Administrator

Administrator

የፍትሕ ሚኒስቴር የሙስና ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ አቶ አብነትገ/መስቀል እና 3 የመሬት አስተዳደር ሰራተኞችን ጨምሮ በአምስት ግለሰቦች ላይ የሙስና ወንጀል ክስ መስርቷል።
 
አቶ አብነት ገ/መስቀል በቂርቆስ ክ/ከ ወረዳ 2 የሚገኘውን ከሼክ አላሙዲን መሀመድ ጋር የጋራ ንብረታቸው የሆነውን የ1 ሺህ 971 ካሬ ሜትር ይዞታ በ83 ሚሊየን ብር በመሸጥ ለግል ጥቅም አውለዋል በሚል በተጠረጠሩበት ወንጀል በጊዜ ቀጠሮ ችሎት ሲቀርቡ እንደነበር አና ዐቃቤ ሕግ ከፌዴራል ፖሊስ የተረከበውን የምርመራ መዝገቡን ተመልክቶ ክስ ለመመስረት የ15 ቀን ይሰጠኝ ብሎ መጠየቁን ተከትሎ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት ክስ የመመስረቻ ጊዜውን ለዐቃቤ ሕግ መፍቀዱን መዘገባችን ይታወሳል።
 
ይሁንና ዐቃቤ ሕግ ከተፈቀደለት የክስ መመስረቻ ጊዜ አስቀድሞ ዛሬ አቶ አብነትን ጨምሮ በአምስት ግለሰቦች ላይ የሙስና ወንጀል ክስ መስርቷል።
ክሱ የቀረበለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ክሱን ለመመልከት ለፊታችን ዓርብ ቀጠሮ ይዟል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አቶ አብነት ገ/መስቀል ባሳለፍነው 2015 ዓ.ም በ2 ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት የቦሌ ታወር ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ጅምር ግንባታ ያለበት 3 ሺህ 383 ካሬ ሜትር ይዞታን ያለአግባብ ባለመብት በመሆን ይዞታው ላይ ካርታ በማውጣት ከ321 ሚሊየን ብር በላይ እንዲሸጥ አድርገዋል ተብለው ከሌሎች ከመሬት አስተዳደር ሰራተኞች ጋር ተከሰው ነበር።
 
ይሁንና በአቶ አብነት ላይ ቀርበውባቸው ከነበሩ ሶስት ክሶች መካከል ሁለቱ ክሶች በችሎቱ ዳኛ ከአንድ ሳምንት በፊት እንዲቋረጡ ተደርገዋል።
(ኤፍ ቢ ሲ)

የውጭ ሀገር ገንዘቦችን በማተም እና የተለያዩ ማዕድኖችን በመያዝ ወንጀል የተከሰሱት የፀሐይ ሪል ስቴት ጀነራል ማናጀርን ጨምሮ 9 የውጭ ሀገር ዜጎች ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደረገ።

ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የዋስትና ጥያቄና የዐቃቤ ሕግ የመቃወሚያ ክርክሮችን መርምሮ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ ያደረገው።

የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ ያደረገው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ልደታ ምድብ 8ኛ የገቢዎችና ጉሙሩክ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው።

በቀረበባቸው ተደራራቢ ክስ ላይ የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ከተደረገባቸው ተከሳሾች መካከል የፀሐይ የሪል ስቴት መስራች፣ ባለድርሻ እና ስራ አስኪያጅ ቺያን ኩዊን ጨምሮ ዘጠኝ የውጭ ሀገር ዜጋ የሆኑ ተከሳሾች ናቸው።

የፍትህ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ የወንጀል ተሳትፎ ጠቅሶ ተደራራቢ ሰባት ክሶችን በየድርሻቸው አቅርቦባቸው ነበር።

በተለይም ባቀረበው በ1ኛ ክስ ላይ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ተከሳሾች ላይ ብቻ በቀረበው ክስ ላይ እንደተመላከተው የወንጀል ህግ አንቀፅ 32 ንዑስ ቁጥር 1/ሀ እና አንቀጽ 356 ላይ የተደነገገውን በመተላለፍ ተከሳሾቹ ፀሀይ ሪል ስቴት ኃ/የተ/የግ/ማህበር ውስጥ 11ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው ቤት ውስጥ ከነሃሴ 24 ቀን 2015 ዓ. ም እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ሀሰተኛ ገንዘብ ለመስራት የሚያገለግሉ መሳሪያዎች፣ የተለያዩ ኬሚካሎች እና ወረቀቶች በመጠቀም ሀሰተኛ የአሜሪካ ዶላር፣ ዩሮ፣ የእንግሊዝ ፓውንድ፣ የቻይና ይዋን እና የሌሎች የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦችን አመሳስለው በማተም ላይ እያሉ እጅ ከፍንጅ ተይዘዋል የሚል ክስ ቀርቧል።

በሁለተኛው ክስ ደግሞ የወንጀል ህጉ አንቀፅ 32/ንዑስ ቁጥር 1/ሀ እናአንቀጽ 371 ንዑስ ቁጥር 2 ላይ የተደነገገውን በመተላለፍ፣ በሚኖሩበት ቤት ውስጥ ገንዘቦች ለመስራት የሚያገለግሉ፣ 2 የብር ማተሚያ ማሽን እና የተለያዩ ኬሚካሎች ማለትም በጀሪካን፣ በጠርሙስ፣ በብልቃጥ እና በበርሜል ባለ 500 ኖት ሀሰተኛ ዩሮ ለመስራት የተዘጋጀ 60 ሚሊየን 750 ሺህ ብር የሚገመት ነጭ ወረቀት ብዛት በነጠላ 121 ሺህ 500 ዩሮ እና 42 ሚሊየን 400 ሺህ ዶላር የሚገመት ሀሰተኛ ዶላር ለመስራት የተዘጋጀ ባለ 100 ኖት 424 ሺህ አረንጓዴ ወረቀት የተገኘባቸው መሆኑን ዐቃቤ ህግ ጠቅሷል።

በተጨማሪም 16 ሚሊየን 150 ሺህ የሚገመት ነጭ የዶላር ወረቀት፣ የተለያየ ነጭ ዱቄት፣ አንዱ እሽግ በውስጡ 500 ወረቀት የያዘ 32 እሽግ በብር ቅርፅ የተቆራረጡ ወረቀቶች፣ በአልሙንየም የተጠቀለለ በገንዘብ ቅርፅ የተቆረጠ ጥቁር ቀለም ያለው ወረቀት፣ 28 እሽግ አንዱ 500 የያዘ የገንዘብ መስሪያ ወረቀት፣ እንዲሁም ገንዘብ ለመስራት የሚያገለግሉ መስሪያና መሳርያዎች ይዘው በፀጥታ አካላት በተደረገ ክትትል ይዘውት የተገኙ መሆኑን ዐቃቤ ሕግ ጠቅሶ ሀሰተኛ ነገሮችን ለመስራት የሚያገለግሉ መስሪያ እና መሳሪያዎች መያዝ ወንጀል ክስ አቅርቦባቸዋል።

3ኛ ክስ ደግሞ በ1ኛ ተከሳሸ ላይ ብቻ የቀረበ ሲሆን÷ በዚህም የወንጀል ህግ አንቀፅ 359 ስር የተደነገገውን በመተላለፍ በጳጉሜን 1 ቀን 2015 ዓ.ም በተደረገው ፍተሻ ሀሰተኛ የሆኑ ባለ 100 የገንዘብ ብዛቱ 297 ሺህ 400 የአሜሪካ ዶላር፣ ባለ 50 የገንዘብ ብዛቱ 36 ሺህ 250 የእንግሊዝ ፓውንድ፣ ባለ 500 ዩሮ 62 ሺህ የሆነ፣ እና ባለ 200፣ 650 ሺህ 600 ዩሮ፣ እንዲሁም ባለ 1 ሺህ 567 የቻይና ዩዋን ይዞ የተገኘ መሆኑ ተጠቅሶ ተከሳሹ ላይ ሀሰተኛ ገንዘብ ይዞ መገኘት ወንጀል ክስ ቀርቧል።

በሌላ በኩል በአንደኛ ተከሳሽ ላይ በሌላኛው በቀረበበት 5ኛ ክስ ላይ ደግሞ ተከሳሹ ማዕድን የመያዝ ፍቃድ ሳይኖረው ክብደቱ 108 ነጥብ 43 እና 51 ነጥብ 88 ግራም የሚመዝን ኦፓል የተፈጥሮ ማዕድን እና 4 ነጥብ 99 ግራም የሚመዝን ኳርትዝ እንዲሁም 77 ነጥብ 71 ግራም የሚመዝን አጌት የተፈጠሮ ማዕድን እና 104 ነጥብ 59 ግራም የሚመዝን ማግኔታይት የተፈጥሮ ማዕድን ይዞ የተገኘ መሆኑ በክሱ ተጠቅሶ ፍቃድ ሳይኖረው የተፈጥሮ ማዕድን መያዝ እና የአዋጁን ድንጋጌዎች መተላለፍ ወንጀል ክስ መቅረቡ ይታወሳል።

በተለይም አንደኛ ተከሳሽ በኮንትሮባንድ ወንጀል ክስ የቀረበበት ሲሆን÷ ሌሎቹ ማለትም ከ2ኛ እስከ 9ኛ ተራ ቁጥር የተጠቀሱት ተከሳሾች ላይ ደግሞ የፀና የመኖሪያ ፍቃድ ሳይኖር በሀገር ውስጥ መኖር ወንጀል ክስ ቀርቧል።፡

በአጠቃላይ ተከሳሾቹ ላይ የቀረበባቸው ተደራራቢ የወንጀል ክስን በችሎት እንዲደርሳቸው ተደርጓል ማንነታቸውም ተረጋግጧል።

ከ1 እስከ 6 ኛተራ ቁጥር የተጠቀሱ ተከሳሽ ጠበቆች የአንደኛ ተከሳሽ የልብ ህመምተኛ መሆናቸውንና ቋሚ አድራሻ እንዳላቸው ጠቅሰው የዋስትና መብት እንዲፈቀድ ጠይቀዋል ነበር።

በተጨማሪም ከ2 እስከ 6ኛ ተራ ቁጥር የተጠቀሱት ደንበኞቻቸውን በሚመለከት የቀረበባቸው ክስ ከ7 ዓመት በላይ የማያስቀጣ የወንጀል ድንጋጌ መከሰሳቸውን ጠቅሰው የዋስትና መብት ጥያቄ አንስተዋል።

በዐቃቤ ሕግ በኩል ደግሞ ተከሳሾቹ ከተከሰሱበት ተደራራቢ ክስ የቀረበባቸው እና ቋሚ አድራሻ የሌላቸው ከመሆኑ አንጻር ቢወጡ የዋስትና ግዴታቸውን አክብረው ሊቀርቡ አይችሉም ሲል በመቃወም ተከራክሯል።

የሰበር ሰሚ ችሎት ተደራራቢ ክሶችን በሚመለከት በልዩነት ዋስትናን ሊያስከለክል ስለሚችል ድንጋጌዎች በማብራራት በመከራከር ተጠርጣሪዎቹ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ ጠይቋል።

ሌሎቹ ከ7ኛ እስከ9ኛ ተራ ቁጥር የተከሰሱ በኤሌክትሪክ ባለሙያ እና ሁለት እግር ኳስ ተጫዋች ነን ያሉ የላይቤሪያና የጊኒ ዜግነት ያላቸው ተከሳሾችን በሚመለከት በችሎት የተገኙ ጠበቃ ድጋፍ ለማድረግ በማስፈቀድ ተከሳሹ በቱሪስት ቪዛ ሀገር ውስጥ በገቡ በሁለት ሳምንታቸው በፀሐይ ሪል ስቴት በሄዱበት መያዛቸውን ጠቅሶ ቪዛና ፓስፖርት ያላቸው መሆናቸውን በማመላከት ከሀገር እንዳይወጡ እግድ ተጥሎ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጥያቄ ቀርቦ ክርክር ተደርጎበት ነበር።

የግራ ቀኙን ክርክር የመረመረው ችሎቱ ተከሳሾቹ ላይ የቀረበው ተደራራቢ ከባድ ወንጀል መሆኑን ተከትሎ ቢወጡ ተመሳሳይ ድርጊት ላይ ሊሳተፉና ቋሚ አድራሻ ስለሌላቸው የዋስትና ግዴታቸውን አክብረው ላይቀርቡ ይችላሉ የሚለውን ግምት በመያዝና እንዲሁም ዋስትና ሊገደብ የሚችሉባቸው የሰበር ሰሚ ችሎት ያስቀመጣቸው የድንጋጌ ነጥቦች በምክንያትነት በመጥቀስ የተከሳሾቹን ዋስትና ጥያቄ አለመቀበሉን አብራርቷል።

የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ የተደረገባቸው ተከሳሾች ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ በማለት ከቀጠሮ በፊት የሚቀርብ የክስ መቃወሚያ አስተያየትና የዐቃቤ ሕግ መልስን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለህዳር 4 ቀን 2016 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

ኤፍ ቢ ሲ

  አንድ ንጉሥ ወደ አደንም ሲሄድ፣ ወደ አደባባይም ሲወጣ፣ ወደ ዙፋን ችሎትም ብቅ ሲል፣ ወደ ጦር ሜዳም ሲጓዝ እንደ ቀኝ እጁ የሚያየውና  እንደ ሰው አክብሮ የሚያኖረው አንድ ፈረስ ነበረው። ይህ ፈረስ በንግሥና ዘመኑ ያልተለየውና ፍፁም ባለውለታው ነበር። ስለዚህም ምን ላድርግለት ብሎ ሌት-ተቀን ሲያስብ ቆይቶ በመጨረሻ አንደ ሀሳብ አገኘ። ይህ ፈረስ ቋንቋ ቢማር እንደልብ ሊያጫውተውና ሊያናግረው እንደሚችል ታየው። ንጉሡ የሚጠላው ግን በአዋቂነቱ ምንም ዓይነት ወጥመድ ያለበት ጥያቄ ቢጠይቀው መልስ የማያጣ በመሆኑ የሚያናድደውን ሊቅ አዋቂ ምሁር አስጠርቶ እንዲህ አለው፡-


“እንደምታውቀው ይሄ ፈረሴ ባለውለታዬ ነው። በመጣምርና በመረሸት አስጊጬ፣ ገላውን በየእለቱ አሳጥቤ፣ ተገቢ የመኖሪያ ስፍራ ሰጥቼ፣ መኖሪያው እንዳይጓደል ተጠንቅቄ፣ እንደሰው አቅርቤና አክብሬ ይዤዋለሁ። ሆኖም እሱ የእኔን ንግግር ባለማወቁ፣ ቋንቋ ለቋንቋ ልንግባባ አልቻልንም። እኔ የእሱን ቋንቋ ልማር እንዳልል አንተም አስተማሪያዬ ራስህ ቋንቋውን ስለማታውቅ ማን ያስተምረኛል? ስለዚህ የሚሻለው አንተ ለፈረሴ ቋንቋ ብታስተምረው ነው። የፈለግኸውን እርዳታና የተመቻቸ ሁኔታ እንዲኖርህ  አደርግልሃለሁ። ታዲያ ይህ ኃላፊነት የዋዛ ኃላፊነት እንዳይመስልህ። በመሆኑም ከአሁን ጀምሮ እስከ አምስት ዓመት ድረስ ይህ ፈረስ ቋንቋ እንዲማር አድርግ። ያ ሳይሆን ቢቀር ግን ትገደላለህ!” አለው።


ምሁሩም፡-
“ንጉሥ ሆይ እርስዎ የፈለጉት እንዲሆን ማድረግና እርስዎን ማስደሰት ተገቢ መሆኑን አምናለሁ። እንዳሉኝም አደርጋለሁ። በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ፈረስዎ በእኛ ቋንቋ እንዲናገር አደርገዋለሁ” ሲል ቃል ገባ።
ንጉሡ በዚሁ አሰናበቱት።
ያ ሊቅ ምሁር ከንጉሡ እንደተለየ ከአንድ ብልህ ወዳጁ ጋር  ይገናኛል።  ለዚህ ወዳጁ ለንጉሡ ስለገባው ቃል አጫወተው። ወዳጁም፡-
“ሰማህ ወይ እንደዚህ ያለ እብደት እንዴት ትፈጽማለህ? ፈረስ ቋንቋ ሲማር ያየኸው የት አገር ነው? ንጉሥ አስደስታለሁ ብለህስ እንዴት አንገትህን ለሰይፍ ታመቻቻለህ? ከእንዳንተ ያለ ሊቅ  አዋቂ ይህንን አልጠብቅም” ይለዋል።
ሊቁ እንዲህ ሲል መለሰ፡-
“ወዳጄ እኔም አስቤበታለሁ። የንጉሡን ትዕዛዝ የተቀበልኩት ለምን መሰለህ? በእኛ አገር  እስከ አምስት ዓመት ድረስ የሚሆነው ምን ይታወቃል? ወይ ንጉሡ ይሞታሉ። ወይ እኔ እሞታለሁ። ወይ ፈረሱ ቋንቋ ይማር ይሆናል!”
***
በነሲብና በአቦ ሰጡኝ፣ ተስፋ በመቁረጥና ንጉሥ ለማስደሰት ብሎ ከህሊናው ውጭ የማይሆነውን ይሆናል የሚል የተማረ ዜጋ አይጣል ነው። እንዲህ ያለው ምሁር የሀገር እዳ እንጂ የሀገር መድህን አይደለም። አገራችን እንኳን የነሲብና የ”ጥንቆላ” መላምት ተጨምሮባት እንዲያውም እንዲያው ናት። የዛሬ ሃያ ዘጠኝ ዓመት ግድም አንድ ለብዙ ጊዜ ውጭ ሀገር የቆዩ ኢኮኖሚስት አዛውንት “የሀገራችን ኢኮኖሚ ሁኔታ ምን ይመስለዎታል?” ሲል አንድ ወጣት ቢጠይቃቸው፤ “አይ ልጄ እንዲያው ባጠቃላይ ይሕቺ ሀገር‘ዲካርቴ’ ገብታለች ለማለት ይቻላል።” ብለው ነበር። እውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር ነው የአዛውንቱ ጨዋታ። ምሁራን በሹመት ከተደለሉ፣ ግለኝነት ካጠቃቸውና የዘለቄታውን ሳይሆን የእለት የእለቱን ብቻ የሚያዩ ከሆነ፣ “ፈረሱ ቋንቋ ይማር ይሆናል” ከማለት የተሻለ ሚና አይኖራቸውም። ተደናግረው ከማደናገር፣ በአእምሮአቸውም፣ በአካላቸውም፣ ሙስናውስጥ ተዘፍቀው፣ አሉ እየተባሉ ቢንከላወሱ፣ “አያድን ጋሻ ቂጥ ያስወጋል” እንዲሉ፣ ለሀገርም ለህዝብም ሳይበጁ መቅረታቸው ነው።


አልበርት ካሙ እንዳለው፤ “ምሁር ማለት አዕምሮው ለራሱ ዘብ የሚቆምለት ሰው ነው። መልካም ራዕይ ያላቸው ምሁራን ለሀገር ያስባሉ። ለህዝብ ይቆረቆራሉ። ይህን ለመፈጸም ከሁሉ አስቀድመው ለአካዳሚው ህብረተሰብ ሰብዕናና መብት መከበር ያስባሉ። ለሙያ ክብር ይቆማሉ። እንዲያም ቢባል ለሙያቸው ተቀዳሚነትና ህልውና ማሰብ ብቻውን አያጸድቅም። የሙያቸው ህልውና መታወቁ ዋና ጠቀሜታው በተግባር ሥራ ላይ አውለውት እራሳቸው ተጠቅመው ህብረተሰባቸውን ሲያገለግሉበት ነው። ያኔ ለሀገር የሚበጅ እሴት ይሆናሉ። ለሙያ መታመን ታላቅ ህሊናዊ ኃላፊነት ነውና በማናቸውም መንገድ ቀዳሚውና ክብሩ ጉዳይ እሱ ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ሊመጣ የሚችል ተጠቃሽ አደጋ ግን አለ- የሙያ- ተአብዮ (Intellectual Arrogance)። የሁሉ ዳኛ የሁሉ ችግር ፈቺ እኔ ነኝና አንቱ በሉኝ፤ እንደመካኒክ ሻንጣ ተሸክማችሁኝ ዙሩ። ለሁሉ ችግር እኔ ነኝ መፍቻው፤ ሁሉ ሀገር እኔ ልሂድ፤ ሁሉ ሀሳብ ከኔ ይምጣ የማለት አባዜ ሲጠናወት ደግሞ ይብስ ይጎዳል። በተደጋጋሚ የተከሰተው ዛሬም ያልጠፋ ቀንደኛ ችግራችን ነው።


ሌላው በሰራው ድንገት ብቅ ብሎ ሹመት ሽልማቱን ልቋደስ ማለቱም ሌላ ጣጣ ነው። በፖለቲካው ትግል አንፃርም ቢሆን በልባዊነትና በልባምነት የደከመው እያለ “የለውጥ አርበኛ” መሆን፣ የ”ለውጥ ሐዋርያ” መሆን፣ “አዲስ ግልብጥ” መሆን፣ “የነቃ የበቃ” ካድሬ መሆን፣ ጮማ ምሁር ነኝ ከማለት (Crean of the intelligentia) ጋር በእብሪት ሊተሳሰር ሲሞክር አደጋው የዛኑ ያህል የግለኝነት ጥንስስ እንዳለበት አመላካች ነው። “አርሶ እህል ያደረሰ መቆፈሪያ ግድግዳ ላይ ሲሻጥ፣ ግድግዳ ላይ የነበረ ማንኪያ ምግብ ላይ ይቆማል” እንደሚለው የወላይታ ተረት መሆኑ ነው።


የሀገር ጉዳይ ያገባኛል የሚል ምሁር ችግሯን መጋራት፣ መፍትሔዋን መፈለግና ማፋለግ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሙያን ለመለገስ ንፉግ አለመሆን ይኖርበታል።  መማር አዲስ ነገርን ለመቀበልም ሆነ ለመስጠት አዕምሮን መግራት ነው። የታነጸ አዕምሮ ያለው ዜጋ ችግሮችን አስቀድሞ የመረዳት፣ መፍትሔዎችንም ፈጥኖ የመሰንዘር ብቃት ይኖረዋልና ለሀገር ጉዳይ ምሁሩ ቅርበት አለው የሚባልበት ሁነኛ ምክንያቱ ይህ ነው። እንጂ አካዳሚክ አባ-ወራነት ብቻውን የሀገሩ “ባለቤት”፣ የሕዝቡ “ጌታ” አያደርግም። የአካዳሚ መሳፍንትነት (Accadamic aristocracy) ወደ ማንአለብኝነት ስርዓት እንጂ ወደ ጤናማ ዲሞክራሲያዊ የእውቀት አምባ አያመራም። ከሁሉም በላይ ከምሁሮቻችን የሚጠበቀው ከስንዝር ወዲያ ክንድ ማሳየት ነው። የቅርቡን ዳገት ሳይሆን ከጀርባው ያለውን ገደል  ወይም ሜዳ መጠቆም  ነው። በነቢብ የሚነገረው በገቢር ምን ይሆናል ብሎ መተርጎም ነው። ሁሌም አንድ እርምጃ ቀድሞ የያዝነው መንገድ ወዴት ያደርሰናል ማለት ነው።


“የአህያ ጆሮ ቆሟል ዝናብ ይመጣል” ከሚል ግምት እንድንላቀቅ ማገዝ ነው። “ንፋስ በዛ ትልቅ ሰው ይሞታል” ከሚል መላ ምት ወጥተን ትክክለኛውን የአየር ጸባይ የመገመት፣ የህብረተሰብ ሳይንስን መሰረት ያደረገ ትንተና የመጠቀም  መላ እንድንጨብጥ ማመላከት ነው።
ለምሳሌ የዩኒቨርስቲው የወደፊት ራዕይና እጣ ፈንታ ምንድን ይሆን፣ የክልል ፖለቲካና  የሊብራሊዝም ዝምድና ከየት ወዴትስ (Cause, process and effect) ምንድን ነው፣ “ዳሩ ሲነካ መሐከሉ ዳር ይሆናል” ማለት ለስልጣነ- መንበሩ ያለው ትርጓሜ ምንድን ነው? ወዘተ የሚሉትን ሐሳቦች የሚያሳይ አብይ ትንተናና ፋና ወጊ ሐሳብ መስጠት እንጂ በትናንሽ ስልጣን ኮርቻ ዙሪያ ተቀምጦ በጉዳይ አስፈጻሚነት ከአፍንጫ ያልራቀ ወይም እስከ አፍንጫም ያልደረሰ አስተያየት ቢሰጡ፣ “ይሄ ሳር ፍለጋ ዱባ ለመስረቅ ነው” ከማሰኘቱ ሌላ  የምሁር ንፍቀ ክበብ ደንብና ወግ አይሆንም።

“ምሁር የማስጠንቀቂያ ደወል ነው” እንዲል መጽሐፉ፤ በእውቀቱ የሕብረተሰብ ቃፊርነቱን ማሳየት ይገባዋል። እንቅስቃሴ- አልባ መሆን (Non-Dinamic) ወይ በምቾት ከመስባት፣ ወይ በወሬ ከመትባትና ከመተበት አሊያም ያለውሉ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ ከማረጥረጥ ያለፈ ሚና አይኖረውም። ይሄው እንዳይበቃው ይህንኑ ለመሸፈን ሲል ስሜን ያስነሳል ለሚለው አንዳች ረብ- የለሽ ጉዳይ ዙሪያ አውሎ ነፋስ ማስነሳትን ስራዬ ብሎ ይያያዛል። “የመቀመጥ ብዛት የደረቀ ቁስል ያስፍቃል” ይሏል ይሄ ነው። ይሄ በሁሉ ሰፈር፣ በሁሉም ካምፕ፣ በሁሉም ጎራ፣ በመጤው፣ በፖለቲከኛው፣ በባለሙያው ዘንድ መታየቱ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል። ኋላ አቧራው መሬት ሲወርድና ንፋሱ ሲቆም ከተቀመጠበት ፎቀቅ ያላለ ምሁር መኖሩ ይፋ መሆኑ አይቀርም። ሕዝቡም እንደፈረደበት እንደዘፋኙ
“ቃልሽን ያንቆርቁረው በቀለመ-ወርቁ
እኔ አንቺን ስጠብቅ እየተኙ ነቁ”
በማለት ወቅታዊ ጥሪውን ማቅረቡን ይቀጥላል። ምሁራን ንፉግ አይሁኑ። ብዙ ጾመው ብዙ አስጹመውናልና።

ኢትዮጵያ በኃይልና በወረራ ፍላጎቷን ማሳካት እንደማትሻና በጎረቤት አገራት ላይ ወረራ የመፈጸም ፍላጎት እንደሌላት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገለፁ ። “አገሪቱ ቃታ በመሳብ በሀይልና በወረራ ማሳካት የምትሻው አንዳችም ነገር እንደሌላትም ተናግረዋል ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ከትላንት በስቲያ ሃሙስ ጥቅምት 15 ቀን 2016 ዓ.ም.፣ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተከበረው “116ኛ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ቀን” በዓል ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ኢትዮጵያ ቃታ በመሳብ በኀይልና በወረራ ማሳካት የምትሻው አንዳችም ነገር የለም፤ ይልቁንም በንግግርና በድርድር የጋራ ጥቅሞችንና ፍላጎቶችን ለማሟላት ቁርጠኛ ነን፤” ብለዋል።


የዘንድሮው የመከላከያ ሠራዊት ቀኑ “በተፈተነ ጊዜ ሁሉ የሚፀና የድል ሠራዊት” በሚል መሪ ቃል  የተለያዩ ወታደራዊ ትርኢቶችና የሠራዊቱን አቅምና ብቃት የሚያሳዩ ደማቅ ዝግጅች በቀረቡበት ሥነ-ስርዓት ላይ መልዕክት ያስተላለፉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ “ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኢትዮጵያ በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ውይይት ያስፈልገናል የሚል ጥያቄ ስታነሳ ወረራ ሊካሄድ ይችላል የሚል ስጋት እንዳለ ይደመጣል። ነገር ግን  ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብና ለሀገር መከላከያ ሰራዊት በዚሁ በተከበረ ቀን መግለጽ የምፈልገው ኢትዮጵያ በሃይልና በወረራ ማሳካት የምትፈልገው አንዳች ነገር አለመኖሩን ነው”  ብለዋል።


በሀይል ፍላጎቶቻችንን ለማሳካት ወንድሞቻችን ላይ ቃታ የምንሰነዝር እንዳልሆን በአጽንኦት ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ ለጋራ ጥቅም፣ ለጋራ እድገት፣ ለጋራ ብልጽግና ሁሉንም አሸናፊ በሚያደርጉ ጉዳዮች ከወንድሞቻችን ጋር ተወያይተን የጋራ ጥቅም ለማስከበር እንጥራለን ብለዋል። “የሀገሪቱ መከላከያ ሰራዊት ሰላም ከማስከበር፣ ሰላም ከመጠበቅና የሀገር ብልጽግና እንዲቀጥል ከማድረግ ውጭ ሌላ አላማ የለውም” ሲሉም ጠ/ሚኒስትሩ አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።


የአገሪቱ ሠራዊት ሌሎችን ለማጥቃትና ለመውረር እንደማያስብ የተናገሩት ጠቅላይ ሚንስትሩ አገሪቱን ግን ይከለከላል ብለዋል።
ባለፉት ሳምንታት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባላት ባደረጉት ንግግር፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ወይም ወደብ ያስፈልጋታል በሚል ሃሳብ ምክንያታቸውንም በዝርዝር ማቅረባቸው አይዘነጋም። አገራት ግን የጠ/ሚኒስትሩን የባህር በር ሃሳብ ወይም ጥያቄ በቀና የተመለከቱት አይመስልም። ኤርትራ፣ ጂቡቲና ሶማሊያ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጡት ምላሽ፣ የጠ/ሚኒስትሩን ሃሣብ የሚቃወሙና የማይቀበሉ መሆናቸውን  በመግለጽ ምላሽ መስጠታቸው አይዘነጋም።


ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ኢትዮጵያ ከህዝብ ቁጥሯ ብዛትና ከተለያዩ የጎረቤት አገራት ወደቦች በቅርብ ርቀት ላይ መገኘቷን በመጥቀስና ሰጥቶ በመቀበል አግባብ የባህር በር ወይም ወደብ  የምታገኝበት መንገድ መፈጠር እንዳለበት መናገራቸውን ተከትሎ፣ በርካታ ምሁራን በሚዲያ እየቀረቡ የጠ/ሚኒስትሩ ሃሳብ የሚደግፍና የሚያጠናክር ማብራሪያ ሲሰጡ ተደምጠዋል። ትላንት በኢቢሲ በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየት የሰጡት ምሁር ኢትዮጵያ መድሃኒትና ነዳጅን ጨምሮ ወደ አገር  ውስጥ ለምታስገባቸው የተለያዩ ምርቶች ወደብ እንደሚያስፈልጋት ጠቁመው፣ ዓለማቀፍ ተቋማት የኢትዮጵያን የባህር በር የማግኘት ፍላጎት ወይም ጥያቄ ይደግፉ ዘንድ ጥሪ አቅርበዋል።
ጎረቤት አገራትም በንግግርና በውይይት ኢትዮጵያ የባህር ወደብ እንድታገኝ ትብብር ያደረጉ ዘንድ ምሁሩ ጥያቄ አቅርበዋል።

Friday, 27 October 2023 07:20

አሜባ 'ኪንታሮት' ያመጣል?

አሜባ 'ኪንታሮት' ያመጣል?

ከእለት ተእለት የህክምና ስራችን ላይ ከሚያጋጥሙን እና በማህረሰባችን ዘንድ በተሳሳተ መልኩ ከሚታዩ የጤና ሁኔታዎች አንዱ በፊንጢጣ በኩል ደም መፍሰስን ወይም ፊንጢጣ አካባቢ የሚኖሩ እባጮችን  እና ተያያዥ ምልክቶችን አብዛኛውን ጊዜ ከ 'ሄሞሮይድስ' (የፊንጢጣ ኪንታሮት) ወይም  አሜባ ህመም ጋር ብቻ ማያያዝ ነው::

በሚያሳዝን መልኩ ብዙ ታካሚዎቻች ደም መድማትን ካዩ በኋላ በተለያዩ ምክንያቶች ወደ ጤና ተቋም በቶሎ ባለመቅረባቸው ወይም በእኛ በባለሙያዎች ዘንድ ምልክቱን በአግባቡ ባለመጠየቅ የህመማቸው ደረጃ ገፍቶ እናያቸዋል::

የተለመዱ በፊንጢጣ በኩል ደም እንዲፈስ የሚያደርኩ የህመም አይነቶች
1. ሄሞሮይድስ (የፊንጢጣ ኪንታሮት)
2. የፊንጢጣ ውስጠኛው ክፍል መላጥ (መሰንጠቅ)
3.የአንጀት ደም ስር ችግሮች
4. የአንጀት ላይ እባጮች (intestinal polyps)
5. የአንጀት ወይም የፊንጢጣ ካንሰር (የቀኝ የአንጀት ክፍል ካንሰር የሚታይ መድማትን ሳያመጣ ግለሰቡ የደም ማነስ ምልክት ብቻ ሊኖረው ይችላል) የግራው የአንጀት ክፍል ግን የረጋ (የጠቆረ) ደምን ሊያሳይ ይችላል

6.የተለያዩ የአንጀት ኢንፌክሽኖችና የአንጀት መቆጣት
7. የደም አለመርጋት ህመሞች ወይም ተያያዥ መድሀኒቶች

ስለሆነም በፊንጢጣ በኩል የሚኖር ደም መፍሰስ የፊንጢጣ ኪንታሮት ወይም የአሜባ ህመም ብቻ ሳይሆን ከላይ የተዘረዘሩት እና  የሌሎችም ህመሞች ምልክት ሊሆን ስለሚችል ተገቢውን ምርመራ በማድረግ ተገቢውን ህክምና ማግኘት ይቻላል::

ሰላም!!

ዶ/ር ቢንያም ዮሐንስ: General Surgeon, Colorectal Surgery Fellow

Tuesday, 03 October 2023 00:00

ዝምተኛ ልቦች

አርቲስት ጌትነት እንየው
አምነው የወደዱ፣
ወደው የተካዱ፣
ተክደው የራዱ፣
ፍርሃት አንሸራቶ ቁልቁል የጣላቸው፣
የብቸኛ ልቦች የትነው መውደቂያቸው?
የትነው መድረካቸው?
ማነው አጃቢያቸው?
እንዴት ነው ምታቸው?
የተካዱ ልቦች አጋር የራቃቸው፣
የሚያቀነቅኑት ምንድን ነው ዜማቸው?
የተመረኮዙት እምነት ታጥፎባቸው፣
ድንገት የወደቁ ፍቅር ያዳጣቸው፣
ሚስጥር የሚያጋሩት ሰው የበረዳቸው፣
ብቸኝነት ሰርጎ ብቻ ያስቀራቸው፣
ዝምተኛ ልቦች ምን ይሆን ቋንቋቸው?
ከየት ነው ጥሪያቸው?
በየት ነው ጉዟቸው?
የት ነው መድረሻቸው?
እንደ ሰብአሰገል ጠቅሶ የሚመራቸው፣
የቃተቱ ልቦች የታል ኮከባቸው?
መቼም ከአምላክ ትንፋሽ ከውሃ ከአፈሩ፣
ከእምንት እና እውነት ከፍቅር ሲሰሩ፣
ዝምተኛ ልቦች ጥንቱን ሲፈጥሩ፣
ተገፍትረው ወድቀው፣
ደቀው እንዳይቀሩ፣
በተስፋ ጸንተው ነው ዘላለም ሊኖሩ።
አርቲስት ጌትነት እንየው ባለ ብዙ መልክ የጥበብ ስብእና ያለው ነው። ተውኔት ይፅፋል፣ ያዘጋጃል፣ ይተውናል። ግጥም ይፅፋል ።ደግሞም ደራሲ ነው። ለሃገራችን የኪነጥበብ ጉዞ ሁለገብ አስተዋፅኦ ከሚያበረክቱ የሀገራችን ከያኒዎች መካከል አንዱና ግንባር ቀደም ነው። ብዙዎች የቃላት ሃብት አለው ይሉታል። ቴአትርን ማዘመን ፤ ለቴአትር ህይወት መስጠትን ደግሞ ተክኖበታል። ታላቁ ባለቅኔ ጌትነት እንየው። የህይወት ታሪኩን እዝራ እጅጉ እና ዘቢባ ሁሴን ሰንደውታል፡፡
➻ ውልደት እና እድገት
ጌትነት እንየው ከጎጃም ምድር የፈለቀ ጠቢብ ነው። ወላጆቹ አርሶ አደሮች እርሱም የገበሬ ልጅ ነው። በደብረማርቆስ ከተማ አብማ ማርያም በምትባል መንደር በ 1950 ዓ.ም ተወልዷል።
ጌትነት ያደገው ከታላቅ እህቱ እና ከባለቤቷ ጋር ደብረማርቆስ ከተማ ሲሆን በ 1964 ዓ.ም የእህቱ ባል በስራ ምክንያት ወደ ጅማ ሲዘዋወር ጌትነትም ከእህቱና ከባለቤቷ ጋር ወደ አባጅፋር ሃገር ጂማ ተጓዘ።
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በጎጃም፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በጅማ ተምሯል። ገና በለጋ እድሜው በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳለ የተጠናወተው የኪነ-ጥበብ አባዜ በጅማም አብሮት ነበር።
➻ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ
ጌትነት ትምህርቱን አጠናቆም በጥሩ ውጤት ወደ ዩኒቨርሲቲ መግባት ችሏል። በ 1971 ዓ.ም የመጀመሪያ ምርጫው የሆነውን የትያትር ጥበብን ማጥናት ቀጠለ።
በዩኒቨርሲቲ ቆይታውም የግቢውን ባህል ማዕከል እንደርሱ በሚገባ የተጠቀመበት አልነበረም። ባህል ማዕከል ራሱን የሚፈትሽበት እና ራሱን የቀረፀበት ትወናን በማንያዘዋል እንዳሻው "በጠልፎ በኪሴ" ዝግጅት የጀመረበት የራሱንም የመጀመሪያ ተውኔት "ስንብትን" አዘጋጅቶ ለመድረክ ያበቃበት ባለውለታው ስፍራ ነበር።
ጌትነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሲማር ዘወትር ኬኔዲ ላይብረሪ እየገባ በርካታ መፅሃፍትን ያነብ ነበር። አባኮስትር የተጠነሰሰው ያኔ ነው። አባኮስትር የካቲት መፅሄትን ሲያነብ ያገኘውና የተሳበበት ሀሳብን ያነሳበት ስራው ነበር።
ጌትነት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የትያትር ትምህርቱን በ 1974 ዓ.ም ተመርቆ ወጥቶ በ 1975 ዓ.ም ለተመረቁ ተማሪዎች የመመረቂያ እለት ስለ እናት ፣ ስለ ሃገር፣ ስለማገልገል የሚሰብክ መዝሙርን አዘጋጅቶ ነበር።
ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ ወዲያው በዝና እንጂ በውል በማያውቀው ብሄራዊ ትያትር ቤት ገብቶ ህልሙን እውን ማድረግ ጀመረ። በብሄራዊ ትያትር በነበረው ቆይታም ከተመልካች አእምሮ ውስጥ በጉልህ የተጻፉ ስራውን ማቅረብ ችሏል፡፡
ጌትነት ጎበዝ ገጣሚም ነው። ግጥምን የሚያነብበት መንገድ ከማንም ጋር የማይመሳሰል የራሱ ዜማ ያለው ፣ ወኔውና ስሜቱ ከነድምፀቱ እጅግ የሚማርክና የሚነዝር ነው።
➻ አበርክቶዎች
የኢትዮጵያ ኪነጥበብ ዋርካ !ታላቁ ከያኒ ፀሐፊ ተውኔት ጌትነት እንየው በቴአትር ድርሰት ፣ በዝግጅት ፣ በትወና እና በገጣሚነት ዘመን ተሻጋሪ የሆኑ በርካታ ጥንቅቅ ያሉ ስራዎችን ያበረከተ ፣ ሥነሥርዓት ሞልቶ የተረፈው ጨዋ ፣ ስራዎቹ በፍቅር የሚታዩለት ፣ የኪነጥበብ ታላቅ ሰው ነው። ከስራዎቹ ውስጥ ፦
➻ "ውበትን_ፍለጋ "
ይህ የጌትነት እንየው ድንቅ ተውኔት ሲሆን ግሩም አድርጎ ፅፎት ድንቅ አድርጎም አዘጋጅቶታል። ይኼ ቴአትር የመድረክ ዕይታው ሲጠናቀቅ ወደፊልም ተቀይሮም ተሰርቷል። ወደፊልም ሲቀየር ጌትነት እንየው የመሪ ተዋናዩን "ይገረሙ" የተሰኘውን ገፀ ባህሪ ወክሎ ተውኗል። ቴዎድሮስ ተስፋዬም ፊልሙን ዳይሬክት አድርጎለታል።
"ውበትን ፍለጋ" ጌትነት ከሰባት አመት በላይ የለፋበትና ውጤት ያገኘበት ተወዳጅ ተውኔት ነበር። የኔ የሚለው እምነትና ማንነቱም የተንፀባረቀበት ስራ ነበር። የአፃፃፍ ቴክኒኩ ከመምህሩ መንግስቱ ለማ ያገኘውን እውቀትም ተግባራዊ ያደረገበት ነው።
➻"በላይ_ዘለቀ" (አባኮስትር)
ይህን ቴአትር ጌትነት መድረክ ላይ ሲተውነው : በሚያስገመግም ድምፁ መድረኩ ላይ ጎብለል ጎብለል እያለ ሲምነሸነሽበትና ሲሞላው እጅግ ድንቅ ነው።
ጌትነት እንየው በላይ ዘለቀን ሲተውን ጥላሁን ገሰሰን በፍቅር ያንበረከከ በስራው ያሳመነ እና ያስጨበጨበ ሰው ነበር። ጥላሁን ገሰሰ ብቻ ሳይሆን በዘመኑ መድረክ ላይ የተመለከተው ሁሉ እጅግ የተደመመበት ታላቅ ስራ ነበር።
➻ " የእግዜር_ጣት"
ጌትነት እንየው የፃፈው ትያትር ሲሆን በዚህ ተውኔት ላይ ተስፋዬ ገ/ሃና ፣ አበባየሁ ታደሰ ፣ ስናፍቅሽ ተስፋዬ ፣ ህንፀተ ታደሰ እና ሱራፌል ወንድሙ ድንቅ ትወናቸውን አሳይተውበታል።
የድራማው ዋና ጭብጥ እግዚአብሔር ከፃፈው ውጪ ምንም ነገር ሊፈፀም አይችልም የሚል መልዕክት የሚያስተላልፍና ድንቅ አስተማሪ ቴአትር ነው።
➻"የቴዎድሮስ_ራዕይ"
ጌትነት ሙዚቃን ከትያትር ጋር አዋህዶ ታሪካዊና ሙዚቃዊ ተውኔቶችን መስራት ተክኖበታል። በዚህም "የቴዎድሮስ ራዕይ" ጉልህ ማሳያ ነው። ቴዎድሮስ ታሪካዊ ትያትር ሲሆን ከ 150 በላይ ተዋንያን የተሳተፉበት ስራ ነው።
ጌትነት ቴዎድሮስን የተመለከተው ሌሎች ካዩበት የሃይለኝነትና የጀግንነት ባህሪ በዘለለ ነው። የጌትነት "ቴዎድሮስ" እጅግ ለሰው የቀረበ ሰውነት ጎልቶ የሚታይበት አፍቃሪና ለፍቅር ተረቺነት ያለው ሰው ነው። ይህንንም ያሳየበት ድንቅ ስራ ነው።
ከበላይ ዘለቀ እና የቴዎድሮስ_ራዕይ ታሪካዊ ተውኔቶች በተጨማሪ "እቴጌ ጣይቱ" ቴአትርንም ፅፏል።
➻"ወይ_አዲስ_አበባ"
ይህ በ 1996 ዓ.ም የብሄራዊ ትያትር ቤት ለእድሳት ተዘግቶ ሲከፈት በአዲስ ስራ መከፈት አለበት ተብሎ በመታሰቡ በርካታ ተዋንያን የተሳተፉበት በጌትነት የተዘጋጀ ስራ ነው ።
ተውኔቱ የአፄ ሀይለስላሴን ፣ የደርግንና የኢህአዴግን የሶስቱንም መንግስታት የአገዛዝ ዘመን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ሙዚቃዊ ድራማ ሲሆን ጌትነት ፅፎና አዘጋጅቶ ከጨረሰ በኋላ ለዕይታ ሊበቃ በነበረበት ሰዓት በጊዜው መድረክ ላይ እንዳይታይ ቀጭን ትዕዛዝ ተላልፎ ታግዶበታል።
➻ ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ ለእይታ የበቁ አጫጭርና የሙሉ ግዜ ተውኔቶች:-
1, ስንብት አአዩ የባህል ማዕከል 1974
2, የግርማ ቀላቢት በብሄራዊ ትያትር ቤት ለእይታ የቀረበ 1974
3, እንቁላል በብሄራዊ ትያትር ቤት እና በአሜሪካን ሀገር ለእይታ የቀረበ 1978-81
4, (final moment) እንግሊዘኛ ሲሆን ወደ አማርኛ ሲመለስ "እውነተኛ ቅፅበት " በብሄራዊ ትያትር ቤት: ካሜሮንና ስዊዲን ሃገር ለእይታ የቀረበ
5, ዲሞቴራፒ በብሄራዊ ትያትር ቤት ለእይታ የቀረበ 1985
6, ሃምሳ አመት ስንት ነው? በአ.አ ዩኒቨርሲቲ (50ኛ ዓመት ክብረ በዓል
= ጌትነት ከተወነባቸው ቴአትሮች መካከል፦
★ ባለካባ እና ባለዳባ ፣ አሉላ አባነጋ ፣ ነፃ ወንጀለኞች ፣የቬኑሱ ነጋዴ ፣ የእጮኛው ሚዜ ፣አንድ ጡት ፣ ውጫሌ አስራሰባት ፣ እርጉም ሀዋርያ እና ሐምሌት ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው።
= በዝግጅት ከተሳተፈባቸው ተውኔቶች ውስጥ፦
የለሊት እርግቦች ፣ የእግዜር ጣት ፣ ውበትን ፍለጋ ፣ ምስጢረኞቹ ፣ ሕንደኬ ፣የቴዎድሮስ ራዕይ ፣ አዙሪት ፣ አባትየው ( ትርጉም ተውኔት ) አዲስ ፀሐይ እና እቴጌ ጣይቱ ጀግና አዘጋጅ መሆኑን ያስመሰከረበት ስራዎቹ ሲሆኑ እነዚህንና ሌሎች ያልተካተቱ ቴአትሮች ላይ በመሪ ተዋናይነት በብቃት ተውኗል።
ጌትነት እንየው ከመድረክ ቲአትሮች በተጨማሪ ብዛት ያላቸው አጫጭር ልብ ወለዶችን፣ አጫጭር የሬዲዮና የቴሌቪዥን ሥራዎችን ለህዝብ አበርክቷል፣
★ “ላይመለስ”፣ “ዲሞቴራፒ”፣ “የቅርብ ሩቅ” እና ለ13 ተከታታይ ሳምንታት የቀረበው፣ “ጥንዶቹ” የተሰኙ የሬዲዮ ድራማዎች በብዙኃን የሬዲዮ ተደራሲያን ዘንድ እንዲታወቅ አድርጎታል::
ከእነዚህ ውስጥ “ላይመለስ” እና “የቅርብ ሩቅ” በሚል ርዕስ የሚታወቁት ድራማዎች በአገራችን ተከስቶ በነበረው ረሀብ ላይ የሚያጠነጥኑ ሥራዎች ሲሆኑ፣ በተለይ “ላይመለስ” የሚለው ሥራ በሬዲዮ ከመቅረቡ በፊት በቴሌቪዥን መታየቱ ይታወሳል፡፡
ጌትነት በሬዲዮ የመጻሕፍት ዓለም ፕሮግራም ላይ የሰርቅ ዳንኤልን፣ “ቆንጆዎቹ”ን ረዥም ልብወለድ መጽሐፍ መተረኩም ይታወቃል፡፡ የአተራረክ ስልቱ እጅግ በጣም ማራኪ በመሆኑ በጊዜው ከፍተኛ እውቅናን አስገኝቶለት ነበር፡፡ በርካታ የሙዚቃ ግጥሞችን ለሙዚቀኞች እንካችሁም ብሏል።
ጌትነት ለሀገሩ ያለው ፍቅር ልዩ ነው፡፡ በጥበባቸው ለህዝብ ከሚደርሱ ተዋንያን መካከል አንዱ ነው። ኢትዮጵያን በብእሩ አሞካሽቷታል። በነጎድጎዳማ ድምፁ አነብንቦላታል። በወኔ ገልጿታል። ለብዙ ችግሮቻችን መፍትሄ ብሎ በግጥሞቹ ተንፍሶልናል። አስቆናል። ደግሞም አስለቅሶናል።
➻ ምስጋናና ሽልማት
ጸሐፌ- ተውኔት፣ ገጣሚ፣ ተዋናይ እና አዘጋጅ ጌትነት እንየው ለጥበብ ላበረከተው አስተዋጽዖ በርካታ የእውቅና ምስጋናን ተችሮበታል፡ የአማራ ክልል ባህልና ኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል "ለባህልና ኪነ-ጥበብ እድገት" ላበረከተው የላቀ አስተዋጽኦ የሕይወት ዘመን ተሸላሚ ሆኖ የክብር የእውቅና ሽልማት ሰጥቷታል።
በ 1991 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሥነ ጥበባትና የመገናኛ ብዙኃን የሽልማት ድርጅት በቲአትር የረዥም ጊዜ አገልግሎት ተሸላሚም ነበር።
ጌትነት ከቲአትር ሙያ ጋር በተያያዘ ከኢትዮጵያ ውጪ ወደ ተለያዩ የዓለም ሃገራት የተዟዟረ ሲሆን፣ ከአፍሪካ ኬንያና ካሜሮን፣ ከአውሮፓ ስዊድንን፣ ከአሜሪካ የተለያዩ ስቴቶችን ጎብኝቷል፡፡ ወደ ቻይናም አቅንቶ የቲአትር ስልጠና ወስዶ ተመልሷል።
መዝጊያ፤ ይህ መዝጊያ የተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን አቋም የሚንጸባረቅበት ነው፡፡
ጌትነት እንየው ዛሬም የሙያ ክብሩን እንደጠበቀ ያለ ግሩም የኪነጥበብ ሰው ነው፡፡ በትወና ክህሎቱ ፤ በድርሰት እና በዝግጅት ብቃቱ ብዙ ባለሙያዎች መስክረውለታል፡፡ ስለ 1970ዎቹ አጋማሽ የሀገራችን የቴአትር ታሪክ ስናወሳ ጌትነት በዛን ዘመን ብቅ ካሉት አንዱ ነው፡፡ ጌትነት ከ 1975 ጀምሮ ላለፉት 40 አመታት በጽናት ሙያው ላይ የቆየ ነው፡፡ ለዚህ ጽናቱ ልናመሰግነው ግድ ይላል፡፡ የህይወት ታሪኩንም በዚህ መልኩ የሰነድነው የጽናት ተምሳሌትነቱን ለማሳየት ነው፡፡ ስለ ጌትነት ታዳሚያንም ልዩ ፍቅር እንዳላቸው አስተውለናል፡፡ በተለይ የቴዎድሮስ ራእይ ላይ ሲተውን ሙሉ ብቃቱን አሳይቷል፡፡ ታዲያ ጌትነት ከትወና እና ከዝግጅት ባሻገር ጎበዝ ገጣሚነቱም ተመስክሮለታል፡፡ እኛም ለአዲሱ ትውልድ አርአያ የሚሆን ስንል ታሪኩን ሰንደናል፡፡
ታሪክን_ወደኋላ
Tewedaji Media
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
 
Tuesday, 24 October 2023 00:00

የሎሚ ጥቅም

ሎሚ በዓለም ላይ በጣም ተወዳጅ ከሆኑ  የፍራፍሬ አይነቶች አንዱ ነው። ምንም እንደኳን ሎሚ ጣዕሙ ኮምጣጣ ቢሆንም በርካታ የጤና ጥቅሞች እንዳሉት የጤና ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ሎሚ ለጤና ከሚያበረክታቸው ጥቅሞች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

1: ሎሚ ለልብ ጤናን ያገለግላል፤

ሎሚ ጥሩ የቫይታሚን ሲ እና አንቲኦክሲደንትስ ምንጭ መሆኑን ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ እነዚህ  ንጥረ ነገሮች ለልብ ጤንነት ጠቃሚ ከመሆናቸውም በላይ ለልብ ህመም እና ስትሮክን ለመከላከል የሚያገለግሉ ሲሆን በሎሚ ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ ፋይበሮች ደግሞ ለልብ ሕመም የሚያጋልጡ ሁኔታዎችን በእጅጉ ሊቀንሱ እንደሚችሉ የጤና መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡
የሎሚ ጭማቂ መውሰድ የደም ግፊትን ለመቀነስ እንደሚረዳ ጥናቶች አረጋግጠዋል።

2. ሎሚ በሽታ የመከላከል አቅምን ከፍ ያደርጋል፤

ሎሚ በሽታ የመከላከል አቅምን ከፍ የሚያደርግ ፍራፍሬ  በመሆኑ ለጉንፋን እና ለጉንፋን መሰል በሽታዎች  መንስኤ የሚሆኑ ጀርሞችን የመከላከል አቅምን ይገነባል። አንድ ብርጭቆ የሞቀ ውሃ በሎሚ ጭማቂ በአንድ የሾርባ ማንኪያ መውሰድ ሳልንና ጉንፋን ለመከላከል እንደሚያግዝ የጤና ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡

3: ሎሚ ለምግብ መፈጨት የጎላ አስተዋጽኦ አለው፤

ሎሚ ከፍተኛ መጠን ያለው የሚሟሟ ፋይበር የያዘ በመሆኑ መደበኛ የአንጀት እንቅስቃሴን ለመጠበቅ እና የምግብ መፈጨትን እንደሚያሻሽል የጤና መረጃዎች ያመላከታሉ። በሎሚ ውስጥ የሚገኘው ፖክቲን የተባለው ፋይበር የስታርች እና የስኳር የምግብ አይነቶችን በመፈጨትና በማፋጠን  የአንጀት ጤናን ለማሻሻል ይረዳል።

4.  ሎሚ  ክብደትን ለመቆጣጠር ያግዛል፤

ሙሉ በሙሉ የተጨመቀ ሎሚ በአንድ ብርጭቆ ለብ ባለ ውሃ አንድ የሾርባ ማንኪያ ማር በማድረገ መጠጣት ክብደትን ለመቀነስ እንደሚረዳ የጤና መረጃዎች ያስረዳሉ። ሎሚ  ክብደትን የሚጨምሩ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችን ከመመገብ የሚከለከል  ፔክቲን የተባለ ንጥረ ነገር ያለው በመሆኑ ለክብደት መቀነስ ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡
አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት በሎሚ ውስጥ የሚገኙት አንቲኦክሲደንትስ ክብደትን ለመቆጣጠር ይጠቅማሉ፡፡

5፡ ሎሚ የካንሰር ተጋላጭነትን ለመቀነስ ይረዳል፤

ሎሚ እና የሎሚ ጭማቂ የበለፀጉ የቫይታሚን ሲ ምንጭ በመሆናቸው እንደ ካንሰር ያሉ ገዳይ በሽታዎችን ለመከላከል የሚረዱ ፀረ-አንቲኦክሲዳንቶች እንዳሏቸው የጤና መረጃዎች ያመልክታሉ፡፡

6: ሎሚ በአፍ ውስጥ የሚከሰትን ህመም ያስታግሳል፤

ቫይታሚን ሲ ለጥርስ እና ለድድ አስፈላጊ በመሆኑና ሎሚ ደግሞ  በቫይታሚን ሲ የበለፀገ በመሆኑ በአፍ ውስጥ የሚከሰቱ በሽታዎች ለመከላከል ይጠቅማል። ስኩዊቪ በቫይታሚን ሲ እጥረት የሚመጣ በሽታ ሲሆን  ለድድ እብጠት፣ መድማት ወዘተ የሚዳርግ በሽታ ሲሆን ሎሚን በመጠቀም ይህን በሽታ ለመከላከል ያግዛል እንደ ጤና ባለሙያዎች መረጃ፡፡

7: ሎሚ ለቆዳ ጠቃሚ፤

ሎሚ ከፍተኛ መጠን ያለው የቫይታሚን ሲ ይዘት ስላለው ለቆዳችን ወፍራም እና ወጣት መልክ የሚሰጠውን ኮላጅንን ያመነጫል፡፡ ኮላችን ቆዳችንን እንዲያመር ከማድረጉም ባለፈ በፊት ላይ የሚገኙ ጥቃቅን መስመሮችን ለመቀነስ እና ቆዳን ለማጥራት ያገለግላል፡፡

ሎሚ በረካታ  ንጥረ ነገሮች ያሉት በመሆኑ ከተለያዩ  ምግቦች ጋር መጠቀም መቻል የበለጠ ገንቢ እና ጤናማ ቆዳ እንዲኖር ያደርጋል፡፡

የሎሚ ዘይት ጭንቀትን በማረጋጋት እና መንፈስን በማደስ ስሜትን ሊያሻሽል እንደሚችልም ነው የጤና ባለሙያዎች የሚያስረዱት።

8. ሎሚ የኩላሊት ጠጠርን ለመከላከል ይረዳል፤

በትኩስ ፍራፍሬ ውስጥ የሚገኘው ከፍተኛ የሲትሪክ አሲድ እና የሎሚ ጭማቂ ክምችት የሽንት መጠንን ሳይቀይር የሽንት ሲትሬትን መጠን በሁለት እጥፍ ለማሻሻል ያስችላል፡፡ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሎሚ ጭማቂ የኩላሊት ጠጠርን ለመከላከል የሽንት ሲትሬትን በመፍጠር ለክሪስታል እድገት መከላከያ ዘዴ ሆኖ ተገኝቷል፡፡

9. ሎሚ ለጉሮሮ ኢንፌክሽን ጠቃሚ፤

ሰዎች ጉሮሯቸውን በሚታመምበት ጊዜ  ብዙውን ጊዜ የሎሚ ጠብታዎችን እንዲጠቀሙ እንደሚመከር የጤና መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ምክንያቱም ሎሚ በተፈጥሮ ፀረ-ባክቴሪያ ባህሪያት ስላለው የባክቴሪያውን ተፅእኖ ስለሚቀንስ ነው፡፡

በአጠቃላይ ሎሚ በርካታ የጤና በረከቶች እንዳሉት በጤና ባለሙያዎች ይነገራል፡፡ስለዚህ ሎሚን የምግባችን አካል በማድረግ ጤናችንን መጠበቅ ይገባል፡፡

አንጋፋው ተመራማሪ ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኢጄታ የአሜሪካን ብሄራዊ የሳይንስ ሜዳሊያ ሽልማትን ከፕሬዚደንት ጆ ባይደን ተቀብለዋል።
ፕሮፌሰር ጋቢሳ በፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ብሔራዊ የክብር ሽልማት ከተሸለሙ 21 አሜሪካውያን ተመራማሪዎች መካከል አንዱ ሆነዋል።
መምህርና ተመራማሪው ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኤጄታ ለሽልማቱ ያበቃቸው በከፍተኛ የምርምር ስራቸው የእፅዋት ዘረመል ምህንድስና በመጠቀም በረሃማ የአየር ንብረት እና ነፍሳትን የሚቋቋሙ የአዝርዕት ዘሮችን በማግኘታቸው ነው።
ግኝታቸው በሚሊዮን ለሚቆጠሩ የምግብ ዋስትናን እንደሚያረጋግጥ ታምኖበታል።
ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኤጄታ በምግብ ዘርፍ ላበረከቱት አስተዋፅዖ ከዚህ በፊት ከዓለም የምግብ ፕሮግራሙ ሽልማት የተበረከተላቸው መሆኑ የሚታወቅ ነው።
ፕሬዚደንት ባይደን በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ይፋ ባድረጉት የተሸላሚዎች ዝርዝር በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ ለሽልማት የበቁትን ተመራማሪዎች እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።
Page 9 of 677