Administrator

Administrator

 በ2016/17 የውድድር ዘመን የአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች  ሲገባደዱ  ቼልሲ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ    ፤ ጁቬንትስ በጣሊያን ሴሪ ኤ ፤ ባየር ሙኒክ በጀርመን ቦንደስ ሊጋ፤ ሪያል ማድሪድ በስፔን ላሊጋ እንዲሁም ሞናኮ በፈረንሳይ ሊግ 1 ሻምፒዮንነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ከ5ቱ ታላላቅ ሊጎች ባሻገር በሳምንቱ አጋማሽ ላይ  በዩሮፓ ሊግ ማንችስተር ዩናይትድ ከአያክስ ተፋልመዋል፡፡ ማንችስተር ዩናይትድ 2ለ0 በማሸነፍ ለመጀመርያ ጊዜ የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን ያሸነፈ ሲሆን እንዲሁም በሊጉ አምስተኛ ደረጃ ይዞ በማጠናቀቁ በቀጣይ የውድድር ዘመን የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አሳክቷል፡፡ በሌላ በኩል ከሳምንት በኋላ በ62ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ጨዋታ  የስፔኑ ላሊጋ ሻምፒዮን  ሪያል ማድሪድ ከጣሊያኑ ሴሪ ኤ አሸናፊ ጁቬንትስ  ይፋጠጣሉ፡፡
በቅርቡ ይፋ ባደረገው  ሪፖርት The CIES Football Observatory የተባለ የእግር ኳስ ጥናት አድራጊ ተቋም በ5ቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች እንደተለመደው የኃይል ሚዛኑ ከታላላቅና ውጤታማ ክለቦች ሊወጣ አልቻለም፡፡ በተለይ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ከ1993 እኤአ ወዲህ በአዲስ አሰራር መካሄድ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በየሊጎቹ የገቢ ሁኔታዎች በከፍተኛ ደረጃ ያደጉ ቢሆንም፤ በትልልቅ እና ትንንሽ ክለቦች መካከል ያለው የሃይል ሚዛን ሊጠብብ ግን አልቻለም፡፡  
በሲአይኢኤስ ሪፖርት መሰረት  ከ1993 እኤአ ወዲህ በነበሩት  25 የውድድር ዘመናት በአምስቱ ታላላቅ ሊጎች  ሻምፒዮን የሆኑ ክለቦች በዝርዝር ሲጠቀሱ የጥቂት ክለቦች የበላይነት ቀጥሏል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 6 ፤ በጣሊያን ሴሪ ኤ 5፤ በስፔን ላሊጋ 5፤ በጀርመን 6 እንዲሁም በፈረንሳ ሊግ 1 10 የተለያዩ ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት ማሳካታቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በሻምፒዮናነት የጨረሰው  ቼልሲ ሲሆን፤  ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት በአጠቃላይ የሻምፒዮናነት ክብሩን ለማግኘት የበቁት 6 ክለቦች ናቸው፡፡ ማንችስተር ዩናትድ 13 ጊዜ፤ ቼልሲ 5 ጊዜ፤ አርሰናል 3 ጊዜ፤ ማችስተር ሲቲ 2 ጊዜ እንዲሁም ሌስተር ሲቲ እና ብላክበርን ሮቨርስ እኩል አንድ ጊዜ የሊጉን የሻምፒዮናነት ክብር ተጎናፅፈዋል፡፡
በጣሊያን ሴሪ  ኤ ለስድስተኛ ተከታታይ የውድድር ዘመን የስኩዴቶውን ክብር ለመቀዳጀት ከጫፍ ላይ የደረሰው ጁቬንትስ ሲሆን፤ ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት የስኩዴቶውን ክብር  ለመጎናፀፍ የበቁት አምስት ክለቦች ናቸው፡፡ ለ11 ጊዜያት የስኩዴቶውን ክብር በመቀዳጀት ከፍተኛውን ስኬት ያስመዘገበው ጁቬንትስ ሲሆን ከ2012 ጀምሮ እስከ 2017 ለስድስት ተከታታይ ጊዜያት ሻምፒዮን መሆኑ ክብረወሰን ሆኖ የሚመዘገብ ነው፡፡  ለ6 ጊዜያት የሴሪኤውን የስኩዴቶ ክብር በመጎናፀፍ ኤሲ ሚላን ሲከተል፤ ኢንተርሚላን ለአምስት ጊዜ ፤ ላዚዮ እና ሮማ እኩል አንድ ጊዜ የስኩዴቶውን ክብር ተጎናፅፈዋል፡፡
በስፔን ላሊጋ ከ2012 በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሪያል ማድሪድ ሲሆን 25 የውድድር ዘመናት 5 ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን አግኝተዋል፡፡ ባርሴሎና  በድምሩ ለ12 ጊዜያት የስፔን ሻምፒዮን በመሆን ቀዳሚ ሲሆን  ሪያል ማድሪድ ለ7 8 ጊዜያት ሻምፒዮን በመሆን በሁለተኛ ደረጃ ተቀምጧል፡፡ አትሌቲኮ ማሪድ እና ቫሌንሽያ እያንዳንዳቸው እኩል ሁለቴ እንዲሁም ዲፖርቲቮ አንዴ ዋንጫውን አንስተዋል፡፡
በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የዘንድሮ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ባየር ሙኒክ ሲሆን፤ ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት 6 የተለያዩ ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን አግኝተዋል፡፡ 16 የቡንደስሊጋ የሻፒዮንነት ክብሮችን በመሰብሰብ ግንባር ቀደም የሆነው ባየር ሙኒክ ሲሆን፤ ቦርስያ ዶርትመንድ  3 ጊዜ፤ ዌርደር ብሬመን ሁለት ጊዜ እንዲሁም ካይዘስላውተርን ፤ ስቱትጋርት እና ዎልፍስበርግ እኩል አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን ችለዋል፡፡
በፈረንሳይ ሊግ 1  ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሞናኮ ሲሆን ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት 10 የተለየዩ ክለቦች ሻምፒዮኖች ሆነዋል፡፡  ኦሎምፒክ ሊዮን ለ7 ጊዜያት፤ ፒኤስጂ ለ4 ጊዜያት፤ ሞናኮ ለ3 ጊዜ፤ ናንትስ እና ቦርዶ እያንዳንዳቸው እኩል 2 እንዲሁም ኦክዜር፤ ሌንስ፤ ማሴይ፤ ሊል እና ሞንትፕሌየር እኩ 1 ሻምፒዮን ሊሆኑ ችለዋል፡፡
በሌላ በኩል በ2016/ 17 የውድድር ዘመን The CIES Football Observatory በሰራው ሪፖርት በተጨዋቾች ስብስብ የዋጋ ግምት ደረጃ ውዱ ክለብ የነበረው የእንግሊዙ ማንችስተር ዩናይትድ በ626 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ የስፔኑ ሪያል ማድሪድ በ553 እና ማንችስተር ሲቲ በ533 ሚሊዮን ፓውንድ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ባርሴሎና በ423፤ ቼልሲ በ419፤ ፒኤስጂ በ397፤ ጁቬንትስ በ345፤ አርሰናል 332፤ ባየር ሙኒክ በ312 እንዲሁም ሊቨርፑል በ310 ሚሊዮን ፓውንድ የተጨዋቾች ስብስብ የዋጋ ተመናቸው እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃ ይወስዳሉ፡፡
በውድድር ዘመኑ በ5ቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች  የእግር ኳስ ገበያው እስከ 25 ቢሊዮን ዩሮ የተንቀሳቀስበት ሲሆን በየሊጎቹ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች ድምር ገቢ ከ15 ቢሊዮን ዩሮ በላይ እንደሚሆን ተገምቷል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ  718 ፤ በጀርመን ቡንደስ ሊጋ 316፤ በስፔን ላሊጋ 264፤ በጣሊያን ሴሪኤ 133 እንዲሁም በፈረንሳይ ሊግ 35 ሚሊዮን ዩሮ ተንቀሳቃሽ ትርፍ ይጠበቃል፡፡
የአምስቱ ሊጎች የተጨዋቾች ደሞዝ ወጭ  ከ7.4 ቢሊዮን ዩሮ በላይ የነበረ ሲሆን በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ እስከ 4.2 ቢሊዮን ዩሮ ወጥቷል፡፡  በትራንስፈርማርከት  በዝርዝር በሰፈረው መረጃ መሰረት የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ላይ የተወዳደሩ 20 ክለቦች የነበሩት 521 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 4.91 ቢሊዮን ዩሮ ፤ በስፔን  ላሊጋ የተወዳደሩ 20 ክለቦች  484 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 3.65 ቢሊዮን ዩሮ ፤ በጣሊያን ሴሪ ኤ የተወዳደሩ 20 ክለቦች  529 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 2.88 ቢሊዮን ዩሮ  ፤ በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የተወዳደሩ 18 ክለቦች  506 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 2.63 ቢሊዮን ዩሮ እንዲሁም በፈረንሳይ ሊግ 1  የተወዳደሩ 20 ክለቦች  553 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 1.73 ቢሊዮን ዩሮ ነበር፡፡

   የአውሮፓ የቅርብ አመታት የሽብር መዝገብ፣ ከፓሪስ እስከ ማንችስተር

      አሁንም አውሮፓ ተሸበረች…
ባለፈው ሰኞ ምሽት በእንግሊዟ ማንችስተር ከተማ ሙዚቃን ሊያጣጥሙና መንፈሳቸውን ዘና ሊያደርጉ ከየአቅጣጫው የተሰባሰቡ የሙዚቃ አፍቃሪያን፣ በአንድ አዳራሽ ውስጥ ታድመው ነበር፡፡ በርካታ ወጣቶችና ህጻናት የታደሙበት የአሜሪካዊቷ አሪያና ግራንዴ የሙዚቃ ኮንሰርት ሞቅ ደመቅ ብሎ ወደ መገባደጃው ተቃርቧል፡፡
የሆነች ቅጽበት ላይ ግን…
አዳራሹን ያናወጠና ከሙዚቃው ድምጽ በላይ ጎልቶ ያስተጋባ፣ ያልተጠበቀ ፍንዳታ ድምጽ ተሰማ፡፡ ለሙዚቃ የታደሙት ተመልካቾች በድንገተኛው ፍንዳታ ተደናግጠው ነፍሳቸውን ለማዳን በየአቅጣጫው ተራወጡ፡፡ ጭንቅ ሆነ፡፡ ሁሉም ራሱን ለማዳን የቻለውን ሁሉ ማድረግ ያዘ፡፡
ከአይሲስ ጋር ግንኙነት እንዳለው በተነገረለት አጥፍቶ ጠፊ የተፈጸመውና የሽብር ቡድኑም ሃላፊነቱን እንደሚወስድ በይፋ ባስታወቀበት የማንችስተሩ የሽብር ጥቃት፤ 22 ያህል ሰዎችን ሲገድል፣ ሌሎች 59 ሰዎችን አቆሰለ፡፡ እንግሊዝ ብቻ ሳትሆን መላ አውሮፓ በድንጋጤ ክው አለች፡፡
የማንችስተሩ የሽብር ጥቃት እ.ኤ.አ ከ2015 ወዲህ በምዕራብ አውሮፓ አገራት የተፈጸመ 13ኛው ጥቃት ሲሆን፣ በእነዚሁ ጥቃቶች ከ300 በላይ ሰዎች ለህልፈተ ህይወት እንደተዳረጉ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ ለአብዛኛዎቹ የሽብር ጥቃቶች ሃላፊነቱን የወሰደውም አሸባሪው ቡድን አይሲስ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
ሽብር ከወትሮ በተለየ አምና እና ዘንድሮ አውሮፓን ደጋግሞ ሰለባው አድርጓታል፡፡ አህጉሪቱ ሽብርንና ሽብርተኞችን ለመዋጋት የቻለቺውን ያህል ታጥቃ ብትነሳም፣ ችላ መመከት እንዳቃታት ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ የሽብር ጥቃቶች ከፈረንሳይ እስከ ቤልጂየም፣ ከእንግሊዝ እስከ  ጀርመን በየአቅጣጫው መፈጸማቸውንና የከፋ ጥፋት ማድረሳቸውን ቀጥለዋል፡፡
አምና እና ዘንድሮ ብቻ በአህጉሪቱ ከተፈጸሙት ዋና ዋና የሽብር ጥቃቶች መካከልም የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡
ባለፈው ሚያዝያ ወር በፈረንሳይ መዲና ፓሪስ የተፈጸመው የሽብር ጥቃት አንድን ፖሊስ ለሞት የዳረገ ሲሆን፣ አሸባሪው ቡድን አይሲስ ለሽብር ጥቃቱ ሃላፊነቱን ወስዷል፡፡
በሚያዝያ መጀመሪያ በስቶክሆልም የተፈጸመው የሽብር ጥቃትም አምስት ሰዎችን ለሞት፣ ከ15 በላይ የሚሆኑትን ደግሞ ለመቁሰል አደጋ ዳርጓል፡፡ ትልቅ መኪና ይዞ ጥቃቱን የፈጸመው ራክማት አኪሎቭ የተባለ ኡዝቤክስታናዊ ሲሆን፣ ግለሰቡ የአይሲስ አባል እንደነበረም ተናግሯል፡፡
በመጋቢት ወር መጨረሻ አካባቢ ካሊድ ማሱድ የተባለ ግለሰብ፣ በታዋቂው የለንደኑ ዌስትሚኒስቴር ድልድይ አቅራቢያ በከፈተው የተኩስ ጥቃት አራት ሰዎችን ገድሎ፣ ሌሎች ከ40 በላይ የሚሆኑትንም አቁስሏል፡፡ በስተመጨረሻም ሊያመልጥ ሲሞክር ከፖሊስ በተተኮሰበት ጥይት ተገድሏል፡፡ አይሲስም እንደ ልማዱ ሽብሩን የፈጸምኩት እኔ ነኝ ሲል በኩራት አውጇል፡፡
ያለፈው አመት 2016 ሃምሌ ወር ለጀርመን የተደራራቢ የሽብር ጥቃትና የሃዘን ወር ነበር፡፡ በዚያው ወር በበርሊን ሆስፒታል ውስጥና በኡዝበርግ ባቡር ላይ የተፈጸሙትን የሽብር ጥቃቶች ጨምሮ በአንድ ሳምንት ብቻ አምስት የሽብር ጥቃቶች ተፈጽመዋል፡፡
በመጋቢት ወር 2016 መጨረሻም በቤልጂየም መዲና ብራስልስ እጅግ አሰቃቂ የሽብር ጥቃቶች ተፈጽመዋል፡፡ በብራስልስ አውሮፕላን ማረፊያ እና በባቡር ጣቢያ አካባቢ የተፈጸሙት ሁለት የሽብር ጥቃቶች በድምሩ 32 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት ሲዳርጉ ከ300 በላይ የሚሆኑትንም ለመቁሰል አደጋ ዳርገዋል፡፡
በፈረንጆች አመት 2015 የመጀመሪያ ሳምንት በቻርሊ ሄቢዶ መጽሄት ዝግጅት ክፍል ቢሮ ላይ በተፈጸመ የሽብር ጥቃት 17 ዜጎቿን ያጣቺው ፈረንሳይ፣ ከወራት በኋላም 130 ሰዎችን ለሞት የዳረገ ሌላ የሽብር ጥቃት አስተናግዳለች፡፡

ሰሜን ኮርያ ጃፓንንና ዋና ዋና የአሜሪካ ወታደራዊ ካምፖችን የማጥቃት ብቃት ያለውን አዲስ የመካከለኛ ርቀት ተወንጫፊ ባለስቲክ ሚሳኤል በገፍ ለማምረት ዝግጅቷን ማጠናቀቋን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን ባለፈው ማክሰኞ አስታወቁ፡፡
ፕሬዚዳንቱ ፑክጉሶንግ 2 የተባለውን ባለስቲክ ሚሳኤል በብዛት ለማምረትና በአገሪቱ ስትራቴጂካዊ የጦር ሰፈሮች በማስፈር፣ ለተልዕኮ ዝግጁ እንዲደረጉ ትዕዛዝ እንደሰጡ ማስታወቃቸውን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፣ ፕሬዚዳንት ኡንም አዲሱ ባለስቲክ ሚሳኤል ብቃቱ በሙከራ መረጋገጡንና ውጤታማ መሆኑን በመጥቀስ፣ ኢላማውን አነጣጥሮ ያለ አንዳች ስህተት መምታት የሚችለው የዚህ ሚሳኤል ባለቤት በመሆናችን ኩራት ይሰማናል ማለታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የኒውክሌርና የሚሳኤል ፕሮግራሟን እንድታቋርጥ ቻይና እና አሜሪካን ጨምሮ ከተቀረው አለም በተደጋጋሚ እየቀረበላት ያለውን ጥሪ ላለመስማት የወሰነቺው ሰሜን ኮርያ፤ ከአሜሪካ የሚቃጣብኝን ወረራ ለመመከት በበቂ ሁኔታ መታጠቅ ግድ ይለኛልና አልሰማችሁም ብላለች፡፡
ሰሜን ኮርያ በዚህ አንድ ሳምንት ብቻ ሁለት የሚሳኤል ሙከራዎችን ማድረጓን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤትም አገሪቱ የተጣለባትን ማዕቀብ በመጣስ እያደረገቺው ያለውን እንቅስቃሴ በተመለከተ ሰሞኑን ተሰብስቦ ውሳኔ ላይ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አክሎ ገልጧል፡፡

  88 የባንክ አካውንቶችና የ14 ኩባንያዎች ሃብቶች እንዳይንቀሳቀሱ በፍ/ ቤት ታግደዋል

       በምርጫ ቢሸነፉም ስልጣኔን አልለቅም ብለው ሲያንገራግሩ ከቆዩ በኋላ በደረሰባቸው ከፍተኛ ጫና ባለፈው ጥር ወር አገር ጥለው የተሰደዱት የቀድሞው የጋምቢያ ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜህ፤ ከመንግስት ካዘና ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ ዘርፈዋል መባሉን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ያያ ጃሜህ ባለፉት አስር አመታት ብቻ ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ የህዝብ ገንዘብ ዘርፈው ከአገር ማስወጣታቸውን የአገሪቱ የፍትህ ሚኒስቴር ባለፈው ሰኞ ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገር ውስጥ ያሉ የጃሜህ ሃብቶችና ንብረቶች በሙሉ እንዳይንቀሳቀሱ በፍርድ ቤት መታገዳቸውንም ገልጧል፡፡ ከቀድሞው ፕሬዚዳንት ጋር ንክኪ አላቸው የተባሉ 14 ኩባንያዎች እና በስማቸው ወይም በወዳጆቻቸው ስም የተከፈቱ 88 የባንክ አካውንቶችም እንዳይንቀሳቀሱ በፍርድ ቤት መታገዳቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በርካታ መኪኖችን ጨምሮ በፕሬዚዳንቱ ስም የተመዘገቡ በርካታ ንብረቶችም መታገዳቸውን አብራርቷል፡፡
ጃሜህ ከመንግስት ካዝና የዘረፉት ገንዘብ 11 ሚሊዮን ዶላር ያህል ይሆናል ተብሎ ሲገመት የቆየ ቢሆንም፣ የአገሪቱ ፍርድ ቤት ባደረገው ምርመራ ገንዘቡ ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንደሚደርስ ማረጋገጡን እንዳስታወቀ ቢቢሲ በዘገባው አስረድቷል፡፡
ምዕራብ አፍሪካዊቷን አገር ለ22 አመታት የመሩትና ባለፈው ታህሳስ በተካሄደው ምርጫ በተቀናቃኛቸው አዳማ ባሮው መሸነፋቸውን ተከትሎ ስልጣን አልለቅም በማለታቸው የጎረቤት አገራት ባሳደሩባቸው ከፍተኛ ጫና ወደ ኢኳቶሪያል ጊኒ የተሰደዱት ያያ ጃሜህ፣ በርካታ ውድ መኪኖችንና ሌሎች ንብረቶቻቸውን ይዘው እንደሄዱ ዘገባው አስታውሷል፡፡

 የእርስ በእርስ ግጭት እየተስፋፋ በመጣባት ማይንማር በየቀኑ እድሜያቸው ከ5 አመት በታች የሆኑ 150 ያህል ህጻናት ለህልፈተ ህይወት በመዳረግ ላይ እንደሚገኙ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየተስፋፋ በመጣው የእርስ በእርስ ግጭት፣ በድህነት እና በበሽታ ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ህጻናት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ነው ያለው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ ድርጅት፣ በተለይም ግጭት ባለባቸው አካባቢዎች የጤና አገልግሎት በመቋረጡ በርካታ ህጻናት በኒሞኒያና በሌሎች በሽታዎች እየተሰቃዩ፣ ምንም አይነት የህክምና እርዳታ ሳያገኙ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉም አስታውቋል፡፡
በመላ አገሪቱ 2.2 ሚሊዮን ያህል ህጻናት የሰብአዊ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የጠቆመው ድርጅቱ፣ የአገሪቱ መንግስት እየተስፋፋ የመጣው ብጥብጥና የእርስ በእርስ ግጭት ሰለባ ለሆኑት ለእነዚሁ ህጻናት አስቸኳይ የሰብአዊ ድጋፍ ማድረግና በህጻናቱ ላይ የሚፈጸሙ የመብቶች ጥሰቶችን ለማስቆም አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድም ጠይቋል፡፡
ከግማሽ በላይ የሚሆኑ የአገሪቱ ህጻናት ከድህነት ወለል በታች የሆነ አስከፊ ኑሮ እንደሚመሩ የጠቆመው ዘገባው፣ 30 በመቶ ያህሉ የማይንማር ህጻናት የከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂ እንደሆኑም አመልክቷል፡፡

  የህንድ ህዝብ 1.32 ቢሊዮን ሲደርስ፣ የቻይና ግን 1.29 ቢሊዮን ቢደርስ ነው ተብሏል

     የቻይና የህዝብ ቁጥር ሆን ተብሎ በመጋነን በ90 ሚሊዮን ያህል እንዲጨምር መደረጉንና 1.32 ቢሊዮን ህዝብ ያላት ህንድ በቻይና ተይዞ የነበረውን የዓለማችን የህዝብ ብዛት ደረጃ መረከብ እንደምትችል በጥናት ማረጋገጣቸውን አንድ ታዋቂ  የስነ ህዝብ ተመራማሪ ማስታወቃቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአሜሪካው የዊስከንሰን ማዲሰን ዩኒቨርሲቲ የስነ ህዝብ ተመራማሪ የሆኑትና በህንድ እና በቻይና የህዝብ ብዛት ዙሪያ ጥናት ሲሰሩ የቆዩት ዪ ፉክሲያን፣ የቻይና ባለሙያዎች በህዝብ ቆጠራ ወቅት ሆን ብለው የህዝቡን ቁጥር እንዳጋነኑት በመጠቆም የአገሪቱ ህዝብ ቁጥር በ90 ሚሊዮን እንዲጨምር ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
የቻይና የህዝብ ቁጥር የአገሪቱ መንግስት እንደሚለው 1.38 ቢሊዮን ሳይሆን፣ ከዚያ ያነሰ ነው፤ የህዝብ ቁጥሩ እስካለፈው የፈረንጆች አመት 2016 መጨረሻ ቢበዛ 1.29 ቢሊዮን ያህል ቢደርስ ነው፤ በመሆኑም ህንድ በህዝብ ብዛት ከቻይና በመቅደም በአንደኛነት እንድትቀመጥ ያደርጋታል ብለዋል - ተመራማሪው፡፡
ተመራማሪው ይህን ቢሉም በርካታ ህንዳውያንና ቻይናውያን የስነህዝብ ባለሙያዎች ግን የተመራማሪውን ድምዳሜ በበቂ መረጃዎች ላይ ያልተመሰረተና ስሜታዊነት የሚንጸባረቅበት፣ ሙያዊ ያልሆነ አደገኛ ነገር ነው በማለት በስፋት እያጣጣሉት እንደሚገኙም ዘገባው ገልጧል፡፡

   በዩኒቨርሲቲው የ81 አመታት ታሪክ በዚህ መልኩ የተመረቀ የመጀመሪያው ተማሪ ነው
     በታዋቂው ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ተመራቂ የሆነውና ለመመረቂያ ጽሁፍ የራፕ ሙዚቃ አልበም ሰርቶ ያቀረበው የሃያ አመቱ ወጣት ኦባሲ ሻው፣ በትምህርት ክፍሉ ተቀባይነት በማግኘት በማዕረግ መመረቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የ81 አመታት ታሪክ የሙዚቃ አልበምን በመመረቂያ ጽሁፍነት አቅርቦ በማዕረግ በመመረቅ የመጀመሪያው ተማሪ የሆነው ኦባሲ ሻው፣ በራፕ ስልት የተቀነቀኑ 11 ሙዚቃዎቹን ያካተተበትንና “ሊሚናል ማይንድስ” የሚል ስያሜ የሰጠውን አልበሙን ለመመረቂያ ጽሁፍነት እንዲያቀርብ ሃሳብ የሰጡት እናቱ እንደሆኑ ተናግሯል፡፡
ወጣቱ የራፕ የሙዚቃ አልበም በመመረቂያ ጽሁፍነት የማቅረብ ሃሳቡ በዩኒቨርሲቲው ተቀባይነት ያገኛል ብሎ በፍጹም ባይገምትም፣ የእናቱን ሃሳብ ተከትሎ የመመረቂያ ፕሮጀክት ፕሮፖዛሉን ለትምህርት ክፍሉ ሃላፊዎች ሲያቀርብ ያገኘው በጎ ምላሽ ግን በሃሳቡ እንዲገፋበት እንዳበረታታው ይናገራል፡፡
“ኤ” ውጤት ያስገኘለትንና በማዕረግ ያስመረቀውን ይህንን የራፕ ሙዚቃ አልበሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት ያህል እንደወሰደበት የጠቆመው ዘገባው፣ ወጣቱ በአልበሙ ባካተታቸው ሙዚቃዎቹ የጥቁሮችን ህይወት፣ የቀለም ልዩነትንና ሌሎች ርዕሰ ጉዳዮችን መዳሰሱንም አክሎ ገልጧል፡፡

  ከእለታት አንድ ቀን አንድ ዛፍ ቆራጭ ከወንዝ ዳር ዛፍ እየቆረጠ ሳለ፣ መጥረቢያው ከእጁ ወጥቶ፣ ግንዱ ላይ ነጥሮ ወንዙ ውስጥ ወደቀበት፡፡ በወንዙ ዳር ቆሞ፣
“አዬ ጉድ! የእንጀራ ገመዴ ተበጠሰ!” እያለ ሲያለቅስ፤ የውሃው አማልክት መልክተኛ ሜርኩሪ ብቅ አለና፤
“ምን ሆነህ ታለቅሳለህ? ለምን አዘንክ?” አለው፡፡
“የሥራ መጥረቢያዬ ወንዝ ውስጥ ገባብኝ” አለው፡፡
ሜርኩሪ ወደ ውሃው በዋና ጠለቀና አንድ የወርቅ መጥረቢያ ይዞ ወጣ፡፡ ከዚያም፤ይሄ መጥረቢያ ያንተ
ነውን?” ሲል ጠየቀው፡፡
ዛፍ ቆራጩም፤
“የለም ይሄ የእኔ መጥረቢያ አይደለም” አለና መለሰ፡፡
ሜርኩሪ ለሁለተኛ ጊዜ በዋና ወደ ወንዙ ጠለቀና አንድ ሌላ ከብር የተሰራ መጥረቢያ ይዞ ብቅ አለ፡፡
“ይሄስ ያንተ ነውን?” አለና ጠየቀው፡፡
“እረ የለም፤ ይሄ የእኔ አይደለም” አለ ዛፍ ቆራጩ፡፡
ሜርኩሪ ለሦስተኛ ጊዜ ወደ ውሃው ጠልቆ ሌላ ተራ መጥረቢያ አወጣ
“ይሄስ?” አለው
ዛፍ ቆራጩ፤“በትክክል ይሄኛው የእኔ መጥረቢያ ነው!” አለ በከፍተኛ ሐሴት ተውጦ፡፡ “እጅግ አድርጌ
አመሰግናለሁ!” አለ፡፡
ሜርኩሪም በጣም ረክቶ፤
“ስለ ታማኝነትህ እነዚህን ሁለት መጥረቢያዎች - ከወርቅ የተሰራውንና ከብር የተሰራውን፤ ሸልሜሃለሁ!”
ብሎ ሰጠው፡፡
ዛፍ ቆራጩ ወደ ሰፈሩ ሲደርስ፤
“ዛሬ ትልቅ ፌሽታ ነው ያጋጠመኝ!” ብሎ የሆነውን ሁሉ ለባልንጀሮቹ ነገራቸው፡፡
ከዛፍ ቆራጮቹ አንዱ ቅናት ይይዘዋል፡፡ ስለዚህ ወደ ወንዙ ሄዶ፣እሱም እድሉን ለመሞከር ይወስናል፡፡
ቀናተኛው ዛፍ ቆራጭ፤ አንድ ከወንዙ ዳር ያለ ዛፍ መቁረጥ ይጀምራል፡፡ ከዚያም አውቆ ወደ ውሃው
መጥረቢያውን ይወረውረውና፤
“ወይኔ መጥረቢያዬ! ወይኔ የሥራ መሣሪያዬ!” እያለ ይጮሃል፡፡
ይሄኔ ሜርኩሪ ብቅ አለ፡፡
“ምን ሆነህ ነው የምትጮኸው?”
“መጥረቢያዬ በሥራ ላይ ሳለሁ ውሃ ውስጥ ወደቀብኝ” አለ፡፡
ሜርኩሪ ወደ ውሃ ውስጥ ጠለቀና አንድ የወርቅ መጥረቢያ ይዞ ብቅ አለ፤ ከዚያም
“የጠፋብህ መጥረቢያ…” ብሎ ሊጠይቀው ሲጀምር፤
ዛፍ ቆራጩ በስግብግብነት፤
“አዎን፡፡ የኔ የራሴ መጥረቢያ ነው! የገዛ ራሴ መጥረቢያ ነው!!” አለና ሁለት እጆቹን ዘረጋ፡፡
ሜርኩሪ የማይታመን ሰው በመሆኑ በጣም በመከፋት፤
“አንተ ታማኝ አይደለህም! ስለዚህም እንኳንስ፤ የወርቅ መጥረቢያ፣ ውሃ ውስጥ የጣልከውን የራስህን
ተራ መጥረቢያም፣ አታገኝም!” አለው፡፡
*   *   *
ታማኝነት የህይወታችን መሰረት መሆን አለበት፡፡ ለሥራ ታማኝ መሆን አለብን፡፡ ለእውቀት ታማኝ
መሆን አለብን፡፡ ለፖለቲካ ታማኝ መሆን አለብን፡፡ ለኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴያችን ታማኝ መሆን አለብን፡፡
ከሁሉ በላይ ደግሞ ለሀገራችንና ለህዝባችን ታማኝ መሆን አለብን፡፡ በሌሎች ላይ ልናደርገው ያሰብነውን ወይም ያደረግነውን በራሳችን ላይ ሲሆን የምንሸሽ፣ አሊያም መመሪያ የምናወጣበት ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡ “ሲያቃጥል በማንኪያ፣ ሲበርድ በእጅ” የምንል ከሆነ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” የምንል ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡
ጐር ቫይዳል ምቀኝነትን ሲገልፅ፤ “ጓደኛዬ ሲሳካለት፣ አንድ ነገር ከውስጤ ይሞታል/ይቀንሳል”
እንዳለው፤ ጓደኛችን የተሻለ አገኘ ብለን ዐይናችን የሚቀላ ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው መንፈስ ነው። “ጐረቤታችን ጫጩት ሲያረባ ስናይ፣ እኛ ሸለምጥማጥ ማርባት የምንጀምር” ከሆነ፣ ፍፁም ታማኝነት የጐደለው የምቀኝነት ድርጊት ነው፡፡ ለእድገት የበቃ ባልደረባችን በደስታ ሲጥለቀለቅ ስናይ፣ እንባ የሚተናነቀን ከሆነ ፈርዶብናል ማለት ነው፡፡ የ”ተያይዘን እንለቅ” ፍልስፍና የትም አያደርሰንም - እርግማን ነው፡፡ በሌሎች ደስታ ውስጥ የእኛን ደስታ ለማየት መቻል አለብን፡፡ ደስታችንን ለሌሎች እናጋራ፡፡ ራስ ወዳድነትን እንታገል!
“ደስታን ከራሱ ጋር፣ አጥብቆ ያሰረ
ክንፍ - ያላትን ህይወት፣ ትንፋሽ አሳጠረ፡፡
ደስታ እየከነፈች፣ የሳማት ሰው ግና
የዘለዓለም ፀሀይ ይሞቀዋል ገና”፤ እንዳለው ነው ዊልያም ብሌክ፡፡
ደስታችን የአገር ይሁን እንደ ማለት ነው፡፡ ደስታ የእኔና የእኔ ብቻ ይሁን ብሎ የሙጥኝ አለማለት ነው። ከአገር ካዝና የወጣ ደስታ፤ የአገር ነውና ለህዝብ እናዳርሰው፡፡ ለራሳችን ሸሽገን አንቀራመተው ማለት ነው። የጋራ ቤታችንን እናስብ፡፡ በፓርቲ አጥር አንታጠር፡፡ ደፋር - መሀይም ብቻ ሳይሆን፣ ጭምት - ምሁር የሚኖርባትም አገር እናልም! ዕቡይ - ምሁር ብቻ ሳይሆን ያልተማረ - ጨዋ ህዝብ ያላት አገር እናስብ። ከፓርቲም ውጪ በቤተሰብ፣ በቢሮ፣ በተቋም፣ በንግድ ድርጅት ውስጥ የሚኖር ነፃ ዜጋ አለ ብለን፣ ከሳጥን ውጪ እንመልከት! ቢያንስ ባስበው ያስበኛል ብሎ ግንዛቤ መውሰድ ያባት ነው፡፡ “የእኔ ወንበር እስካልተነካች ድረስ” የሚል እሳቤ፤ ኃላፊነትን ዘንግቶ አጥር ማጠር፣ ረጅም ጊዜ መኖርን ከዘለዓለማዊነት ጋር ማምታታት ነው (Mistaking Longevity for immortality እንደ ማለት ነው)፡፡ በዚህም እሳቤ ምክንያት ነው መተካካትን ከብወዛ ጋራ አንድ አድርገን (Mistaking Replacement for Reshuffling እንደ ማለት) የምናየው፡፡ ወደድንም ጠላንም ቢያንስ ማንም ሰው ሊተካ የሚችል ነው፤ የማይተካ የለም (No one is indispensable) የሚለውን ሁለንተናዊ መርህ ያለ ራስ ወዳድነት፤ ያለ ምቀኝነት እንቀበል፡፡
ከአጠቃላይ ነባራዊ እውነታው፤ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር፤ አናመልጥም፡፡ እውነታውን ተቀብሎ መፍትሄውን መሻት ከአላስፈላጊና ከማናመልጥበት ሽሽት ይገላግለናል፡፡ አገርም ለቅቀን እንሽሽ ብንል አይሆንም፡፡ ከራስ የህሊና ቁስል ማምለጥ አይቻልምና፡፡ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ የናዚም ወታደር ይያዛል፤ ተብሏል፡፡ በመሸሽ፣ በመሸሸግና ሌላ አገር በድሎት ከመኖር ጋር ራስን ማስተሳሰር ቢያንስ የዋህነት ነው። እንኳን በባሌ በቦሌም ምቾት ቅርብ አደለም፡፡ ምቾትና ነፃነትን በሌላ ምድር ማግኘት ቀላል አይደለም፡፡ በሰሜንኛ፤“ጠላ አገኛለሁ ብለህ ውሃ ረግጠህ አትሂድ”ይባላል፡፡ በወላይትኛ ደግሞ፤“በውሃ የሚያቦኩበት አገር መጥፎ ነው ብላ፤ በምራቅ የሚያቦኩበት አገር ደረሰች”ማለት ነው፡፡ በማህል አገርኛ፤“ከድጡ ወደ ማጡ” ብለው ያጠቃልሉት ይሆናል፡፡ ብቻ ከዚህ ይሰውረን!!

• ፓርቲ በመንግስት ተቋማት ውስጥ ጣልቃ መግባቱ መገታት አለበት
• ተቃዋሚዎች በፓርላማ አለመኖራቸው ለስርአቱ ስጋት ነው ተባለ

የፌደራል ስርአቱ በህገ መንግስቱ መሰረት በአግባቡ እየተተገበረ አለመሆኑ፣ የሀገሪቱን አንድነት ስጋት ላይ እንደጣለ ሰሞኑን የቀረቡት ጥናቶች ያመለከቱ ሲሆን በፓርላማው የተቃዋሚ ድምፅ አለመኖሩም ለፌደራል ስርአቱ ስጋት ነው ተብሏል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት ከትናንት በስቲያ በተከናወነ የአንድ ቀን አውደ ጥናት ላይ በዩኒቨርሲቲው ምሁራን “በፌደራል ስርአቱ ላይ” የቀረቡ ጥናቶችን መነሻ በማድረግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሳተፉበት ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡ በመድረኩ ላይ ጥናታዊ ፅሁፍ ካቀረቡት ምሁራን መካከል ፕ/ር አሰፋ ፍሰሀ፤ባለፉት 26 ዓመታት የተገነባው የፌደራል ስርአት የተለያየ ማንነት ያላቸውን ህዝቦች በራስ የመተዳደር መብት በማጎናፀፍና እርስ በእርስ በማቀራረብ በኩል ውጤታማ መሆኑን ጠቁመው፤በዚህ መሃል ግን የዜጎች መብት በተለያዩ ግለሰቦች መጣሱ ለፌደራል ስርአቱ አደገኛ ነው ብለዋል፡፡
ዜጎች ከሀገራዊ እሳቤ ይልቅ ክልላዊና መንደራዌ እሳቤ ላይ ማተኮራቸው አሳሳቢ መሆኑን የጠቆሙት ምሁሩ፤ ይህን አመለካከት ለመቀየር በርካታ የፖለቲካ ስራዎች መሰራት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ የፌደራሊዝም ስርአቱ ዋነኛ አላማ፤ ጎሰኝነትንና ክልላዊነትን ማስፈን እንዳልሆነ ባልተገነዘቡ ሰዎች፣ ባልተገባ መንገድ እየተተረጎመ መሆኑንም አስረድተዋል -ምሁሩ፡፡  
በፌደራሊዝም ስርአት ግንባታ ውስጥ ዋነኛ ምሰሶ የሆነው ህገ መንግስቱ በሚገባ በተግባር ላይ ካልዋለ ቅሬታና ግጭት እንደሚያስነሳ በጥናታቸው ያመለከቱት ሌላው የፅሁፍ አቅራቢ ፕ/ር ካሣሁን በሪሁን፤ ህገ መንግስቱ መሬት ላይ ሲተረጎም በአግባቡ አለመሆኑ የፌደራሊዝም ስርአቱ ተግዳሮት ነው ብለዋል፡፡ የመንግስትና የፓርቲ ጉዳይ መደበላለቅም የወቅቱ የፌደራሊዝም ስርአቱ እንቅፋቶች መሆናቸውን የጠቆሙት ጥናት አቅራቢዎቹ፤ ፓርቲ በመንግስት ተቋማት ውስጥ ጣልቃ መግባቱ መገታት አለበት ብለዋል፡፡  
“በቤኒሻንጉል፣ ኦሮሚያና ሌሎች ክልሎች፣የሌላ ብሄር ተወላጆች በየጊዜው መፈናቀላቸው ብሄርና ቋንቋን መሠረት ያደረገው ፌደራሊዝም ውጤት ነው” የሚል አስተያየት ከመድረኩ የተሰነዘረ ሲሆን ጥናት አቅራቢዎች፤ ”የመንግስት አስፈፃሚ አካላት ችግር የፈጠረው ነው” ብለዋል፡፡ ፌደራሊዝሙ ለምን በመልከዓ ምድራዊ አቀማመጥና በህዝብ ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ አይሆንም የሚል ጥያቄም ከተሣታፊዎች የተሰነዘረ ሲሆን ከመድረኩ በተሠጠው ምላሽ፤ ከዚህ በኋላ አሁን ያለውን የፌደራል ስርአት ቅርፅና ይዘት አጠናክሮ ከማስቀጠል ውጪ ወደ ኋላ መመለስ አደጋ እንዳለው ተጠቁሟል፡፡ “ችግሮቹን ነቅሶ አውጥቶ፣ እያረሙና እያስተካከሉ መጓዝ እንጂ ከዚህ በኋላ እንደገና መመለስ የሚፈጥረው ቀውስ ከባድ ይሆናል”
“የማንነት፣ የወረዳና ዞን እንሁን” ጥያቄዎች በሰፊው እየቀረቡና ለግጭትም መንስኤ እየሆኑ መምጣታቸው ፌዴራሊዝሙን አደጋ ላይ እንደጣለው የተጠቆመ ሲሆን መፍትሄው ፖለቲካዊ መግባባት መፍጠርና የዜጎች ድምፅ የሚሰማበትን አማራጭ ማስፋፋት ነው ተብሏል፡፡
የዘንድሮ 26ኛው የግንቦት 20 በዓል፤ ‹‹የህዝቦች እኩልነት፣ ፍትሃዊነትና ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ፌደራላዊ ስርአት እየገነባች ያለች ሃገር›› በሚል መሪ ቃል እየተከበረ ሲሆን በዓሉ በዋናነት በክልሎችና በውጪ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች በድምቀት እንደሚከበርም ለማወቅ ተችሏል፡፡  

የፍርድ ቤት የእግድ ትእዛዝ በመጣስ፣ በአዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ፣ ልዩ ስሙ የካ አባዶ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የምትገኘውን የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ያፈረሱ፣ የወረዳ 12 አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈጻሚና የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት ሓላፊ፣ በ15 ቀን ቀላል እስራት እንዲቀጡ የከተማው ይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት ወሰነ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትፈርስ የሥር ፍ/ቤት የሰጠው ውሳኔ ግን፣ “ይግባኝ አያስቀርብም” ብሏል፡፡
በይግባኝ ባይ፥ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር እና በመልስ ሰጪ፥ የየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ደንብ ማስከበር አገልግሎት ጽ/ቤት መካከል ያለውን የይግባኝ ቅሬታ ሲመረምር መቆየቱን ከትላንት በስቲያው ውሳኔው ያስታወቀው ፍ/ቤቱ፤ መልስ ሰጪዎቹ፥ የወረዳው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ደመላሽ ጎሳ እና የደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ ሓላፊ አቶ ዳዊት ሙሉጌታ፤ የፍ/ቤትን የእግድ ትእዛዝ እያዩ፣ ክርክር የቀረበባትን ቤተ ክርስቲያን ማፍረሳቸው፣ የፍርድ ቤትን ሥራ ማወክ በመኾኑ ጥፋተኛ ኾነው እንደተገኙ ገልጿል፡፡
በይግባኝ ባይ በኩል የቀረቡ አራት ምስክሮች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳዳሪ ሊቀ ካህናት በየነ አሰፋ፥ “የፍ/ቤት የእግድ ትእዛዝ አለ፤ በሕግ አምላክ አታፍርሱ” እያሉ ለተጠቀሱት ሁለት ሓላፊዎች እንዳሳዩዋቸው፤ እነርሱ ግን ለማቆም ፈቃደኛ እንዳልነበሩና በግብረ ኃይል ቤተ ክርስቲያኒቱን እንዳስፈረሱ፣ በበቂ ሁኔታ ማስረዳታቸውን ፍ/ቤቱ በውሳኔው ጠቅሷል፡፡ በመልስ ሰጪዎች የቀረቡ ሁለት ምስክሮች፣ አፍራሽ ግብረ ኃይል ሆነው የማፍረስ ተግባር ያከናወኑና ምስክርነታቸው እርስ በርሱ የሚጋጭ ሆኖ በመገኘቱ፣ “ገለልተኛና ተኣማኒነት ያለው ኾኖ አላገኘነውም፤” ብሏል፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ “የጣስነው ሕግ የለም፤ የወሰድነው ርምጃም ተቋሙን ወክለን ነው፤” በሚል የቅጣት ማቅለያ ያቀረቡ ቢኾንም፣ ፍ/ቤቱ፥ “ጥፋተኞችንም ኾነ ሌሎች ግለሰቦችን ያስተምራል፤” በሚል አቶ ደመላሽ ጎሳ እና አቶ ዳዊት ሙሉጌታ፣ ውሳኔው ከተሰጠበት ቀን ጀምሮ በ15 ቀን ቀላል እስራት እንዲቀጡ ወስኗል፤
በሌላ በኩል፣ የሥር ፍ/ቤት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ይዞታና ግንባታ ሕገ ወጥ ነው፤ በሚል መጋቢት 13 ቀን 2009 ዓ.ም.፣ የሰጠው ውሳኔ፣ የሚነቀፍበት ምክንያት እንዳላገኘበት የይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤቱ ጠቅሶ፤ “መልስ ሰጪን መጥራት ሳያስፈልግ፣ ይግባኙ አያስቀርብም” በማለት መዝገቡን መዝጋቱን በተጨማሪ ትእዛዙ አስታውቋል፡፡ የደብሩ አስተዳደር፣  ለሰበር ሰሚ ይግባኝ እንደሚጠይቅ ተጠቁሟል፡፡