Administrator

Administrator


               “ትራምፕ የልቡን ስለሚናገር እወደዋለሁ” - የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ

   የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ናህማት፣ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ በአፍሪካውያን ላይ አስጸያፊ ንግግር ማድረጋቸው አግባብነት የሌለውና የአገራቱ መሪዎች በጋራ የሚያወግዙት ነው ቢሉም፣ የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ በአንጻሩ፣”ትራምፕ ምን ይሉኝ ሳይል የልቡን ስለሚናገር እወደዋለሁ፤ አደንቀዋለሁ” በማለት በዘለፋው አለመቀየማቸውን ገልጸዋል፡፡
ትራምፕ በቅርቡ አፍሪካውያንንና ሃይቲያውያንን በሚመለከት አስጸያፊ ንግግር ማድረጋቸው በተመድ ሳይቀር መነቀፉን ያስታወሰው ኒውስ 24፤ የህብረቱ ሊቀመንበርም ከትናንት በስቲያ ከአዲስ አበባ በሰጡት መግለጫ፣ ዘለፋው አፍሪካውያንን ያስከፋና የጥላቻ ንግግር ነው፤ ህብረቱም አጥብቆ ያወግዘዋል ያሉ ሲሆን  ህብረቱ በማካሄድ ላይ ያለውን ጉባኤ ሲያጠናቅቅ በጉዳዩ ላይ ይፋዊ መግለጫ ይሰጣል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተናግረዋል፡፡
የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ በበኩላቸው፣ ትራምፕ አፍሪካውያንን በተመለከተ ያለውን አመለካከትና ስሜት ሳይሸፋፍን እቅጩን ስለሚናገር እወደዋለሁ፤ እኛ አፍሪካውያን ያለብንን ድክመት ለመናገር ቃላት አይመርጥም፣ አካፋን አካፋ ይላል በማለት በትራምፕ ንግግር አለመቀየማቸውን ገልጸዋል ብሏል ዘገባው፡፡

ለ90ኛ ጊዜ የሚካሄደው የ2018 የኦስካር ሽልማት ዕጩዎች ዝርዝር ከሰሞኑ ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ 13 ጊዜ ለሽልማት የታጨው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር፣ በአመቱ በብዛት በመታጨት ቀዳሚነቱን የያዘ ፊልም ሆኗል፡፡
የሮማንቲክ ሳይንስ ፊክሽን ዘውግ ያለው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር፣ በዘንድሮው የኦስካር ሽልማት በብዛት በመታጨት ታሪክ ቢሰራም፣ በኦስካር ታሪክ 14 ጊዜ በመታጨት ክብረወሰኑን ከያዙት ታይታኒክ፣ ኦል አባውት ኢቭ እና ላላ ላንድ ተርታ በመሰለፍ ሌላ ታሪክ መስራቱ ለጥቂት ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡
በ24 የተለያዩ ዘርፎች ዕጩዎች በቀረቡበት በዘንድሮው ኦስካር፣ በብዛት በመታጨት የሚመራው በስምንት ዘርፎች የታጨው ዳንኪርክ ሲሆን፣ ስሪ ቢልቦርድስ አውትሳይድ ኢቢንግ ሚሱሪ በ7፣ ፋንተም ትሬድ በ6 ይከተላሉ፡፡ የ22 አመቱ የፊልም ተዋናይ ቲሞቲ ቻላሜት፣ በኦስካር ታሪክ በለጋ እድሜው ለምርጥ ወንድ ተዋናይነት በመታጨት የሶስተኛነት ደረጃን መያዙን ያስታወቀው ተቋሙ፣ ሁለቱን ደረጃዎች የያዙት ጃኪ ኩፐር የተባለው የ9 አመት ታዳጊና ሚኪ ሩኒ የተባለው የ19 ወጣት መሆናቸውን አስታውሷል፡፡
ኦል ዘ መኒ ኢን ዘወርልድ በሚለው ፊልሙ በምርጥ ረዳት ተዋናይ ዘርፍ ለሽልማት የታጨው የ88 አመቱ የፊልም ተዋናይ ክሪስቶፈር ፕላመር፣ ረጅም እድሜ የገፋ የኦስካር ዕጩ በመሆን በታሪክ ተመዝግቧል፡፡
በብዛት በታጨው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር ላይ የምትተውነው ኦክታቪያ ስፔንሰር፣ ለሶስት ጊዜ ለኦስካር ሽልማት በመታጨት ቀዳሚዋ ጥቁር ሴት ተዋናይት የሚለውን ማዕረግ ከቪዮላ ዳቪስ ጋር ተጋርታለች፡፡ ዴንዘል ዋሽንግተን በበኩሉ፤ ስምንት ጊዜ በመታጨት ቀዳሚው ጥቁር የፊልም ተዋናይ በመሆን ታሪክ ሰርቷል፡፡ ሁለቱም ጥቁር ተዋንያን በብዛት በመታጨት ብቻ ሳይሆን፣ በተከታታይ አመታት ለዕጩነት በመቅረብም ታሪክ መስረታቸው ተነግሯል፡፡የዘንድሮው የኦስካር ሽልማት አሸናፊዎች የሽልማት አሰጣጥ ስነ-ስርዓት፣ በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ በደማቅ ሁኔታ ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

   የተጣራ ሃብታቸው 113.5 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል
   የታዋቂው አማዞን ኩባንያ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ አሜሪካዊው ቢሊየነር ጄፍ ቤዞስ ሃብት፣ ባለፈው ማክሰኞ ብቻ በ2.8 ቢሊዮን ዶላር መጨመሩን ተከትሎ፣ ግለሰቡ በአለማችን ታሪክ እጅግ ከፍተኛውን የሃብት መጠን ያካበቱ ቁጥር አንድ ባለጸጋ መሆናቸውን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
ጄፍ ቤዞስ፤ አማዞን ጎ የተባለውን አዲስ ቅርንጫፍ በሲያትል ባለፈው ማክሰኞ መክፈታቸውን ተከትሎ፣ የኩባንያቸው የአክስዮን ድርሻ መጠን በ2.5 በመቶ ማደጉን የጠቆመው ዘገባው፣ በዚህም የግለሰቡ የሃብት መጠን በ2.8 ቢሊዮን ዶላር በመጨመር 113.5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን አመልክቷል፡፡
ከአማዞን በተጨማሪ የዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ ባለቤት የሆኑት ባለሃብቱ፤ በአሁኑ ሰዓት ያካበቱት የ113.5 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት መጠን በታሪክ ከፍተኛው ሆኖ መመዝገቡን የጠቆመው ዘገባው፣ ቢል ጌትስ በ92.5 ቢሊዮን ዶላር፣ ዋረን በፌት በ92.3 ቢሊዮን ዶላር የሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ይዘው እንደሚከተሉ ገልጧል፡፡
ከኩባዊ ስደተኛ አባትና ከአሜሪካዊት እናት የተወለዱት ጄፍ ቤዞስ፣ በርካታ ኩባንያዎችን በመክፈት ትርፋማ ቢዝነስ ላይ መሰማራታቸውንና ከአጠቃላዩ ሃብታቸው 16 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ የሚይዘው በቴክኖሎጂ የታገዘ የሽያጭ ስራ በሚያከናውነው አማዞን ኩባንያ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለሃብቱ በበጎ አድራጎት ስራ ላይ በስፋት እንደተሰማሩና በቅርቡም ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች መርጃ የሚውል የ33 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ልገሳ ማድረጋቸውን አስታውሷል፡፡


“ኦፕራ ከኔ ጋር ልትፎካከር? አታደርገውም! የምታደርገው ከሆነ ግን፣ ግጥም አድርጌ ነው የማሸንፋት!” - ዶናልድ ትራምፕ

    በቅርቡ በተካሄደው የጎልደን ግሎብ ሽልማት ስነስርዓት ላይ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ንግግር ማድረጓን ተከትሎ፣ በመጪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዲሞክራቶችን በመወከል ከትራምፕ ጋር ትፎካከራለች ተብሎ በስፋት ሲነገርላት የሰነበተቺው ታዋቂዋ የቶክ ሾው አቅራቢ ኦፕራ ዊንፍሬይ፣ በፕሬዚዳንትነት የመወዳደር ፍላጎት እንደሌላት በይፋ ማስታወቋን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ብዙዎች ለፕሬዚዳንትነት እንደምትወዳደር ሲዘግቡ ሰንብተዋል፤ እኔ ግን የምችለውንና የማልችለውን ነገር ጠንቅቄ የማውቅ ሰው ነኝ! የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጎት የለኝም ስትል፣ ኢንስታይል ከተባለው መጽሄት ጋር ከሰሞኑ ባደረገቺው ቃለ መጠይቅ ኦፕራ አቋሟን መግለጧን  ዘገባው አመልክቷል፡፡
ኦፕራ በ2020 በሚካሄደው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደምትሳተፍ የሚገልጸው ወሬ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃንና በማህበራዊ ድረገጾች በስፋት መሰራጨቱን ተከትሎ፣ በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ የተጠየቁት ፕሬዚዳንት ትራምፕ፣ “ይህ እጅግ አስቂኝ ነገር ነው፤ ኦፕራ ከኔ ጋር ልትፎካከር? አታደርገውም! የምታደርገው ከሆነ ግን፣ ግጥም አድርጌ ነው የማሸንፋት!” ሲሉ ምላሽ መስጠታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ቻይና ቴሲጁ ሲቪል ኢንጂነሪንግ ግሩፕ የተሰኘው የቻይና የግንባታ ተቋራጭ ኩባንያ፣ ፉጂያን በተባለው የአገሪቱ ደቡባዊ አውራጃ የሚገኘውን የአንድ ግዙፍ የባቡር ጣቢያ ግንባታ ፕሮጀክት፣በ9 ሰዓታት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ አጠናቅቆ ማስረከቡን ዴይሊ ሜይል ዘግቧል፡፡
ናንሎንግ በተባለው ግዙፍ የባቡር ጣቢያ ፕሮጀክት የግንባታ ስራ ላይ 1 ሺህ 500 ቻይናውያን የግንባታ ሰራተኞች መሳተፋቸውንና ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት በ9 ሰዓታት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ የተቻለው የተጠናና የተቀናጀ ስራ በማከናወናቸው መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሰራተኞቹ በሰባት ቡድኖች ተከፋፍለው እንዲሰሩ የተደረገ ሲሆን፣ በአንድ ጊዜ የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን የሚያስችላቸውን ስልጠና አግኝተው ወደ ስራ መግባታቸውም ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት በዚህ የሚገርም ፍጥነት እንዲያጠናቅቁ እንዳስቻላቸው ተነግሯል፡፡
ባለፈው አርብ በተከናወነው በዚህ እጅግ ፈጣን የግንባታ ስራ፣ ሰባት ባቡሮችንና 23 የቁፋሮ ማሽኖችን ጨምሮ የተለያዩ የግንባታ መሳሪያዎችን መጠቀሙን የጠቆመው ኩባንያው፣ በግንባታው ሶስት የባቡር ሃዲዶችን ወደ አንድ የማቀላቀል፣ የትራፊክ መብራቶችን የመግጠም፣ የተለያዩ የእንቅስቃሴ መቆጣጠሪያ መሳሪያዎችን የመትከልና ሌሎች ስራዎች በሚገርም ፍጥነትና ጥራት መጠናቀቃቸውንም አመልክቷል፡፡


  ታዋቂው የአሜሪካ ኩባንያ ማይክሮሶፍት፣ ቶምሰን ሮይተርስ ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የዓመቱ የአለማችን ምርጥ 100 ታላላቅ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዝርዝር ውስጥ በአንደኛ ደረጃ ላይ በመሪነት መቀመጡን አስታውቋል፡፡
ተቋሙ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ትርፋማነትና ተቋማዊ ብቃት በመመዘን በየዓመቱ ይፋ በሚያደርገውና ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ፣ የኮምፒውተር መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው ኢንቴል የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዝ፣ የኔትወርክ መሳሪያዎች አምራቹ ሲስኮ ሲስተምስ ኩባንያ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ከማይክሮሶፍት፣ ኢንቴልና ሲስኮ በተጨማሪ የአሜሪካዎቹ አፕል፣ አልፋቤት፣ ኢንተርናሽናል ቢዝነስ ማሺንስ ኮርፖሬሽንና ቴክሳስ ኢንስትሩመንት እስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
አስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ውስጥ የተካተቱት የሌሎች አገራት የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ደግሞ የታይዋኑ ሰሚኮንዳክተር ማኑፋክቸሪንግ፣ የጀርመኑ ሳፕ እና ተቀማጭነቱ በደብሊን የሆነው አክሴንቸር መሆናቸውን ተቋሙ ባወጣው መረጃ አስታውቋል።
በዘንድሮው የቶምሰን ሮይተርስ የዓለማችን ምርጥ 100 የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት ሌሎች ታላላቅ ኩባንያዎች መካከልም አማዞንና ፌስቡክ ይገኙበታል፡፡ ከ100ዎቹ ምርጥ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች መካከል 45 በመቶ ያህሉ መቀመጫቸውን በአሜሪካ፣ ጃፓንና ታይዋን  ያደረጉ መሆናቸው የጠቆመው ተቋሙ፤ ሰሜን አሜሪካ 47፣ እስያ 38፣ አውሮፓ 14 እና አውስትራሊያ 1 ኩባንያ በዝርዝሩ ውስጥ ማካተታቸውንም አመልክቷል፡፡

በናሚቢያ የሚገኙ ስደተኛ ዚምባቡዌያውያን ከሰሞኑ አገሪቱን የጎበኙትን አዲሱን ፕሬዚዳንት ኤመርሰን ምናንጋግዋን በአካል በአይነስጋ ለማየት የሚችሉት 16 ዶላር ከከፈሉ ብቻ እንደሆነ ከኤምባሲያቸው በተላለፈላቸው መመሪያ ክፉኛ መቆጣታቸው ተዘግቧል፡፡
የበጀት እጥረት የገጠመው በናሚቢያ የሚገኘው የዚምባቡዌ ኤምባሲ፣ ሙጋቤን ተክተው ወደ ስልጣን የወጡትን የፕሬዚዳንት ምናንጋግዋን ጉብኝት እንደ አንድ የገቢ ማግኛ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም፣ በናሚቢያ የሚገኙ ዜጎቹንና ድሃ ናሚቢያውያንን ፕሬዚዳንቱን በቅርበት ለማየት 16 ዶላር ክፈሉ ማለቱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ኤምባሲው በአንድ ሆቴል ውስጥ 300 ሰዎችን የሚይዝ አዳራሽ በመከራየት ፕሬዚዳንት ምናንጋግዋ በቦታው ተገኝተው ከፍለው ለሚገቡ ዚምባቡዌያውያን ንግግር ያደረጉበትን ፕሮግራም ያዘጋጀ ሲሆን፣ ከፍለው የታደሙ የመኖራቸውን ያህል እንዴት መሪያችንን እንደ ቱሪስት መስህብ ከፍለን እናያለን በሚል ቁጣቸውን የገለጹም ነበሩ ተብሏል፡፡
ምንም እንኳን ደህና ገቢ ያላቸው ስደተኛ ዚምባቡዌያውያን ቀደም ብለው ትኬት ቆርጠው፣ መሪያቸውን ለማየት በሆቴሉ ቢታደሙም፣ ገና አዳራሹ ሳይሞላ የጥበቃ ሰራተኞች ከፍለው ለመግባት የተዘጋጁትንና ከውጭ ቆመው ይቃወሙ የነበሩትን ሰዎች ማባረራቸውንና ይህም ቁጣን መቀስቀሱን ዘገባው አስረድቷል፡፡

 ለኢየሩሳሌም የእስራኤል መዲናነት እውቅና በመስጠታቸው የደረሰባቸውን ዓለማቀፍ ውግዘት ተከትሎ፣ “ብዙ እየረዳኋት አታከብረኝም” በሚል ለፍልስጤም የሚሰጡትን እርዳታ እንደሚቀንሱ ሲዝቱ የነበሩት ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንዳሉትም፣ ለፍልስጤም ስደተኞች ይሰጡት ከነበረው እርዳታ ላይ ከግማሽ በላይ መቀነሳቸው ተዘግቧል፡፡
አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኩል ለፍልስጤም ስደተኞች ስትሰጠው ከነበረው 125 ሚሊዮን ዶላር እርዳታ ከግማሽ በላይ የሚሆነውን ወይም 65 ሚሊዮን ዶላሩን መቀነሷን በይፋ ማስታወቋን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ ይህን ተከትሎም በዌስት ባንክ፣ ጋዛ ሰርጥ፣ ሊባኖስ፣ ዮርዳኖስና ሶርያ የሚገኙ ፍልስጤማውያን ስደተኞች ህልውና ከፍተኛ አደጋ ላይ ይወድቃሉ የሚል ስጋት መፈጠሩን አመልክቷል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፣ አገራቸው ይህንን ውሳኔ ያስተላለፈቺው ማንንም ለመበቀልና ለማጥቃት በማሰብ ሳይሆን፣ ገንዘቡን ከመለገሳችን በፊት በተመድ ስር የሚገኘውን የእርዳታ ተቋም አጠቃላይ አሰራር በጥንቃቄ መፈተሽ በማስፈለጉ ነው ብለዋል፡፡ ተቋሙ ለፍልስጤም ታጣቂዎች ድጋፍ በማድረግና አድልኦአዊ አሰራር በመከተል በእስራኤል ተደጋጋሚ ትችት ሲሰነዘርበት እንደቆየ ያስታወሰው ዘገባው፤የትራምፕ አስተዳደር በተቋሙ አሰራር ላይ ፍተሻ ለማድረግ መወሰኑም ከዚህ ጋር ግንኙነት ሊኖረው እንደሚችል እየተነገረ ነው ብሏል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ከሰሞኑ አፍሪካውያንን በአደባባይ ዘልፈዋል በሚል ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሳይቀር ከፍተኛ ውግዘት የገጠማቸውና በብዙዎች ዘንድ በአእምሮ ጤና ችግር ሲታሙ በቆዩት ዶናልድ ትራምፕ ላይ ምርመራ ሲያደርጉ የቆዩት የዋይት ሃውሱ ሃኪም፣ ማክሰኞ ዕለት በሰጡት መግለጫ፤ ትራምፕ በአእምሮም ሆነ በአጠቃላይ ጤንነታቸው ቅንጣት ታህል ችግር የሌለባቸው ጤነኛ ሰው መሆናቸውን አረጋግጫለሁ ብለዋል፡፡
ከምርጫ ቅስቀሳቸው ጊዜ አንስቶ በሚናገሯቸው አጉል ንግግሮችና በሚወስዷቸው አስደንጋጭ ውሳኔዎች አለም በወፈፌነት ሲጠረጥራቸው የቆዩት ትራምፕ፤ ሌሎች ምርመራዎችን ለሚያደርግላቸው ሃኪም “እባክህን የአእምሮዬንና የአስተሳሰብ ሁኔታዬንም አብረህ መርምረኝ” የሚል ጥያቄ ማቅረባቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤በዚህ መሰረት በተደረገው ምርመራ ሙሉ ጤናማ መሆናቸው መረጋገጡን ገልጧል፡፡ የአእምሮ ብቃታቸው አገር ለመምራት የሚያስችልና ትክክለኛው ደረጃ ላይ ነው የተባለላቸው ትራምፕ፣ አጠቃላይ ጤንነታቸው በጥሩ ደረጃ ላይ ቢገኝም፣ እንቅስቃሴ ማድረግና ከ10 እስከ 15 ፓውንድ ክብደት መቀነስ እንደሚገባቸው በሀኪማቸው መመከራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በሳይቤሪያ በምትገኘው ኦይማይኮን የተባለች የገጠር መንደር ውስጥ በሳምንቱ መጀመሪያ ከዜሮ በታች ኔጌቴቭ 62 ዲግሪ ሴንትግሬድ የደረሰ ሃይለኛ ቅዝቃዜ የተመዘገበ ሲሆን ቅዝቃዜው በመንደሯ የነበረውን የሙቀት መለኪያ መሳሪያ በመስበር ከጥቅም ውጭ ማድረጉ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1993 ከዜሮ በታች 67.7 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ሃይለኛ ቅዝቃዜ የተመዘገበባት መንደሯ፤500 ያህል ቋሚ ነዋሪዎች እንደሚገኙባትና ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰት ያላት መሆኗን የጠቆመው ዘገባው፣ ነዋሪዎች ቅዝቃዜውን ለመቋቋም ተቸግረው እንጨትና ከሰል በማቀጣጠል ህይወታቸውን ለማትረፍ ደፋ ቀና እያሉ እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡
በአለማችን ታሪክ ዝቅተኛው የሙቀት መጠን ሆኖ የተመዘገበው በምስራቃዊ አንታርክቲካ እ.ኤ.አ በ2013 የተከሰተው ከዜሮ በታች ኔጋቲቭ 94.7 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ቅዝቃዜ እንደነበር ዘገባው አስታውሷል፡፡

   ሹዋን ቮኬሽናል ኮሌጅ  ኦፍ ካልቸር ኤንድ ኮሙኒኬሽን የተባለው የቻይና ኮሌጅ ተማሪዎች ሰሞኑን በወሰዱት የሴሚስቴር ማጠቃለያ ፈተና ላይ የመምህራቸውን ስም እንዲጽፉ የሚያዝዝ አንድ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡
ቤጂንግ ታይም እንደዘገበው፤ተማሪዎቹ የሰባት ሰዎችን ፎቶግራፍ የያዘ የጥያቄ ወረቀት የቀረበላቸው ሲሆን ከሰባቱ መካከል መምህራቸውን መርጠው ከስሩ ስሙን እንዲጽፉ ተጠይቀዋል። ጥያቄውን በትክክል የመለሱት ተጨማሪ ማርክ ባይሰጣቸውም፣ የተሳሳቱና መምህራቸውን ወይም ስሙን መለየት ያልቻሉት ግን ካገኙት ውጤት ላይ 41 ነጥቦች ተቀንሶባቸዋል፡፡
በኮሌጁ የሚያስተምሩት ሁ ቴንግ እንደሚሉት፤ በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውን ይህን ጥያቄ በፈተናው ውስጥ ማካተት ያስፈለገው፣ ተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው ባሻገር በዙሪያቸው ላለው ነገር ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጡ ለመገምገም በሚል ነው፡፡ ይህ የኮሌጅ ፈተና ጥያቄ በቻይናውያን ማህበራዊ ድረገጾች መነጋገሪያ ጉዳይ ሆኖ መሰንበቱን የጠቆመው ዘገባው፣ አንዳንዶች ክፉኛ ቢያብጠለጥሉትም የተወሰኑት ግን የመምህርን ስም ማወቅ ግዴታ ነው ሲሉ ድጋፋቸውን እንደሰጡት አመልክቷል፡፡