Administrator

Administrator

በመካከለኛው ምስራቅ በፐርሺያን ገልፍ ሰሜን ምእራብ ጫፍ የምትገኝ በረሀማ ነገርግን ስትራቴጂካዊ እና በነዳጅ ሀብት የበለፀገች አገር ናት። ለዜጎቿም ሆነ ለሌሎች አገሮች ዜጎች በነፃ ህክምና ትሰጣለች፡፡ የአገሪቱ ዜጎች ከመንግስታቸው ሌሎች የተለያዩ ጥቅማጥቅሞችን ያገኛሉ፡፡ የኩዌት ዲናር አቅም ካላቸው ገንዘቦች በቀዳሚነት የሚመደብ ሲሆን አንዱ ዲናር ሶስት ብር ከሀምሳ የአሜሪካን ዶላር ይመነዘራል፡፡ ኩዌት በህገመንግስታዊ የንጉስ ስርአት የምትመራ አገር ናት፡፡
ባለፈው ሳምንት ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ አረብ ጉባኤ 34 የአገር መሪዎችን፤ 7 ምክትል ፕሬዚደንቶች፣ 71 አገሮች እና ድርጅቶች ተሳትፈዋል። የጉባኤው ዋና አጀንዳ በአፍሪካ እና በአረብ መካካል ያለውን ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ማጠናከር ነበር። ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የኩዌት አሚር ሼክ ሰባህ አሀመድ አል ሰባህ የሁለቱ አካባቢ ህዝቦች ቆየት ያለ ታሪካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት እንዳላቸው በመግለፅ በዝቅተኛ የወለድ መጠን የሚከፈል  በአፍሪካ አህጉር ለተለያዩ ኢንቨስትመንት የሚውል አንድ ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በቀጣዩ አምስት አመት እንደሚሰጥና ለተለያዩ የምርምር ስራዎች የሚውል  አንድ ሚሊዮን ዶላር ከኩዌት ለአፍሪካ እንደሚለግስ ቃል ገብተዋል፡፡ በሁለቱም አካባቢ ህዝቦች የምግብ ዋስትና  እና የፀጥታ እና የደህንነት ጉዳዮች  ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫዎች  ሊሆነ እንደሚገባ በአፅንኦት የተናገሩት አሚሩ፣ ነገር ግን አንዱ ወገን እርዳታ እየሰጠ ሌላው ወገን ምንም አስተዋፅኦ የማያደርግበት አካሄድ መስተካከል እንዳለበት በንግግራቸው አስምረውበታል፡፡ የጉባኤው ትኩረት ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ቢሆንም አሚሩ የሶሪያን ጉዳይ በተመለከተ የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ሀላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበው እስራኤል የምትወስዳቸው እርምጃዎች እንደሚያሳስቧቸው ተናግረዋል፡፡
ሁለተኛው አፍሮ አረብ ጉባኤ በሊቢያዋ ስርት ከሶስት አመት በፊት ሲካሄድ ከ2001 እስከ 2016 ይተገበራሉ የተባሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተቀርፀው የነበረ ቢሆንም ቱኒዚያን፣ ሊቢያን፣ ግብፅን እና የመንን ያናወጠው ህዝባዊ አመፅ እና የመሪዎች ከስልጣን መውረድ  እንዲሁም እስከ አሁን የቀጠለው የሶሪያ ቀውስ ፕሮጀክቶቹ ብዙም እንዳይራመዱ ቀስፈው የያዙ ምክንያች ናቸው፡፡
ጉባኤውን በሊቀመንበርነት የመሩት የኢትዮጲያ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ለቀመንበር አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፣ የስደተሦች ጉዳይ የጉባኤው አጀንዳ መሆኑ ተገቢ እና ወቅታዊ እንደሆነ በመግለፅ ጉዳዩ አሳሳቢ በመሆኑ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ  መፍትሄ መፍትሄ እንደሚያስፈልገው አስቀምጠዋል፡፡ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ካለ ችግሩን መፍታት ይቻላል ያሉት አቶ ሀይለማርያም ጉዳዩ እንደ ከዚህ ቀደም ዝም ብሎ የሚታይ አይደለም ብለዋል፡፡ የጉባኤውን ዋና አጀንዳ አስመልክቶም በአረብ በኩል ያለው አቅም እና በአፍሪካ በኩል ያሉ የተለያዩ  እምቅ ሀብቶች ሁለቱን አካባቢዎች እንደሚያስተሳስሯቸው ተናግረዋል። ከመሪዎቹ ስብሰባ ቀደም ብሎ በተካሄደው የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ የስደተኞችን በሚመለከት ይቋቋማል የተባለው የአፍሮ አረብ የተቀናጀ ኮሚቴ ጥሩ ውጤት ያመጣል በለው እንደሚጠብቁ ተናግረዋል፡፡
ከጉባኤው ጎን ለጎንም ከሰላሳ በላይ ውይይቶች የተካሄዱ ሲሆን ከግጭቶች እና ከኢንቨስትመንት ጋር የተያያዙ አጀንዳዎች አብላጫውን ቁጥር ይይዛሉ።  የኢትዮጲያ እና የግብፅ መሪዎች መሀመድ ሙርሲ ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ ለመጀመሪያ ግዜ ተገናኝተው  ኢትዮጲያ  እየገነባች ስላለው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ተወያይተዋል፡፡ የግድቡን ግንባታ አስመልክቶ በግብፅ በኩል የቀረበው ግንባታው ላይ የመሳተፍ ጥያቄ በኢትዮጲያ በኩል ተቀባይነት ያላገኘ ሲሆን ግድቡን አስመልክቶ በያዝነው ወር ግብፅ፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ካርቱም ላይ ተገናኝተው ውይይት ያደረጉ ሲሆን ቀጣዩ ስብሰባም  በታህሳስ ወር ካርቱም ይደረጋል፡፡
ጉባኤው ባወጣው የአቋም መግለጫ በአፍሪካ እና በአረብ አገሮች መንግስታት እና ህዝቦች መሀል የቀረበ ትስስር መፍጠር፣ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን ማጠናከር፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የአረ ሊግ የአፍሮ አረብ የድርጊት መርሀ ግብሮች እና ፕሮጀክቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያግዝ ግብረ ሀይል እንዲያቋቁሙ፣ የአፍሪካ እና የአረብ አገሮ የገንዘብ ተቋሞች የግሉን ዘርፍ እና  የሲቪል ማህበራትን በማጠናከር የሁለቱን አካባቢዎች የንግድ ትስስር እንዲያፋጥኑ ማስቻል፣ የአፍሪካ እና የአረብ የንግድ ምክር ቤቶች እና የኢንዱስትሪው ዘርፍ እነዲሁም ሌሎች የግል ተቋሞች ተከታታይ የሆነ የምክክር መድረኮችን በመፍጠር የሁለቱን አካባቢዎች ትስስር ለማፋጠን እገዘ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በሁለቱም አካባቢዎች ያሉ መንግስታት፣ የግሉ ዘርፍ እና የሲቪል ማህበራት የግብርናውን ዘርፍ እንዲያሳድጉ ማበረታታት፣ የገጠርልማት፣ የግብርና እና የምግብ ዋስትና ላይ የሚሰሩ ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የአረብ ሊግ ይህ የአቋም መግለጫውም ሆነ የአፍሮ አረብ የአጋርነት ስትራቴጂ ተግባራዊ እንዲሆኑ በገንዘብም ሆነ በቴክኒክ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል። ፍልሰትን በተመለከተም የተቋቋመው የአፍሮ አረብ የቴክኒክ እና የቅንጅት ኮሚቴንም ሆነ ከጉዳዩ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ስትራቴጂዎች ሁለቱ አካባቢዎች በቅንጅት እንዲሰሩ፣ ለፈለሱ ሰዎች የደህንነትና ማህበራዊ ጥበቃ ማድረግ፣ ስደተኞችን፣ ተፈናቃዮቸችን  እንዲሁም የፈለሱ ሰዎችን ለሚቀበሉ አገሮች በተለይም ለቡርኪናፋሶ እና የመን እገዛ ማድረግ እንደሚገባና ህገወጥ ፈላሾችን ለመለየት የአፍሮ አረብ የመረጃ ልውውጥ ማእከል እንዲቋቋም ስምምነት ላይ መደረሱን መግለጫው ያሳያል፡፡
የባህር ላይ ውንብድና እና የካሳ ጥያቄ፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የአደንዛዝ እፅ ዝውውር  እና የህገወጥ የመሳሪያ ዝውውር ላይ በጋራ ለመሥራትም ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
አንድ የኩዌት ከፍተኛ ባለስልጣን የፍልሰት ጉዳይ አሳሳቢ ችግር ነው ያሉ ሲሆን በጉባኤው ላይ ያነጋገርኳቸው ተንታኝም፣ የፍልሰት ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶት ካልተሰራበት እና መፍትሄ ካልተሰጠው የአፍሪካን እና የአረቡን አለም ግንኙነት እስከማቋረጥ ሊደርስ እንደሚችል አስቀምጠዋል፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአሁኑ ወቅት ከአምስትመቶ ሺህ በላይ አፍሪካውያን ወደ አረብ አገሮች ፈልሰዋል።
ሁለቱ አካባቢዎች በፀጥታ እና አሸባሪነትን በጋራ ለመከላከል ለዚህመም መረጃ ለመለዋወጥ  የተስማሙ ሲሆን በሁለቱ አካባቢዎች ለሚገኙ ግጭቶች እና አለመረጋጋቶች ለዜጎች አመቺ ሁኔታን በሚፈጥሩና ለደህንነታቸው ትኩረት በሰጠ መልኩ እልባት እንዲያገኝ መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡  
የኩዌቱ አሚር ሼክ ሰባህ በጉባኤው መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ከፊታችን ረጅም እና አስቸጋሪ መንገድ ይጠብቀናል፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ምክንያት በሁለቱም አካባቢዎች ያለው ያለመረጋጋት ነው። ስለዚህ ያቀድናቸውን ለማሳካት ብዙ ጥረት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ርካሽ የሰው ጉልበት፣ ለእርሻ የሚውል ሰፊ የሚታረስ መሬት፣ አፋጣኝ የመሰረተ ልማት ፍላጎት  ይገኛል፡፡ ይህን እድል ሁለቱም አካባቢዎች ሚዛኑን በጠበቀ የዜጎቻቸውን ፍላጎት በተከተለ መንገድ እንዴት ሊወጡት ይችላሉ የሚለው ጥያቄ ምላሽ ለግንኙነቱ ምላሽ ይሰጣል ያሉት የጉባኤው ተሳታፊ፣ በተለይ በአፍሪካ በኩል ጥንቃቄ የተሞላበት እርምጃ ግድ ይላል ይላሉ፡፡
ቀጣዩ የአፍሮ አረብ ጉባኤ በአፍሪካ እንዲዘጋጅ የተወሰነ ሲሆን ሰባተኛውን የአፍሮ አረብ ንግድ ትርኢትም  ሞሮኮ በቀጣዩ አመት እንድታስተናግድ ተወስኗል፡፡

(የአዲስ አበባ 22ተኛ ከንቲባ)

መጋቢት በቀድሞው ሐረርጌ ክፍለ ሀገር ኤጀርሳ ጐሮ በተባለ ገጠራማ መንደር ነው የተወለዱት - በ1928 ዓ.ም፡፡

አባታቸው በአርበኝነት ከሞቱ በኋላ፣ መንግሥት የባለውለታ ልጆችን ሰብስቦ ሲያስተምር፣ ሐረር ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ

ትምህርት ቤት ገብተው የመማር ዕድል አገኙ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ሲያጠናቅቁ፤ በ1945 ዓ.ም ተግባረ ዕድ

ኮሌጅ ገቡ፡፡ ሕንፃ ኮሌጅ ሲከፈት ከመጀመሪያዎቹ ተማሪዎች አንዱ ሆነው ለአራት ዓመት የሚሰጠውን ትምህርት

የተከታተሉ ሲሆን ለተጨማሪ ትምህርትም ወደ ዩጐዝላቪያ ሄደዋል፡፡ ከትምህርት በኋላ በበርካታ መንግሥታዊ መሥሪያ

ቤቶች አገልግለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ 22ተኛ ከንቲባ ሆነውም ሠርተዋል፡፡ “የፖለቲካ ፍላጐት የለኝም፤ ኖሮኝም

አያውቅም” የሚሉት ኢንጂነር ዘውዴ ተክሉ፤ አሁን የአዲስ አበባ ከተማ የነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ በመሆን ማህበራዊ

ተሳትፎ እያደረጉ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙ ስላሳለፉት ህይወትና የሥራ ዘመን አነጋግሯቸዋል፡፡


ዩጐዝላቪያ የሄዱበትን የትምህርት ዕድል እንዴት አገኙ?
የሕንፃ ኮሌጅ ትምህርታችንን ስናጠናቅቅ የማዕረግ ሁለተኛ ተሸላሚ ነበርኩ፡፡ ለምረቃ እየተዘጋጀን እያለ የትምህርት ቤቱ

አስተዳዳሪ፤ “የውጭ አገር ትምህርት ዕድል መጥቷል፤ መሄድ ትፈልጋለህ ወይ?” ሲሉኝ ተስማማሁ፡፡ ከእኛ ኮሌጅ

ሁለት፤ ከሌሎች ቦታ የተመረጡ አራት ልጆች ተጨምረው ወደ ዩጐዝላቪያ ሄድን፡፡ በወቅቱ ዩጐዝላቪያ የኢትዮጵያ

ትልቋ ወዳጅ አገር ነበረች፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ቲቶም ብዙ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ይመጡ ነበር፡፡
በሕንፃ ኮሌጅ የተማርኩት ቢዩልዲንግ ቴክኖሎጂ ቢሆንም ተጨማሪ ትምህርትም ይሰጠን ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ፣

ፖለቲካ ሳይንስና የኦርቶዶክስ ሃይማኖትን ተምረናል፡፡ በአገራችን ያለውን የሕንፃ አሰራር ጥበብን ለማየት የተለያዩ

አካባቢዎች እየሄድን እንጐብኝ ነበር፡፡ ጅማ፣ ሐረር፣ ጎንደር፣ ትግራይና ኤርትራ ወደመሳሰሉት ቦታዎች ሄደናል፡፡ እኔ

ለኪነ ህንፃ (አርክቴክቸር) ትምህርት ልዩ ፍላጎት ስለነበረኝ፣ ዩጐዝላቪያ ስሄድ አርክቴትር ፋኩልቲ ነው የገባሁት።

የትምህርት ጊዜ ለእረፍት ሲዘጋ የተለየዩ አገራትን እየዞርኩ እጎበኝ ነበር፡፡ ጀርመንን፣ ኦስትሪያን፣ ቡልጋሪያን፣ ሀንጋሪን

በዚያ አጋጣሚ ነበር ያየኋቸው። በ1961 ዓ.ም ትምህርቴን አጠናቅቄ መጣሁ፡፡
የት የት ሰርተዋል?
ከውጭ እንደመጣሁ ሥራ የጀመርኩት ሥራና ውሃ ሚኒስቴር በሚባል መሥርያ ቤት ነው - በሙያዩ ተመድቤ ምክትል

ዋና አርክቴክት ሆንኩ፡፡ በ1965 ዓ.ም ወደ አስመራ ተቀይሬ ሄድኩ፡፡ አብዮቱ የፈነዳው እዚያ እያለሁ ነበር፡፡ ከአብዮቱ

በኋላ ወደ አዲስ አበባ ተመልሼ ቀድሞ በነበረኝ ኃላፊነት ተመድቤ መሥራት ቀጠልኩ፡፡ ከዚያ በኋላ በተለያዩ መሥሪያ

ቤቶች እየተመደብኩ ሠርቻለሁ፡፡ የዚያ ዘመን አንዱ ችግር ሙያህም ባይሆን “ተመድበሀል። ገብተህ ሥራ፡፡ ሁላችንም

ተመድበን እየሰራን ነው ያለነው” ይባል ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት በሙያዬ ብቻ ሳይሆን እየተመደብኩም በተለያዩ ቦታዎች

ሠርቻለሁ፡፡ በብሔራዊ ሀብት ልማት ሚኒስቴር በመምሪያ ኃላፊነት፤ በከተማ መሬት አስተዳደር በሥራ አስኪያጅነት፤

በኪራይ ቤቶች አስተዳደር ተጠባባቂ ሥራ አስኪያጅነት፤ በከተማ ፕላን በዋና ኃላፊነት፤ በምርት ዘመቻና ማዕከላዊ

ፕላን በቡድን መሪነት … በተለያዩ ቦታዎችና ኃላፊነቶች ሠርቻለሁ።
በከንቲባነት ሊመረጡ የቻሉት እንዴት ነበር?
ለከተማ ፕላንና አስተዳደር ጥናት ተሰርቶ አዋጅ እንዲወጣ ሲታሰብ የቴክኒክ ሪፖርቱን ያቀረብኩት እኔ ነበርኩ፡፡

ከተሞች እንዴት እንደሚለሙና እንደሚደራጁ ነበር ያጠናነው፡፡ በዚያ አጋጣሚ ለከንቲባነት እንድወዳደር መታሰቡን

ሰምቻለሁ፡፡ የከተማ አስተዳደር ምርጫ ሲደረግ ግባና ተወዳደር ተባልኩ፡፡ በሙያዬ ብሰራ ይሻለኛል ብዬ ተቃውሜ

የነበረ ቢሆንም “ያው ነው፤ ምርጫውን አሸንፈህ የምትገባ ከሆነ እዚያም የምትሰራው ተመሳሳይ ነው” ተባልኩ፡፡
የምርጫው ሂደት ምን ይመስል ነበር?
አዲስ አበባ ከጃንሆይ ጊዜ ጀምሮ በቻርተር ነው የምትተዳደረው፡፡ በዘመኑ የምርጫ ውድድሩ የሚጀምረው ከቀበሌ

ነው፡፡ ያንን ያሸነፉ በከፍተኛ ደረጃ ይወዳደራሉ፡፡ ከከፍተኞቹ ቀጥሎ ዞን ቢኖርም ዞኖቹ ምርጫውን የማስተባባር ሥራ

ነበር የሚሰሩት። በዚህ መልኩ ተወዳድሬ ነው ከንቲባ ለመሆን የቻልኩት፡፡  
የአዲስ አበባ ስንተኛው ከንቲባ ነዎት?
22ተኛው ነኝ፡፡ በዚህ ኃላፊነት ከ1973 እስከ 1981 ዓ.ም ድረስ ነው የሠራሁት፡፡ ሥራ ስንጀምር ቀደም ብሎ ታቅዶ፤

ጠረጴዛ ላይ ካገኘነው ሥራ አንዱ የሌኒን ሐውልት ግንባታን የሚመለከት ነበር፡፡ እቅዱ ሞዴል የተሰራለትና ብዙ ደረጃ

የተጓዘ ነበር፡፡ ሞዴሉ ሁለት ሐውልቶችን ይዟል፡፡ አንዱ የሌኒን ሐውልት ሲሆን ሁለተኛው 30 ሜትር ርዝመት

የሚኖረውና ከሌኒን ሐውልት በስተጀርባ የሚቆም የአክሱም ሐውልት አምሳያ እንደሚኖር ያሳያል፡፡ ለዚህ ሥራ ደግሞ

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሠረት 30 የተለያዩ አገራት መሪዎች የተከሏቸው ባህር ዛፎች ሙሉ ለሙሉ ይመነጠራሉ

ይላል፡፡ በሐውልቶቹ ዙሪያ ፏፏቴ እንደሚኖርም ተመልክቷል፡፡
እኛ ሥራ ስንጀምር በእቅዱና በሞዴሉ ዙሪያ አስተያየችሁን አቅርቡ ተባልን፡፡ የአክሱም ሐውልት የአርክቴክት ሚስጢሩ

ያልታወቀ፤ የኢትዮጵያና የዓለምም ትልቅ ቅርስ ነው፡፡ ሌኒን የወዛደር መሪ ነው፡፡ ሁለቱን ነገሮች የሚያገናኝና

የሚያመሳስል ምንም ነገር የለም፡፡ ሐውልቶችን ማዳቀልም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት የሌለውና የተከለከለ ነው።

ከዚህም ባሻገር የ30 አገራት መሪዎችን ሥም የያዘ ዛፍ አጥፍቶ፣ ሌላ ታሪክ መሥራት አሳማኝ አይደለም ብለን

አስተያየታችንን አቀረብን፡፡
ሪፖርቱን ያቀረብነው ለከተማው ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ነበር፡፡ አስተያየታችንን ለሊቀመንበር መንግሥቱ ኃይለማርያም

እንድናቀርብ ታዘዝን፡፡ ቀጠሮ ተይዞልን ሄደን ሀሳባችንን ስንነግራቸው “እነዚህ ሰዎች የሚሉት ትክክል ነው፡፡ እኛ

በጊዜው እንደዚህ አላሰብንበትም ነበር፡፡ የሶቪየት መሪ ሲመጡ ለሌኒን ሐውልት መሥሪያ ቦታ አዘጋጁ ሲባል ነው

ቦታው ተመርጦ የመሠረት ድንጋይ የተቀመጠበት …” ስላሉ ሐውልቶቹን ማዳቀሉ ቀርቶ፤ ታሪካዊ ዛፎች ሳይቆረጡ

የሌኒን ሐውልት ተሰራ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ 100ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ በዓልም የተከበረው በእናንተ የስልጣን ዘመን ነው፡፡ ዝግጅቱ ምን ይመስል

ነበር?  
የከተማዋን 100ኛ ዓመት የማክበር እቅድም እኛ ከመምጣታችን በፊት የታቀደ ነበር፡፡ ሊከበር የታሰበው ግን በ1976

ዓ.ም የነበረ ቢሆንም እኛ ከመጣን በኋላ ተክለፃዲቅ መኩሪያን የመሳሰሉ የታሪክ ምሁራንን በመጠየቅ ማስተካከያ

ተደርጐ በዓሉን በ1979 ዓ.ም አክብረናል፡፡ አዲስ አበባ ከአፄ ምኒልክና ከእቴጌ ጣይቱ ጋር የተያያዘው ታሪኳ የቅርብ

ቢሆንም ከአብርሐ አጽብሃና ከንጉሥ ዳዊት ጋር የሚያያዝ ጥንታዊ ታሪክ እንዳላትም ይታወቃል፡፡ ከተማዋ

የተመሠረተችበትን 25ተኛ፣ 50ኛና 75ተኛ ኢዮቤልዩ ስለማክበሯ የሚገልጽ መረጃ አላገኘንም ነበር፡፡ 100ኛው ኢዮቤልዮ

የመጀመሪያ ነበር፡፡
ለበዓሉ ምን አቀዳችሁ? ምን ተሳካ? ያልተሳካውስ?
ለበዓሉ ብሔራዊ ኮሚቴ እንዲዋቀር ስንጠይቅ፣ ከእናንተ ውጭ ማንም አይመጣም፤ ሥራችሁን ቀጥሉ ተባልን፡፡ የአዲስ

አበባ ከተማ አስተዳደር የሥራው ባለቤት ሆኖ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትንና ባለሙያዎችን እያሳተፍን መሥራት

ጀመርን፡፡ እንጦጦ ማርያም ቤተክርስቲያንን ስንጐበኝ በዕቃ ማስቀመጫ ክፍል ውስጥ ብዙ ታሪካዊ ቅርሶችን ስላየን፣

ከባህል ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እንጦጦ ላይ ሙዚየም አሰርተን ቅርሶቹ እዚያ እንዲቀመጡ አደረግን፡፡
መስቀል አደባባይ በራስ ብሩ ቤት ለተመሳሳይ አገልግሎት የሚውል ሙዚየም አደራጀን፡፡ ከቤተመንግሥት በውሰት

ያመጣናቸው ቅርሶችንና ከግለሰቦች የተበረከቱልንን ይዘን ነው ሙዚየሙን ያቋቋምነው፡፡ ከሽሮ ሜዳ እስከ እንጦጦ

ያለውን መንገድ በአፋልት ያሰራነው የመቶኛ ዓመቱን በዓል ምክንያት በማድረግ ነው፡፡ ከራጉኤል እስከ ጐጃም በር

ፍተሻ ጣቢያ ያለውን ጥርጊያ መንገድንም አስፋልት ለማድረግ አቅደን የነበረ ቢሆንም በገንዘብ እጥረት ምክንያት

አልተሳካም፡፡
ሌላው ያልተሳካልን እቅድ እንጦጦ ራጉኤል ቤተክርስቲያን አጠገብ፣ አዲስ አበባንና በዙሪያዋ ያሉ አካባቢዎችን

የሚያሳይ ማማ ሬስቶራንት መስራት አለመቻላችን ነው፡፡ 50 ሜትር ከፍታ ያለውን ሕንፃ ለመሥራት ከማሰብም በላይ

የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦለት ነበር፡፡ ቦታውን የመረጥንበት ምክንያት አፄ ምኒልክ ከባለስልጣኖቻቸውና ከአገር

ሽማግሌዎች ጋር ተቀምጠው የሚመክሩበት መስክ መሆኑን ስለተነገረን ነበር፡፡
ቦታው ላይ ለሕፃናት መዝናኛ አምባ የመሥራት ዕቅድም ነበረን፡፡ ይህም አልተሳካም፡፡ ከተሳኩልን ሥራዎች ሌላኛው

ለከተማዋ ስድስት አዳዲስ ፓርኮችን አዘጋጅተን ማስመረቅ መቻላችን ነው፡፡ ሐምሌ 19፣ ፒኮክ፣ የካ ማካኤል፣ መርካቶ

ራጉኤል፣ ጐላ ሚካኤል መናፈሻ ቦታዎች የዚያ ዘመን ውጤት ናቸው፡፡ አራቱ የመናፈ ቦታዎች አሁንም አገልግሎት

በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ በአዲስ አበባ ታሪክ ዙሪያ ምሁራን የሚወያዩበት ሲምፖዚየምም ተካሂዷል፡፡ ታስበው

ያልተሳኩ ነገሮች ቢኖሩም የከተማዋ 100ኛ ዓመት ኢዮቤልዮ በደመቀና በተሳካ ሁኔታ ነበር የተከበረው፡፡
በ1981 ዓ.ም የከንቲባነት ዘመንዎ ሲያበቃ የት ገቡ?
ቀድሞ ወደነበርኩበት ማዕከላዊ ፕላን ተመልሼ፣ በኮሚሽነርነት የአንድ መምሪያ ኃላፊ ሆኜ መሥራት ቀጠልኩ፡፡ እዚያ

እያለሁ ነው የስርዓት ለውጥ የተካሄደው፡፡ ከደርግ ባለስልጣናት  አንዱ ስለነበርኩ ‘ትፈልጋላችሁ’ ተብለው ከታሰሩት

አንዱ ሆኜ በሰንደፋ ፖሊስ ማሰልጠኛ ለተወሰነ ጊዜ ታስሬያለሁ። በኋላ በነፃ ተሰናበትኩ፡፡ ከዚያ በኋላ በግልም በጋራም

የራሴን ሥራ ሞክሬያለሁ፡፡ በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ መሳተፍ ያስደስተኛል፡፡
አሁን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ ነዎት፡፡ እንዴት ወደዚህ ኃላፊነት መምጣት ቻሉ?
መንግሥት ወይም የአገር መሪ የሚኮነው በሦስት መንገድ ነው፡፡ አንዱ ከንጉሳዊያን ቤተሰብ መወለድ ነው፡፡ ሌላኛው

በምርጫ ተወዳድሮ መመረጥ ሲሆን ሦስተኛው አንዱ ሌላውን ታግሎ በማሸነፍ ነው፡፡ ኢሕአዴግም ከእነዚህ በአንዱ

መንግሥት ሆኗል፡፡ እኔ አንድ መሠረታዊ የሆነ የግል እምነት አለኝ፡፡ የአካባቢዬ የስልጣን አካል ሲጠራኝ መሄድ አለብኝ

ብዬ አምናለሁ፡፡ ቀበሌ ማለት መንግሥት ነው፡፡ ከቀበሌው ጋር ያልተገናኘ ከላይኛው አካል ጋር እንዴት ሊገናኝ

ይችላል? በዚህ እምነትና አቋሜ ምክንያት በተጠራሁባቸው መድረኮች እየተገኘሁ የተሰማኝን አስተያየት አቀርባለሁ፡፡ ይህ

ደግሞ የምጋበዝባቸውን መድረኮች ቁጥር አበራከተው፡፡
መሠረታዊ የሆነው የሕዝብ አደረጃጀት የሚፈጠረው በጉርብትና ነው፡፡ በጉርብትና ለመገናኘት ደግሞ መሠረታዊ የሆነ

የጋራ ነገር ያስፈልጋል፡፡ መሠረታዊው ነገር በቦታ፣ በጊዜና በአገልግሎት ይገለፃል፡፡ እያንዳንዳችን በየዕለቱ ሦስት

ተግባራትን በተደጋጋሚ እንፈጽማለን፡፡ 8 ሰዓት በሥራ፣ 8 ሰዓት በእንቅልፍና 8 ሰዓት ደግሞ በእረፍት ወይም

በመዝናናት እናሳልፋለን፡፡
በአንድ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ሕዝቦች እርስ በእርስ ካልተገናኙ፣ ካልተወያዩና በጋራ ካልተዝናኑ ከተማ ነው አይባልም፡፡

የከተማ ሕዝብ አደረጃጀት ፍልስፍና መሠረቱም አብሮነትን የሚያጐላ ነው። ይህንን አመለካከትና ፍልስፍና

ስለማምንበት ባለፉት 12 ዓመታት ለሊዝ ፖሊስ የማሻሻያ ውይይት ሲደረግ፣ የአዲስ አበባ ተሐድሶ ኮንፈረንስ ሲጠራና

በመሳሰሉት መድረኮች እየተጋበዝኩ ተሳትፌያለሁ፡፡ በእነዚህ መድረኮች ተገኝቼ ሃሳቤን መግለጽ በመቻሌ ደስተኛ ነኝ፡፡
ይህንን ተሳትፎ የማደርገው በጡረታ ዕድሜዬ ነው፡፡ ልማት የጋራ ነው፡፡ ብንወድም ብንጠላም እየሰራን ነው

ልዩነታችንን ወደ አንድ ለማምጣት መጣር ያለብን፡፡ ሥራና ልማትን ትቶ መሟገትና መጨቃጨቁ የሚያስገኘው ጥቅም

የለም፡፡ በአሰራሮች ላይ ችግሮች እንዳሉ አያለሁ፡፡ ለምሳሌ ለልማት እንዲነሱ የሚደረጉ ሰዎች የሚከፈለው ካሳ

የገበያውን ዋጋ መሠረት ያደረገ አለመሆኑ ትክክል አይደለም፡፡
የከተማ መሬት በመንግሥት መያዙ ብዙ ጥቅም እንዳለው አምናለሁ፡፡ በደርግ ዘመንም መሬት የመንግስት ነበር፡፡

በከተሞች መሬት በነፃ እናድል ነበር፡፡ ኢሕአዴግ በሊዝ አለ፡፡ ይህ ደግሞ ገንዘብ በማስገኘት ብቻ ሳይሆን መንግሥት

ለከተማው ፕላን መሥራት እንዲችልም አድርጎታል፡፡ ነገር ግን ለሕዝብ አገልግሎት፡- ትምህርት ቤት፣ ገበያ፣ መዝናኛ፣

ጤና ጣቢያ ሊሰራባቸው የተከለሉ ቦታዎች ላይ ማስተር ፕላኑ ባስቀመጠው መሠረት ለምን እንዳልተሰሩ

የሚመለከታቸው አካላትን በሕግ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ለምን እንዳልተሰሩ ይህን መሰል ሀሳብና አስተያየቼን በየመድረኩ

እየተገኘሁ መግለፄ በሂደት የከተማ ነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ ሆኜ እንድመረጥ ምክንያት ሆኗል፡፡
ተቃውሞ አልገጠመዎትም?
ከ1997 እስከ 1999 ዓ.ም መንግሥት ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጋር ቅሬታ ላይ በነበረበት ጊዜ እንዴት አብረህ ትሰራለህ?

የሚሉኝ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ይህንን መሰል ጥያቄ የሚያቀርብልኝ የለም፡፡ የሚጠይቀኝ ከመጣም ‘አገሬ አይደለም ወይ?

ለምንድነው በልማት ሥራ የማልሳተፈው?’ ብዬ መልሼ መጠየቄ አይቀርም፡፡ ይህንን ተሳትፎ በነፃና በፍላጐቴ ነው

የማከናውነው፡፡ የፖለቲካ ፍላጐት የለኝም፤ ኖርኝም አያውቅም፡፡
ቤተሰባዊ ሕይወትዎ ምን ይመስላል?
የማከብራት ባለቤትና ሦስት ሴት ልጆች አሉኝ፡፡ ቤተሰቤ የተባረከ ነው፡፡ እኔም ሰላምና እርጋታ ያለኝ ሰው ነኝ፡፡

በደስታና በሰላም ነው የምንኖረው፡፡  


ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት ትላልቅ ገበሬዎች በጣም አባያ ሆነው በየጫካው እየደነበሩ እፅዋቱን እየረመረሙ አገር-ምድሩን እያመሱ አስቸገሩ፡፡ የዱር አራዊቱ ሁሉ በግዙፍነታቸውና በጉልበተኝነታቸው ፈሯቸው፡፡ የደኑ አራዊት አንድ ቀን ተሰበሰቡና
“እነዚህን በሬዎች ምን ብናደርግ ነው በቀላሉ ልንበላቸው የምንችለው?” ይባባሉ ጀመር፡፡ ሆኖም ሁሉም ፈሩ፡፡ የበሬዎቹ ትላልቅ መሆን ከወኔያቸው በላይ ሆነ፡፡ ስለዚህም ምንም ሳያረጉዋቸው ቆዩ፡፡
አንድ ቀን አንድ ብልጥ ጅብ መጣና “ቆይ ግዴላችሁም፤ እኔ እነዚህን በሬዎች እነጣጥልላችኋለሁ” አለ፡፡ ከዚያም ወደ በሬዎቹ ሄደና እንዲህ አላቸው፡-
“እባካችሁ ተራ በተራ ላናግራችሁ እፈልግ ነበር፡፡ ትፈቅዱልኛላችሁ?”
በሬዎቹም፤
“እንደፈለክ ልታናግረን ትችላለህ” አሉት፡፡
አያ ጅቦም በመጀመሪያ ጥቁሩን በሬ ጠርቶ፤
“ከእናንተ መካከል የነጩ በሬ ነገር ያሳስበኛል”
“ለምን ያሳስብሃል?” አለና ጠየቀ ጥቁሩ በሬ፡፡
“ጠላቶች ከሩቁ በነጩ ቆዳው ምክንያት ይለዩታል፡፡ ስለዚህም በቀላሉ ስለሚለዩዋችሁ ያጠቋችኋል፡፡ የሚሻለው ገለል ብታደርጉት ነው-ተመካከሩበት” አለው፡፡
በሬዎቹ ተመካከሩና ነጩ በሬ ለብቻው ራቅ ብሎ እንዲኖር አደረጉ፡፡ የደኑ አውሬዎች፤ ብቻውን ያገኙትን በሬ አድነው፣ አሳድደው በሉት፡፡ አያ ጅቦ ቀጠለና ጥቁሩን በሬ እንደገና ጠራው፡፡
“የዚህ የጓደኛህ የቀዩ በሬ ነገር በጣም አሳሳቢ ሆኖብኛል” አለው፡፡
“ለምን አሳሳቢ ሆነብህ?” አለው፡፡
“ምክንያቱም፤ ደም የመሰለ ቀይ በመሆኑ፤ ሰዎች ከሩቅ ይለዩታል፡፡ ስለሆነም ባንድ አፍታ የት እንዳላችሁ ይለዩና ይከታተሉዋችኋል! ራቅ አርገህ ብትልከው አንተ እንደዛፍ ወይም እንደዛፍ ጥላ የጠቆርክ በመሆንህ አይለዩህም” አለው፡፡
ጥቁሩ በሬም ሄዶ ለቀዩ በሬ ስለተባለው አደጋ አዋየው፡፡ ቀዩ በሬ ተስማማና ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደ፡፡
ቀዩ በሬ ብቻውን ሲሆንላቸው የዱር አውሬዎቹ አሳደው ሰፈሩበት፡፡
በመጨረሻም ወንድም የሌለው ጥቁሩ በሬ በግላጭ ተገኘና የዱር አውሬዎች ሁሉ ተቀራመቱት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አያ ጅቦ “የአፍ-አጣፋጭ” የሚል ስም ወጣለት፡፡  
*   *   *
የባለተራ ደወል የሚለውን አለማሰብ የዋህነት ነው፡፡ አዳዲስ አካሄዳችንን አለማስተዋልም ጅልነት ነው! “እኔ እዚህ መሆኔ በቂ ነው” ከማለት ባሻገር፤ “እገሌ የት ደረሰ?” ማለት ያባት ነው፡፡ የኃይል ሚዛንን አውቆ ማን ምን እያደረገ ነው? ምን ዘዴ እየተጠቀመ ነው? ማለት ደግ ነው፡፡ “የከፋፍለህ ግዛውን መርህ የምንንቀውና የምንሳለቅበትን ያህል፤ ዕውነት ቢሆንስ? ማለት ከማኪያቬሊ ጀምሮ የኖረ ያለ፤ “ደባ” መሆኑን ማስተዋል ታላቅነት ነው፡፡
የሀገር፣ የህዝብ እና የተቋም ሚሥጥር ግራ ሊያጋባን አይገባም፡፡ የሚሥጥር ትርጉም ብዙዎችን ቢያወዛግብም፤ የግል - ሚሥጥርና የአገር ሚሥጥር ግን መለየት ይኖርበታል፡፡
ስልክ ወይም ኢሜይል ጠለፋ አዲስ ኃይላዊ ማረጋገጫ (Coerced confession) ነው ይባላል፡፡ አዲስ ሚሥጥር መያዣ ዘዴ ነው፡፡ ዱሮ፤ በጉልበት በማገት የምናደርገውን፤ ዛሬ በሽቦና በኤሌክትሪክ ኃይል ጠለፋ ላይ መፈፀም ማለት ነው፡፡ ይሄ እንግዲህ “ተመርማሪውን ከማስገደድ፣ ቢያስፈልግም በቶርቸት (በወፌ-ላላ)፤ ከማወጣጣት ዶክመንቶቹን ከመውረስ፣ የግል መረጃዎችን ከመውሰድ፣ ቤቱን ሰብሮ ከመግባት ይልቅ፤ ሌላ ዘዴ መተካት ማለት ነው፡፡ ይሄ በዘመናዊ መንገድ ሲታሰብ፣ የኢ-ሜይል መዛግብት መውረስ ማለት ነው፡፡
ይሄ ደሞ፤ የኤሌክትሮኒክ መገናኛ ዘዴዎችን የፈጠሩት ሰዎች ራሳቸው፤ የማያውቁት ዘዴ የለም ብለን እንመን እንደማለት ነው፡፡
“ፖስታህ ከተከፈተ አለቀልህ፡፡ ገበናህ ተቀደደ፡፡ ፈረሱ ከጋጣው ወጥቷል”
 “ዱሮ ሚሥጥር የቤተ ክህነት ነበር፡፡ ዛሬ ቴክኖሎጂ ወርሶታል፡፡ ነገር ከካህን ወደ ልዑል ካለፈ - ነገር ጠፋ” ይላል - ዘ ኒውዮርከር፡፡ ገዢ የማያቀው ሚሥጥር የለም ነው ቁም ነገሩ፡፡
ከግልጽነት ይልቅ ሚሥጥራዊነትን የሚፈልግ ወገን - ባሁኑ ዘመን ቀልጧል፤ የሚል እሳቤ ቢኖረን ይሻላል፡፡ “ሚሥጥር ከኮተኮታችሁ ሁሉ ነገር ተጀመረ፡፡ ጐበዝ! ሚሥጥራዊነት የሤራ መሣሪያ ናት (ጄሬሚ ቤንታም)” በድብቅነትና በሚሥጥራዊነት መኖር አይቻልም፡፡ ከህዝብ የምትደብቀው ሚሥጥር በተለይ፤ ውሎ አድሮ መሸማቀቂያህ ነው!
ድብቅነት ነገ ከነግ - ወዲያ ይገለጣል፡፡ ሚሥጥራዊነት ግን የጥብቅነቱን ያህል ይቆይ እንጂ የሚታወቅ አደጋ ይሆናል፡፡ ሚሥጥራዊነት ብዙ ሽፋን አለው:- የሉዓላዊነት ሽፋን፣ የመንግሥት ደህንነት ሽፋን፣ የተቋም ህልውና ሽፋን፣ ያለመከሰስ መብት ሽፋን…ምኑ ቅጡ! ዜጋ የግል - ሚሥጥሬ ነው ቢል ግን፤ በብዳቤ፣ በኢ-ሜይል፣ በሞባይል፣ በአካል ሊያስጠይቅህ ይችላል የሚባለው ሚሥጥር የመብቱን መገፈፍ አያመላክትም፡፡
“መንግሥት ዜጐቹን ላለመሰለል መጠንቀቅ ይገባዋል” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ “እኛ ብቻ ነን መሪዎች” የሚሉ ህዝቡን እንዲህ ይላሉ:- “ለማመዛዘንና ለመፍረድ አትችሉም፡፡ ደንቆሮ ናችሁና፡፡ ያም ሆኖ፤ ደንቆሮ ሆናችሁ መቀጠል ይኖርባችኋል - ምነው ቢሉ ማመዛዘንና መፍረድ እንዳትችሉ ይፈለጋልና፡፡” ይላል /ቤንታም/፡፡
ፖስታ እየገለጡ ሚሥጥር ስለሚያዩ ፖስታ ቤቶች፣ ዲዝሬኤሊ እንዲህ ይላል፤ “ደብዳቤዬን ክፈቱ ግን መልስ መስጠት ቻሉ!”
ዋናው ጥያቄ ግን በግል - ሚሥጥር (Privacy)፣ በግልጽነት  (Publicity) መካከል ልዩነት እንዳለ ልብ - ማለት ያሻል የሚለው ነው፡፡
ሆኖም እንደ ኤድጋር አላን ፖ - አመለካከት፤ “ሁሉም ድብቅ ነገር (mystery) ነገ ተገላጭ ነው፡፡ ምንም ነገር ተሸሽጐ አይቀርም፡፡ ወንጀሎች መፈታት አለባቸው፡፡ ግርግዳዎች መፍረስ አለባቸው፡፡ መቃብሮች ይፈነቀላሉ፡፡ ፖስታዎችም ተቀደው ይታያሉ” ይላል፡፡
ሙሰኛን፣ ኢፍትሐዊን፣ ሃሳዊ - መሲህን፣ ደካማ - ፖለቲከኛን፣ አድርባይን፣ አሻጥረኛን፣ አስመሳይ ተራማጅን የሚያውቅና የሚከስ፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዕውቀቱ ያለው ነው፡፡ “ሰርቆ የሚያውቅ፣ በምልክት ያሰራል” የሚለው የወላይትኛው ተረት ይሄው ነው፡፡   

ከ120 በላይ ኢትዮጵያውያን ከሊቢያ ይመለሳሉ

እስራኤል ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ 60ሺህ የሚጠጉ አፍሪካውያን ስደተኞችን ከሃገሯ እንደምታስወጣ ያስታወቀች ሲሆን በህገወጥ መንገድ በሊቢያ የሚኖሩ ከ120 በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ወደ ሃገራቸው ይመለሳሉ ተብሏል፡፡ የእስራኤል ካቢኔ ባለፈው እሁድ ስደተኞቹን የሚያስወጣ አዲስ ህግ ካፀደቀ በኋላ የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያዊን ኔትያሁ፣ ህገወጥ ስደተኞቹን ከሀገራቸው እንደሚያስወጡ አስታውቀዋል፡፡ የአገሪቱ ካቢኔ ባፀደቀው መመሪያ መሰረት እስራኤል በመጀመሪያው ዙር 4ሺ ስደተኞችን የምታስወጣ ሲሆን በቀጣይም በዘላቂነት ህገወጥ ስደተኞች ወደ ሀገሯ እንዳይገቡ በዘላቂነት ለመከላከል ከግብጽ የምትዋሰንበትን ድንበር ጥበቃ እንደምታጠናክር ገልፃለች፡፡ ከሀገሪቱ ይወጣሉ ተበለው የሚጠበቁት አብዛኞቸ ሱዳናውያንና ኤርትራውያን ሲሆኑ ኢትዮጵውያኑም የገፈቱ ቀማሽ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ወደ አውሮፓ ለመሻገር ሊቢያን ማረፊያ ያደረጉ ከ120 በላይ ኢትዮጵያውያን በግብጽ ካይሮ ባለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ትብብር የጉዞ ሰነዳቸው ተዘጋጅቶላቸው በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና በአለማቀፍ የስደተኞች ተቋም (IOM) ትብብር እንደሚመለሱ ታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በባህሬን በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ ትሠራ የነበረች ኢትዮጵያዊት በሶስት ወንዶች ተጠልፉ መደፈሯንና በሴተኛ አዳሪነት እንድትሰራ መገደዷን ገልፃ፤ ድርጊቱን ፈጽሟል የተባለውን ባንግላዲሻዊ እንደከሰሰች ሰሞኑን ተዘግቧል፡፡ የ28 አመቷ ኢትዮጵያዊት ቆሻሻ ለመድፋት ወደ ውጪ ስትወጣ ሁለት ማስክ ያጠለቁ ወንዶች አፍነው በመውሰድ አፓርታማ ቤት ውስጥ ከነበሩ አራት የተለያዩ አገራት ሴቶች ጋር በሴተኛ አዳሪነት እንድትሰራ መደረጓን ገልፃለች፡፡ በቀን አስር ጊዜ ያህል ከተለያዩ ወንዶች ጋር ወሲብ እንድትፈጽም ትገደድ እንደነበርም ለፍ/ቤት አስረድታለች፡፡

መልስ አልባ ጥያቄ መልስ እንዳለው ያውቃል
ምልእቲ ኪሮስ
ምስልሽን ለመሳል መች አልወጠርኩ ሸራ
ዓይንሽን ለማየት መች አጣኝ መከራ
የዓይንሽን ብሌን ቅንድብሽን አስታውሶ
የስዕልን ብሩሽ በፍቅር ቃል ለውሶ፤ ቀለም ማንጠባጠብ
በመውደድሽ ምትሀት በፍቅርሽ መተብተብ
ከዚያም ቀለም ማፍሰስ …….
ማፍሰስ … ማፍሰስ … ማፍሰስ …
በማፍቀር መ ኮ ፈ ስ!!
ከጠጉሮችሽ መሀል ገብቶ መንፈላሰስ
ድንገት ያምረኝና … ድንገት ያምረኝና
ከበድን ሸራዬ ጠጉር እስልና
ዕልመት እስልና
ከብርሀን ግንባርሽ፣ ከዕድሜ ቀጣይ ዓይንሽ፣ ድንገት እደርስና
ከጠጉርሽ ጥቁር ፅልማት ቀላቅዬ ብሌንሽን ቀባለሁ … ደሞ ፀልያለሁ
ጥቁርሽን ‘ሚያሳዬኝ ዓይኔን አጥፋ እላለሁ
ብሌንሽ ተቀባ ዳር ዳሩ ተኳለ
የእግዚሀር መልኩ ጠፋ
ከኔ ምስልሽ አለ ፊቴ ካለው ፊትሽ
ምስልሽ ሸራዬ ላይ ቡሩሼ ላይ ወዝሽ
ድምፅሽ ላይ ትዝታ … ድምጼ ላይ ስቅታ
ስቅታዬ ደስታሽ ሳጌ ደማቅ ሳቅሽ
ታዲያ እንዲ አይደል ስዕል?
ካንቺ እየተያዩ ቀለም መቀላቀል
ሰማያዊ ህብር ከቀዩ መቀየጥ
ከጥቁሩ ነክሮ ነጩ ላይ መገልበጥ
ከስዕል ሸራ ላይ ዓይንን ተክሎ ማደር
ኋላም መጮህ ማበድ በቀለማት መስከር
ማይታወቅ ቀለም እስኪመጣ ድረስ
አንዱን ካንዱ መድፋት እላዩ ላይ ማፍሰስ
በእጅ እያፈሱ ወደ ሰማይ መርጨት
ምስልሽን ሽቶ ከአምላክ መጋጨት
ጠያቂን መጠየቅ … ጥያቄን … ማስጨነቅ
የቆዳዋን አይነት ቀለም ደባልቄ
ይሄው ከትቤያለሁ ልቤ ውስጥ አርቅቄ
እንድትፈርድ እያት
የአንገቷን ጠረን በምን ልሳላት?
የማይተው ሆኖ ክፉ ዝቋን መግለጥ
እስኪ በል ንገረኝ ምን ከምን ልቀይጥ?
ከሸራዬ ሸራ የሷን ድምፅ መስማት
ምን ይሉት መቀደስ እንዴት ያለ ምትሀት
የዕድሜ ልክ እርግማን ሴት የመሳል ምክንያት!!!
መልስ አልባ ጥያቄ
ሀዘንተኛ ሳቄ
ያውም በኮሳሳ በደሳሳ ጎጆ
ከየዋህ አፍቃሪ ብርታቱን ኮርጆ
ሽንቁሩ በበዛ በተሰበረ በር
ከነብሴ ሚነጣ ውብ ሸራ መወጠር
ከደሜ ቀይ ቀለም ከላቤ ወዝ መንከር
ከድሜ እየቀነሱ እሷ ላይ መከመር
በነገረ ነብሷ ጠልቆ መመራመር
በቃል ኪዳን አስሮ ቀለማት ማጋባት
እ…ሰይ…!! ብዙ ብሎ ንግስናን መቀባት
ከዚያ … …
ከቆሙበት ብሩሾችን ማንሳት
እልባት እስኪገኝ ላመታት መረሳት
ከሸራው ምስልሽን ከምስልሽ ላይ አንቺን እያነቡ … መቅደድ
ወደ ማይታወቅ ወደ ሩቅ መስደድ
ቀለማት አርግዘው ቀለም እስኪወለድ
ምስልሽን ሚተካ፣ ዓይን ሚሞላ ውበት፣ በጣት የሚነካ፣ ህብር ቅኔ እስኪገኝ
ምስልሽና ነብስሽ ከሸራ እስኪገናኝ
ውበትሽን ሸርፌ አላጓድልሽም
እስከጊዜው ድረስ ተይኝ አልስልሽም!!!
…….//……

እኛ ተርፈናል፤ እዛ ላሉት ድረሱላቸው
ኢትዮጵያውያን ሴቶች ተገደው እየተደፈሩ ነው
እስር ቤት አንዲት ነፍሰ ጡር ሞታብናለች - የስደት ተመላሾች  

ሳኡዲ አረቢያ በህገወጥ መንገድ ወደ አገሯ የገቡ ስደተኞችን በሃይል ማስወጣት ከጀመረች ሁለተኛ ሳምንቷን ያስቆጠረች ሲሆን ህገወጥ ኢትዮጵያውያን ስደተኞችን ወደአገራቸው የመመለስ ዘመቻው አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ ዜጐችን ከሳኡዲ ለማምጣት ባለፈው ሳምንት በቀን ሰባት በረራዎች ይደረጉ እንደነበር ያስታወሱት የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፤ በዚህኛው ሳምንት በቀን 12 በረራዎች እየተደረጉ ዜጐችን ማምጣቱ እንደቀጠለና እስከትላንት ድረስ ከ19ሺ በላይ ዜጐች መመለሳቸውን ገልፀዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በቦሌ አየር ማረፍያ ተገኝተው ተመላሾቹን ያነጋገሩ ሲሆን፤ ስደተኞቹን ለማቋቋም ከክልል መንግስታት ጋር ውይይት ማድረጋቸውንም ገልፀዋል፡፡ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲን ጨምሮ ሁለት ሌሎች ቦታዎች ለስደተኞቹ በጊዜያዊ መጠለያነት እያገለገሉ እንደሆነም ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ከሶስት የሳኡዲ ተመላሾቹ ጋር ባደረገችው ቆይታ የስደት መከራቸውን እንደሚከተለው ነግረዋታል፡፡

“ኤምባሲያችን አይሰማም እንጂ ደጋግመን ነግረናል”
ራውዳ ጀማል ትባላለች፡፡ የሃያ ዓመት ወጣት ናት፡፡ ስለራስዋም ሆነ በሳኡዲ ስላሉ ኢትዮጵያውያን ወቅታዊ ሁኔታ ስታወራ እያለቀሰችና እየተወራጨች ነው፡፡ ለማነጋገር ስቀርባት “ወንድ ከሆናችሁ ጋዜጠኞች ነን፣ የህዝብ አፍ ነን ካላችሁ፤ እዚህ ተቀምጣችሁ፣ “ሁለት ሰው ሞተ” እያላችሁ ከምታቅራሩ ሳኡዲ ሂዱና በየቀኑ ሁለት ሶስት ሰው የሚሞትበትን እልቂት ተመልከቱ፣ “ሰዎቹን ምን እየሰራችሁ ነው?” ብላችሁም ጠይቁልን” አለችኝ። መቅረፀ ድምፄን ሶስት አራት ጊዜ ያስጠፋችኝ ቢሆንም በመጨረሻ ግን ለቃለ ምልልስ ፈቃደኛ ሆነችልኝ፡፡
ስንት ዓመት ቆይተሽ መምጣትሽ ነው?
ከሁለት ዓመት በኋላ ነው የመጣሁት፡፡ እስከ አስረኛ ክፍል የተማርኩት አዲስ አበባ ቢሆንም፤  የኮምቦልቻ ልጅ ነኝ፡፡
እንዴት ነበር የሄድሽው?
በፓስፖርት… በኮንትራት ነበር የሄድኩት … ካላስ! የሰውየው ልጆች ግን “የማይሆን” ፊልም ተመልከቺ እያሉ ያስቸግሩኝ ነበር፡፡ ሲመረኝ ጠፍቼ ወጣሁ፡፡ ከዚያም ከጓደኞቼ ጋር በነፃነት ቤት ተከራይተን እየኖርን፣ በ1800 ሪያል ተቀጥሬ መስራት ጀመርኩኝ፡፡ ቤተሰቤንም ገንዘብ እየላኩ እረዳ ነበር፡፡
ወደ አገርሽ እንዴት ተመለስሽ?
ውጡ ሲባል… ረብሻ ሲነሳ.. ጓደኞቻችን ሲሞቱ.. ሲደፈሩብን.. ‘ድሮም ስደተኛ ክብር የለውም’ ብዬ ተመልሼ መጣሁ..ከሚገሉኝ ከሚያበለሻሹኝ ብዬ እጄን ሰጠሁ፡፡ ብዙ ኢትዮጵውያኖች ችግር ላይ ናቸው.. እባካችሁ ድረሱላቸው፡፡ ብርዱም ፀሃዩም ሲፈራረቅባቸው.. ያሳዝናሉ፡፡ ብዙ ያልመጡ አሉ፤ መምጣት እየፈለጉ፡፡ ስቃይ ላይ ናቸው፡፡ እኔ አሁን አስራ ሶስት ቀን ታስሬ ነው የመጣሁት፡፡
እስቲ ስለ እስሩ ንገሪኝ …
ሁለት ቀን ያለ ምግብ ያለ ውሃ ነው የታሰርነው። ከዛ በኋላ ግን ጥሩ ምግብ ሰጥተውናል፣ ጥሩ መኝታም አግኝተናል፡፡ ብዙዎቹ ግን ከእኛ የባሰ ችግር ላይ ናቸው፡፡ መጠለያ ያላገኙ አሉ…ኤምባሲያችንም አይሰማም እንጂ ስንት ጊዜ ደውለን ተናግረናል መሰለሽ፡፡ ግን የሚሰማ የለም፡፡  
ከአገራችን ውጡ ካሉ በኋላ ትዕግስት ያጡና መልሰው ይዩዙናል፡፡ በዛን ጊዜ አበሻው፣ ሻንዛ/ጩቤ ይመዛል፡፡ ፖሊስ ራሱን ለማዳን ይተኩሳል። እኔ እንደውም ደህና ነኝ፤ እዛ ላሉት ድረሱላቸው። በምድረ ዱርዬ እየተደፈሩ ነው ያሉት /ለቅሶ/ ስንት ህፃናት አሉ የሚሞቱ፣ የሚታመሙ፡፡ ስንመጣ ደሞ፤ ሻንጣ  አትያዙ ተብለን ተመናጭቀን…በጥፊ ተመትተን..መከራችንን በልተናል፡፡
ወንዶችና ሴቶች ለብቻ ነበር የተቀመጣችሁት?
የተቀመጣችሁት አትበይ! የታሰራችሁት በይ፡፡ … የሴት እስር ቤት ለብቻው ነው በሴቶችና በህፃናት ለቅሶ የተሞላ ነው፡፡ እኔ ራሴ ስድስት ያበዱ ሴቶችን ይዤ መጥቻለሁ…/ለቅሶ/
አሁን ቤተሰብ እየጠበቅሽ ነው?
ነበረ ግን ሻንጣዬ ጠፋብኝ፡፡ በርግጥ ጤነኛ ሆኖ መምጣትም ቀላል አይደለም፡፡ እዛ ያሉትን ጥለናቸው ስንመጣ እያለቀስን ነው፡፡ እስር ቤቱ ውስጥ አንድ እርጉዝ ሞታብናለች፡፡ እዛው እስር ቤት እያለን ምጥዋ መጣ፤ ግን የህክምና እርዳታ ባለማግኘትዋ ሞተች፡፡
እስር ቤት ያሉት ምን ያህል ይሆናሉ?
ሰማኒያ ክፍል አለ..በየክፍሉ ስልሳ አምስት ስልሳ አምስት ሰው ነው ያለው፡፡ መካሲመሺ እስር ቤት ይባላል፡፡ የወንድና የሴት እስር ቤት የተራራቀ ነው፡፡ በጣም ረጅም ከመሆኑ የተነሳ በመኪና እንጂ በእግር  አይሞከርም፡፡ በአሁኑ ሰዓት በከተማው ያለው እስር ቤት ሞልቶ የመዝናኛና የስብሰባ አዳራሹን ሁሉ እስር ቤት አድርገውታል፡፡ የተደፈሩት የሞቱት..ሴቶች ብዙ ናቸው፡፡ አንዷን እርጉዝ ለሶስት ሲደፍሯት ሞታለች፡፡
የሌሎች አገር ስደተኞችም እየወጡ ነው ተብሏል…
አዎ፡፡ ኢትዮጵያዊው ከበደሉ ብዛት የተነሳ እየተናነቀው እኮ ነው ግጭቱ የሚከረው፡፡ ሚስቱንኧ እህቱን ከእጁ መንትፈው ሊወስዱበት ሲሉ ነው ጦርነት የሚነሳው፡፡ አበሻ ወንድ እየሞተ ያለው ‹‹ሴቶቻችንን አትንኩብን..›› ስለሚል እኮ ነው፡፡ ኤምባሲው ሊደርስላቸው ይገባል፡፡

“የሁለት ሰው መርዶ ይዤ መጥቻለሁ”
ስምሽ ማን ነው?
ፀጋ ኪዳኔ ገብረኪዳን
ምን እየጠበቅሽ ነው?
ዘመድ አለችኝ አዲስ አበባ የምትኖር፤ እስዋ እስክትመጣ እየጠበቅሁ ነው፡፡
ሳኡዲ ምን ያህል ጊዜ ቆየሽ?
ከአንድ ዓመት ቆይታ በኋላ ነው ከሪያድ/ሞንፋ የመጣሁት፡፡ ከኢትዮጵያ ስሄድ በኮንትራት ቢሆንም በባህር ከሄዱት ስደተኞች የተለየ ክብር አላገኘሁም፡፡ ጭቅጭቅ፣ ስድብና ድብደባ  ሲበዛብኝ ከተቀጠርኩበት ቤት በስምንተኛ ወሬ ወጥቼ ጠፋሁ፡፡ የሄድኩት ለአንድ ስራ ብቻ ተዋውዬ ነበር። የምተኛው ግን ከሁለት ሰዓት አይበልጥም ነበር፡፡ ሥራ ብቻ ነው 24 ሰዓት!
እስቲ ስለደረሰብሽ ችግር በዝርዝር ንገሪኝ..
በ700 ሪያድ ተቀጥሬ ነበር ከዚህ የሄድኩት፡፡ አሰሪዬ ቤት አራት ትላልቅ ወንድ ልጆች አሉዋት። የእህትዋ ልጆችም እዚያው ነው የሚኖሩት፡፡ ‹‹ወሲብ ካልፈፀምን..›› ብለው ያስቸግራሉ፡፡ በጣም ተሰቃየሁ፡፡ ከአቅሜ በላይ … ለህይወቴ በጣም አስፈሪ….ሲሆንብኝ ወጣሁ፡፡
ከአቅሜ በላይ ስትይ …
ልጆቹ ወሲብ ካልፈፀምን ብለው አሻፈረኝ ስላቸው፣ “በቢላ እናርድሻለን” እያሉ ያስፈራሩኝ ነበር፡፡ እምነቴን እንድቀይር ሁሉ ይፈልጋሉ። አፈር ድሜ በላሁ፡፡ ሰርቼ ለፍቼ … በዚያ ላይ ነፃነት አልነበረኝም፡፡ ወገቤ፣ ዓይኔ ታመመ፡፡ እነሱ እኮ ሃያ አራት ሰዓት እየበሉ እየጠጡ ነው፡፡ በዚያ ላይ በእጅሽ ላይ ስልክ ማየት አይፈልጉም፡፡ ሁሉ ነገር ሲያንገፈግፈኝ ሁለት ወር የሰራሁበትን ገንዘብ ጥዬ ወጣሁ፡፡ ከዛ ኤጀንሲው ለሌላ ሰው ሸጠኝ፤ በአስር ሺህ ሪያድ፡፡ እዚያም ግን  አልተመቸኝም። ስራው ሃያ አራት ሰዓት ነበር፡፡ አምስት ሰው እንኳን የማይችለው ስራ ነበር፡፡ አንድ ኩንታል ሊጥ አብኩቼ፣ ለሱቅ የሚሸጡት ብስኩት ጠብሼ፣ ሰባት መቶ ሪያል ነበር የሚከፈለኝ፡፡ ሁለት ወር ሙሉ እንደምንም ድምጼን አጥፍቼ ሰራሁ… በእንቅልፍ እጦት ልወድቅ እየተንገታገትኩ፡፡ እፊታቸው ላይ ግን ደስተኛ እመስል ነበር፡፡ ሰውነቴ እየመነመነ መጣ፡፡ ይሄኔ ድጋሚ ለመጥፋት ተዘጋጀሁ፡፡
“ለሌላ ሰው ሸጠኝ” ያልሽው … ኢትዮጵያዊ ነው?
/እንባዋ እየፈሰሰ/አረብ ነው፡፡ ወደ ሳኡዲ ከላከኝ ኤጄንሲ ጋር አብሮ ይሰራል፡፡ የረመዳን ጊዜ ደግሞ ሱቃቸው ወሰዱኝ፤ የአንድ ሰዓት መንገድ ተጉዞ ሌላ ቤት አላቸው፡፡ እዛ ይዘውኝ ሲሄዱ  ስራ ይቀልልኛል ብዬ ነበር፡፡ … ግን የባሰ ሆነብኝ፡፡ ለካ ጓደኞቻችን ወደው አይደለም ራሳቸውን የሚያጠፉት፤ አብደው ጨርቃቸውን ጥለው በየጎዳውና የወጡትና መንገዱ የወደቁት ... የወገብና የአእምሮ በሽተኞች የሆኑት? “ምነው እናቴ ስትወልጅኝ በመሃፀንሽ ውስጥ ደም ሆኜ በቀረሁ? እናቴ እባክሽ መልሰሽ ዋጪኝ” አልኩኝ፡፡ ራሴንና ቤተሰቤን ልረዳ ስንገታገት ከፊታቸው ድፍት ብል እኮ … እንደሰው ከቆጠሩኝ ... ሬሳዬን ለእናቴ ይልኩላት ይሆናል፡፡ ያለዚያ ግን የሀገራቸው መንግስት አውጥቶ ይቀብረኛል፡፡
ከዚያ ሁሉ በፊት ጠፍቼ መውጣት እንዳለብኝ አሰብኩ፡፡ አንድ ቀን ረመዳን ካፈጠሩ በኋላ ቤተሰቡ ተሰብስቦ ሊዝናኑ ወጡ፡፡ ደስ አለኝ፡፡ ቶሎ ብዬ የሴትየዋን ሙሉ ልብስ ለብሼ፣ ሽፍንፍን ብዬ ወጣሁ፡፡
ሻንጣ ምናምን ሳትይዢ?
ባዶ እጄን ነው የወጣሁት፡፡ የሰራሁበት ገንዘብ እንኳን በእጄ የለም፡፡ በቃ ዝም ብዬ ወጣሁ፡፡ ፓኪስታናዊ የታክሲ ሾፌር አገኘሁ፡፡ ‹‹ምን ሆንሽ?›› ብሎ ሲጠይቀኝ በዝርዝር ነገርኩት፤ አዘነ፡፡ ‹‹ሪያድ የሀበሻ ሃገር ነው፤ ብዙ ኢትዮጵያዊ አለ›› ብሎ እዛ (በነፃ) ወሰደኝ፡፡ ብዙ ኢትዮጵያውያን አገኘሁ፡፡
እዚያ መኖር ጀመርሽ ማለት ነው?
ሳያቸው በጣም ነው ያለቀስኩት፡፡ አገሬ የገባሁ ይመስል..መሬት ሁሉ ስሚያለሁ፡፡ ከኢትዮጵያ በባህር (በህገወጥ መንገድ) የመጡ ሴቶች ነበሩ። ከእነሱ ጋር አንድ ቤት በስድስት መቶ ሪያድ ለስድስት ወር ተከራይተን አብረን እየኖርን እንሰራ ጀመር፡፡
ቤቱን ለስንት ተከራያችሁ?
አስር ነበርን፡፡ ሁለት ወር እንደሰራሁ ግን በአካባቢው ግጭት ተነሳ፡፡ እግሬ አውጪኝ ብለን በየፊናችን ተበታተንን፡፡
ምን ዓይነት ግጭት?
መንግስት የሌለበት አገር ይመስል ጐረምሶች በር እያንኳኩ በሽጉጥ፣ በካራ፣ ሰው መግደል ጀመሩ፡፡ ስለዚህ ‹‹እጃችንን እንስጥ›› ብለን ተማከርን፡፡ ሌላው ችግር ፖሊስ፤ ትዳር መስርተው የሚኖሩትን የአበሻ ወንዶች እየወሰደ፣ ሴቶችን ለብቻቸው ይተዋቸው ነበር፡፡ በቤቱ ወንድ አለመኖሩን የተገነዘበ የአገሩ ዱርዬዎች (እንኳን ለአበሻው ለመንግስትም ልባቸው ያበጠ ነው) ሴትዋን ለአራትና ለአምስት እየሆኑ መድፈር ያዙ፡፡ ከእኛ ጎን የነበሩትን ሲያሰቃይዋቸው አይተናል፡፡ ወንዶቹን ፖሊስ ሲወስዳቸው ጎረምሶቹ ተከትለው ይገቡና ሴቶቹን መጫወቻ ያደርጓቸዋል/ለቅሶ/፡፡ አንድ ያየሁትን ልንገርሽ../ረጅም ትንፋሽ/እነዚህ ጐረምሶች…ሶስት ሴቶች ያሉበት ክፍል ውስጥ ገብተው ለሰባት ደፈሯቸው፡፡ /ማውራት አልቻለችም፤ ሳግና እንባዋ እያቋረጣት/..ከሶስቱ አንዷ የሰባት ወር ነፍሰጡር ነበረች፤ ሲገናኝዋት ሞተች፡፡ አንዷን ደግሞ ለሰባት ደፈሯትና ገድለው ጥለዋት ሊወጡ ሲሉ ሽርጣ/ፖሊስ መጣ፡፡ ከፖሊስ ጋር ተኩስ ገጥመው እርስ በርስ ተገዳደሉ፡፡ የሀበሻ ወንድ ከእህቱ ወይንም ከሚስቱ ሊለዩት ሲመጡ አልለይም ይልና ይገደላል፤ ይደበደባል … በቃ እልቂት ይሆናል፡፡ አዲስ አበባ ብለሽ ካራ ቆሬ እንደምትይው..ሪያድ ብለሽ ሞንፋ የሚባል አካባቢ በርካታ አበሾች ይኖራሉ፡፡ እኔ እንኳን የማውቀው … ከአምስት በላይ ሴቶች እንደተገደሉ ነው፡፡  መላ አካላቸውን ቆራርጠው ነው የጣሏቸው፡፡ ግን ይሄ ሁሉ መከራ ምን አድርገን ነው?
አንቺ እንዴት መጣሽ ወደ አገርሽ?
እጄን ሰጠኋ፡፡ አሰሪዬ ‹‹የት ልትሄጂ ነው?›› ብላ ስትጠይቀኝ፡፡ ‹‹አንድ ጓደኛዬ ልትወልድ ነውና ልጠይቃት ..›› ብዬ የሰራሁበትንም ሳልቀበል ወጣሁ፡፡ ምክንያቱም ብትገለኝስ ብዬ ፈራሁ፡፡ አብዛኛው አበሻ ከስራ ወደቤቱ ሲሄድ እየተያዘ ነው የሚመጣው፡፡ የሰራበትን የለፋበትን ሳይዝ ባዶ እጁን፡፡ እና እኛም ነገሩ ስላስፈራን እጃችንን ሰጠን። በቃ እኔም ወደ እዚህ መጣሁ፡፡
ዛሬ ላይ ሆነሽ ስታስቢው ወደዛ በመሄድሽ ምን ይሰማሻል?
መጀመሪያ ከዚህ ስሄድ በጣም ደስ ብሎኝ ነበር፤ የራሴንና የቤተሰቤን ህይወት ላሻሽል እንደሆነ ተስፋ በማድረግ፡፡ ከዛ በኋላ ግን  ከስራው ብዛት የተነሳ ከጥቅም ውጪ ልሆን ነው ብዬ እጅግ አምርሬ አለቅስ ነበር፡፡ በጣም ስጋት ያዘኝ፡፡ ግን ከሞት ተርፌ ወደዚህ ስመጣ አምላኬን አመሰገንኩ፡፡
ቤተሰብሽ መምጣትሽን አውቀዋል?
አላወቁም፡፡ ምን እያሰቡ ይሆን? ይሄን ሁሉ ነገር እየሰሙ፡፡ እናቴ መንገድ መንገድ እያየች ይሆናል፡፡ ደሞ ከእኛ አካባቢ ልጆች ብዙ የሞቱ አሉ፡፡..አሁን እኔ ራሴ የሁለት ሰው መርዶ ይዤ መጥቻለሁ፡፡ እናቴም ሰው ሲመጣ ‹‹ልጄን አይታችኋል?›› ትል ይሆናል፡፡ እኔስ መጣሁ..በረሃ ላይ ተደፍተው ለመምጣት ወረፋ እየተጠባበቁ ያሉ ህጻናትና ሴቶች ብዙ ናቸው፡፡ እዚህ የመጣነው እኮ ግማሽ አንሞላም፡፡ በሳኡዲ የኢትዮጵያውያን እንባ ያሳዝንሻል፡፡ ብዙዎቹ በሃዘን ላይ ናቸው፤ ድረሱላቸው፡፡


“ሰባት ያበዱ ሴቶችን አይቻለሁ”

ስምሽን ንገሪኝ..?
ሀያት አህመድ
እስቲ አካሄድሽን ንገሪኝ …
ከደሴ ነው በኤጀንሲ የሄድኩት፡፡ የምሰራው በጠለብ/በህጋዊ መንገድ ነበር፡፡ ሰዎቹ ሳይመቹኝ ሲቀሩ..ብዙ ጓደኞቻችን ችግር ሲደርስባቸው ሳይ፣ ስልካችንን ቀምተው ቤተሰቦቻችን በሃሳብ ሲያልቁ፣ እኔም ነገሩ ስላልተመቸኝ ጥዬ ጠፋሁ፡፡ ከዛም በሃጂና ኡምራ የሄድኩ አስመስዬ ተቀጥሬ መስራት ጀመርኩ፡፡
በጠለብ ስንት ጊዜ ሰራሽ?
ሶስት ወር ነው የሰራሁት፡፡
አሰሪዎችስ ቤት የሚደርስብሽ ችግር ምን ነበር?
በቤት ውስጥ ያሉ ወንዶች ያስቸግሩኝ ነበር፤ አስገድዶ ለመድፈር ይተናነቁኛል፡፡ አሰሪዬ በስራዬ  አትደሰትም፣ ያጠብኩትን ነገር እንደገና እጠቢ ትለኛለች፡፡
“የኢትዮጵያ ሰራተኞች ሞያ የላቸውም፣ “ሞዴስ እንኳን በአግባቡ መጠቀም አይችሉም፣ በዚያ ላይ ወንዶቻችንን ያባልጋሉ” የሚል ክስ ከሳኡዲ ሴቶች ይሰማል፡፡ አንቺ ምን ትያለሽ?
በጭራሽ! እኛ ደልቶን ይሄን ልናስብ? አንገታችንን ቀና አድርገን እንኳን ለመሄድ እንቸገራለን እኮ፡፡ እዛ ቦታ ላይ እኛን ብታይ ኢትዮጵያዊነት ያስጠላሻል፡፡ አለባበሳችን ምንድን ነው፣ ሁኔታችንስ፣ ኑሮዋችንስ..እኛ የእነሱን ባል የምናባልግ ምን አምሮብን፣ እንዴት ሆነን ነው?  እኛን እኮ ይጠየፉናል፡፡ በምን አንገታችን ቀና ብለን ነው የእነሱን ወንዶች የምናባልገው? እኛ እኮ ለህይወታችን እየሰጋን ነው… እያንዳንዷን ቀን የምናሳልፈው፡፡ በርግጥ የገጠር ልጆችም ይሄዳሉ። እንግዲህ በንፅህና የሚታሙት እነሱ ናቸው፡፡ ግን ስንቱን አእምሮውን አሳጡት…. ወይኔ!!..አሁን ስንመጣ እንኳን ጅዳ ኤርፖርት ውስጥ ሰባት ያበዱ ልጆችን አይቻለሁ፡፡ ‹‹ይዛችኋቸው ሂዱ›› ሲሉን ነበር፤ እንዴት አድርገን እንይዛቸዋለን? ጥለናቸው ነው የመጣን፡፡ አይ ዜጎቻችን! እየቀወሱ፣ እየተደፈሩ፣ እየተደበደቡ፣ እየተጣሉ ነው ሜዳ ላይ ….ተመልካች አጥተው፡፡
ጣትሽ ላይ የጋብቻ ቀለበት አያለሁ … ባለትዳር ነሽ?
ፈትቻለሁ፡፡ የአስር ዓመትና የስምንት ዓመት ልጆች አሉኝ፡፡ እነሱን ላሳድግ ብዬ ነው በሰው አገር የተንገላታሁት፡፡ ገንዘብ እልክ ነበር፡፡ ሆኖም እኔም አልተለወጥኩም፤ ለልጆቼም አልሞላልኝም፡፡ አንድ ጊዜ ሆድ ብሶኝ ራሴን ለማጥፋት ሞክሬ ነበር፡፡ ታውቂያለሽ… ልጆቼ በዓይን በዓይኔ መጡብኝና … ከድርጊቴ ታቀብኩ፡፡
አይኔ እንቅልፍ ካጣ ስንት ጊዜው ሆነ መሰለሽ… አይኔ ስር ጥቁር ብሎ የምታይው፣ የበለዘ የሚመስለው እኮ በእንቅልፍ እጦት የተፈጠረብኝ ነው፡፡ ጀርባዬን ያመኛል፡፡ ብዙ ሰዓት የምቆምበት እግሬንም እጅግ ታምሚያለሁ፡፡ አሁን ለትንሽ ጊዜ  ማገገም አለብኝ፡፡
ጂዳ ኤርፖርት ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት የሚጠባበቁ በርካታ ኢትዮጵያዊያን አሉ ይባላል…?
በጣም ብዙ እንጂ! ‘ኢትዮጵያዊ ሁሉ አገር ነቅሎ ነው እንዴ የወጣው ብዬ ተደንቄያለሁ፡፡ በጣም ያዘንኩት ግን ወደዚህ ስመጣ ኤርፖርት ሰባት ያበዱ ልጆች ስመለከት ነው፡፡ እዛ ያለው ኤምባሲያችን እንዴት  ወደ አገራቸው አይመልሳቸውም? ‹‹እህ›› ብሎ ችግራቸውን የሚያደምጣቸው ይፈልጋሉ፡፡ እስቲ አስቢው…ሰባት ሴቶች አብደው አይቻለሁ፤ በአይኔ በብረቱ፡፡ አንዷ ልጅዋ ሞታባት (በረሃብ ነው) የቀወሰችው፡፡ ስድስቱ ደግሞ በስራ ቦታቸው ቀውሰው፣ አሰሪዎቻቸው ናቸው አምጥተው የጣልዋቸው፡፡ የምናየው ነገር ሁሉ ለዓይን ይዘገንናል፡፡
ከዕረፍት በኋላ ምን  ልትሰሪ አቀድሽ…?
አሁን ጤንነት አይሰማኝም፤ ካገገምኩ በኋላ እንግዲህ … እንጃ ምን እንደምሰራ፡፡ አንድ ዓመት ከሶስት ወር ተቀምጬ ነው የመጣሁት፡፡ ከአስርና አስራ አምስት ዓመት በላይ የኖሩትም ‹‹ምንድነው የምንሰራው..›› የሚል ነው ጥያቄያቸው፡፡ ብዙ ጊዜ ኖረው ቢመጡም ምንም የያዙት ነገር የላቸውም፡፡ በጣም ያሳሰበኝ እሱ ነው፡፡
ከአሁን በኋላ ወደ ሳኡዲ የመመለስ ሃሳብ አለሽ?
አላህ ያውቃል፡፡    

ጥንት አንድ አዋቂ ሰው ነበር ይባላል፡፡ በመጪው ዓመት ምን እንደሚከተል ያውቃል አሉ፡፡ አንድ ቀን ንጉሡ የ አዋቂ መጥቶ መጪውን እንዲተነብይ ያስጠራውና ወደ ሸንጐ እየመጣ ሳለ፤ አንድ እባብ ያገኛል፡፡ “ንጉሡ ትንቢት ተናገር ብለውኛል፤ ምን ልበል?” አለና ጠየቀው፡፡ እባቡም፤
“መጪው ጊዜ ጦርነት ስለሆነ ፀልዩ! በላቸው” አለው፡፡
አዋቂው ሸንጐ ቀርቦ እባቡ እንዳለው፤ ለንጉሡ ተናገረ፡፡ “ያለው ዕውነት ነው” አሉና ንጉሡ ሸልመው ሸኙት፡፡ አዋቂው ወደቤቱ ሲመለስ ያን እባብ አገኘው፡፡ በጦሩ ወጋውና መንገዱን ቀጠለ፡፡
በሁለተኛው ዓመት እንደገና ንጉሡ አዋቂውን አስጠሩት፡፡ እዚያው ቦታ የቆሰለውን እባብ አገኘው፡፡
እባቡም፤ “ባለፈው ዓመት መጪው ጊዜ ምን እንደሚመስል ጠይቀኸኝ፤ ነግሬህ፣ ወግተኸኝ ሄድክ፡፡ ሆኖም አሁንም እነግርሃለሁ፡፡ ይህ ዓመት የበሽታ ዓመት ነውና ፀልዩ በላቸው” አለው፡፡
አዋቂው ወደ ሸንጐ ሄደና የበሽታ ዓመት እንደሚሆን ተናገረ፡፡ ንጉሡም “ባለፈው ዓመት የተናገረው ዕውነት ስለሆነ ዘንድሮም የተናገረው ዕውነት መሆን አለበት፡፡ በሉ፤ ሸልሙና ሸኙት” አሉ፡፡
አዋቂው ሲመለስ ያንን እባብ አገኘው፡፡ በድንጋይ መትቶ ወግሮ ወግሮ መንገዱን ቀጠለ፡፡
በሶስተኛው ዓመት እንዲሁ አዋቂው ሸንጐ ተጠራና ሄደ፡፡ መንገዱ ላይ እዛው ቦታ እባቡን አገኘው፡፡
“ዘንድሮስ ምን ብል ይሻለኛል?” አለው፡፡
“ባለፈው ዓመት መክሬህ፣ ተናግረህ፣ ተሸልመህ ስትመለስ በድንጋይ መትተኸኛል፡፡ ሆኖም አልተቀየምኩህም፡፡ በዚህ ዓመት የእሳት ዘመን ነውና ፀልዩ በላቸው” አለው፡፡
ወደንጉሱ ሄዶ “ዘንድሮ የእሳት ዘመን ነው” አላቸው፡፡
ንጉሡም፤ “ባለፉት ሁለት ዓመታት የተናገረው ዕውነት ስለሆነ፤ ዘንድሮም ያለው ዕውነት መሆን አለበት፡፡ ሸልሙትና ይሂድ” አሉ፡፡
አዋቂው ሲመለስ እባቡን አገኘው፡፡ አሁን ግን መምታት ሳይሆን በእባብ ሊያቃጥለው ሞከረና መንገዱን ቀጠለ፡፡
በቀጣዩ ዓመት ለአራተኛ ጊዜ ንጉሡ አስጠራው፡፡ አዋቂው መንገዱ ላይ እባቡን አገኘው፤
“ዘንድሮስ ምን ልበል?” አለው፡፡
እባቡም፤ “ዘንድሮ የጥጋብ ዘመን ስለሆነ ፈንድቁ! በላቸው” አለው፡፡
ንጉሡ የጥጋብ ዘመን መሆኑን ሲሰሙ “እስከዛሬ የተናገረው ምንም መሬት ጠብ የሚል ነገር አልነበረውም፡፡ ዘንድሮም ዕውነት ስለሚሆን በርከት አድርጋችሁ ሸልሙልኝ” አሉ፡፡
አዋቂው ወደቤቱ ሲመለስ እባቡን አገኘው፡፡ በዚህ ጊዜ ግን በሀር የተንቆጠቆጠ ካባ አለበሰው፡፡
እባቡም፤
“የመጀመሪያው ዓመት የፍልሚያ ዘመን ነበረና በጦር ወጋኸኝ፡፡
በሁለተኛው ዓመት የበሽታ ዘመን ነበረና በድንጋይ ወገርከኝ፡፡
በሦስተኛው ዓመት የእሳት ዘመን ነበረና በእሳት አቃጠልከኝ፡፡
በአራተኛው ዓመት ግን የጥጋብ ዘመን በመሆኑ ካባ አለበስከኝ፡፡ እነሆ ጥበቤን ሁሉ ሰጥቼሃለሁ፡፡ ያ ይበቃሃል፡፡ አሁን ካባህን መልሰህ ውሰድ፡፡ የሰጠሁህ ጥበብ ከምንም ነገር በላይ ነው፡፡ ጥበቤን ሁሉ ውሰድ፡፡ ራሴ የነገርኩህን የነገ ዕጣ - ፈንታ፤ ራሴውም መጋራት ስላለብኝ ነው ያልተበቀልኩህ! በምንም ቁሳቁስ ልትተካው አትሞክር”  
                                                        *   *   *
ዕጣ-ፈንታችንን አናመልጥም፡፡ የዕጣ-ፈንታችን አካል ነን፡፡ የምንለው፣ የምናቅደው፣ የምንራዕየው ሁሉ የእኛው አካል ነው፡፡ በተናገርነው እንነገርበታለን፡፡ በደነገግነው እንቀጣበታለን፡፡ በደሰኮርነው እናፍርበታለን ወይም እንኮራበታለን፡፡ በተለይ መንግስት ስንሆን ባወጣነው ህግ እከሌ ከእከሌ ሳንል፣ ወገናዊና ኢፍትሐዊ ባልሆነ መንገድ መተዳደርና መቀጣት አለብን፡፡
የመንግሥትነታችን ትልቅ ቁም ነገር የህዝብን ደህንነትና የሀገርን ህልውና መታደግ ነው፡፡ ይህ ዋና ኃላፊነት ነው፡፡ ህዝብ እንዳይሸበር፣ እንዳይጠራጠር፣ ዕምነት እንዳያጣ ማድረግ፤ በአገሩ፣ በመንግሥቱና በኃላፊዎቹ ላይ የመተማመን ስሜት እንዲያድርበት ያደርገዋል፡፡  
“የመንግሥት መኖር ዓላማው የህብረተሰቡን የተለያዩ ፍላጐቶች ለማርካት፣ አገርን ለማጠንከር መሆን አለበት፡፡ መንግሥታዊ ህጐችና ተቋሞቹም ዘለዓለማዊ ሳይሆኑ ይህንኑ ማህበራዊ ፍላጐት ለማስገኘት ሲባል ከህብረተሰቡ ዕድገት ጋር አብረው የሚያድጉና የሚለወጡ መሆን አለባቸው፡፡ ይህ ካልሆነ ድህነት፣ ሰብአዊ ጉስቁልና፣ ሀዘንና ሰላም - የለሽነት ይቆራኘውና ለውድቀት ይዳረጋል” ይለናል የጥንቱ፣ የታህሣሥ 1953ቱ ንቅናቄ ተዋናይ፤ ግርማሜ ነዋይ (የታህሣሡ ግርግርና መዘዙ)
የህዝብን ችግር ቸል አንበል፡፡ የኋላ ኋላ ጣጣው ይመለከተናልና!
ለትናንሽ የኢኮኖሚ ችግሮች መፍትሔ ሳንሰጥ ወደ ውስብስብና ግዙፍ ችግርነት እንዲያድጉ ከፈቀድንና ቸልታችን ከበዛ፤ ያለ ጥርጥር ወደ ፖለቲካዊ ችግርነት ማደጋቸው አይቀሬ ነው፡፡
የወሎ ረሃብ እንደተነናቀ ወደ አብታዊ ማዕበልነት ተለወጠ፡፡ የሚሊተሪ ዲክታተራዊ አገዛዝ መናጠጥ፣ የቢሮክራሲያዊ በደል ማጠጥ፣ የሥልጣን መባለግና ያላግባብ መበልፀግ የአማጽያንን መፈልፈልና የተቃዋሚን ቁርጠኝነት መውለዱን ወለደ፡፡
ዛሬም የህዝብን ኑሮና የሀገርን ውስብስብ ችግሮች በወቅቱ የመፍታት ቅን ልቦና ከሌለ ዕጣ- ፈንታ ወዳዘዘው ውድቀት ማምራት ግድ ይሆናል፡፡ በዚህ ጉዳይ የመንግሥት ዋንኛ ትኩረት የአንበሳውን ድርሻ ይውሰድ እንጂ የተለያዩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማህበራትና ኃላፊነት የሚሰማቸው ዜጐች ወዘተ የነገዋ አገራችን ዕጣ-ፈንታ ይመለከተናል ማለት ኤጭ የማይባል ነገር መሆኑን ልብ ማለት ደግ ነው!
“የህዝብ ችግር እየተባባሰ በሄደ ቁጥር፤ ኃላፊነት የሚሰማው ሰው እያወቀ እንዳላወቀ፣ እያየ እንዳላየ፣ በዝምታ መኖሩ ከባድ የህሊና ሸክምና ፈታኝ ጥያቄ ነው” ይላል ጄኔራል (መንግሥቱ ነዋይ፡፡)  
አቶ ብርሃኑ አስረስ “ማን ይናገር የነበረ…የታህሣሡ ግርግርና መዘዙ” በተባለው መጽሐፋቸው፤ ህዝብ ጭቆና ሲያንገፈግፈው ስለሚደርስበት ደረጃ ሲናገሩ፤
“የሕዝብን መነሳሳት ለማፍራት ብዙ ሙከራ ተደርጐ ነበር፡፡ ነገር ግን፣ ቀፎው ተነክቶበት የተሸበረ ንብና ተስፋውን ጨርሶ የተነሳ ሕዝብ ተመሳሳይ በመሆኑ፤ የተፈፀመው ሙከራ ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ወደ ድሮው ተገዥነት ቦታው ለመመለስ አልቻለም…” ይሉናል፡፡
የአስተዳደር ብስለታችን፣ የዲፕሎማሲያችን ጥራት፣ ስለፓርቲና ስለ ሀገር ያለን ግንዛቤ፤ የምንመራውን ህዝብ አመኔታና ተቀባይነት የሚያስገኘው ቁልፍ ነገር መሆኑን መቼም ቢሆን መቼም እንወቅ፡፡ የህዝብን የልብ ትርታ፣ የሀገር ወዳዶችንና ውጪ ያሉ ኢትዮጵያውያንን ድምጽ እንደገዝጋዡ ሳይሆን እንደ አጋዡ በማየት ማግባባት፣ ማስማማት፣ ማደራደር ከመሪዎቻችን የሚጠበቅ የብልህ እርምጃ ነው፡፡ ያለድካ


በፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ ከሌሎች ባለስልጣናትና ባለሃብቶች ጋር በመጀመሪያ ተጠሪነት በሶስት መዝገቦች የተከሰሱት አቶ መላኩ ፈንታ ከሚኒስትርነታቸው ጋር ተያይዞ ለተነሣው ጥያቄ ፍርድ ቤቱ ረቡዕ እለት የህገ መንግስት ትርጉም ያስፈልገዋል ሲል ብይን ሠጥቷል፡፡
ቀደም ሲል ሠኞ ህዳር 9 ቀን 2006 ዓ.ም በዋለው ችሎት፣ አቶ መላኩ ፈንታ ባቀረቡት መከራከሪያ፣ በሚኒስትር ማዕረግ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል መሆናቸውን በማስረዳት ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍርድ ቤት ሊታይ እንደሚገባ የገለፁ ሲሆን አቃቤ ህግ በጉዳዩ ላይ በሠጠው አስተያየት፤ ተከሣሹ በእርግጥም በሚኒስትር ማዕረግ የሚኒስትሮች ም/ቤት አባል መሆናቸውን ተቀብሎ፣ ነገር ግን የሚመሩት መስሪያ ቤት ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ባለመሆኑ፣ ተጠቃሹ ያላቸው የሚኒስትር ማዕረግነት ለጥቅማ ጥቅም አላማ ብቻ የሚያገለግል እንደሆነ አስረድቷል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው ፍ/ቤቱም ጉዳዩን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለረቡዕ ህዳር 11 ቀን 2006 ቀጠሮ የሠጠ ሲሆን ረቡዕ እለት የዋለው ችሎትም መዝገቡ የተቀጠረው በፍርድ ቤቱ የቀረበውን ጉዳይ ከማየት ስልጣን ጋር ተያይዞ በተነሣው ጭብጥ ላይ ብይንና ትዕዛዝ ለመስጠት መሆኑን አስታውቆ ብይን ሠጥቷል፡፡
ፍ/ቤቱ ጉዳዩን የማየት ስልጣን ያለው የትኛው ፍ/ቤት ነው የሚለው ሣይረጋገጥ ወደ ክርክር መግባት አይቻልም ካለ በኋላ፣ በተነሣው መከራከሪያ ጭብጥ መሠረት፣ አቶ መላኩ ሚኒስትር ናቸው ወይስ አይደሉም? ሚኒስትር ከሆኑስ ጉዳዩን አከራክሮ የመወሠን ስልጣን ያለው የትኛው ፍ/ቤት ነው የሚለው የግድ እልባት ማግኘት አለበት ብሏል።
ፍ/ቤቱም አቶ መላኩ ፈንታ በሚኒስትር ማዕረግ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል መሆናቸውን ከግራ ቀኙ ክርክር እና ከተለያዩ ሠነዶች ማረጋገጡን በብያኔው አስታውቆ፤ ይህ ከሆነ ደግሞ በፌደራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ እና በተሻሻለው የፀረ ሙስና ልዩ የስነ ስርአትና የማስረጃ ህግ አዋጅ መሠረት፤ የፌደራል መንግስቱ ባለስልጣናት (ሚኒስትሮች ጨምሮ) በስራ ሃላፊነታቸው ምክንያት ተጠያቂ በሚሆኑባቸው ሙስናን ጨምሮ ማናቸውም የወንጀል ጉዳዮች የፌደራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት የመጀመሪያ ደረጃ የስረ-ነገር ስልጣን የተሰጠው መሆኑ በግልፅ ስለ ደነገገ፣ ጉዳዩን የማየት ስልጣን የፌደራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ነው ብሏል፡፡ ነገር ግን የእነዚህ ሁለት አዋጆች ሁለት ንኡስ አንቀፆች ህገ-መንግስታዊ ናቸው? አይደሉም? የሚለው ትርጉም የሚያስፈልገው ጉዳይ ነው ብሏል - ፍ/ቤቱ፡፡
በተለይ የአቶ መላኩ ጉዳይ በፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሚታይ ከሆነ፣ በህገ መንግስቱ የተከበረላቸውን መሠረታዊ ጉዳያቸውን በይግባኝ እንዲታይ የማቅረብ መብት በግልፅ የሚጋፋ መሆኑን ያመላከተው የፍ/ቤቱ ብይን፤ አቶ መላኩ በዋና ወንጀል አድራጊነት ከሌሎች ሠዎች ጋር ተጣምሮ የወንጀል ክስ የቀረበባቸው በመሆኑና የሁሉም ተከሣሾች ጉዳይ በፌደራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ቢታይ ሁሉም ተከሣሾች በህገ መንግስቱ የተከበረውን የይግባኝ ጉዳይ የማቅረብ መብት በግልፅ የሚጋፋ ከመሆኑም ሌላ የአቶ መላኩ ጉዳይ ብቻውን ተነጥሎ በፌደራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲሁም ከእሣቸው ጋር የተከሠሡት ሌሎች ተከሣሾች ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ተነጥሎ ይታይ ቢባል ደግሞ ሁሉም ሠዎች በህግ ፊት እኩል ናቸው፤ በመካከላቸውም ማናቸውም አይነት ልዩነት ሣይደረግ በህግ እኩል ጥበቃ ይደረግላቸዋል ከሚለው የህገ መንግስቱ አንቀፅ 25 መሠረታዊ መርህ ጋር አብሮ የማይሄድ መሆኑን ፍ/ቤቱ በብይኑ አትቷል፡፡ ይሄ ማለት፣ አቶ መላኩ በጠቅላይ ፍ/ቤት ጉዳያቸው ይታይ ቢባልና ሌሎች ተከሣሾች ተነጥለው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ጉዳያቸው ይታይ ቢባል፣ ሌሎች ይግባኝ የመጠየቅ መብታቸው ሲከበርላቸው፣ አቶ መላኩ የይግባኝ መብት እንዳይጠቀሙ የሚከለክል ይሆናል፡፡ የአቶ መላኩም ሆነ የሌሎች ተከሣሾች ሠብአዊ መብት በእኩል እንዲጠበቅ አከራካሪው ጉዳይ የህገ-መንግስት ትርጉም ያስፈልገዋል ብሏል፡፡ በዚህ መሠረት የህገ መንግስታዊ ክርክር ጉዳይ ሲነሣ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሣኔ ሊያገኝ የሚገባ በመሆኑ፣ የህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ፣ ህገ-መንግስታዊ ጉዳዮች የማጣራት ሃላፊነት የተጣለበት በመሆኑና የፌደራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ እና የተሻሻለው የፀረ ሙስና ልዩ የስነ ስርአትና የማስረጃ ህግ አዋጅ ከህገ መንግስቱ አንቀፅ 20(6)፣ አንቀፅ 25፣ አንቀፅ 10 እና አንቀፅ 13(1) ይቃረናሉ ወይስ አይቃረኑም? እንዲሁም የስረ ነገሩ ስልጣን የየትኛው ፍ/ቤት ነው? የሚለውን እንዲመረምርና ትርጉም እንዲሠጠው ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ ጉዳዩ ሊመረመር እንደሚገባ በማመን፣ የህገ መንግስት ትርጉም ያስፈልገዋል በማለት ፍ/ቤቱ በይኗል፡፡
ፍ/ቤቱ በሠጠው ትዕዛዝም የብይኑ ትዕዛዝ ግልባጭ በመሸኛ ለፌደሬሽን ም/ቤት ፅ/ቤት እና የህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ፅ/ቤት በእለቱ እንዲላክ በማለት ለታህሣስ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡
በፍ/ቤቱ ብይንና ትዕዛዝ ዙሪያ የህግ ትንታኔ እንዲሠጡን ያነጋገርናቸው ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ምሁራን፤ እንዲህ አይነቱ ብይን ከዚህ ቀደም በእነ አቶ ታምራት ላይኔ እና አቶ ስዬ አብርሃ ላይ ተግባራዊ ተደርጐ እንደነበር በመጠቆም፣ ፍ/ቤቱ ህገ መንግስታዊ ትርጉም ያስፈልጋቸዋል የሚላቸውን ጉዳዮች በራሱ ከመወሠኑ በፊት ለሚመለከተው አካል መምራቱ ተገቢ ነው ብለዋል።  

የአውሮፓ ህብረት 5.3 ቢሊዮን ብር የልማት እርዳታ ለኢትዮጵያ የሰጠ ሲሆን፤  የልማት እርዳታው ኢትዮጵያ ለምታካሂደው መጠነ ሰፊ የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ የትምህርት የጤናና መሰል መሰረታዊ አገልግሎቶች ግንባታና ጥበቃ፣ለድርቅ መከላከያና መቋቋሚያ እንዲሁም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ለምታደርጋቸው የልማት እንቅስቃሴዎች ማስፋፊያ የሚውል እንደሆነ ታውቋል፡፡
ከህብረቱ የኢትዮጵያ ልዑክ ፅ/ቤት የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ከተሰጠው የ5.3 ቢሊዮን ብር የልማት እርዳታ ውስጥ 1.8 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ኢትዮጵያ ለምታካሂደው መጠነ ሰፊ የመንገድ መሰረተ ልማት ግንባታ ሲውል፣ አንድ ቢሊዮን ብር ደግሞ ድርቅን ለመከላከልና ለመቋቋም ለሚደረገው የልማት እንቅስቃሴ የሚውል ነው፡፡ የተቀረው ገንዘብ ደግሞ ለጤና፣ለትምህርትና መሰል መሰረታዊ አገልግሎቶች ግንባታና ጥበቃ እንዲሁም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንደሚውል ታውቋል፡፡ የልማት እርዳታው ስምምነት የአውሮፓ ኮሚሽን የልማት ኮሚሽነር አንድሪስ ፒባልግስና በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ደኤታ አቶ አህመድ ሽዴ መካከል የፊታችን ሰኞ ይፈረማል ተብሎ እንደሚጠበቅ ከጽ/ቤቱ የተገኘው መረጃ ይጠቁማል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ግንባር ቀደም ከሆኑት የኢትዮጵያ የልማት አጋሮች መካከል ዋነኛው ሲሆን የህብረቱና የኢትዮጵያ የልማት ትብብር ከተመሠረተበት እ.ኤ.አ ከ1975 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ የልማት እንቅስቃሴ በገንዘብና በቴክኒክ ሲረዳ መቆየቱ ይታወቃል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ ካዛንቺስ እምብርቱ ላይ ከአፍሪካ ኢኮኖሚክስ ኮሚሽን ፊት ለፊት በ700 ሚሊዮን ብር የተሠራው ባለ 5 ኮከብ ዘመናዊ ኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ዛሬ ይመረቃል፡፡
አቶ ገምሹ በየነ የተባሉ ባለሀብት ግዙፍ ኢንቨስትመንት የሆነው ባለ 10 ፎቅ መንትያ ሆቴል፤ 154 ክፍሎች ሲኖሩት የዘመኑ ቴክኖሎጂ ያፈራው መሳሪያ የተገጠሙለት መሆኑ ታውቋል፡፡
ኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ ሁለት ፕሬዚዴንሻል ክፍሎችና 16 ጁንየር ሱት፣ ስታንዳርድ፣ ኪንግ ሳይዝ፣ ደብል ትዊን፣ ፔንት ሃውስ ክፍሎች፣ አሉት፡፡ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ሬስቶራንትና ባር፣ የሕፃናት መጫወቻ፣ የወጣቶች የኦሎምፒክ ደረጃ መዋኛ፣ ስፓና ጂምናዚየም…አለው፡፡
ሆቴሉ 10ኛ ፎቅ ፕሬዚዴንሻል ሱት ላይ ሆነው በሁሉም አቅጣጫ ከተማዋን እየቃኙ ለመዝናናት ያመቻል፡፡ ቀልብን የሚስቡት የመኝታ ክፍሎቹ፤ መታጠቢያ ገንዳና ሻወር፣ ብሮድ ባንድ ኢንተርኔት፣ 42 ኢንች ቴሌቪዥን ሳተላይት ቲቪና ስልክ፣…አላቸው፡፡
ኢሊሌ ሆቴል ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ዲፕሎማቶች፣ ኢንቨስተሮች፣ የሃይማኖት አባቶችና፣ ታዋቂ ሰዎች በተገኙበት ዛሬ እኩለ ቀን ላይ በይፋ ተመርቆ አገልግሎት እንደሚጀምር ተገልጿል፡፡
ሆቴሉ፣ በአሁኑ ወቅት ለ300 ሠራተኞች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን፤ በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር የሠራተኞቹ ቁጥር 450 እንደሚደርስ የሆቴሉ ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ ገልፀዋል፡፡