Administrator

Administrator

ለ75ኛ ጊዜ ለሚከናወነው የ2018 “ጎልደን ግሎብ” ሽልማት በዕጩነት የቀረቡ ፊልሞች ዝርዝር ባለፈው ሰኞ ይፋ የተደረገ ሲሆን  ዘ ሼፕ ኦፍ ዎተር የተሰኘው ፊልም፣ ምርጥ ዳይሬክተርና ምርጥ ሴት ዋና ተዋናይትን ጨምሮ በሰባት ዘርፎች ለሽልማት በመታጨት ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
ስሪ ቢልቦርድስ እና ዘ ፖስት የተሰኙት ፊልሞችም እያንዳንዳቸው በስድስት ዘርፎች ለሽልማት የታጩ ፊልሞች እንደሆኑ የዘገበው ቢቢሲ፤ ሌዲ በርድ የተሰኘው ፊልም በበኩሉ፣ በአራት ዘርፎች በመታጨት ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን አመልክቷል፡፡
በቴሌቪዥን ተከታታይ ድራማዎች ዘርፍ፣ ለዘንድሮው የ”ጎልደን ግሎብ” ሽልማት ከታጩት መካከል፣ በስድስት የተለያዩ ዘርፎች የታጨው ቢግ ሊትል ላይስ በብዛት በመታጨት ቀዳሚነቱን ይዟል ተብሏል፡፡
የሆሊውድ የውጭ ፕሬስ ማህበር የሚያዘጋጀው አመታዊው የ”ጎልደን ግሎብ” ሽልማት አሰጣጥ ስነስርዓት በመጪው ጥር ወር መጀመሪያ ላይ በቢቨርሊ ሂልስ ካሊፎርኒያ በደማቅ ሁኔታ ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


    ኩራዝ ኢንተርናሽናል አሳታሚ ድርጅት ኦሮምኛ ቃላትን ወደ እንግሊዝኛና አማርኛ የሚተረጉም “ኦዳ” የተሰኘ መዝገበ ቃላት ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ስታዲየም ፊት ለፊት በሚገኘው የኦሮሞ ባህል ማዕከል ያስመርቃል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ኃላፊዎች፣ የመንግስት ባለስልጣናትና ደራሲያን ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል፡፡

 በሩሲያ የሳይንስና የባህል አዳራሽ (ፑሽኪን) በአይነቱ ልዩ የሆነ የሙዚቃ ኮንሰርት ዛሬ ከቀኑ 9፡30 ጀምሮ እንደሚካሄድ ማዕከሉ አስታወቀ፡፡ የሩሲያ ታዋቂ ሙዚቀኞች  ይሳተፉበታል በተባለው በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ ቫስሊ ፓደለስኒ የተባለው ፒያኖ ተጫዋችና ያና ጋይዱኬቪች የተባለችዋ ቫዮሊን ተጫዋች እንደሚሳተፉ የተገለፀ ሲሆን መግቢያው በነፃ  እንደሆነ ታውቋል፡፡
 በዕለቱ የሩሲያ የሻይ ስነ-ስርዓትና የኮክቴል ግብዣ መሰናዳቱን ገልፀው- ማዕከሉ ሁሉም ሰው በኮንሰርቱ ላይ ተገኝቶ ጥሩ ጊዜ እንዲያሳልፍም ጥሪ አቅርቧል፡፡

 አማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከብሬማን ፊልም ፕሮዳክሽን ጋር በመተባበር በአዕምሮ ህመም ላይ ያተኮረና ለማህበሩ ግንዛቤ ያስጨብጣል የተባለ ነጠላ ዜማ ከነገ በስቲያ ሰኞ ከምሽቱ 12፡00 ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ይመረቃል፡፡
የአገራችን እውቅ አቀንቃኞችና የሙዚቃ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል የተባለው ነጠላ ዜማ፣ ቪዲዮ የተሰራለት ሲሆን የምርቃት ስነ-ስርዓቱ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሙዚቃ ሰዎች፣ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎችና የህክምና ባለሙያዎች በተገኙበት እንደሚካሄድ ሆስፒታሉ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

  ሁለተኛው ምጣት “The second coming” የትኛው “ምጣት” ነው? ዊሊያም በትለር ዬትስ “Things fall apart/the center can not hold/… ያለው ማለቴ ነው፡፡ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት አይደለም፡፡ እሱ አልፏል፡፡ … በወቅቱ የነበሩት ሁለተኛው የዓለም ጦርነት የዓለም ፍፃሜ መስሏቸው ነበር፡፡ አሁን እኔ እየተመለከትኩ ካለሁት ዓለም ጋር ሳነፃፅረው፣ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት እንደ ፍፃሜ ሳይሆን እንደ መልካም መጀመሪያ ውብና የሚናፈቅ ሆኖ ነው፡፡
በአጭሩ አሁን ያለሁበትን፣ የሚታየኝን ዓለም ልገልፀው ፈለግሁኝ፡፡ መግለፅ መፍጠር ነው፡፡ የዊሊያም በትለር ዬትስ “Second coming” የተፃፈው ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት ቀደም ብሎ ነው፡፡ በቅርብ የተነጣጠረ ራዕይ ሊባል ይችላል፡፡ ሁለተኛውን የዓለም ጦርነት እንደ ክርስቶስ መምጫ አድርጎ ነበር የቆጠረው፡፡ ዊሊያም በትለር ዬትስ “በቅርቡ የዓለም ፍፃሜ ይከሰታል” ለማለት ነበር ግጥሙን የፃፈው፡፡
ዓለም እንደ ግጥሙ በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ዳር እስከ ዳር ተንጣለች፡፡ ግን ፍፃሜ ደረጃ አልደረሰችም፡፡ ገጣሚው ራዕዩን ለቅርብና ለሩቅ እንዲሆን አነጣጥሮ ነው የተኮሰው፡፡ ለሰማይና ለጣራ በአንድ ጊዜ አልሞ ነው ግጥሙን ራዕይ አድርጎ የፃፈው፡፡ ጣራው ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ሆነ፡፡ ሰማዩ የመጨረሻው የዓለም ፍፃሜ፣ የክርስቶስ መምጫ፣ የቅያማ ቀን … ወዘተ፡፡ የዊሊያም በትለር ዬትስ ግጥም፣ ለአጭር ጊዜና ለመጨረሻውም ጊዜ የሚሰራ ነው፡፡ የመጨረሻው ዘመን በቅርቡ ከመጣ ጣራው ሰማይ ይሆናል፡፡ መጨረሻ መስሎ ማለፊያ የሆነ የሰቆቃ መሸጋገሪያ ከተገኘም ግጥሙ መጨረሻውን ለመጠባበቂያ ይሆናል፡፡
ምናልባት ልዕለ ጥበበኛ “በጥበብ ዘመን ተሻጋሪ ይሆናል” የሚባለው እንዲህ በስራው ውስጥ የረጅምና የአጭር ጊዜ አላማ እያስቀመጠ ስለሚያልፍ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ጥበበኛው ዬትስ በ“second coming” ግጥሙ እጅግ ስኬታማ ሆኗል፡፡ ግጥሙ በሌሎች ከባድ ሚዛን ገጣሚያንና ደራሲያን ተደጋግሞ ተጠቅሷል፡፡ የቺኑዋ አቼቤ “Things fall apart” የሚለው የአንዱ ድርሰት ስራው አርዕስት በዚሁ “የሁለተኛ ምጣት” ግጥም አንጓ የተቀነጠሰ ነው፡፡
እርግጥ እኔ ገጣሚ አይደለሁም፡፡ ግን ፎርሙላው ገብቶኛል፡፡ ወደፊት የሚከሰተውን ለማወቅ እንደ ታሪክ አዋቂዎች የቀድሞውን ታሪክ ማጥናት አያስፈልገኝም፡፡ ከኋለኛው ታሪክ አንድ ነጥብ ብቻ እይዛለሁኝ፡፡ ወደ ኋላ ያለው ታሪክ “መጀመሪያ” አለው፡፡ ይኼ ነጥብ በቂ ነው፡፡ የኋለኛው ታሪክ መጀመሪያ እንዳለው ሁሉ … መጪው ታሪክ ደግሞ “መጨረሻ” አለው፡፡ ይኼንን የሚያውቅ ሁሉ ባለ ራዕይ ነው፡፡ የተጀመረው ነገር መጠናቀቁ አይቀርም፡፡ መጠናቀቁ እንደማይቀር በደመነፍስ ሳይሆን በሳይንስም ሆነ በፍልስፍና ሜታፊዚካል መጠይቅ መልክ ተጠቅመን ብንመረምር የምንደርሰው አንድ ነጥብ ላይ ነው፡፡ የተጀመረ ነገር ሁሉ መጠናቀቁ … በዚህም ተባለ በዛ አይቀርም፡፡
ምናልባት ልዩነትና የሀሳብ ግጭት ሊነሳ የሚችለው ከዚህ ጥልቅ ስምምነት ወደ ተናጠልና “specific” ጉዳዮች ስንመጣ ነው፡፡ ለምሳሌ መጨረሻው መቼ ነው በእርግጥ የሚሆነው? … ያወዛግባል፡፡ ከጊዜ ጋር የ “ሳቢያ ወይንም መንስኤ” ጉዳይ ይመጣል፡፡  በምን ምክኒያት ነው መጨረሻው በተባለው (መቼ) ላይ የሚያርፈው፡፡ በግርድፉ ነጥብ፤ ማለትም “የተጀመረ ነገር መጠናቀቁ አይቀርም” የሚለውን በተመለከተ ሁላችንም ባለ ራዕይ ነን፡፡ ልዩ ባለ ራዕዮች የሚያስፈልጉት የጊዜና ቦታ፣ የሳቢያና መንስኤን … ትንንሽ ጥያቄዎች እንዲመልሱልን ብቻ ነው፡፡ ትልቁን እውነት ሁላችንም እናውቀዋለን፡፡ ጥቅሉን እውነት በማወቅ ረገድ ሁላችንም አንድ አይነት ነን፡፡ ልዩነት የሚመጣው በትንንሾቹ ጥያቄዎች ላይ ነው፡፡
በአእምሮአችን የሚመጡ ሀይማኖታዊም ሆኑ ዓለማዊ ባለ ራዕዮች ወይንም ትንቢት ተናጋሪዎች ትንንሹን ጥያቄ ለመመለስ የቻሉ ናቸው፡፡ ግን ትንንሾቹን ጉዳዮች በደንብ ቢተነብዩም ስለ መጨረሻው ግን የሰጡት ትንበያ ትክክል መሆኑ የሚታወቀው ፍፃሜው ላይ ነው፡፡
ባለ ራዕይ ማለት፤ መጨረሻውን በቅርብና በሩቅ በሁለቱም አንፃር ገፍቶ ጥሩ ግምት ማስቀመጥ የቻለ ማለት ነው ለኔ፡፡ ዊሊያም በትለር ዬትስ ይሄን ነው በግጥም ያደረገው፡፡ ምጣት አንድ ሆኖ እንደማይቀር ገብቶታል፡፡ እሱ ብቻ ሳይሆን ሁላችንም ይገባናል፡፡ ሁላችንም ባይገባን ኖሮ ግጥሙም በተለያዩ የፍፃሜ አደጋ ሞዴሎች ላይ እየለዋወጥን ባልሞከርን … ግጥሙም ተራ ሆኖ በተረሳ ነበር፡፡
ግን ዊሊያም በትለር ዬትስ እኛ የምንፈራውን የሚፈራ፣ እኛ የምናውቀውን የሚያውቅ ገጣሚ ነው፡፡ እኛ የምንፈራው ፍፃሜውን ነው፤ እኛ የምናውቀው መጨረሻው እንደማይቀር ነው፡፡ አንዴ መጥቶ፣ የመጣበትን ግብ ሳይፈፅም የሄደ ጥፋት ተመልሶ መምጣቱ እንደማይቀር እንሰጋለን፡፡ ስጋታችን ከምናውቀው ነገር የመነጨ ነው፡፡ እውቀታችን ለሁላችንም አንድ ነው፡፡
ክርክሩ ያለው የጊዜና ሳቢያ መንስኤ ላይ እንጂ መምጣቱ የማይቀረው መጨረሻ “እንደወጣ እንደማይቀር” እናውቃለን፡፡ ክርክሩ ያለው “ጊዜው አልደረሰም” እና “ጊዜው ደርሷል” በሚሉ ገማቾች ላይ ነው፡፡ አሁን ባይደርስም መድረሱ ግን እንደማይቀር ሁሉም ያውቃል፡፡
ገጣሚ፣ ጥበበኛ ጥበቡን ዘላለማዊ ለማድረግ ካለው ፍላጎት የተነሳ እሱም ከጊዜ ጋር ጠበኛ ነው፡፡ ሀይማኖተኞች ወይንም ትንቢተኞች (ሳይንስም የትንቢተኛ አይነት ነው፤ የትንበያ ዘዬው ቢለያይም) “ጊዜው አልደረሰም/ደርሷል” ነው የሚያከራክራቸው፡፡ ለቅርብም የሚሆን ዜማ ይፈበርካል፡፡ ቅርበትና ርቀት መሀል ያለውን የጊዜ ትርጉም የሚዋጅ ግጥም ከተፈበረከ ጊዜ ከጥቅም ውጭ ይሆናል፡፡ ወይንም በገጣሚ ሰለሞን ደሬሳ አገላለፅ፡- “የጊዜ ቋንጃ ተበጥሷል፡፡” “የት ይደርሳል የተባለ ጥጃ ልኳንዳ ቤት ቀረ” የሚል የመዘባበቻ ሀረግ አብዝተን ስንጠቅስ እንደመጣለን፡፡ ጥጃውን መመሰል የተፈለገው በሰው ልጅ ነው፡፡ እንጂማ ጥጃ የት ይደርሳል፣ ከልኳንዳ ቤቱ ውጭ? …
ግን እቺ የጥጃ አባባል የቅርቡን ራዕይ የምትገልፅ ትመስለኛለች፡፡ የሰው ልጅ ስንት ጠፈር ቧጥጦ፣ ስንት ተአምር ይፈጥራል ሲባል፣ በሁለተኛው አለም ጦርነት ኒዩክለር ቦንብ እርስ በራሱ እጣ ተጣጥሎ ድምጥማጡ ጠፋ … እንደ ማለት ሊታይ ይችላል፡፡ ግን የፈለገ ጠፈር ቢቧጥጥም “በስተመጨረሻ እህሳ?!” ከተባለ፣ ያው ፍፃሜው ጋር ደረሰ ነው መልሱ፡፡ የጥጃውም መጨረሻ ልኳንዳ ቤቱ፣ የሰውም ፍፃሜ ሞቱ ነው፡፡ አሰቃቂ ወይንም ሰላማዊ ብለን ሞቱ የቀረበበትን ሁኔታ ብንገልፀውም በመጨረሻው ሞቱ ነው፡፡ መጨረሻው ይህ መሆኑን ሁሉም ያውቃል፡፡ የት ይደርሳል የተባለ! እያለ ይዘባበታል፡፡ ህይወቱን በተለያየ ሰው ሰራሽ ትርጉሙ ቅርፅ አንፆ፣ መጨረሻውን የረሳ ይመስላል፡፡ አንድ ባለ ራዕይ በገጣሚ ወይንም በትንቢት ተናጋሪ መልክ ተነስቶ ስለማይቀረው ነገር ሲያስታውሰው ይደነግጣል፡፡ የመደንገጥና የማስደንገጥ ሚና ለራሳቸው በይነው የሚንቀሳቀሱ ሰዎች አሉ፡፡ አስደንጋጮቹ “ጊዜ ደርሷል!” የሚሉት ናቸው፡፡ “ወይኔ ኖሬ ሳልጠግብ፣ መሞት ሳልለማመድበት” ብለው የሚደነግጡትን የሚያስጥሉ አላጋጭ ነን የሚሉ ይነሳሉ - “የዓለም ፍፃሜ ደርሷል” የሚሉት ውሸት ነው … ፀሐይ ተነፋፍታ እስክትፈነዳ 20 ቢሊዮን አመት ገና ይፈጃል ይላሉ፡፡
ካርል ፓፐር የሚባል በሳይንስ ላይ ጥሩ አድርጎ በመፈላሰፉ የሚከበር ሰው፣ ስለ ትንቢት የሚለው ነገር እኔ ከምለው ጋር በጣም ልዩነት እንዳለው መጠቆም እፈልጋለሁኝ፡፡ ፓፐር በመሰረቱ ትንቢትና ሳይንስ ሁለት በተለያዩ ቋንቋ የሚያወሩ፣ አንዱን ቋንቋ ወደ ሌላው መቀየር የማይቻል፣ የተለያዩ አለማት ፍጥረት ናቸው ይላል፡፡ ወይንም እንደማለት ይቃጣዋል፡፡
እሱ ትንቢትን እምነት በሚል መጠቅለያ ነው የሚጠራው፡፡ እምነት ማለት እኔ ከላይ ስፅፍ የመጣሁትን ሁሉ ሳያጓድል ይላል፡፡ ሀይማኖት ግን እኔ ስል ከመጣሁት በተጨማሪ ከማይቀረው መጨረሻ ማስጣያ መፍትሄው እኔው ዘንድ ነው ይላል፡፡ በዓለም ላይ የገነኑ ሀይማኖተኞች በተለይ ከክርስትና በኋላ ያሉት ይሄንን ነው የሚሉት፡፡ የማስጣያ መፍትሄው ሁሉም ሀይማኖቶች ጋር ሳይሆን “እኔ ብቻ” ጋር ነው የሚለው ያስማማቸዋል፡፡ … ለሁሉም የማይቀረው መጨረሻ “ከእኔ ብቻ ጋር ከሆንክ” ለአንተና እኔ የመጨረሻው መጀመሪያ ይሆንልናል…፡፡ ሁሉም በተናጠል … በእየ ዘውጋቸው ሆነው ይሄንን ይላሉ፡፡ ያሉትን ለማሳመን ይጥራሉ፡፡
ካርል ፓፐር “ትንቢት ወይም ሀይማኖት ሊመረመር (verify ሊደረግ) ስለማይችል ውሸት መሆኑንና ማረጋገጥ፣ ወይንም መፈተን አይቻልም” ይላል፡፡ በካርል ፓፐር ፍልስፍና፤ ዋነኛውና እና ቁልፉ ነገር “falsifibility” ነው፡፡ “አንድን ሀሳብ ወይንም ኩነት ውሸት መሆኑን ማረጋገጥ በሚያስችል ደረጃ ሊፈተን የሚችልበት ክፍተት ከሌለው … ይሄ ነገር ሃይማኖት ነው” ይላል፡፡ ይቀጥልናም፤ “ሁሉም “ሳይንስ” … ውሸት መሆኑን የሚያሳይ ክርክርን የማስተናገድና በቤተ ሙከራ የመፈተን ክፍት አቋም አለው” ይላል፡፡
በዚህ ሀሊዮት አንፃር እኔ እየፃፍኩ የመጣሁትን ምልከታዬን አጉልተን ስንመለከተው፣ ትንቢት እንጂ ሳይንስ እያወራሁ እንዳልሆነ ወዲያው ግልፅ ይሆንልናል፡፡ እኔ ከመነሻው እንደ ሚስማር እየደጋገምኩ ስቀጠቅጠው የነበረ አረፍተ ነገር ነበር፡፡ ይኼ አረፍተ ነገር “መጀመሪያው እንዳለ ሁሉ መጨረሻው መኖሩ አይቀርም” የሚል ነው፡፡ መጨረሻው ስለመኖሩ ከእምነት ውጭ ፍፃሜውን አቅርቦ በማሳያ መነፅር አስጠግተን ማጥናት ስለማንችል፣ ይህ አረፍተ ነገርን በሳይንሳዊ መንገድ “falsify” ማድረግ አንችልም፡፡ በሳይንሳዊ መንገድ ሊመረመሩና መረጃ ሊቀርብባቸው የማይችሉ ድምዳሜዎች ሁሉ በ“ሃይማኖት” ወይ “እምነት” ዘውግ ስር ለካርል ፓፐር የሚካተቱ ናቸው፡፡ … በሳይንስ ተመርምረው የእውነት (fact) እና የውሸት (belief) መጠናቸው ሊታወቅ (verify ሊደረግ) አይችልም፡፡ ስለማይችል አይመረመሩም፡፡ ስለማይመረመሩ ሃይማኖት ናቸው፡፡ ሃይማኖት ከትንቢት ንጥረ ነገር የሚሰራ ርዕዮተ ዓለም (world view) ነው፡፡ ሳይንስ ደግሞ ከተጨባጭ መረጃ፡፡         

 “--እውነት እኔ ሌሎችን ለመምራት ተዘጋጅቻለሁ? አቅሙ፣ እውቀቱና ትዕግስቱ አለኝ? በመንገዴ ከእኔ የተሻለ እኔንና ሌሎችን ሊመራ የሚችል ሲገኝ መንገድ የምለቅ ነኝ? ማንንስ ወዴት ለመምራት ነው የተዘጋጀሁት? እንዳሰብኩት ባይገኝ ወይም ቢገኝ ቀጣዩ ሚናዬ ምን ሊሆን ይችላል የሚሉትን እና የመሳሰሉትን ለእራስ መመለስ የግድ ይላል፡፡--”


    አሪቲሚያ ስለሚባለው የልብ የኤሌክትሪክ ስራዎች እክል ሳነብ፣ ሁሌም ወደ አዕምሮዬ ላይ የሚመጣብኝ የአብዛኞቻችን ኑሮ፣ ይበልጥ ደግሞ የአገራችን ሁኔታ ነው፡፡ አብዛኛው ነገር ከዚህ የልብ የአሌክትሪክ ስራዎች እክል ምክንያቶችና መፍትሔዎች ጋር ትልቅ ቁርኝት ያለው ይመስለኛል። እንዲህ ነው ነገሩ፡- ልባችን እንደ ሌሎች የሰውነት ክፍሎቻችን ሴል በሚባሉ ህዋሳት የተገነባች ሲሆን እነዚህ የልብ ህዋሳት (ልባችን የተዋቀረባቸው ማለት ነው) አራት ዋና ዋና ባህሪያቶች አሏቸው። አንደኛው ‘አውቶማቲሲቲ’፣ ይህም ያለ ማንም ትዕዛዝና እርዳታ በእራሷ ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ሲሆን የሁሉ ተቆጣጣሪ የሚባለው አዕምሯችን (አንጎላችን) እንኳን በቀጥታ ጣልቃ የማይገባበት ነው፡፡ ሁለተኛው ‘ኤክሳይተብሊቲ’፣ ይህም በመነጨው ኤሌክትሪክ ስራ ለመስራት የመነቃቃት አቅምን የሚገልጽ ነው። ሶስተኛው ‘ኮንዳክሽን’፣ ያገኙትን ኤሌክትሪክ ለሌላውም የልብ ክፍል በቅብብሎሽ የማድረስ ወይም በሌላ ቋንቋ ኤሌክትሪክ የማስተላለፍ አቅም ነው። አራተኛው ወይም  የመጨረሻው፣ በደረሳቸው የኤሌክትሪክ ንዝረት የልብ ጡንጫዎች በመኮማተር ደምን ወደተለያዩ የሰውነት ክፍሎች የመርጨት አቅም፣ ማለትም ‘ኮንትራክቴቢሊቲ’ ናቸው፡፡ ታዲያ ሁሉም የልብ ህዋሳት (ክፍሎች) እነዚህ አራቱም ባህሪያት አሉን ብለው፣ በየራሳቸው ኤሌክትሪክ ቢያመነጩ ወይም ቢያስተላልፉ በልብ ውስጥ ዝብርቅርቅ ያለ፣ ያልተደራጀና ደምን ወደተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ሊረጭ የማያስችል ሁናቴ ውስጥ እንገባለን፡፡ ይህ ደግሞ ወደ ሞት ጎዳና የሚወስደን ይሆናል፡፡
 ፈጣሪያችን ሲሰራን ታዲያ ለዚህ መፍትሔ አዘጋጅቶ ነው፡፡ ይህም በልባችን ውስጥ ዋነኛ ስራቸው ኤሌክትሪክ ማመንጨት የሆኑ የጎበዝ አለቆችን ከመረጠ በኋላ ከእነርሱ የመነጨውን ኤሌክትሪክ ወደተለያዩ የልብ ክፍሎች የሚያደርሱ ማስተላለፊያዎችን (ትራንስፎርመር ልንላቸው የምንችል ይመስለኛል) በማዘጋጀት፣ ወጥ የሆነ የኤሌክትሪክ ፍሰት እንዲከናወንና  ደምን በትክክል መርጨት የሚችል የጡንቻ መኮማተር እንዲኖር በማድረግ ነው፡፡ እነዚህ የጎበዝ አለቆች ኤስ ኤ ኖድ፣ ኤቪ ኖድ እና ፑርኪንጅ ፋይበር (ከአራቱ በበላይነት ኤስ ኤ ኖድ ይህን ስራ ይሰራል) በመባል ይጠራሉ። ወደ ገደለው ግባ ሳትሉ እንደማትቀሩ እገምታለሁ። በመቀጠል ለማነሳቸው ሃሳቦች ደጋፊ ስለሆኑ፣ በደንብ ተከተሉኝማ፡፡ እናላችሁ ከላይ እንደገለጽኩት፣ በሞት እስከምንለይ ያለማቋረጥ ኤስ ኤ ኖድ ከሚባለው ኤሌክትሪክ እየመነጨና ወደተለያዩ የልብ ክፍሎች እየተላለፈ፣ የልብን ጡንቻዎች እንዲኮማተሩ በማድረግና ደምን በመርጨት ህይወት ትቀጥላለች። ይህ ተፈጥሯዊው የልብ አሰራር ሲሆን በተቃራኒው በተለያዩ ችግሮች ምክንያት የልብ ኤሌክትሪክ አሰራር እክል ሊፈጠር ይችላል፡፡ ይህም የእዚህ ጽሑፍ አስኳል ነው፡፡ አሁንም ተከተሉኝማ፡፡
የዚህ የልብ የኤሌክትሪክ እክል (ህመም) ቬንትሪኩላር ፊብሪሌሽን ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህ ችግር የሚከሰተው የጎበዝ አለቆች የተባሉት እነ ኤስ ኤ ኖድ፣ በትክክል ኤሌክትሪክ ማመንጨት ሲያቅታቸውና ደምን ወደተለያዩ ክፍሎች የሚረጩት ቬንትሪክል የተባሉት የልብ ጡንጫዎች ላይ ያሉት ህዋሳት ሲያምጹ የሚከሰት ነው፡፡ አመጹ እንደ ሁከት አይነት ነው፡፡ ልክ መሪዎች በትክክል አልመራ ሲሉ በየአካባቢው ሁሉም እየተነሳ መሪ ልሁን እንደሚለው አይነት ነገር! በቃ ሁሉም ህዋሳት ከተለያዩ ቦታዎች ያልተናበበና የጡንቻ መኮማተርን የማይፈጥር፣ ከዚህም ብልጭ ከዚያም ብልጭ የሚል ኤሌክትሪክ የማመንጨት ስራ ይጀምራሉ። ይህም ልብን በጭንቅ የማንቀጥቀጥ፣ የማራድ አይነት ሰቀቀን ይፈጥራል፤ ወይ እነዚህ ሃይል ኖሯቸውና ተናበው ደም እንድትረጭ አልሆነ፤ በሌላ በኩል ደግሞ አቅሙና ችሎታው ያላቸው የጎበዝ አለቆች ካንቀላፉበት ተነስተው ልብን ወደተሻለ እንቅስቃሴ አልመሯት፡፡ አቤት በዚህ ጊዜ ያለው የልብ ጭንቀት! ነፍስ ውጪ ነፍስ ግቢ በሉት። በነገራችን ላይ ይህ አይነቱ ችግር በድንገተኛ ህክምና ዘርፍ ለአፍታ ጊዜ ከማይሰጣቸው ገዳይ ህመሞች መካከል ዋንኛው ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ ታዲያ በዚህ ጊዜ ነው ሁነኛ የህክምና ባለሙያና የህክምና መሳሪያ የሚያስፈልገው፡፡ እነዚህን ከተለያዩ ስፍራዎች የሚነሱትን ወጀቦች ጸጥ የሚያደርግና ወደቀደመው መልካሙ የመርከቧ (የልባችን) እንቅስቃሴ እንዲመለስ የሚያደርግ መላ! ይህ መላ በህክምና አጠራሩ ዲፊቢሪሌሽን ሲባል፣ ለዚህ የሚረዳን የህክምና መሳሪያ ደግሞ ዲፊቢሪሌተር ይባላል፡፡ ስራው ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? በቃ ከተለያዩ የልብ ክፍሎች እዚህም እዚያም እየመነጨ ዘራፍ የሚለውን ኤሌክትሪክ ቀጥ በማድረግ፣ ለጎበዝ አለቆች (ዋንኛ ኤሌክትሪክ አመንጪዎች) እድል መስጠት ሲሆን በዚህም መሪና ተመሪን እንዲደማመጡ በማድረግ፣ ሁሉንም በሚጠቅምና በሚያኖረው የኤሌክትሪክ ፍሰት ተዋረድ ልብን መታደግ ነው፡፡
ታዲያ ልባችንን በአገር ብንመስለው፣ ሃገር የተዋቀረበትን ህዝብ፣ የልብ ህዋስ (ሴል) ብንለው፣ የጎበዝ አለቆች የአገር መሪዎች ቢሆኑ፣ ምሳሌው አሁን ያለንበትን የፖለቲካ ሁኔታ አያሳይ ይሆን?
ተመልከቱ እስቲ! ህዝባችን በትክክል የሚመሩት የሀገር መሪዎች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የመስሪያ ቤት ሃላፊዎችና የመሳሰሉትን አጥቶ፣ ታግሶ ታግሶ! ጠብቆ ጠብቆ! ቀምበር ሲበዛበት መፍትሔ ይሰጡኛል በሚላቸው የተለያዩ ሃሳቦችና ቡድኖች፣ ከዚህም ከዚያም የመሰለውን እንቅስቃሴ እያደረገ ያለ አይመስላችሁም፡፡ በዚህም መነሾነት ምንም እንኳን እንቅስቃሴው ብሶት የወለደው ቢሆንም በእራሱ ሌላ ችግር እየፈጠረ፣ ፍሬ ያላፈራና አለመደማመጥን እየፈጠረ ያለ እንደሆነ አይሰማችሁም? እንደው በዚህች አጭር ጊዜ እንኳን ስንቱ በተለያየ ቦታ ደሙ ፈሰሰ፣ አካሉን አጣ፣ ተሰደደ፣ እንቅልፉን አጣ፣ ስንቱ ከፈጣሪው ኮበለለ፣ ስንቱ ሃይማኖት ጭራሽ አያስፈልገኝም አለ፣ ስንቱ ንብረቱን በከንቱ አጣ፣ ሃሞቱ ፈሰሰ፣ አረ ስንቱ ስንቱ…
ከወዲህ ገዢው መንግስት ዘላቂ መፍትሔ መስጠት ሲያቅተው፤ ወዲህ መምራት እንችላለንም ከሚሉት ተቃዋሚዎች ጠብ የሚል ነገር ሲጠፋ፤ በሌላ በኩል ጦማሪዎች (አክቲቪስት) ሃገሪቱን ከወዲህ ወዲያ ከማንቀጥቀጥ በዘለለ ለውጥ ማምጣት ሳይችሉ ሲቀር፤ ከወዲህም አቅሙ እያላቸው “ጎመን በጤና” ብለው እያንቀላፉ ባሉት ሰዎች ሁሉ ድምር፣ የሰይጣን ጆሮ ይደፈንና---- እቺ ሃገር ወደ መቃብሯ እየሄደች ያለ አይመስልም? አረ ዲፊብሪሌተር ወዴት አለህ? ወጀቡን ጸጥ አስደርገህ፣ አቅሙ ላለው በትሩን የምትሰጥ ወዴት አለህ?!!
እስቲ በህዝብ ወገን ሆነን እራሳችንን እንመልከት፡፡ እያንዳንዳችንስ በሚገባን ሚናችንን እየተወጣን ነው? በትክክል የተመሪነት ሃላፊነታችንስ  ስራ እንደሚጠይቅ ተረድተናል? በሃገራችን ጉዳይ እውነት ነው በእኩል ሁላችንም ያገባናል፡፡ ነገር ግን በተሰማራንበት የስራ ዘርፍና ሚና፣ ይህን ያገባኛል ስሜት ካልተወጣነው ምን ዋጋ ይኖረዋል! በትክክል ተመሪ ሆኖ ያላለፈ ሰውስ እንዴት ወደፊት መሪ ሊሆን ይችላል? እስቲ የመሪነት እድሉን ይስጡኝ እና በተፈተንኩ የምንል ብዙ አለን፡፡ በተቃራኒው ግን አሁን እየሰራን ባለነው ስራ ላይ እንኳን ጉድለታችን ብዙ ነው፡፡ የመሪው ወንበር እኮ አይደለም ስራ የሚሰራው፤ እኛ ነን ፈላጭ ቆራጩ! የሃገራችን የአዙሪት የኋልዮሽ ጉዞ ምክንያትም ይህ ተመሳሳይ ስህተትንና አስተሳሰብን ሁሌ በተለያየ ቀለም እየቀቡ መኖሩ ላይ ይመስለኛል። እስቲ አኗኗራችንን፣ አሰራራችንንና አካሄዳችንን እንመልከት! በጣም ቅጥ ያጣ ዲፊብሪሌሽን (አስቁሞ እንደ አዲስ ስራ ማስጀመር) የሚያስፈልገው እየሆነ እኮ ነው፡፡ ሁላችንም እራሳችንን በመሪነት ስፍራ ብቻ ካስቀመጥን ሁሉስ መሪ፣ ሃላፊና አዛዥ ከሆነ፣ ሌላውን የተመሪነት ስራ ማን ይስራው? የተሻለ መሪ ናፍቆን የተሻለ ተመሪ ካልሆንን ለውጥስ እንዴት ሊመጣ ይችላል? የተሻለ የመስሪያ ቤት ኃላፊ ፈልገን፣ የተሻለ ለለውጥ የተዘጋጀ ታታሪ ሰራተኛ ካልሆንን ምን ዋጋ አለው? እውነቱን እንነጋገር ከተባለ፣ ልክ እንደዛች የታመመች ልብ በተለያዩ ስፍራዎች፣ አስተሳሰቦችና ርዕዮተ አለሞች ተቧድነን፣ ሁላችንም ሃገሪቱን እንምራት እያልን እኮ ነው! ዘንድሮ ያልተገኘ እድል መቼም አይገኝም በሚመስል አስተሳሰብ፣ ሃገሪቱና አለማችን ነገ የማይገኙ እስኪመስል ድረስ መንገብገብ፣ ለወለድናቸው ቀጣዩ ትውልድ አለማሰብም ጭምር ይመስለኛል፡፡ ይህ ደግሞ የሃገርን ፊብሪሌሽን (መንቀጥቀጥ) ከመፍጠር የዘለለ ምንም ውጤት አያስገኝልንም፡፡ አንዳንዴም እኮ አቅሙ ላላቸውና ሁላችንንም ሊያኖሩን ለሚችሉ አለቆች፣ እድል የመስጠትና የመመራት ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል፡፡ እሺ ይሁን ግን እንዴት? ካልን፣ መጀመሪያ ሁላችንም አቅማችንን መፈተሽ ይኖርብናል ነው መልሱ፡፡ እውነት እኔ ሌሎችን ለመምራት ተዘጋጅቻለሁ? አቅሙ፣ እውቀቱና ትዕግስቱ አለኝ? በመንገዴ ከእኔ የተሻለ እኔንና ሌሎችን ሊመራ የሚችል ሌላ ሲኖር መንገድ የምለቅ ነኝ? ማንንስ ወዴት ለመመራት ነው የተዘጋጀሁት? እንዳሰብኩት ባይገኝ ወይም ቢገኝ ቀጣዩ ሚናዬ ምን ሊሆን ይችላል የሚሉትን እና የመሳሰሉትን ለእራስ መመለስ የግድ ይላል፡፡ ያለበለዚያ ግን ጊዜው ስለፈቀደልን ብቻ በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃንና ማህበራዊ ድረ-ገጾች አልያም እጃችን ላይ ባለው መሳሪያና አሰራር ብቻ ተማምነን፣ ሃገሪቱን ወደተሻለና ሰላማዊ ወደሆነው ጉዞ በማይወስዳት ጽንፍ ውስጥ መግባት፣ ሃገርን ከማንቀጥቀጥና ከመግደል ውጪ ምንም ውጤት የለውም፡፡
የሃገራችን መሪዎች (ኤስ ኤ ኖድን የመሰላችሁ) ሃላፊነታችሁ ከባድ መሆኑን በትክክል ተረድታችሁት ይሆን? በታሪክ ይህን የመምራት እድል አግኝታችኋል፤ ይህም ማለት በሰውነታችን በየደቂቃው ደምን (ለህዝባችን መሰረታዊ የሆኑ ነገሮች) አንጋጠው ከልብ እንደሚጠብቁ የተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ጠባቂያችሁ ብዙ ነው ማለት አይደል፡፡ በትክክል ወቅቱና ጊዜውን የጠበቀ ኤሌክትሪክ (ተፈጻሚ ህግና አሰራር ልንለው እንችላለን) ከእናንተ መመንጨት ካልቻለ፣ ከህዝቡም ተሽላችሁ አገርን ፈር ማስያዝ ካልቻላችሁ፣ የልብ (የሃገር) መንቀጥቀጥና ሞት ተከሰተ ማለት አይደል። ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት፣ ልብ ሞታ ደግሞ ማንም አይተርፍም አያተርፍም! ወላ የጎበዝ አለቆች (ኤስ ኤ ኖድና የመሳሰሉት) ሆነ ሌሎች የልባችን ክፍሎች (ህዝባችን) ማንም አይተርፍም፡፡ አሁን የምናየውን አይነት የልብ (የሃገር) መንቀጥቀጥ ሲያጋጥም፣ እራስን እንደ ዲፊብሪሌተር ቆጥሮ፣ ወጀቡን ለማቆም፣ ቆም ብሎ በትክክል ማሰብ አልያም ከታች እንደምገልጸው ሚናቸው የዲፊብሪሌተር ለሆኑ አካላት እድል መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ካልሆነ ግን መንቀጥቀጡ አደገኛ ነውና፣ እንደ ጎርፍ ጠራርጎ ይዞን እንዳይሄድ!
በሃገራችን የዲፊብሪሌተር ስራ የሚሰሩ ብዙ ተቋማትና ስርዓቶች ነበሩን፡፡ በተለይ የሃይማኖት ተቋማቶቻችንና የሽምግልና ባህላችን በአበይትነት ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ እንደዚህ አይነት መራር ግርግር ሲያጋጥም፣ በእግዚአብሔር/በአላህ ይዤሃለሁ የሚሉና ወጀቡን ጸጥ የሚያስደርጉ፤ በሌላም ወገን ገና ከወንበራቸው ብድግ ሲሉ ሃገር የሚርድላቸው የሃገር ዋርካ የሆኑ ብዙ ሽማግሌዎችም ነበሩን፡፡ ጎበዝ መሪም ተመሪም መሆን ተቸገርን እኮ! የሃገሬ ዋርካዎች የሆናችሁ ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች- የእኛ ዲፊብሪሌተሮች አረ ወዴት ናችሁ? እኛ እናንተን ማየት አቆምን ወይስ እናንተ ከፊታችን ጠፋችሁ? መልሱ ከሁላችንም የአዕምሮ ጓዳ ውስጥ የሚገኝ ይመስለኛል፡፡
በመጨረሻ በታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ በአንዱ ክፍል የተጻፈውን  ታሪክን ለጽሁፌ መቋጫነት ልጠቀም፡፡ እንዲህ ይላል፡-
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሃዋርያቱ ጋር በታንኳ ሲሄድ አንቀላፋ፣ ማዕበልም ተነሳና መርከቢቱን በጣም አናወጣት፡፡ ሃዋርያቱም አብዝተው በወቅቱ አንቀላፍቶ ወደነበረው ክርስቶስ እየጮሁ፣”ልንጠፋ ነው” ብለው ቀሰቀሱት፡፡ እርሱም ወዲያው ተነስቶ ማዕበሉን ገሰጸው፤ መርከቢቱም ወደቀደመ ሰላሟ ተመለሰች፡፡
ታዲያ በየእምነታችን ከልብ ፈጣሪያችንን ብንለምን፣ እኛም  በሚገባን ሃላፊነታችንን ብንወጣ መርከቢቱ ሃገራችንን የሚታደግ ዲፊብሪሌተር እናጣ ይሆን? ፈጣሪያችን በቸርነቱ ይርዳን!!

አንዳንድ ዕውነተኛ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ የሚከተለውን እንደዚያው ነው።
ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ፣ አገር ሳያውቀው የሞተ ሰዓሊ ነበረ፡፡ ይህ ሰዓሊ የአገሩን ባንዲራ በልዩ እሳቤ ያስጌጠ፣ ማንም ያልደረሰበት ረቂቅ ሰዓሊ ነበረ። ስለሰራው ሥራ ዋጋው አልተከፈለውም፡፡ ስለዚህም ወዳጆቹ፤ ያንን ባንዲራ “ያልተከፈለ ዕዳ” በሚል የቅፅል ስም ይጠሩታል፡፡
ይህ ሰዓሊ የተከራየው ግቢ ውስጥ አንድ ካቲካላ ‹አረቄ› የሚሸጥበት ቤት አለ፡፡ እዚህ ቤት የሚጠጡት ሰዎች ሁሉ ሰዓሊውን፤ ፀጉሩ የተንጨባረረና ነጠላ ጫማ (ሸበጥ) የሚያደርግ ስለሆነ ሰላይ ነው ብለው ይጠረጥሩታል፡፡ ስለሆነም እሱ ወደ ካቲካላው ቤት ሲገባ አፍ ሁሉ ይዘጋል፡፡ የተጀመረ ታሪክ ይቋረጣል፡፡ ሰው ሁሉ አፉ ላይ ማብሪያና ማጥፊያ የተገጠመለት ይመስል፣ በማጥፊያው ጠቅ አድርገው እንዳጠፉት ሁሉ አንዴ ጭጭ ይላል፡፡
አንድ ቀን ሰዓሊው ወደ ግቢው ሲመጣ፣ የግቢው ውሻ ይጮኽበታል፡፡ ይሄኔ ሰዓሊው ኮሮጆውን ከትከሻው ያወርድና አስፋቱ ላይ ያስቀምጣል፡፡ ከዚያም ከውሻው ፊት ለፊት ይንበረከካል፡፡ ቀጥሎም፤ “ው! ው! ው! ው!” አለ ውሻው ላይ ይጮህበታል። ውሻው ደንግጦ ዝም፤ ጭጭ ይላል፡፡ “ሁለተኛ ትጮህና እጮህብሃለሁ!” ይለዋል፡፡ ይሄንን ሲያደርግ ከሰዓሊው ጀርባ እየመጡ ያሉ ካቲካላ ጠጪዎች፣ ሁኔታውን ሁሉ ይከታተሉ ኖሯል፡፡ ቀድመው ወደ ካቲካላ ቤት ሄደው ሁኔታውን ሁሉ ለጠጪዎቹ ይናገራሉ፡፡ ሰዓሊው ቆይቶ ወደ አረቄው ቤት ሲመጣ፤
አንዱ፤ “ሁለት ስጡት!”
ሌላው፤ “ሶስት ጨምሩለት!”
ሌላው፤ “ሰው ማለት ይሄ ነው! እንጋብዘው እንጂ ጎበዝ!” እያለ ሰዓሊውን በግብዣ አንበሸበሹት፡፡
በሰላይነት መጠርጠሩ ቀርቶ እንደ ሰው ተጋበዘ! እንደ ሰው ተከበረ! ይህንን የተገነዘበው ሰዓሊ፤
“እዚህ አገር ሰው ለመሆን እንደ ውሻ መጮህ ያስፈልጋል!” አለ፡፡
የዚህን፤ የውሻን አፍ ያስዘጋ፤ የሰውን አፍ ያስከፈተ፣ ታላቅ ሰዓሊ ነብስ ይማር!!
*        *      *
ታላቅ ሰዎቻችንን እናክብር፡፡ ታላላቅ ሰዎቿን የቀበረች አገር ብዙ ያልተከፈለ ዕዳ ይኖርባታል፡፡ ዕዳው የትውልድ ነውና መጪውን ትውልድ ሳይቀር ባለዕዳ ታደርጋለች። የድንቁርና ዕዳ፣ ከዕዳ ሁሉ የከበደው ዕዳ ነው! የጤና ማጣት ዕዳ፣ ሁለተኛው ከባድ ዕዳ ነው! የዕብሪትና የማናለብኝ ዕዳ ቀጣዩ አባዜ ነው! ሁሉም ዋጋ እንደሚያስከፍለን በጭራሽ አንዘንጋ! ሁላችንም ባለሳምንት፣ የጠጣነውን ፅዋ በተራችን እንከፍላለን! ሌላው ብርቱ ችግራችን የመስባት ችግር ነው፡፡ (The fattening process እንዲሉ)
አንድ አዛውንት፤ “ስሙ አባታችን፤ እኛ እንደቀደሙት ገዢዎች ወፋፍራም አደለንም!” ቢሏቸው፤ “አዬ ልጄ፤ እነሱም ሲጀምሩ እንደናንተ ቀጫጭኖች ነበሩ!” አሉ፤ አሉ፡፡ የሀገራችን መሪዎች ችግር “አትፍረድ ይፈረድብሃል” የሚለውን መሪ ቃል መዘንጋት ነው! መጪዎች ከቀደሙት አይማሩም፡፡ የማይቀረውን ውድቀት እንደ ፅዋ መቀባበል አይቀሬ የሚሆነው ለዚህ ነው!
ጊዜያዊ የዘመቻ ሂደት ዘላቂ ለውጥን አያመጣም፡፡ የአፍታ - ለአፍታ የፕሮፓጋንዳ ቅስቀሳ ዘላቂ ዕውቀትን አያሰርፅም! ይልቁንም ህዝብን ማሳወቅ፣ ማስተማርና ማንቃት ፈር የያዘ ብቃትን ይፈጥራል! ትውልድ ዘላቂ ንቃትና ብቃት ሲኖረው፣ እርባና ያለው ለውጥ፣ ብሎም እርባና ያለው ዕድገት ያመጣል፡፡ የአልሸነፍም ባይነት ግትርነት፣ ጊዜያዊ ሥልጣንን ሊያቆይ ይችላል እንጂ የአገርና የህዝብን ዘላቂ ዕድገት አይፈጥርም! ነባር ግንኙነቶች ቀስ በቀስ መላላታቸው፣ ቀስ በቀስ መለወጣቸው ግድ ነው፡፡ አዳዲስ የሰው ኃይል መደባለቅ ለለውጥ መምጣት አንዱ ግብዓት ነው፡፡
አዳዲስ አስተሳስብ እንዲመነጭ የአዳዲስ ሰው ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ ነገሩ ሁሉ ባለበት እርገጥ ይሆናል፡፡ ምንም ያህል ብንሮጥ መላና ብልሃት ከሌለበት የጭፍን ሩጫ ነው የሚሆነው፡፡ የጣልነውን ስለረገጥነው የእኛን ዕድገት ማረጋገጫ አይሆንም፡፡
እርጋታና አደብ መግዛት ወሳኝ ነው፡፡ መንገዶች በሙሉ ሊሾ አይሆኑም። ኮረኮንቹ እንዳይበዛ መታገሉ ሁነኛ አማራጭ ነው፡፡ “ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም” የሚለውን ተረት ሳንዘነጋ፣ ዛሬም ተለዋጭ ኃይል ማስፈለጉን እናስብ። ልዩነትን እናድንቅ፡፡ ሌጣ የሆነን አጓጓዝ እናስወግድ፡፡ የተለየ ሀሳብ አያስበርግገን። ጉዞአችን የጭፍን እንዳይሆን መሬት የያዘ ፍጥነት ይኑረን፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የሰከነ መላ እንዘይድ፡፡ ለዚህም “የዕውር የድንብሩን ከሚሮጥ ፈረስ መንገድ የምታውቅ አይጥ ትሻላለች” የሚለውን ተረት እንገንዘብ!!

ሰማያዊ ፓርቲ ባለፈው እሁድ በአምባሳደር ሲኒማ አዳራሽ “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” በሚል ርዕስ ያካሄደውን ስብሰባ አንድ ቀን ቀደም ብሎ በወጣው የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ  መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ፓርቲው  አንጋፋ ምሁራን፣ፖለቲከኞችና ታዋቂ ግለሰቦች በህዝባዊ ስብሰባው ላይ እንደሚገኙና በደብዳቤ ጥሪ እንደደረሳቸው የገለጸ ሲሆን ስማቸውንም በዝርዝር መጥቀሱ አይዘነጋም፡፡
እሁድ በሰማያዊ ፓርቲ ህዝባዊ ስብሰባ ላይ የተገኘው ሪፖርተራችን እንደታዘበው፣ ፓርቲው የገመተውን ያህል ታዳሚ አልተገኘለትም፡፡ ፓርቲው በመድረኩ እንደሚገኙ ከዘረዘራቸው ግለሰቦች መካከልም ጥቂቶች ብቻ መገኘታቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል። አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣የስብሰባው ጥሪ እንደደረሳቸው ነገር ግን በግል ምክንያት ሊገኙ አለመቻላቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ አቶ ክቡር ገናም በተመሳሳይ ጥሪው ደርሷቸው፣ ከሃገር ውጪ በመሆናቸው መገኘት እንዳልቻሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ሞሼ ሰሙ ደግሞ ጥሪው አልደረሰኝም ብለዋል - ጥሪው ቢደርሳቸው ኖሮ ይገኙ እንደነበር በመግለጽ፡፡ ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ በበኩላቸው፤ጥሪው እንዳልደረሳቸውና አዲስ አድማስም ጥሪው ባልደረሳቸው ሁኔታ ፎቶግራፋቸውን ጭምር በመጠቀም ባሰራጨው ዘገባ ቅሬታ እንደተሰማቸው ለዝግጅት ክፍሉ አስታውቀዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ በበኩሉ፤ባለፈው ሳምንት በስም ተጠቅሰው ለተዘረዘሩት ታዋቂ ምሁራንና ግለሰቦች በሙሉ የጥሪ ደብዳቤ መላኩን ጠቁሞ፣ በትክክል መድረስ አለመድረሱን ግን ለዚህ ሥራ ከተመደቡት ሰዎች ጋር እንደገና እንደሚነጋገርበት ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡


 ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ አሜሪካን ሀገር ከሚገኘው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በቢዝነስ አድምኒስትሬሽን በሁለተኛና በመጀመሪያ ዲግሪ ያስተማራቸውን ተማሪዎች  ለሁለተኛ ጊዜ ያስመርቃል፡፡
ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ፣ ይህን የትምህርት መርሃ ግብር በተለይ የንግድ ስራ አመራር ላይ አተኩሮ የሚሰጥ ሲሆን ለ7ኛ ጊዜ በMBA እና ለ2ኛ ጊዜ በBA ፕሮግራም ያስተማራቸውን ተማሪዎች ነው ነገ በአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የስብሰባ ማዕከል የሚያስመርቀው፡፡
በምርቃት ስነ ስርአቱ ላይም የፐብሊክ ፋይናንስ ኢንተርፕራይዝ ኤጀንሲ ዳይሬክተር ጀነራል ዶ/ር ስንታየሁ ወ/ሚካኤል፣ የሊንከን ዩኒቨርሰቲ ካሊፎርኒያ ፕሮፌሰርና የዩኒቨርሲቲው የባላደራ ቦርድ ሊቀ መንበር ዶ/ር አላን ሳምሶን እና የአሜሪካ ኤምባሲ ተወካይ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት ባለስልጣናት ይገኛሉ ተብሏል፡፡


        “የአለማችን ቁጥር አንድ ፉንጋ ተብዬ፣ የአገሬን ስም አስጠራለሁ!” ብሏል

   ባለማማር ውስጥ ያለውን ውበት የማሳየት ዓላማ ይዞ በዚምባቡዌ በየአመቱ በሚካሄደው የ“አቶ መልከ-ጥፉ - ዚምባቡዌ” የቁንጅና ውድድር ለሁለት ጊዜያት አሸናፊ የነበረው ሚሊያም ማስቪኑ የተባለው የአገሪቱ ዜጋ፤ዘንድሮም ክብሩን በማስጠበቅ ሃትሪክ መስራቱንና የፉንጋነቱን ዘውድ መድፋቱን ኦል አፍሪካ ዶት ኮም ዘግቧል፡፡
በመዲናዋ ሃራሬ ባለፈው እሁድ ምሽት ለአምስተኛ ጊዜ በተከናወነው የ2017 “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር ላይ በዕጩነት ከቀረቡ አራት ተወዳዳሪዎች መካከል አንደኛ በመውጣት ብሄራዊውን የፉንጋነት ዘውድ የደፋው ማስቪኑ፤ ከውድድሩ አዘጋጅ ድርጅት የ500 ዶላር እና የአንዲት ላም ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡
“በመላው ዚምባቡዌ ከእኔ ጋር የሚስተካከል አስጠሊታ ሰው እንደሌለ ሳይታለም የተፈታ ነው!... በቀጣይ ይህንን ፉንጋ መልኬን ይዤ አገሬን በአለም መድረክ ላይ በኩራት ለማቆምና ስሟን ለማስጠራት የቻልኩትን ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እርግጠኛ ነኝ፤ የ2018 የአለማችን ፉንጋ ክብርን በመጎናጸፍ፣ የአገሬን ስም በአለም አደባባይ አስጠራለሁ!” ብሏል ማስቪኑ፤ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ባደረገው ንግግር፡፡
የ2018 የአለማችን “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ የጠቆመው ዘገባው፤ በብሄራዊ ደረጃ አሸናፊ የሆኑ የተለያዩ አገራት መልከ-ጥፉዎች፣ አገራቸውን ወክለው እንደሚወዳደሩና ከፍተኛ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡