዜጦች አጀብ ብዛት
ለዓመቱ ዜና ገብ ቂጥ፣ “ካሜራ ማን ዙም-ኢን ዙም አውት”
ዘንድሮ ለማወዳደር፣ ከሀቻምናው የዝናብ መዓት
የዓመቱን ፋንፋር ለሕዝቡ፣ በቴሌቪዥን ለመንፋት! …
አደጋ ባሕል ከሆነን፣ እስቲ እግዚአብሔር ይመስገና፤
እኛም ለዓመት ጉድ በቃና፤ …
ከተማው በዶፍ ታጠበ፣ ዝናብ ሳይሆን መዓት ጣለ
ዘቀጠ ተብከለከለ
ቤት ንብረት ተግበሰበሰ፣ ገደል መቀመቅ ተጣለ
መኪናው እንደ አሻንጉሊት፣ ከምድር በላይ ተንጣለለ
ተዋጠ ተጥለቀለቀ፣ ጣራና ፎቅ ግቻ አከለ
ወረደ መዓት ወረደ
ሰማይ ቁልቁል ተቀደደ
እንደ ኦሪት ውሃ ጥፋት፣ አራዳ በማጥ ተናደ
የቤት እንስሳው ንብረቱ፣ ስንቱ አስከሬን ተወሰደ
ከእንጦጦ ፍልውሃ ሜዳ፣ ቄራ እንጦሮጦስ ወረደ
አጠበው ምድሩን ጠረገው፣ ዛፍ ግንዱን እየማገደ
ፎቁን ተሸክሞት ሄደ! …
አቤት ጉድ እየተባለ፣ እንዲያው ብቻ በደፈና
አዲስ አበባ ያለ ዕቅድ፣ ከዓመት ዓመት በጥገና
የዘለቄታ መፍትሔው፣ በአስተማማኝ ሳይጠና
በማዘጋጃ ቤት ዲስኩር፣ የተናደው ፎቅ ላይ ቀና
ለአዲስ ጥናት በአዲስ እቅድ፣ላይ ነን እኮ እየተባለ
ጋዜጣም ምሱን ሸለለ
ቴሌቪዥን ተቀበለ
ሬዲዮም ተንበለበለ
ዘንድሮም ልክ በዓመቱ፣ አዲሳባ ጉድ ተባለ!
ዝነኛው የአቃቂ ውሃም፣ ከጊንፊሌ ጋር ፏለለ
ስንቱን ሰው በልቶ ቤት ነዶ
ለዓመት ምሱ ሕዝቡን ማግዶ
እንደ ቅድመ ታሪክ ዘንዶ
ደሞ ለዓመት ያብቃን ብሎ፣ ተንጐማሎ እየኮራ
እየተወሳለተ ዝናው፣ በጋዜጣ በካሜራ
እያስገመገመ ሄደ፣ እንደሞላ እንደ ተፈራ! …
አደጋ ባሕል ከሆነን፣ እስቲ እግዚአብሔር ይመስገና፤
እኛም ለዓመት ጉድ በቃና፤ …
ዝግጁው ማዘጋጃ ቤት፣ ዜና መግለጫ ለማውጋት
ደረሰ ላጋር ቁልቁለት፣ በጋዜጦች አጀብ ብዛት፣
ካሜራ ማን ዙም-ኢን ዙም አውት! ራዲዮ ማይክሮፎንክን አጉላ
ፊንፊኔም ጥማድ ቀበና አቃቂም ድምር ቡልቡላ
የዓመት መዓቱን ወረደ ሞላ ፈላ ሰው ተበላ!
የቀበሌ አዋጅ እምቢልታ
የእሳት አደጋ ኡኡታ
አስከሬን ጠፋ ዕድር ውጡ፣ ዋይታ ጡሩምባ ቱልቱላ
የእግዜር ቁጣ የእግዜር ዱላ! …
እንደ አምልኮ ጣኦት ልማድ፣ እንደ ባሕሎች አሸክላ
ለአዲሳባ ውሃ ግብር፣ የሰው ልጅ እየተቀላ
ክረምት በመጣ ቁጥር፣ ዓማን ዘራፍ ይባላላ! …
አደጋ ባሕል ከሆነን፣ እስቲ እግዚአብሔር ይመስገና፤
እንኳን ለዓመት ጉድ በቃና!
ጸጋዬ ገብረ መድኅን

 

በወጣትና አንጋፋ ከያንያን በየወሩ የሚቀርበው “ግጥም በጃዝ” 29ኛ ዝግጅቱን የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 11፡30 ጀምሮ በራስ ሆቴል አዳራሽ እንደሚያቀርብ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ በምሽቱ የጥበብ ዝግጅት ላይ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ ሰዓሊና ቀራጺ በቀለ መኮንን፣ አበባው መላኩ፣ ሜሮን ጌትነትና ገዛኸኝ ፀጋው ግጥም ሲያቀርቡ፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ወግ፣ በኃይሉ ገብረመድሕን ደግሞ ዲስኩር ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ የዝግጅቱ መግቢያ በነፍስ ወከፍ 50 ብር ነው፡፡

በሻሸመኔ ከተማና አቅራቢያዋ ኪነጥበብ አፍቃሪዎች የተቋቋመው “ከአድማስ ፊት” የኪነጥበብ ማህበር 45ኛ ዝግጅቱን ነገ ከቀኑ 7 ሰአት በሻሸመኔ የባህል አዳራሽ እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡ የዕለቱ የክብር እንግዳ በ “ትናንሽ ፀሐዮች” እማ ጨቤን ሆና የምትተውነው አርቲስት ሰብለ ተፈራ ነች። በነገው ዝግጅት የጭውውት፣ የግጥም፣ የዘፈን፣ የመነባንብ ሥራዎች ይቀርባሉ፡፡ ማሕበሩ ካሁን በኋላ በየወሩ በተለያዩ የጥበብ ዘርፎች ውድድር እያካሄደ ለአሸናፊዎች የሚሸልም ሲሆን የነገው ውድድርም በኮሜዲ ዘርፍ እንደሚሆን ማሕበሩ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ከ“አድማስ ፊት” የተመሰረተበትን 6ኛ ዓመት በ50ኛ ዝግጅቱ በመጪው ሰኔ ለማክበር እየተዘጋጀ መሆኑንም አስታውቋል፡፡

የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከዓመቱ ምርጥ የአፍሪካ ሶስት ብሄራዊ ቡድኖች አንዱ መሆኑን አስታወቀ፡፡ አስቀድሞ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በዓመታዊ የኮከብ ተጨዋቾች ምርጫው በሁለት ዘርፎች 3 ኢትዮጵያውያን በእጩነት እንደጠቀሳቸው ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት ከፍተኛ ስኬት በማግኘት በአገሪቱ እግር ኳስ ላይ ከፍተኛ መነቃቃትን ፈጥሯል። የዋልያዎቹ ስብስብ በ2013 የአፍሪካ ምርጥ ቡድኖች የመጨረሻ እጩ ሆኖ የቀረበው ከምእራብ አፍሪካዎቹ ቡድኖች ናይጄርያ እና ቡርኪናፋሶ ጋር ነው፡፡ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ በማለፍ በ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ የበቃው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለ20ኛው ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ የመጨረሻው ጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ በ2014 እኤአ በደቡብ አፍሪካ በሚስተናገደው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ እንደሚሳተፍም ይታወቃል፡፡ በካፍ ዓመታዊ ኮከብ እግር ኳስ ተጨዋች ምርጫ በመላው ዓለም ከሚጫወቱ አፍሪካዊ ፕሮፌሽናሎች በእጩነት ከቀረቡት 25 ተጨዋቾች ሳላዲን ሰኢድ ሲጲጁ በሌላው በአፍሪካ ብቻ በሚጫወቱ ከቀረቡት 23 እጩዎች ደግሞ አዳነ ግርማና ጌታነህ ከበደ ተካትተዋል፡፡ የአፍሪካ ኮከብ ተጨዋቾች ምርጫ ላይ በተለያዩ ዘርፎች ያሸነፉት የሚሸለሙት ከወር በኋላ በናይጄርያ ሌጎስ በሚካሄድ ስነስርዓት ይሸልማሉ፡፡ በተያያዘ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በወጣቶች ላይ በማተኮር ጠንክረን ከሰራን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዕድገት በጣም ተጠናክሮ ይቀጥላል በማለት ለፊፋ ድረገፅ በሰጡት ምላሽ ተናግረዋል፡፡ ፊፋ በድረገፁ በሰውነት ቢሻው ላይ ያተኮረ ዘገባውን ሲሰራ ዋና አሰልጣኙን ቀድሞ የባይሎጂ መምህር እና የእግር ኳስ ተማሪ መሆናቸውን ጠቅሶ ነበር፡፡ ‹‹መምህርነት እና የእግር ኳስ አሰልጣኝነት ተመሳሳይ ሙያ መሆናቸው እጅግ በጣም ጠቅሞኛል፡፡ አስተማሪነቴን ካቆምኩ በኋላ በመጀመርያ በአገር አቀፍ ደረጃ በርካታ የእግር ኳስ ስልጠና ኮርሶችን ወስድኩ ፡፡ ከዚያም የካፍ እና የፊፋ ኮርሶችንም ተከታትያለሁ፡፡ በውጭ አገርም የትምህርት ኮርሶችን አግኝቻለሁ፡፡ አሁን ሙያዬ መምህርነት አይደለም የማስተምረው እግር ኳስን ሆኗል ›› በማለት አሰልጣኝ ሰውነት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ኢንተርናሽናል ውድድሮችን የጀመርነው ለአፍሪካ ዋንጫ እና ለዓለም ዋንጫ የማለፍ ግቦችን በማቀድ ነበር፡፡ ግቦቻችን ለማሳካት በጣም ጠንክረን መስራት እንዳለብንም በመገንዘብ ቀን ከሌሊት ልምምድ አድርገናል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ መሻሻልን ለመረዳት ብዙ እንደማያስቸግር ለፊፋ ድረገፅ ዘገባ ያስረዱት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ‹‹ዋናው ምስጥር በርትቶ መስራት እና ሁሉም ተጨዋቾች በአንድ አይነት አስተሳሰብ እንዲሰሩ ማስቻል ነው፡፡ የቡድናችን ጥንካሬ ያለው አንድነት እና ትስስር ነው፡፡›› ብለዋል የኢትዮጵያን እግር ኳስ ቀጣይ እድገት ብሩህ ለመናድረግ መሰራት ስላለበት ሲናገሩ‹‹ በወጣቶች ደረጃ ወርደን በመስራት የኳስ ተሰጥኦ ያላቸውን ልጆች ማሳደግ አለብን፡፡ በሚቀጥሉት ሁለት እና ሶስት አመታት በርካታ ምርጥ ችሎታ ያላቸውን ተጨዋቾች ማሰባሰባችን አይቀርም፡፡ በእነሱ ላይ አተኩረን ከሰራን የብሄራዊ ቡድናችን ጥንካሬ ይቀጥላል፡፡›› ብለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የ2013 የዓለም ኮከብ እግር ኳስ ተጨዋቾች ምርጫ ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ አነጋጋሪ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ ከሮናልዶ ወይም ከሜሲ የቱ ያሸንፋል በሚል የተፈጠረው ክርክር ትኩረት እንደሳበ ነው፡፡ አንዳንድ ዘገባዎች ፉክክሩ በክርስትያኖ ሮናልዶ፤ ሊዮኔል ሜሲ እና ፍራንክ ሪበሪ መካከል እንደሚሆን እየገለፁ ናቸው፡፡ እንደውም በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ኤጀንሲያ ኒውስ የተባለ ታዋቂ የስፔን ሚዲያ አሸናፊውን ደርሸበታለሁ ብለው ዘግቧል፡፡ እንደኤጀንሲያ ኒውስ መረጃ ሜሲ ለአምስትኛ ጊዜ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ሆኖ የወርቅ ኳሱን እንደሚሸለም ተገልፆ፤ ክርስትያኖ ሮናልዶ፤ ፍራንክ ሪበሪ ፤ አንድሬስ ኢንዬስታ እና ዝላታን ኢብራሞቪች እስከ አምስተኛ ደረጃ እንዳገኙ ታውጇል፡፡ ከግብ ጠባቂዎች በምርጥ 11 ቡድኑ ለመካተት የቀረቡ 5 የመጨረሻ እጩዎች ከሳምንት በፊት ይፋ ሲደረጉ ጣሊያናዊው የጁቬንትስ ግብ ጠባቂ ጂያንሉጂ ቡፎን፤ ስፔናዊው የማድሪድ ግብ ጠባቂ ኤከር ካስያስ፤ ቼካዊው የቼልሲ ግብ ጠባቂ ፒተር ቼክ፤ ጀርመናዊው የባየር ሙኒክ ግብ ጠባቂ ማኑዌል ኑዌር እንዲሁም ስፔናዊው የባርሴሎና ግብ ጠባቂ ቪክቶር ቫልዴዝ ናቸው፡፡ ለዓመቱ ምርጥ ጎል ለሚሸለመው የፑሽካሽ አዋርድ 10 ተጨዋቾች በአስር ምርጥ ጎሎቻቸው በእጩነት ሲቀረቡ የኔይማር እና የኢብራሞቪች ጎሎች ይገኙበታል፡፡ በፊፋ ድረገፅ የተሰጡ ድምፆች ከተሰበሰቡ በኋላ ለመጨረሻ ፉክክር የሚበቁ ሶስት የዓመቱ ምርጥ ጎሎች የሚታወቁት ሰኞ ነው፡፡ በዓመቱ ምርጥ አሰልጣኝ ምርጫ ለመፎካከር የቀረቡ አስር እጩዎች ካርሎ አንቸሎቲ፤ ራፋ ቤኒቴዝ፤ አንቶኒዮ ኮንቴ፤ ቪሰንቴ ዴልቦስኬ፤ አሌክስ ፈርጉሰን፤ ጁፕ ሄንየስ፤ የርገን ክሎን፤ ጆሴ ሞውሪንሆ፤ ሊውስ ፊሊፕ ስኮላሬ እና አርሰን ቬንገር ናቸው፡፡ በሌላ በኩል የቢቢሲ የዓመቱ ምርጥ አፍሪካዊ ተጨዋች ሆኖ ለማሸነፍ የበቃው አይቮሪኮስታዊው ያያ ቱሬ ነው፡፡ የማንችስተር ሲቲ ወሳኝ አማካይ ተጨዋች የሆነው ቱሬ በቢሲሲ የዓመቱ አፍሪካዊ ኮከብ ተጨዋች ሆኖ ከመመረጡ ባሻገር ለፊፋ የወርቅ ኳስ ሽልማት የታጨ ብቸኛው አፍሪካዊ ነው። ዘንድሮ ለ11ኛ ጊዜ በተካሄደው የቢቢሲ የዓመቱ ኮከብ ተጨዋች ምርጫ ላይ በመጨረሻ እጩነት ከቀረቡት ተጨዋቾች ናይጄሪያውያኑ ጆን ኦቢ ሚኬል እና ቪክቶር ሞሰስ እንዲሁም የዛምቢያው ጆናታን ፕሪቶፕያ ይገኙበት ነበር፡፡

አንድ የፈረንጆች ተረት አለ፡፡
ኮረዶች በማፍቀር ዕድሜ ላይ ያሉ ጐረምሶች፤ “የት ሄደን ነው ራት የምንገባበዘው?” ሲባባሉ፤ አንደኛው፤
“ኦሽን-ቪው ሆቴል እንሂድ” አለ
“ለምን?” ሲሉት፤
“እዚያ ቆንጆ ቆንጆ፣ የሚታዩ ኮረዶች አሉ!” አለ፡፡
ሁሉም ተስማሙና ሄደው በርቸስቸስ ሲሉና ሴት ሲያጫውቱ አመሹ፡፡
ይህ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ እንደዚሁ ተገናኙ፡፡ “የት እናምሽ?” የሚል ጥያቄ ተነሳ!
“ኦሸን-ቪው ሆቴል” አለ አንዱ፡፡  
“ለምን?” አሉት፡፡
“ጥሩ ራትና ጥሩ መጠጥ አለ” አለ፡፡
ይህ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ ዳግም ተገናኙ፡፡ አሁን ወደ ሰባ ዓመት ተጠግቷቸዋል እንግዲህ
“የት እንብላ ራት?” ተባለ፡፡
“ኦሺን ቪው ሆቴል” አለ አንደኛው፡፡
    *    *     *
“ለምን?” አሉት፡፡
“በጣም ፀጥ ያለ፣ የውቂያኖሱን ሰላምና ነፋሻ አየር የምናገኝበት ቦታ ነዋ!” አላቸው፡፡
ተያይዘው ነፋሻውንና ፀጥ ያለውን አየር ሲኮመኩሙ አመሹና ተለያዩ፡፡
ይሄ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ እንደገና ተገናኙ፡፡ አሁን ጎብጠዋል፡፡ ከዘራ ይዘዋል፡፡ ባርኔጣ አድርገዋል፡፡ በጣም በዝግታ ነው የሚራመዱት፡፡ እየተደጋገፉ እየተቃቀፉ ነው የሚቆሙት፡፡
“ዛሬስ ለእራት የት እንሂድ?” አለ አንደኛው፡፡
“ኦሽን ቪው ሆቴል” አለ ሌላው፡፡
“ለምን?” ብለው ጠየቁ ሌሎቹ፡፡
ሰውዬውም፤
“እዛ ሆቴል ሄደን አናውቅማ!”
“ብራቮ! አዲስ ሆቴል ማየት በጣም ደስ ይላል” አለ አንዱ፡፡  
“ድንቅ ሀሳብ!”
“አስገራሚ ሀሳብ!”
“ጉደኛ ሀሳብ!” እየተባባሉ እየተጓተቱ፣ እየተገፋፉ፣ መሰሰሰስ እያሉ፤ ወደ ኦሽን ቪው ሆቴል አመሩ፡፡
*   *   *
የተፈጥሮን ሂደት ለማቆም አይቻልም፡፡ ይህን የተፈጥሮና የዕድሜ መሰላል፤ በየዕለቱ ከሚገጥመን አገራዊ ችግርና አፈታቱ ጋር ለማስተያየት ብንሞክር፤ አርጅተን ጃጅተን የሠራነውንና ያልሠራነውን፣ የሄድንበትንና ያልሄድንበትን ለመለየት የማንችልበት የመርሳት ዕድሜ እስከምንደርስ ንቅንቅ አልልም ብለን፤ በያዝነው ሥልጣንና ሹመት ሙጭጭ ካልን፤ በዚያውም ለተተኪው ትውልድ ቦታ ካልለቀቅን፤ የአገር- ለውጥ- ቀን እየራቀ ነው የሚሄደው፡፡ በእርግጥም ይሄ ቦታን በሰላም የመልቀቅ ባህል የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ፖለቲካዊ-ገፅ አለው፡፡ የኢኮኖሚ-ገፅ አለው፡፡ የግል ጥቅም-ገፅ አለው፡፡ ከፓርቲ ጋር፣ከራስ ጥቅም ጋር፣ ከራስ ህሊና ጋር መሟገትንና መታገልን ይፈልጋል፡፡ ይህን ዋጋ ለመክፈል ፈቃደኛ የሆነ በማይገኝበት ዘመን የአገር ምጧ ብዙ ነው፡፡
ወጣቱ ላይ ዕምነት ይኑረን፡፡ ያለ ጥርጥር ወጣቱ አሸናፊ ነው፡፡ The New is invincible ይሉ ነበር የጥንት ፖለቲከኞች፡፡ ዛሬም ይሄ ዕውነታ አይሻርም፡፡ አዲስ ኃይል መፍጠር የአገር አቅም መፍጠር ነው። ይህ ማለት ግን የግድ በፖለቲካ የሚታቀፍ ወጣት ይኑረን ማለት አይደለም፡፡
“ያፈረሰ ቄስ ተመልሶ አይቀድስ፣ የሸሸ ንጉሥ ተመልሶ አይነግሥ” በሚባልበት አገር የማይሻሩና በልብ ፅላት ላይ የተፃፉ ህግጋት አሉ፡፡ እነዚህ በባህልና በማህበራዊ ልምድ የዳበሩና የታመኑ ናቸው! አገር ያወቃቸውና ያመነባቸው የወል ህግጋት እንዳሉ ሁሉ፤ ሰው በግሉ በራሱ ላይ የሚወስንባቸው ግለ-ደንቦችም አሉ፡፡ እንዲህ ያሉት ህገ-ደንቦች ሲበራከቱ ስደት ልጓም ያጣል፡፡ ስደተኛው የትየለሌ ቢሆን የማይገርመው ለዚህ ነው! ውጤቱን እንደ ዛሬው በአስከፊ መልኩ ባንቀምሰውም በውሱን መልኩ የምናውቀው ስደትና አስከፊ ውጤት ነበር፡፡ “የራሱን ጭራ ሳያይ ውሻ ፍየልን ጭራሽን ዝቅ አድርጊ” ይላል የሚል ኦሮምኛ ተረት አለ፡፡ የራሳችን ነውር ሳይታየን ስለ ሌላው አስነዋሪ ነገር መናገር ክፉ እርግማን ነው! የሌሎቹን አገሮች፤ ፓርቲዎች፣ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ስንተች እኛስ? የእኛስ? ብለን መጠየቅን አንርሳ! ልማዶቻችንን፣ በዓሎቻችንን ስብሰባዎቻችንን እንገምግም፣ እንመርምር፣ እናሻሽል፡፡ በዓላት በራሳቸው ግቦች አይደሉም፡፡ ወደፊት መራመጃ እንጂ!  
ከፖለቲካ ባህላችን ውስጥ እጅግ ሚዛን የሚደፋ አንድ ባህል አለ፡፡ ብዙ ሊጤን ይገባል! የይቅር መባባል ባህል!  ቂም፣ የወንጀለኝነት-ስሜት፣ ብድር-የመመለስ ፍላጎት፤ አጥፊ ናቸው፡፡ ዴቪድ ሀውኪንስ እንዲህ ይለናል፡፡ “የ2ኛው የዓለም ጦርነት አንጋፋ ተሳታፊዎች አሰቃቂውንና አንገፍጋውፊን ጦርነት ከተወጡ በኋላ አብዛኞቹ የጠላት ተፋላሚዎች በፍጥነት ይቅርታ ተደራረጉ፣ ይቅር ተባባሉ፡፡ ሰላምታ ተሰጣጡ፡፡ የፍልሚያውን ፍፃሜም በዓል አከበሩ፡፡ በአዲስ የመተሳሰብ መንፈስ ተጨባበጡ፡፡ አሜሪካኖች አቶሚክ ቦምብ የጣሉና በሺዎች የሚቆጠሩ ሲቪሎችን የቀጠፉ ነበሩ፡፡ ጦርነቱ ካበቃ በኋላ ግን “በቃ ጦርነትኮ ይሄው ነው” ተባለ! የትላንት ተፋላሚዎች የዛሬ ጓደኛ ሆኑና ይጠያየቁ ጀመር፡፡ ይሄው እስካሁንም የተረፉት ታላቁን የጦርነት ቀን ያከብራሉ”
በአያሌ ሰዎች በተግባር እንደተረጋገጠው፤ አሉታዊ አመለካከትና የወንጀለኛነት ስሜት ፤በአዎንታዊ የመረዳት ስሜት፣ በመረዳዳትና በትውስታ ስሜት፤ ሊተካ ይችላል፡፡ … በዚህ ስሜት ሲታይ ከዚህ ቀደም ይጠሉ የነበሩ ሰዎች ይቅርታን ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ ከዚህ ቀደም ያስፈሩ የነበሩ ሰዎችም አሁን ሰላማዊ ሆነው ሊታዩ ይችላሉ፡፡ ዋናው ራስን ለማየትና ጥፋትን ለመቀበል ዝግጁ የመሆን ጉዳይ ነው። እርግጥ እንደኛ በፊውዳሊዝም ለተተበተበ፣ ባልለየለት ካፒታሊዝም ለታጠረና ሁሉን ጥፋት በሌሎች ላይ መላከክን ሥራዬ ብሎ ለያዘ ህብረተሰብ ፤ ከአባዜው በቀላሉ ለመገላገል አይቻልም! ሆኖም ይቻላል ብለን አዕምሮአችንንና ልቡናችንን ክፍት እናድርግ፡፡ ለዚህ ቁልፉ ነገር፤ አንዱ ከሌላው መማሩ ነው፡፡ ችግሩ ግን ያልተማረው የተማረውን ካላስተማርኩ፣ አላዋቂው አዋቂው ካላዳመጠኝ የሚልበት፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ በአዕምሮም በአካልም ያልዳበረው ሰው፤ ልምድ ያለውንና የዳበረውን ሰው፤ ዘራፍ ሲልበት፣ ሲፎክርበት፣ ከእኔ ወዲያ ላሣር ሲለው የታየበት አገር መሆኑ ነው! “አውራ ዶሮ ፈረሱን ረግጦ፤ ‘እርግጫ ከእኔ ተማር!’” አለው፤ የሚለው የኦሮምኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

“አገራችን ታላቅ ልጇን አጥታለች፣ ህዝባችን አባቱን ተነጥቋል፣ ይህቺ ቀን መምጣቷ እንደማይቀር ብናውቅም የዛሬዋ እለት ይዛው የመጣችው ሃዘን ፍጹም ጥልቅና በምንም ነገር የማይሽር ነው!!” የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮቭ ዙማ፣ ጥቁር ለብሰው በአገሪቱ ብሄራዊ ቴሌቪዥን መስኮት ብቅ አሉና መሪር ሃዘን ባጠላበት ፊት፣ በተሰበረ አንደበት ተናገሩ፡፡ ይህ ደቡብ አፍሪካን ብቻ ሳይሆን መላውን አለም ያስደነገጠ፣ የብዙዎችን ልብ ክፉኛ የሰበረ ትልቅ መርዶ ነው - ብሄራዊ ሃዘን፡፡ ከትናንት በስቲያ እኩለ ሌሊት ገደማ አለም የማዲባን መፈጸም ተረዳ፡፡ የጸረ አፓርታይድ ታጋዩ፣ የመብት ተሟጋቹ፣ የነጻነት ተምሳሌቱ፣ የይቅርታ ምልክቱ፣ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ሮሊህላላ ማንዴላ በተወለዱ በ95 አመታቸው ሃሙስ ሌሊት ተፈጸሙ፡፡ ትራንስኪ ላይ የጀመረው የማንዴላ የህይወት ጉዞ፣ ዘመናትን ከዘለቀ የትግል፣ የፈተና፣ የድል… የክፉና የደግ፣ የዳገትና የቁልቁለት ፍሰት በኋላ፣ ከትናንት በስቲያ ጆሃንስበርግ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ተቋጨ፡፡ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚደንት ኔልሰን ማንዴላ ጤና ከራቃቸው አመታት ተቆጥረዋል። የጤናቸው ጉዳይ አልሆን ብሏቸው ከአደባባይ የራቁትና ቤት መዋል የጀመሩት እ.ኤ.አ በ2004 የመጀመሪያዎቹ ወራት ገደማ ነበር፡፡ ጤና ውሎ ማደር ያቃታቸው ማንዴላ፣ ከዚህ በኋላ ያሉትን አመታት በቤታቸውና በሆስፒታሎች መካከል እየተመላለሱ ነው ያሳለፉት፡፡ የጤናቸው ጉዳይ እየዋል እያደር አሳሳቢ መሆኑን የቀጠለው ማንዴላ፣ እስካለፈው መስከረም የነበሩትን ሶስት ወራት ፕሪቶሪያ በሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ ተኝተው ክፉኛ የጸናባቸውን የሳንባ ኢንፌክሽን በመታከም ነበር ያሳለፉት፡፡ ህክምናው ተስፋ እማይሰጥ መሆኑ ታውቆ በመስከረም ወር መጀመሪያ ወደ መኖሪያ ቤታቸው እንዲመለሱ የተደረጉት ማንዴላ፣ ዙሪያቸውን በቤተሰቦቻቸው ተከበው በተኙበት ነው ሃሙስ ምሽት ይህቺን አለም የተሰናበቱት፡፡ የማዲባን ህልፈት በውድቅት ሌሊት የሰሙት ደቡብ አፍሪካውያን፣ በእንቅልፍም ሆነ በእረፍት የሚያሳልፉት ቀሪ ሌሊት አልነበራቸውም፡፡ መሪር ሃዘን ልባቸውን የሰበረው ደቡብ አፍሪካውያን ስለ ማንዴላ እንባቸውን አፈሰሱ፡፡ ከሶዌቶ እስከ ፕሪቶሪያ፣ ከኬፕታውን እስከ ጆሃንስበርግ በመላ አገሪቱ ሃዘን ሆነ፡፡ “ማዲባ!... ማዲባ!... ማዲባ!...” ሁሉም ይህን ስም መጥራት፣ ይህን ሰው ማሰብ ያዘ፡፡ ደቡብ አፍሪካውያን ስለ ጀግናቸው ሻማ ለኩሰው አደባባይ ወጡ፡፡ በጥቁሩ ጨለማ ውስጥ ‘የጥቁሩን ብርሃን’ ፎቶግራፎች ይዘው ጎዳናዎችን ሞሏቸው፡፡ “ማንዴላን አላየነውም የታሰረበት ሄደን ማንዴላን አላየነውም!...” እያሉ የክፉ ቀን ዜማቸውን አቀነቀኑ፡፡ የአፓርታይድ አገዛዝ ዘመን መዝሙሮችን ከፍ ባለ ድምጽ ዘመሩ፡፡ የደቡብ አፍሪካ ሰንደቅ ዓላማ፣ በትግልና በመስዋዕትነት ከፍ ላደረጓት የአርነት ታጋዩዋ ዝቅ ብላ ተውለበለበች፡፡ ሀዘኑ የደቡብ አፍሪካውያን ብቻ አይደለም፡፡ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ከጃኮቭ ዙማ አንደበት የተሰማውን መርዶ እየተቀባበሉ አስተጋቡት። የአለም ህዝቦች በሰሙት ነገር ክፉኛ ደነገጡ፣ አብዝተው አዘኑ፡፡ “እሳቸው የሰሩት፣ ከማንኛውም ሰው ከሚጠበቀው በላይ ነው፡፡ ስራቸውን ፈጽመው ወደማይቀረው ቤታቸው ቢሄዱም፣ ማንዴላ የዘመናት ሁሉ ሃብት ናቸው” አሉ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ከወደ ኋይት ሃውስ ባሰሙት የሃዘን መግለጫ ንግግራቸው፡፡ በሞታቸው ጥልቅ ሃዘን እንደተሰማቸው በስሜት ተውጠው የተናገሩት ኦባማ፤ የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማዎች በሙሉ እስከ ሰኞ ድረስ ስለማንዴላ ክብር ዝቅ ብለው እንዲውለበለቡ ትዕዛዝ ሰጥተዋል፡፡ የአሜሪካም ብቻ ሳይሆን የፈረንሳይና ሌሎች አውሮፓ አገራት፣ የአውሮፓ ህብረት እና የፊፋ ባንዲራዎችም ዝቅ ብለው እንዲውለበለቡ ተወስኗል፡፡ ከአፍሪካ እስከ አውሮፓ፣ ከእስያ እስከ መካከለኛው ምስራቅ በአለም ዙሪያ ያሉ የሌሎች በርካታ መንግስታትም ስለ ማንዴላ ሞት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን መግለጽ ይዘዋል፡፡ “እጅግ እጅግ አዝኛለሁ! ለአገሩ በጎ ነገር ለማምጣት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ሲሰራ የኖረ ታላቅ ሰው ነው፡፡ የማንዴላን ታላቅነት የምትመሰክረው፣ ሰላም ውላ የምታድረው ደቡብ አፍሪካ ናት!” ብለዋል የእንግሊዟ ንግስት ኤልዛቤጥ መርዶውን እንደሰሙ ከቤኪንግሃም ቤተመንግስት ባስተላለፉት የሃዘን መግለጫ መልዕክት፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን በበኩላቸው፣ “ለፍትህ የተጋ ታላቅ ሰው፣ ለሰው ልጆች የበጎነት ምሳሌና የመነቃቃት ምንጭ” በማለት ነው ማንዴላን የሚገልጹዋቸው፡፡ “በታሪካችን ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ተገኝቶ ይመራን ዘንድ ማንዴላን የፈጠረልን አምላክ፣ እኛን ደቡብ አፍሪካውያንን አብዝቶ ይወደናል” ያሉት ደግሞ ታዋቂው ጳጳስ ዴዝሞን ቱቱ ናቸው፡፡ ከነገ በስቲያ ሰኞ ጆሃንስበርግ ውስጥ በሚገኘውና 90 ሺህ ሰው በሚይዘው ኤፍ ኤን ቢ ስቴዲየም በሚከናወን ብሃራዊ የሃዘን ስነስርዓት በድምቀት የሚዘከሩት ማንዴላ አስከሬን፣ ለሶስት ቀናት ያህል በመዲናዋ ፕሪቶሪያ በህዝብ ሲታይ ይቆያል፡፡ በመጪው ሳምንት መጨረሻም በብሄራዊ ክብር ታጅቦ በምስራቃዊ ኬፕታውን አቅራቢያ በምትገኘው የዕድገት መንደራቸው ኮኑ ወደሚማስለት መቃብር ይሸኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል፡፡

በኢትዮጵያ የብሪጅስቶን ጎማ ብቸኛ አስመጪና አከፋፋይ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር በ15 ሚሊዮን ብር ወጪ በአዲስ አበባ ቃሊቲ መናኸሪያ አካባቢ ያስገነባው ‘ብሪጅስቶን ትራክ ታየር ሴንተር’ (BTTC) የተሰኘ አዲስ የጎማ ጥገና ማዕከል ትናንት ተመርቆ ተከፈተ፡፡ ላለፉት አስራ ሶስት አመታት ጥራታቸውን የጠበቁ የብሪጅስቶን ጎማዎችን በማስመጣት የሚታወቀው ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር፤ በአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ ውስጥ የራሱን ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንዳለ ይታወቃል፡፡ አገራት በሚጠቀሙበት ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ዘርፈ ብዙ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎት ለመስጠት በማሰብ ማዕከሉን እንደገነባ የብሪጅስቶን ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሁሴን አህመድ በምረቃ ሥነሥርዓቱ ላይ ተናግረዋል፡፡

ደንበኞች የተለያዩ አገልግሎቶችን በምቹ ሁኔታ በሚያገኙበት መልኩ በ6 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነባውና በዘመናዊ ቁሳቁስ የተደራጀው ማዕከሉ፣ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸውን የጎማ ምርቶች ከማቅረቡ በተጨማሪ፣ የካበተ ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች አማካይነት ሰባት አይነት የተለያዩ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎቶችን እንደሚሰጥም ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ ከዚህ በተጨማሪም፤ ከጎማ አጠቃቀም፣ ከአጠቃላይ የተሽከርካሪዎች ደህንነት አጠባበቅና ጥገና ጋር በተያያዘ ለአሽከርካሪዎችና ባለሃብቶች የተሟላ መረጃና ሙያዊ ምክር ይሰጥበታል ተብሏል። ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ በጥናት ላይ ተመስርቶ ባቋቋመው በዚህ ማዕከል ሊሰጣቸው ያቀዳቸው በቴክኖሎጂ የታገዙና የተሻሻሉ አገልግሎቶች፣ የተሽከርካሪዎችንና የጎማዎችን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለአዳዲስ ጎማዎች ግዢ፣ ለጥገናና ለእድሳት የሚወጣውን ወጪ በመቀነስ ረገድም የጎላ ሚና እንደሚጫወት በማዕከሉ ምረቃ ላይ ተነግሯል።

ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ ከአቶ ሰኢድ አል አሙዲ ጋር በመሆን ማዕከሉን መርቀው የከፈቱት የዕለቱ የክብር እንግዳና የብሪጅስቶን ኩባንያ የአፍሪካና የመካከለኛው ምስራቅ ፕሬዚዳንት ሚስተር ሳኩማ በበኩላቸው፤ የማዕከሉ መገንባት ለተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡ ኩባንያው ለወደፊትም ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ጋር ያለውን የስራ ግንኙነት በማጠናከር፣ የተሻሻሉ አሰራሮችንና ጥራታቸውን የጠበቁ የጎማ ምርቶችን ለደንበኞች ማቅረቡን እንደሚቀጥልበትም ሚስተር ሳኩማ ገልጸዋል፡፡ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ፣ ከብሪጅስቶን ጎማ አስመጪነት በተጨማሪ በቡና ኤክስፖርት፣ በሲኖትራክ ተሽከርካሪዎች አስመጪነትና በሳኡዲ ኤርላይንስ ብቸኛ ወኪልነት ሰፋፊ የንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎችን በማከናወን ላይ የሚገኝ ድርጅት ነው፡፡

Saturday, 30 November 2013 11:18

መነሻ ስዕል

አያልቅም ይህ ጉዞ…
ማስመሰል - መተርጐም
በቀለም መዋኘት
ከብርሃን መጋጨት
ለማወቅ ለመፍጠር ባዶ ቦታ መግባት፡፡
መፈለግ… መፈለግ
አዲስ ነገር መፍጠር
ከማይታየው ጋር ሄዶ መነጋገር፡፡
ህይወትን መጠየቅ
ሃሳብን መጠየቅ
መሄድ መሄድ መሄድ…
ከጨረቃ በላይ
ከኮኮቦች በላይ
ከሰማዩ በላይ፡፡
መጓዝ ወደ ሌላ - ባዶ ቦታ መግባት፡፡
በሃሳብ መደበቅ
መፈለግ ማስገኘት፡፡
አያልቅም ይህ ጉዞ…

ከከተማዋ ነዋሪ ውስጥ ከአንድ ሚሊየን በላይ የሚሆነው ሜዳ ላይ ይፀዳዳል

ለ62 ዓመታት አዲስ አበባን ኖረውባታል፡፡ ከልጅነት እስከ ዕውቀት የሚያውቋት ይህቺው ከተማ በዘመን ብዛት እየዘመነች፣ እያደገችና እየተሻሻለች መሆኗን ባይክዱም በንጽህናዋ ረገድ ዕለት ተዕለት ቁልቁል መሄዷ ሁሌም ያስገርማቸዋል፡፡ በተለይ በተለይ ልጅነታቸውን ያሳለፉበትንና ወጣትነታቸውን ያጣጣሙበትን የከተማዋን እምብርት ፒያሣን ፈጽመው አይዘነጉትም፡፡
በዘመናቸው አራዳ እየተባሉ ይጠሩ የነበሩት እኒህ አካባቢዎች፣ እንደሣቸው ባሉ ዘመነኞች እጅግ ይዘወተሩ ነበር፡፡ አካባቢዎቹ የመጠጥ እና የጭፈራ ቤቶች የሚበዙባቸው ሥፍራዎች ቢሆኑም ሁልጊዜም ንፁህና ለአይን ማራኪ እንደነበሩ ያስታውሳሉ፡፡ “አራዳው ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ዙሪያ የነበሩ የመናፈሻ ሥፍራዎች የስንቶቻችን መቀጣጠሪያና የእርቅ ሽምግልና መፈፀሚያ ቦታ ነበር መሰለሽ፤ ያኔ እንዲህ እንደዛሬው ቅጥ አንባሩ የጠፋበት ዘመን አልነበረም፡፡ ያኔ እንዲህ እንደአሁኑ በቤተክርስቲያን ደጃፍ እንደልብ መፀዳዳት ፈጽሞ የማይታሰብ ነገር ነበር፡፡ በየጥጋጥጉና በየሜዳው የሚፀዳዱ ሰዎችን ይዘው የሚያስቀጡ ደመወዝተኛ የሚባሉ ሰዎች ነበሩ፡፡ ግን ህብረተሰቡም እራሱ ፈሪሃ እግዚአሃብሔር ያደረበት፣ ሜዳ ላይ መፀዳዳት የሚያሳፍረውና እርስበርሱ የሚከባበር ስለነበር ከተማዋ እንዲህ እንደዛሬው የህዝብ መፀዳጃ ቤት አትመስልም፡፡ አሁን አሁንማ አፍንጫው ሥር ሲፀዳዳ እፍረት የማይሰማውን የከተማ ነዋሪ ማዘጋጃ ቤቱ የሚያበረታታውና አይዞህ የሚለው ይመስላል። ማዘጋጃ ቤቱ እንኳንስ የከተማዋን ጽዳትና ውበት ሊጠብቅና ሊቆጣጠር ቀርቶ የራሱን ደጃፍ ከህዝብ መፀዳጃ ቦታነት ሊከለክልና ሊያስጥል አልቻለም። አላሙዲን የልጆቻችን ኳስ መጫወቻ የነበረውን ሰፊ ሜዳ ወስደው ሲያጥሩ እንዴት ያለ ሆቴልና መዝናኛ ቦታ ሠርተው አካባቢውን ሊያሣምሩልን ነው፡፡ ተመስገን አይናችን ጥሩ ነገር ሊያይ ነው ብለን ተደስተን ነበር፡፡ ምን ዋጋ አለው፡፡ ይኸው ሃያ ዓመት ሙሉ በአጥር ተከልሎ የመፀዳጃና የመዳሪያ ቦታ ሆኗል፡፡ እኔ የሚገርመኝ ማዘጋጃ ቤቱ እዚሁ ዓይኑ ሥር ያለውን የሠገራ ክምር ማጽዳት አቅቶት፣ የከተማ ጽዳት፣ የአካባቢ ጽዳት እያለ መለፍለፉ ነው፡፡ ለነገሩ የሰው አይን ላይ ያለች ጉድፍ እንደሚታይሽ በራስሽ ፊት ላይ ያለው ትልቅ ግንድ መች ይታይሻል።”
 ገዳም ሰፈር ተወልደው ላደጉትና የከተማዋ ጽዳት በእጅጉ ለሚያሳስባቸው አቶ አሰፋ ታዬ፤ የከተማዋ አስተዳደር የከተማዋን ንጽህናና ጽዳት በመጠበቁ ረገድ ምን እየሠራ እንደሆኑ ፈጽሞ አይገባቸውም። በከተማዋ ዋና ዋና ጐዳናዎች ላይ ተከምረው ሃላፊ አግዳሚውን የሚያሰቅቁ የቆሻሻ ክምሮች ማንን እየጠበቁ እንደሆነም ግራ ይገባቸዋል። “የድሮዎቹ ደመወዝተኞች የአካባቢውን ንጽህና ለመጠበቅና ህብረተሰቡ በተገቢው ቦታ መፀዳዳት እንዳለበት በማስተማሩ ረገድ ሰፊ ሥራን ይሰሩ ነበር። የዛሬዎቹ ደንብ አስከባሪዎች ግን ከሱቅ በደረቴዎች ጋር ሌባና ፖሊስ ሲጫወቱ ነው የሚውሉት፡፡ ‘መሽናት ክልክል ነው’ ብሎ በመፃፍና በመለጠፍ ብቻ ምንም ለውጥ ማምጣት አይቻልም። የግንዛቤ ለውጥ ለማምጣት መስራት አለበት፡፡ እንደውም እኮ ሰው የሚፀዳዳው “መሽናት ክልክል ነው” የሚሉ ጽሑፎች በተለጠፋባቸው ቦታዎች ላይ ነው፡፡
እናም ባለስልጣናቱ በዚህ ጉዳይ ላይ ቢያስቡበት ጥሩ ነው፡፡ ፎቅና መንገድ መሥራት ብቻ አንድን ከተማ ሊያሣድጋት አይችልም፡፡ ንጽህናዋም ወሳኝ ነው፡፡ የከተማዋ አስተዳደር በዚህ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ ካልሰራ በስተቀር አሁን እንዲህ ከፍተኛ ወጪ እየወጣበት የሚሰራውና ብዙ የተባለለት አዲሱ የባቡር ሐዲድ መፀዳጃ ላለመሆኑ ማረጋገጫ የለንም፡፡” የአቶ አሰፋን ትዝብትና ሥጋት የሚጋሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ቁጥር በርከት ያለ ነው፡፡ ከተማዋ ያለ ፕላን የተሰሩ መንገዶችና ቤቶች የሚበዙባት፣ የፍሳሽ ማስወገጃዎች በአግባቡ ያልተሰራባትና አሮጌ መንደሮች የተበራከቱባት እንደመሆኗ በቂ የመፀዳጃ ቤቶች የሏትም፡፡ አብዛኛው የከተማዋ ነዋሪ የሚፀዳዳው በየመንገዱና በየጥጋጥጉ ላይ ነው፡፡
የህብረቱ መቀመጫ፣ የአፍሪካ መዲና፣ የታላላቅ አለምአቀፋዊ ድርጅቶችና ሆቴሎች መናኸሪያ እየተባለች የምትሞካሻው ከተማችን አዲስ አበባ፤ እጅግ ደካማ የንጽህና አጠባበቅ እንዳላትና በሚሊዮን የሚቆጠረው ነዋሪ ህዝቧ ዛሬም በሜዳ ላይ እንደሚፀዳዳ አንድ መረጃ ይፋ አድርጓል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ይፋ ያደረገው ይኸው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በከተማዋ ከሶስት ሚሊዮን በላይ ህዝብ የሚኖር ሲሆን ከዚህ ቁጥር ውስጥ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ወይንም 25 ከመቶ የሚበልጠው የከተማዋ ነዋሪ የመፀዳጃ ቤት የለውም፡፡ ይኸው መፀዳጃ ቤት አልባ የከተማዋ ነዋሪ በየመንገዱ ላይ እና በየቤቶቹ ጥጋጥግ ይፀዳዳል፡፡
የመኖሪያ ቤቶች ተጠጋግተው በተሰሩባቸውና እጅግ በርካታ ህዝብ በሚኖርባቸው አካባቢዎች፣ ነዋሪዎቹ በአብዛኛው የመፀዳጃ ቤት አገልግሎት ለማግኘት አለመቻላቸውን መረጃው አመልክቶ ሜዳ ላይ የመፀዳዳት ሂደቱም በእነዚህ አካባቢዎች ላይ ጐልቶ እንደሚታይ ጠቁሟል፡፡
ይህንን ችግር ለማስወገድ ህብረተሰቡ ከመንግስት ጋር መተባበርና በሜዳ ላይ መፀዳዳት እጅግ አሣፋሪ ተግባር እንደሆነ ተገንዝቦ፣ ከድርጊቱ መቆጠብ ይገባዋል ሲልም መረጃው አመላክቷል። ለነዋሪው ህብረተሰብ በቂ የመፀዳጃ ቤት ሊገነባ እንደሚገባም አስገንዝቧል፡፡
ሰሞኑን በ(Wash Ethiopia movement) አስተባባሪነት በአዳማ ከተማ ውስጥ በተከበረው አምስተኛው አገር አቀፍ የሃይጂንና የአካባቢ ጤና አጠባበቅ ፌስቲቫልና አለም አቀፍ የመፀዳጃ ቤት ቀን በዓል ላይ እንደተገለፀው፤ በአገሪቱ ከ60-80 በመቶ የሚሆነው የጤና ችግር ተላላፊ ሲሆን ከዚህ ውስጥ ደግሞ 75 በመቶ የሚሆነው በንፁህ የመጠጥ ውሃ እጥረትና በአካባቢ ንፅህና ጉድለት ሣቢያ የሚከሰት ነው፡፡ በአገራችን የህፃናት ገዳይ በሽታዎች ከሆኑ የጤና ችግሮች መካከል ግንባር ቀደም የሆነው የተቅማጥ በሽታም ከንፅህና ጉድለት ጋር ተያይዞ የሚከሰት እንደሆነ ተጠቁሞ፤ በአፍሪካ ከንፁህ መጠጥ ውሃ እጥረትና ከግልና ከአካባቢ ንፅህና ችግር ጋር በተያያዙ የጤና ችግሮች በየሰዓቱ 115 ሰዎች እንደሚሞቱ በዚሁ ፌስቲቫል ላይ ተገልጿል፡፡
የአገሪቱ ርዕሰ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ፤ በዚህ መልኩ ሜዳ ላይ የሚፀዳዳ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ህዝብ እንዳለባት ስሰማ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል ውስጥ የምትገኘው የዶርዜ ሃይዞና የሸበዲኖ ወረዳ ነዋሪዎች ይህንን ሲሰሙ ምን እንደሚሉ ማሰቡ አቃተኝ፡፡ በእነዚህ ወረዳዎች እጅግ አሣፋሪው ተግባር ሜዳ ላይ መፀዳዳት ነው፡፡ እነዚህ ቦታዎች “ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት የነፃ” (Open deification Free) ተብለው በተለያዩ መንግስታዊና መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት ሽልማት ተሰጥቷቸዋል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች ሜዳ ላይ መፀዳዳት እጅግ አሣፋሪ ተግባር መሆኑን ያምናሉ፡፡ ይህንን አሣፋሪ ተግባር ላለመፈፀም በእጅጉ ይጠናቀቃሉ፡፡ ይህንን እምነታቸውን ጥሶ መንገድ ላይ የሚፀዳዳ ሲያዩ በዝምታ አያልፉትም፡፡ ነዋሪዎቹ እንዲህ አይነት “አደጋ” በአካባቢያቸው ሲፈፀም የሚጠራሩበት የራሣቸው የሆነ የኮድ መጠራሪያ ድምፅ አላቸው። ይህንን ጥሪ የሰማ የአካባቢው ነዋሪ ሁሉ ጥሪው ወደተደረገበት ቦታ በፍጥነት ይሄዳል፡፡ ሰውየው (ሴትየዋ) መፀዳዳታቸውን እስኪጨርሱ ድረስ ይጠብቁና ሠገራውን በፕላስቲክ ከረጢት ውስጥ እንዲከት ያስገድዱታል፡፡ በሠገራው ላይ የሰውየው ሙሉ ስም ይፃፍበትና በዋናው መንገድ ላይ ይንጠለጠላል፡፡ “የእከሌ ሰገራ ነው” የሚለውን ፅሁፍ የሚያነበው የአካባቢው ነዋሪ ህዝብ ለሰውየው የሚሰጠው ግምት እጅግ ያነሰና የወረደ ይሆናል፡፡ ይህም ድርጊቱን በፈፀመው ሰው ሞራልና ስብህዕና ላይ ከፍተኛ ውድቀትና በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድም መገለልን ያስከትልበታል፡፡ ማንም ሰው ይህ እንዳይደርስበት  ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት ይቆጠባል፡፡ አዲስ አበቤዎች ከዚህ ምን ይማሩ ይሆን?