Administrator

Administrator

“ገዴ” እና “ቢሰጠኝ” በተሰኙ ቀደምት አልበሞቿ ተቀባይነትን ያገኘችው ዝነኛዋ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ፤ “የፍቅር ግርማ” የተሰኘ ሶስተኛ አዲስ አልበሟ ለአድማጭ ቀረበ፡፡ አልበሙ 11 ዘፈኖችን ያካተተ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አንዱ የተፈራ ደምሴ ግጥም የሆነው “ካምፕፋየር” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ሙዚቃ እንደሆነ ድምፃዊቷ ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡ የአምስቱን ዘፈኖቿን ግጥም አንጋፋው ገጣሚ ይልማ ገ/አብ፣ አንዱን ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ጌትነት እንየው፣ ሶስቱን ፋሲል ከበደ የተሰኘ አዲስ ገጣሚ፣አንዱን ደግሞ #ህመሜ” የተሰኘው ነጠላ ዜማዋ ገጣሚ አብዲ ራዋ የሰሩላት ሲሆን ዜማውን በአብዛኛው ራሷ ድምፃዊቷ እንደሰራችና አንዱን ሄኖክ መሀሪ እንደሰራላት ተናግራለች፡፡
“ካምፕፋየር” የተሰኘውን የእንግሊዝኛ ሙዚቃ ቅንብር ኬሊ አለን የሰራላት ሲሆን  የሌሎቹን ቅንብር አቤል ጳውሎስ መስራቱንና አሳትሞ ያከፋፈለው ኤራ ኮሙዩኒኬሽንና ኤቨንት እንደሆነ ድምጻዊቷ ጠቁማለች፡፡  
 ጸደንያ በዘንድሮ ዓመት ብቻ የ“አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” (አፍሪማ)፣ የ“ለዛ አድማጮች” እና ለ“ሀሪየት” ፊልም በሰራችው የማጀቢያ ሙዚቃ የ#ጉማ አዋርድ” ሶስት ሽልማቶችን አሸናፊ ለመሆን የበቃች ሲሆን በአገራችን ብቸኛዋ የ“ኮራ አዋርድ” ተሸላሚ እንደሆነችም ይታወቃል፡፡


ከ10 ብር እስከ 34 ሺ ብር የተገዙ መጻህፍት ይገኛሉ
በቅርቡ “The Book Cafe” ይከፈታል ተብሏል
ካፌው ሲከፈት በዓመት 3 መጻህፍትን በነጻ ያሳትማል

     በተለምዶ 22 ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ልዑል ሲኒማ የሚገኝበት “አናት ህንፃ” ፊት ለፊት አንድ ባርና ሬስቶራንት ያገኛሉ፡፡ ከስሙ ጀምሮ ከለመድናቸው ባርና ሬስቶራንቶች በእጅጉ ይለያል። እግርዎ አንዴ ወደ ውስጥ ከዘለቀ ወደ የትኛውም ክፍል ሲገቡ (መፀዳጃ ቤትና በረንዳውን ጨምሮ) በሚያዩት ነገር ግራ ሊጋቡ አሊያም ሊደመሙና ሊደነቁ ይችላሉ፡፡ ባሩም ሬስቶራንቱም፣ መፀዳጃ ቤቱም፣ በረንዳውም የሚያመሳስላቸው በመጻሕፍት የተከበቡ መሆናቸው ነው፡፡ በዓለም ላይ አሉ የተባሉ ዝነኛ መፅሐፍት እዚህ ይገኛሉ፡፡ ምን መፅሐፍት ብቻ ---- በአገሪቱ ያሉ የህትመት ውጤቶችም አይቀሩም፡፡ ደንበኞች መፅሄትና ጋዜጦችን ከትኩስ ቡና ጋር ያወራርዳሉ፡፡ ንባብ ክፍያ የለውም፡፡  
መፅሐፍቱ አይነታቸው ብዙ ነው፡፡ የርዕዮተ ዓለም ቢሉ፣ የፍልስፍና አሊያም ግለ ታሪኮች፣ የ60ዎቹ ፖለቲካ መጻህፍት፣ የአማርኛ ልብወለዶች፣ የጥናትና ምርምር ሥራዎች --- ብቻ የሚነበብ ሞልቷል፡፡ ይህ በከተማችን ምናልባትም በአራችን ለየት ያለ የመዝናኛም የማንበቢያም ቦታ #ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንት ይባላል፡፡ ለስጋም ለነፍስም የሚሆን ምግብ የሚገኝበት ሥፍራ በሉት፡፡ እንዲያው ለነገሩ ባለቤቶቹን ምን አሳስቧቸው ይሆን ለደንበኞቻቸው መረጃና ዕውቀት እንዲህ ጭንቅ ጥብብ ያሉት፡፡ ለነገሩ ሌላም ዕቅድ አላቸው፡፡ በቅርቡ “ዘ ቡክ ካፌ” የተባለ ቡና ብቻ እየተጠጣ የሚነበብበት ካፌ እንደሚከፍቱ ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ለናፍቆት ዮሴፍ ነግረዋታል፡፡ ይህ ካፌ ሲከፈት ኢትዮጵያ ውስጥ በገንዘብ ማጣት መፅሐፍ ማሳተም ያቃተው ፀሐፊ (ደራሲ) አይኖርም፤ይላሉ የባርና ሬስቶራንቱ ባለቤት አቶ ሀብቶም ገ/ሊባኖስ፡፡ እንዴት? የመጀመሪያ ድግሪያቸውን በማኔጅመንት፣ሁለተኛ ድግሪያቸውን በሂዩማን ሪሶርስ እንዳገኙ ከሚናገሩት አቶ ሀብቶም ገ/ሊባኖስ ጋር ሪፖርተራችን ያደረገችውን አስደማሚ ቃለምልልስ እንዲህ አጠናቅረነዋል፡-  
 “ሰለብሪቲ” የተሰኘውን ባርና ሬስቶራንት እንዴት እንደከፈቱ ቢያጫውቱኝ?
አዎ፤“ሰለብሪቲ” የተከፈተው የኢትዮጵያ አርቲስቶች የሚገናኙበትና ሰብሰብ ብለው የሚጨዋወቱበት ሥፍራ እንዲሆን ታስቦ ነው። ውጤታማ ሆነና ጥሩ ነገር አየን፤ከዚያ ደግሞ “ዘ ቡክ”ን ከፈትን፡፡
“ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንትን ለመክፈት እንዴት አሰቡ፤ምክንያቱም በአገራችን የተለመደ አይደለም----
እንደሚታወቀው በተለይ የኢትዮጵያ ፀሐፊያንና ደራሲያን በየቦታው ነው ያሉት፤መፅሐፋቸውም ዲስፕሌይ የለውም፡፡ ምናልባት በዓመት አንድ ጊዜ የሚዘጋጅ አውደ ርዕይ ጠብቀው ነው መፅሃፋቸውን የሚያሳዩት፤ስለዚህ አንድ ዲስፕሌይ ማግኘት አለባቸው በሚል ነው የ “ዘ ቡክ”ን ሀሳብ ያመጣነው። ለወንድሞቼ ሳማክራቸው በጣም ደስተኞች ነበሩ። ወንድሞቼ አንድ ሀሳብ ስታቀርቢላቸው፣እንዴት እንደሚያዳብሩት ብታይ ይገርምሻል፡፡ ጎበዞች ናቸው፡፡ አሁን “ዘ ቡክ” ለዚህ በቃ ማለት ነው፡፡
“ዘ ቡክ” የተከፈተው መቼ ነው? ምን ያህል መፅሐፍትን ይዞ ጀመረ? አሁንስ ምን ያህል መፅሐፍት በውስጡ ይገኛሉ?
የተከፈተው ከሶስት ወር በፊት ነው፤ሲከፈት መኖሪያ ቤታችን ውስጥ የነበሩ አንድ ሺህ ሀምሳ (1050) መፅሀፍት አምጥተን ነው የደረደርነው። አሁን ከሁለት ሺህ በላይ አለም ላይ አሉ የተባሉ መፅሐፍትን ይዘናል፡፡ ይህን አላማችንን ያዩ ምሁራን፣ እዚህ ሻይ ቡና ለማለት የሚመጡ ደንበኞች በስጦታ እየሰጡን ቁጥራቸው ከፍ እያለልን ይገኛል። መፅሀፍት እቤትሽ አንብበሽ ስታስቀምጫቸው ጌጥ ብቻ ነው የሚሆኑት፤እንዲህ ዓይነት ቦታ ስታመጫቸው ግን በርካታ ሰው ያያቸዋል፤ብዙ ሰው ቡና ፉት እያለ አንዳንድ ቁም ነገሮችን ጨብጦበት ይወጣል፡፡ የማንበብ ልማድ ይዳብራል፤በርካታ ጠቀሜታ አለው፡፡
 በእርግጥ እናቴ መፅሐፍቱን ከቤታችን ይዤ ስወጣ፣ ቤቱ ጭር አለብኝ ብላ ቅሬታ ተሰምቷት ነበር፡፡ ወይ ተኩልኝ አለበለዚያ መኖሪያዬን እዚህ አድርጉልኝ እስከማለት ደርሳለች፤እስከ 8ኛ ክፍል ተምራለች፤ጥሩ የማንበብ ልምድም አዳብራለች፡፡
ተዘዋውሬ እንዳየሁት ብዙ አይነት መፅሐፍት አሉ፡፡ እንደው በዋጋ ደረጃ ውድ የሚባለው የትኛው መፅሐፍ ነው? እኔ መንገድ ላይ አግኝቼ የገዛሁትን የአቤ ጉበኛ መፅሐፍም እዚህ አይቸዋለሁ ----
በነገራችን ላይ መፅሐፍን በዋጋ መተመን ያስቸግራል፡፡ አንድ መፅሀፍ ይነስም ይብዛም የራሱ የሆነ ፋይዳ ይኖረዋል፡፡ ዋጋው መብዛቱና ማነሱ የመፅሀፉን ይዘት አይወክልም፡፡ የሆነ ሆኖ የአቤ ጉበኛ መፅሐፍ የተፃፈው በእንግሊዝኛ ቢሆን ከ60ዎቹ የፖለቲካ መፅሀፍት ግንባር ቀደም ይሆን ነበር፡፡ በአማርኛ ቋንቋ በመገደቡ ዛሬ መንገድ ላይ አስር ብርና ከዚያ በታች ቢሸጥ አይገርመኝም፡፡ እኛ እዚህ ሼልፍ ውስጥ ስናስቀምጠው ሰው እቤቱ ጥሎት ከነበረ አስታውሶ እንደገና ሌላ ሰው እንዲጠቀምበት ያደርጋል፡፡ አሁን እኛ ጋ የፕሮፌሰር ጆሴፍ ስቲግሊትዝ ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው “Globalization and Its Discontents” እስከሚለው ድረስ አለን፡፡ ይህ ሰው የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ሌክቸረር፣ የዓለም ባንክ ከፍተኛ ኢኮኖሚስት ሆኖ ያገለገለ ነው፡፡ በተለይ የመጨረሻው መፅሐፉ ከኢኮኖሚ አንፃር ኢትዮጵያንና መለስ ዜናዊን አስመልክቶ የሰጠው ትንታኔ በጣም የሚገርም ነው፡፡ የዚህ ምሁር “Free Fail” የተሰኘ መፅሀፍ አለ፤በአንድ ሺህ ሰባት መቶ ዶላር ከለንደን ነው ያስመጣነው፡፡ እዚህ እኛ ባርና ሬስቶራንት ውስጥ ይገኛል፡፡ ትልቁም ዋጋ እስካሁን ይሄ ነው፡፡ በዋጋ ደረጃ ቅድም እንዳልሽው ባለ 10 ብርና ባለ 1700 ዶላር አለ ለማለት ነው፡፡ ይዘታቸው ሲመዘን ግን የ10 ብሩ ከ1700 ዶላሩ የሚተናነስ አይደለም፤ የጊዜና የመገኘት ሁኔታው ልዩነት እንጂ፡፡
በዚህ ባርና ሬስቶራንት ውስጥ የሚገኙ መፅሐፍትን ደንበኞች በምን መልኩ ነው መጠቀም የሚችሉት?
ደንበኞች እዚህ ቡና እየጠጡ የትኛውንም መፅሀፍ፣ ጋዜጣም ሆነ መፅሄት አንብቦ የመመለስ መብት አላቸው፡፡ በሌላ በኩል እዚህ የታሪክ፣ የርዕዮት ዓለም፣ የልቦለድ፣ የጥናት ውጤቶች ወዘተ-- ምንም የሌለ የለም፡፡ አንድ ሰው መጥቶ ይህን መፅሐፍ ለጥናትና ምርምር እፈልገዋለሁ፤በማጣቀሻነት እጠቀመዋለሁ፤ ለአገሪቱ ይበጃል፤የሚል ከመጣ ደግሞ ደግመን የማናገኘው የመጨረሻ ውድ መፅሐፍ እንኳን ቢሆን በውሰት እንሰጣለን፡፡ እዚህ ዲስፕሌይ የሆነው ለጌጥ ሳይሆን ለዚህ ዓይነት ፋይዳ ነው፡፡ የራሴ ኮርነር እንዲኖረኝ ፍቀዱልኝ የሚል ደራሲም ካለ ኮርነር ይሰጠዋል፡፡ በረንዳ ላይ የአዳም ረታ ኮርነር እንዳለ ተመልክተሻል፡፡ ቤቱን እኛ እንክፈተው እንጂ የህዝብ መማሪያ እንዲሆን ነው የምንፈልገው፡፡
አንድ ግለሰብ መፅሐፍ መዋስ ቢፈልግ፣ በምን ዋስትና መዋስ ይችላል?
እንግዲህ እኛ መፅሐፍ አውሱኝ ለሚለው ሁሉ አናውስም፡፡ ለምናውሳቸው ደግሞ መታወቂያ አንጠይቅም፡፡ ደንበኞቻችንን እናውቃለን፤ እንመዝናቸዋለን እናውሳለን፡፡ እስካሁን ወስዶ ያስቀረብን የለም፤ ሲያቆዩ እንኳን ደውለው ፊልድ ወጥቼ ነው፣ እንዲህ ሆኜ ነው ብለው ያሳውቃሉ፡፡
ባርና ሬስቶራንቱን ሲያስጎበኙኝ በቅርቡ ለሚከፈት ቤተ-መፃህፍት የተዘጋጀ ቦታ አሳይተውኛል፡፡ መቼ ነው የሚከፈተው? ያኔ በሬስቶራንቱ ውስጥ ያሉት መጻህፍት ተሰብስበው ቤተ-መፃህፍት ይገባሉ ማለት ነው?
እነዚህ የ “ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንት ናቸው፤አይነኩም፡፡ ቤተ-መጻህፍቱ በሌሎች በግዢም በስጦታም በሚሰበሰቡ መፅሐፍት ነው የሚሞላው፡፡ የ“ዘ ቡክ ካፌ” ስራ ከላይብረሪው ነው የሚጀምረው፡፡ በረንዳ ላይ አንዱ ዲስፕሌይ በየሶስት ወሩ በአዳዲስ መፅሀፍት ይቀየራሉ፡፡ ሌሎቹ ቋሚ ናቸው፡፡
 ቤቱ ምግብና መጠጥ ይሸጣል፡፡ ንባብና መጠጥ አብረው ይሄዳሉ ብለው ያስባሉ?
ጥሩ ጥያቄ ነው፤ስለተነሳ አመሰግናለሁ፡፡ አብዛኛው ሰው ቡና እየጠጣ ነው የሚያነበው። እኛ  ዋና አላማችን ሰው እየጠጣ ባያነብ እንኳን መፅሐፍቱን አይቷቸው፣ ነገ ቤቱ ሲሄድ ስራ እንዲሰራባቸው እንዲያነባቸው ማስታወሻ መስጠት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ቢራም ዋይንም እየተጎነጩ በተመስጦ የሚያነቡ አሉ፡፡
ቤቱም ብዙ ጫጫታና የሚጮህ ሙዚቃ የለበትም፡፡ እዚህም የሚመጡ ደንበኞች በአብዛኛው ከቤቱ ድባብ ጋር አብረው የሚሄዱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ፀሐፊዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ ምሁራን ---ወዘተ፡፡ መቀመጫውም ድጋፍ ያለው ምቹ ሶፋ ነው፡፡ ብዙዎቹ አንድ ሁለት እያሉ በጥልቀት የሚወያዩ ምሁራን ናቸው፡፡ ቤቱ ሰዎች እንዲሰክሩ የሚጋብዝ ድባብ የለውም፡፡ ሰው ቡና ወይ ሻይ ብቻ እየጠጣ፣ ቀን ብቻ እየተገናኘ መወያየት፣ ማንበብ ሊሰለቸው ይችላል፡፡ ይሄ እንደ አማራጭ ከስራ በኋላ ሰዎች ተሰባስበው ፍሬ ያለው ነገር የሚወያዩበት ነው፡፡
ባር ሁሌ መስከሪያና የፀብ መነሻ መሆኑ ቀርቶ ሰዎች እያረፉ የሚዝናኑበት፣እውቀት የሚገበዩበት የማይሆነው ለምንድን ነው ከሚል እሳቤ ነው ይህን ሁሉ የምንደክመው፤ግን ደስተኞች ነን፤ዓላማችንም ግቡን የሳተ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ አንዳንዴ ሰዎቹ እየተጎነጩ የሚያነሷቸው ሀሳቦች የሚገርሙ ናቸው። እዚህ ተዋውቀው ጓደኛ የሆኑ፣ መፅሐፍ እስከ መዋዋስ የደረሱ ሰዎችን ስመለከት ደስታ ይሰማኛል፡፡
 ከዚሁ ከመፅሐፍት ጋር ግንኙነት ያለው አዲስ ስራ እንዳሰባችሁም ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለሱ ያጫውቱኝ?
እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በቀጣዮቹ ስድስት ወራት ውስጥ “The Book Cafe” የተሰኘና ቡና እየተጠጣ ብቻ የሚነበብበት ካፌ ለመክፈት ዝግጅት ጨርሰናል፡፡ ይህ ካፌ ሲከፈት ኢትዮጵያ ውስጥ በገንዘብ ማጣት መፅሐፍ ማሳተም ያቃተው ፀሐፊ (ደራሲ) አይኖርም፡፡
ያብራሩልኝ ---- እንዴት ማለት?
በዓመት ሶስት መፅሐፍትን በነፃ ለማሳተም እቅድ ይዘናል፡፡ ካፌው የኢትዮጵያን ቡና ያስተዋውቃል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የተፃፉ መፅሐፍት ማሰባሰብ ላይ ይተጋል፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ለህትመት በቅተው የነበሩ በማንኛውም ጉዳይ ላይ የሚያተኩሩ መፅሐፍት ተለቅመው፣ ታድነው ወደ ካፌው ይገባሉ፡፡ ይሄ ማለት የግል የሆነ ልክ የወመዘክር አይነት ቤት ነው የሚሆነው፡፡ ይሄን በወንድሞቼ በኩል አሳካለሁ፡፡ እኔ ኖርኩም አልኖርኩም እነሱ ያሳኩታል፡፡
ሥራችሁ ከመጻህፍት ከአርቲስቶችና ከኪነጥበብ ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው ይመስላል፡፡ ከዚህ ቀደም በስራቸው ውጤታማ የሆኑ አርቲስቶችን እንደሸለማችሁና ነገም በዚሁ ሬስቶራንት የትግርኛ ዘፈን ግጥም ደራሲውን ዳዊት ሰለሞንን እንደምትሸልሙ ሰምቻለሁ ----
አዎ ኪነ ጥበቡም አንዱ እሴታችን ነው፡፡ ከዚህ በፊት የሸለምናቸው አሉ፡፡ አሁን የትግርኛ ዘፈን የጀርባ አጥንት የሆነውን ዳዊትን እሁድ ምሽት እንሸልማለን፤ሽልማቱ ሰርፕራይዝ ስለሆነ ዝርዝር ነገር አልናገርም፤ በሰዓቱ ተገኝተሽ መመልከት ትችያለሽ፡፡     



   አንዳንድ ተረት ካልተደጋገመ የሚሰማ የለም፡፡ ይሄንንም በድጋሚ አቅርበነዋል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ትልቅ ዝሆን አንድ ትልቅ ገደል ውስጥ ወድቆ ይሞታል፡፡ ሌሊቱን የተራቡ ጅቦች ወደ ገደሉ አፋፍ መጥተው፣ ዞር ዞር ሲሉ ዝሆን እጅግ አዘቅት በሆነው ገደል ውስጥ ገብቶ መሞቱን አዩ፡፡
ከፊሎቹ ጅቦች፤
“እንዴት ግዙፍና የሰባ ዝሆን ነው?”
ኧረ እንግባና የተራበ አንጀታችንን እናርስ!” አሉ፡፡
አንዳንድ ብልህ ጅቦች ግን፤
“ኧረ ጐበዝ! እጅግ ሩቅ ወደሆነው ወደዚህ ጉድጓድ ገብተን፤ ኋላ ሆዳችን ሲሞላ ተመልሰን ወደ ገደሉ አፋፍ መውጣት የማይሞከር ነገር ነው” አሉ፡፡
ብዙዎቹ ጅቦች፤
“እቺን ዳገት ብላችሁ ታወራላችሁ? ተደጋግፈን ፉት እንላታለን፡፡ ይልቅ በረሃብ ሳንሞት ቶሎ እንወስን”
ጥቂቶቹ ጅቦች፤
“ኧረ ይሄ ገደል የዋዛ አደለም ጐበዝ! አንዴ ከገባን መመለሻም የለን”
ብዙዎቹ ጅቦችም፤
“የምትጨቃጨቁን ከሆነ፤ ያለው መፍትሔ ድምጽ እንስጥና አብላጫውን ድምጽ ያገኘው አሸናፊ ይሁን!”
ይሄው ዋናው የውሳኔ ሃሳብ ሆነና
“ድምፅ ይሰጥ” ተባለ፡፡
ድምጽ ተሰጠ፡፡
“ወደ ገደሉ ገብተን የሞተውን ዝሆን እንብላና ረሃባችንን እንመክት!” ያሉት አሸነፉ፡፡
ጅቦቹ ሁሉ ተንደርድረው፣ ተግተልትለው፣ ወደ ገደሉ ገቡ፡፡
ያን ድልብ ዝሆን ተያያዙት፡፡
ጠገቡ፡፡ ለጥ ብለው ተኙ፡፡ ነጋ፡፡
የተረፈውን ተቀራመቱ፡፡ ቀናት እየገፉ ሲሄዱ የዝሆኑ ስጋ ተመናመነና አለቀ፡፡
ቀና ብለው የገደሉን ጫፍ አዩት፡፡
በጭራሽ የሚሞከር ነገር አይደለም፡፡
“ኧረ እንዴት ነው ይሄን ገደል የምንወጣው?”  አለ አንዱ ጅብ፡፡
ብዙዎቹ ጅቦች፤
“እስቲ ማታውን አድረን እናስብበትና ጠዋት መላ እንመታለን” አሉ፡፡
ነገም መጥቶ አፈጠጠ፡፡ ዘዴ ግን ከቶ አልተገኘም፤ የዝሆኑ አይደለም ስጋው አጥንቱም አልቋል፡፡ ስለዚህ በራሳቸው በጅቦቹም መንደር ረሃብ ገባ፡፡ ረሀብ መጣ፡፡
አንድ ሌሊት ሁሉም ጅቦች ለጥ ብለው ባሉበት፤ አንድ ሁለት ጅቦች ነቁ፡፡
ምክር ጀመሩ፡፡ አንደኛው ጐኑ ላለው፤
“መቼም በረሃብ ከምንሞት እንቅልፍ የወሰደውን አንዱን ጅብ ብንበላ እሰየው ነው፡፡ ምን ይመስልሃል?”
ሁለተኛው፤
“ጐንህ ያለውን ቀስቅሰውና ሃሳቡን አካፍለው” አለው፡፡ ያም እንዳለው አደረገ፡፡
ደሞ ያኛውም ጐኑ ላለው ቀጠለ፡፡ የመጨረሻው፣ ዳር ላይ ያለው፣ እንዳንቀላፋ ተበላ!
ይሄ ሂደት ቀጠለ፡፡ በሚቀጥለው ሌሊት ዳር ላይ ያንቀላፋ ተበላ! እንዲህ እንዲህ እያለ ያ ሁሉ ጅብ ተራ በተራ ተበላ! በመጨረሻ ሁለት ብቻ ቀሩ፡፡ አንዱን በጣም ያንቀላፋ ጅብ፣ ሌት አንደኛው ቅርጭጭ አረገው!
አንድ ብቻውን የቀረውን፤ እንደፈረደበት ረሀብ ራሱ በላው!!
***
እርስ በርስ የመበላላት ባህል የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡ ከታሪክ እስከ ዛሬ፡፡ ወይ በፖለቲካ ሽኩቻ፣ ወይ በኢኮኖሚ ድቀት አሳቻ፣ ወይ በባህል ልምሻ ዛቻ፣ ወይ በሶሻል ቀውስ ውድቀት አቻ፤ …አገር መበላላትን መቀበል ከጀመረችና ካመነች ቆይታለች፡፡ አያሌ የፖለቲካ ድርጅቶችን አይታለች፡፡
አስገራሚው ነገራችን፤ ትላንት የተበላውን ዛሬ በቦታው የተቀመጠው ጠንቅቆ ለማስተዋል አለመቻሉ! “የማስጠንቀቂያውን ደወል” እንኳን ሳያይ፣ ያለፈውን መራገምና ራሱን መልዐክ ማድረግ፣ ነው ፈሊጡ፡፡ አልፎም ተፈጥሮዬ ነው እስከማለት ደርሶ ወንበሩን ሙጥኝ ማለቱ፡፡ ቀጥሎም በራሱ ጊዜ “አወዳደቄን አሳምርልኝ!” ሳይል የቀደመው ባለስልጣን በወደቀበት መንገድ መንኮታኮቱ ነው፡፡ ስለ ምን አንዱ ካንዱ አይማርም? አካሄዱንስ ስለ ምን አይለውጥም? ኢ-ፍትሐዊነትን፣ ኢ-ዲሞክራሲያዊነትን፣ ሙስናን እንቋቋማለን ተብሎ በተነገረ ማስትግ፣ እዚያው ጥፋት ውስጥ ተዘፍቆ መገኘት እጅግ አሳዛኝ ብቻ ሳይሆን እጅግ አናዳጅም ነው፡፡ በተለይ ስለመልካም አስተዳደር መበላሸት በሰፊው እየተወራ፣ እዚያው ብልሹነት ማጥ ውስጥ በፊት ለፊት ተውጠው የሚታዩ የበላይ ኃላፊዎች ለሀገርም ለህዝብም ጠንቅ መሆናቸው አያጠያይቅም፡፡ መነሳትም አለባቸው፡፡ ህዝብ በኃላፊነት በሰጣቸው ቦታ ላይ ነውና ምዝበራውን ያካሄዱት፣ በከፍተኛ ደረጃ ነው መጠየቅ ያለባቸው፡፡
“በልቼ ልሙት” የማለት ፈሊጥ፤ ተጠናውቶናል፡፡ የሸጥኩትን፣ የሸቀልኩትን በተለያየ ስም ያስቀመጥኩትን፣ ንብረትና ገንዘብ ብታሰርም እየበላሁ እኖራለሁ የሚለው አስተሳሰብ በሰፊው የተንሰራፋ ይመስላል፡፡ ገንዘብን በሺዎች መቁጠር ከቀረ ሰንብቷል፡፡ ምዝበራውን ለመከላከል የተወሰነ ክልል ባለስልጣናት ላይ ብቻ ማተኮር ሳይሆን ሁሉንም ክልሎች መፈተሽ ተገቢ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ዕቅድና አፈፃፀምን ማስታረቅን የግድ ይላል፡፡ ይህ መደረግ ያለበት ነው!
ባሳለፍነው ሳምንት የነፃ ፕሬስ ቀንን አክብረናል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በዓሉ ሲከበር ትኩረት ይደረግባቸው ያላቸውን የፕሬስ ነፃነት መርሆዎች መከበርንና የሚዲያ ተቋማት ምን ያህል ነፃ ናቸው የሚሉ ጥያቄዎችን፣ ማውጠንጠን እጅግ ተገቢ ነው፡፡ አብሮም የዲሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶችን ወቅታዊ ድባብ መፈተሸ ዋና ነገር ነው፡፡ ፈትሾ መቀመጥና የግምገማ ነጥቦችን መደርደር ብቻ ሳይሆን ሁነኛ የእርምት እርምጃ መውሰድ ወሳኝ ነው፡፡ አለበለዚያ ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ ነው የሚሆነው! ተገምግመው እርምጃ ያልተወሰደባቸው ሰዎች አያሌ ናቸው፡፡ አንድም “እሱን ነክተን ማ ይተርፋል” በሚል፤ አንድም “እጅግ ከፍ ያለ ቦታ” በመሆኑ ይዘለላልና ነው፡፡ የመጀመሪያው የሰንሰለት (Network) ጉዳይ ሲሆን፤ ሁለተኛው አንቱ የተባሉ ሰዎች ተጠያቂ ያለመሆናቸው ጉዳይ ነው፡፡ የህግ የበላይነት፣ ከህግ በላይ ያሉ ሰዎች እንደሌሉ የሚያረጋግጥ መርህ ነውና በተግባር መታየት አለበት፡፡ አለበለዚያ ህዝብ፤ “የሰቡት ዋጋቸው ውድ ነው፤ የጉፋያዎቹን ንገሩን” ሲል መኖሩ ነው፡፡

    መነሻውን ከምስራቃዊው የአገሪቴ ክፍል ባደረገውና በቀጣይነት መላውን የአገሪቱን አካባቢዎች ያዳርሳል በተባለው የጎርፍና ሌሎች ቅፅበታዊ የተፈጥሮ አደጋዎች ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን ተጋላጭ ናቸው ተባለ። በተከሰተው የተፈጥሮ አደጋ እስካን ከ100 በላይ ዜጎች ህይወታቸው አልፏል፡፡
የአማራ ክልል፣ ደቡብ ክልል፣ ኦሮሚያ፣ አፋርና ትግራይ ክልሎች ለአደጋው በከፍተኛ ሁኔታ ተጋላጭ መሆናቸውን ለአዲስ አድማስ የገለፁት የብሔራዊ አደጋ መከላከል ብሔራዊ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ምትኩ ካሣ፤ ለአደጋ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ላይ የሚኖሩ ዜጎችን በዘላቂነት ሰላማዊ ወደሆኑ አካባቢዎች ለማዛወር እንቅስቃሴ መጀመሩን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት የጎርፍና የመሬት ናዳ አደጋዎች በደረሱባቸው አካባቢዎች ያሉ ዜጎችን በፕላስቲክ መጠለያ ውስጥ ለማስፈር ርብርብ እየተደረገ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
አደጋው በተከሰተባቸው አካባቢዎች ለሚኖሩ ዜጎች የምግብና ጊዜያዊ የመጠለያ እርዳታዎች እየተደረጉ እንደሆነ የተናገሩት ኮሚሽነሩ፤ ዝናቡ ባለማቋረጡ ምክንያት የእርዳታ አሰጣጡ ላይ ችግር መፈጠሩንና ጎርፍ የተረጂዎችን ምግብና አልባሳት ጠራርጎ እንደወሰደው ጠቁመው ተጎጂዎቹ በሚደረግላቸው እርዳታ መጠቀም እንዳይችሉ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡
የአማራ ክልል ደሴ፣ ወልዲያ፣ ሸዋሮቢት ጣና ዙሪያ፣ በኦሮሚያ ክልል በተለይም ከአዋሽ ተፋሰስ ጋር ያሉ እንደ ዝዋይና መቂ ያሉት አካባቢዎች፣ ከደቡብ ክልል ጎሞጎፋ ዞን፣ ወላይታ ሃዲያ፣ ስልጤ፣ ሲዳማ ዞን፣ ሐዋሳ ዙሪያ፣ ከትግራይ ክልል አላማጣና አካባቢው እንዲሁም ከአፋር ክልል አሚባራ፣ ዱቢቲ፣ አዳይቱና ሚሎ ለአደጋ ተጋላጭ ናቸው ተብለው ከተጠቀሱት አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡
ሰሞኑን በደቡብ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ላይ በተከሰተው የጎርፍና የመሬት ናዳ እስካሁን 39 የሚሆኑ ሰዎች መሞታቸው የተረጋገጠ ሲሆን በናዳው የተቀበሩ ሰዎችን የማፈላለግ ሂደቱ እንደቀጠለ ታውቋል፡፡ በሥፍራው ከሚገኙ ምንጮች ባገኘነው መረጃ መሰረት፤ በወላይታ ዞን ኪንዶዳ ዲዬ ወረዳ ውስጥ በሚገኙ አራት ቀበሌዎች ሰሞኑን እየጣለ በሚገኘው ከባድ ዝናብና በዚሁ ሳቢያ በተከሰተ የመሬት ናዳ ምክንያት የሰዎች ህይወት የጠፋ ሲሆን ወላይታን ከዳውሮ ዞን የሚያገናኘው መንገድ በጎርፍ ተሰብሯል፡፡ የወላይታ ዞንን ከሲዳሞ ዞን ጋር የሚያገናኘው ትልቅ ድልድይም በብላቴ ወንዝ ተወስዷል፡፡ በአደጋው ከ135 በላይ ቤቶች በጎርፍ በመወሰዳቸው ምክንያት 1385 አባወራዎች ከቀዬአቸው ተፈናቅለዋል፡፡
ኮይሻ ዋሙራ፣ ሞጊሳ፣ ዋሙራ ቦረከሼ ፋታታና ጎጨ በተባሉት ቀበሌዎች ላይ በደረሰው በዚሁ የጎርፍና የመሬት ናዳ አደጋ፤ በናዳው የተቀበሩ ሰዎችን ህይወት ለማትረፍ የአካባቢው ህብረተሰብና የነፍስ አድን ሰራተኞች ቢጣጣሩም መንገዶቹ በጎፍርና በመሬት ናዳው በመዘጋታቸው የነብስ አድን ስራውን አስቸጋሪ እንዳደረገውና ይህም በናዳውና በጎርፍ አደጋው ህይወታቸውን የሚያጡ ሰዎችን ቁጥር ከፍ ሊያደርገው እንደሚችል ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢው ዝናቡ አሁንም ያለማቋረጥ እየዘነበ ሲሆን መሬቱ የንቅናቄና ለየት ያለ ድምፅ የሚያሰማ በመሆኑ አካባቢው በስጋት ውስጥ እንደሚገኝም ከስፍራው ያገኘናቸው ምንጮች ገልፀውልናል፡፡
የደቡብ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ደሴ ዳልኬ፤ አደጋው የደረሰባቸው ቀበሌዎች በመዘዋወር ተጎጂዎችን ያነጋገሩ ሲሆን በጊዜያዊነት መጠለያ ስለሚያገኙበት ሁኔታና በዘላቂነት ከአካባቢው ርቀው የሚሰፍሩበትን ሁኔታ ለማመቻቸት መንግስት ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግ ቃል መግባታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ በምስራቃዊው የአገሪቱ ክፍል ከፍተኛ የጎርፍ አደጋ ሥጋት እያንዣበበ ሲሆን ሰሞኑን በጣለው ከፍተኛ ዝናብ ሳቢያ በተከሰተው ጎርፍ፤ ድሬደዋን ከአዲስ አበባ የሚያገናኘው አስፋልት መንገድ መሰንጠቁን ከአካባቢው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡ ኬላ (ገነት መናፈሻ) እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ላይ በጎርፍ የተሰነጠቀው አስፋልት መንገድ ለተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ችግር እየፈጠረ ሲሆን በ1998 ዓ.ም ከተማዋ ላይ ደርሶ ከነበረው የጎርፍ አደጋ በኋላ የተሰራው የጎርፍ መከላከያም መፍረሱ ታውቋል፡፡ በምሽት ከድሬደዋ የሚመጡና ወደ ድሬደዋ የሚገቡ መኪኖች ልዩ የመብራት ታፔላ አድርገው እንዲንቀሳቀሱ መመሪያ የወጣ ሲሆን መኪኖቹም በዚሁ መንገድ በመንቀሳቀስ ላይ መሆናቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
የድሬደዋ ከተማ ከንቲባ አቶ ኢብራሂም ኡስማን፤ ስፍራው ድረስ በመሄድ ሁኔታውን የተመለከቱ ሲሆን አካባቢው በከፍተኛ ሁኔታ በጎርፍ አደጋ ስጋት ውስጥ መውደቁን ምንጮች አመልክተዋል፡፡
የመንግስት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ ከትናንት በስቲያ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ድርቅ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ላይ ደራሽ የጎርፍ አደጋ እንደሚከሰት አስቀድሞ መተንበዩን ጠቁመው፤ ዝናቡ ቀጣይነት ያለው በመሆኑ ለአደጋዎች መዘጋጀት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
እስከ አሁን ድረስ ባለው መረጃ፤ ከአንድ መቶ በላይ ሰዎች በጎርፍ አደጋ ህይወታቸውን ማጣታቸውን ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ ተናግረዋል፡፡



      የአሜሪካ የተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤአይዲ፣ በኢትዮጵያ በተከሰተው ድርቅ ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች 128 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ተጨማሪ የሰብአዊ እርዳታ ለመስጠት መወሰኑን ከትናንት በስቲያ አስታወቀ፡፡
በዩኤስኤአይዲ የዲሞክራሲ፣ የግጭትና የሰብዓዊ ጉዳዮች ቢሮ ረዳት አስተዳዳሪ ቶማስ ኤህ ስታል፣ ተጨማሪ የሰብዓዊ ድጋፍ እርዳታው ምግብ፣ ንጹህ የመጠጥ ውሃ፣ የስነምግብ አገልግሎቶችና ተንቀሳቃሽ የጤና ቡድኖችን የሚያጠቃልል መሆኑንና ለአርሶ አደሮችም የተለያዩ የእህል ዘሮች እንደሚከፋፈሉ ተናግረዋል፡፡
ተጨማሪ እርዳታው አሜሪካ ድርቁ አስከፊ ሰብዓዊ ቀውስ እንዳያስከትል ለመከላከል ስታደርገው የቆየቺውን ጥረት አጠናክራ ለመቀጠል ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል ያሉት ስታል፣ አሜሪካ ከጥቅምት ወር 2014 አንስቶ፣ ለኢትዮጵያ 705 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የሰብዓዊ ድጋፍ ማድረጓንም አስታውሰዋል፡፡

       በደቡብ አፍሪካ ምስራቃዊ ኬፕታውን በሚገኘው ሴንት ፍራንሲስ ቤይ የተባለ አካባቢ በንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ የሚኖር አንድ ኢትዮጵያዊ ባለፈው ሳምንት በዘራፊዎች መገደሉንና ይህን ተከትሎ በአካባቢው የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎች መደብሮች በአገሬው በመዘረፍ ላይ እንደሚገኙ ተዘገበ፡፡
ኢዮብ ማዴሞ የተባለው ኢትዮጵያዊ የ27 አመት ወጣት ከ9 ቀናት በፊት ክዋኖምዛሞ በተባለው አካባቢ በሚገኘው መደብሩ ውስጥ እያለ በአንድ ዘራፊ መገደሉን ያስታወሰው ዘገባው፣ ወጣቱን በመግደል የተጠረጠረው ዘራፊ የሌላን ኢትዮጵያዊ መደብር ዘርፎ ካመለጠ በኋላ፣ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያውያን ናቸው በተባሉ የአካባቢው ነዋሪዎች በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ማለፉን ገልጧል፡፡
ይህም በአካባቢው በሚገኙ ደቡብ አፍሪካውያን ላይ ቁጣ መቀስቀሱንና የተደራጁ ዘራፊዎች ሲ ቪስታ በተባለው አካባቢ የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎችን መደብሮች መዝረፍ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የአካባቢው የፖሊስ ቃል አቀባይም ስምንት ያህል የውጭ አገራት መደብሮች መዘረፋቸውን እንዳረጋገጡ ገልጧል፡፡
ፖሊስ ዝርፊያውን ለማስቆም በአካባቢው መሰማራቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በዘረፋው ላይ ተሰማርተዋል በሚል የተጠረጠሩ ሶስት ደቡብ አፍሪካውያንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ከትናንት በስቲያ በሁማንስ ድሮፕ ፍርድ ቤት መቅረባቸውን አስታውቋል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ የሉዋንግዋ ፍርድ ቤት በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ወደ ዛምቢያ ገብተዋል በሚል በተከሰሱ 41 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ሉሳካ ታይምስ የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘግቧል፡፡ በቀረበባቸው ክስ ጥፋተኛ ሆነው የተገኙት ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች፤ የገንዘብ ወይም የሶስት ወራት እስር እንደሚጠብቃቸው የገለጸው ዘገባው፣ ስደተኞች ዕድሜያቸው ከ30 አመት በታች መሆኑን አስታውቋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች ሉዋንግዋ ተብሎ በሚጠራው የድንበር አካባቢ አቋርጠው ወደ ዚምባቡዌ ሊያመሩ ሲሉ በዛምቢያ ፖሊስና የደህንነት አካላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ተነግሯል፡፡
ባለፈው ወርም በተመሳሳይ ሁኔታ ይህን ድንበር ለማቋረጥ የሞከሩ 16 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በአገሪቱ የደህንነት ሃይሎች በቁጥጥር ስር እንደዋሉም ዘገባው አስታውሷል፡፡

          በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ቡሌ ሆራ ወረዳ ገርባ ከተማ፣ ከሑዳዴ ጾም እና የፋሲካ እርድ ጋር በተያያዘ ከበዓሉ ቀን ጀምሮ ሁከት ተፈጥሮ እንደነበር የተገለጸ ሲኾን፤ በቡድን ተደራጅታችሁ ሁከት ፈጥራችኋል በሚል የታሰሩ ከኻያ ያላነሱ ሰዎችም ፍ/ቤት ቀርበው በነፃ እና በዋስ ተለቀዋል፡፡
በጾም ወቅት የከተማዋ ሉካንዳ ቤቶች እንዳይዘጉ ሲከላከሉ ነበር በተባሉ ግለሰቦች ስጋት ተፈጥሮ መቆየቱን የተናገሩ የከተማዋ ነዋሪዎች፤ በበዓሉ ዕለት በተከፈተ አንድ ሉካንዳ ቤት ደግሞ ሕገ ወጥ እርድ ተካሒዷል በሚል ሁከቱ መቀስቀሱን ጠቁመዋል፡፡
በሁከቱ በሉካንዳው ላይ ጉዳት የደረሰ ሲኾን ባለቤቱን ጨምሮ የከብቱን ቆዳ ገዝቷል የተባለ ነዋሪና ሥጋም ለመሸመት ሞክሯል የተባለ ሌላ ሰው በማዘጋጃ ቤቱ ታስረው መዋላቸው ተገልጧል፡፡
በበዓሉ ማግሥት፣ የሉካንዳው ባለቤት ይቅርታ ጠይቆ የከብቱ ሥጋ ከተወገደ በኋላ ሉካንዳው ሥራውን ቀጥሎ የዋለ ሲኾን፤ ከቀትር በኋላም የከተማው አስተዳደር ሓላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች በተገኙበት በጉዳዩ የምክክር ስብሰባ ተካሒዶ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
ስብሰባው ምሽቱን መጠናቀቁን ተከትሎ ግን፣ ማንነታቸው ያልታወቁ ግለሰቦች የወረዳውን ሊቀ ካህናት እና በከተማው የሚገኘውን የገርባ ደብረ ሰላም ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ ጉባኤ አባላት በድንጋይ እሩምታ ሲያሳድዱ፣ መኖርያ ቤቶቻቸውንም እየለዩ በመደብደብ ጉዳት አድርሰዋል፤ ተብሏል፡፡ የከተማዋ ፖሊስ ኹኔታውን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረገ በነበረበትም ወቅት፣ ግለሰቦቹ የቤተ ክርስቲያኑን ክልል በመክበባቸውና ደወልም በመሰማቱ ለሁከቱ መባባስ ምክንያት መሆኑ ተገልጿል፡፡
በቀጣዩ ቀን በወረዳው ባለሥልጣናት በተጠራውና የሁከቱን መንሥኤ በመለየት ላይ ያተኮረ ነበር በተባለው ስብሰባ፤ ፖሊስ በቡድን ተደራጅተው ሁከት ፈጥረዋል ያላቸውን ተጨማሪ ሰዎች ማሰሩን ምንጮች ተናግረዋል፡፡ ከበዓሉ ማግሥት ጀምሮ በወረዳዋ ፖሊስ ጣቢያ የታሰሩ ከኻያ የማያንሱ ግለሰቦች ማክሰኞ እና ኃሙስ በቡሌ ሆራ ፍ/ቤት የቀረቡ ሲኾን፤ ፖሊስ እና ዐቃቤ ሕግ በቂ ማስረጃ አላገኘሁባቸውም በማለታቸው በነፃ እና በዋስ መለቀቃቸው ታውቋል፡፡
ሁከቱ የዓመት በዓሉን የሉካንዳ ንግድ መነሻ ያደረገ ይኾናል ብለው እንደሚገምቱ የተናገሩ አንድ የሃይማኖት አባት፤ “ጉዳዩ የሃይማኖት ግጭትም አይደለም፤ የብሔረሰብ ግጭትም አይደለም፤ ችግሩ የተወሰኑ ሰዎች ስሜትና አጀንዳ ነው፤” ብለዋል፡፡
“ሕዝቡ አብሮ የኖረ ነው፤ ነገም አብሮ የሚኖር ነው፤” ያሉት እኚሁ አባት፤ በግለሰብ ደረጃ ያሉ ጠብ አጫሪዎችና በሕዝቡ ወይም በሃይማኖት ተቋማት ሽፋን በመጠቀም የብጥብጥ ሙከራ የሚያደርጉ በየመሥሪያ ቤቱም ኾነ በየሃይማኖት ተቋማት ሊኖሩ እንደሚችሉ ጠቁመው፤ የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ ከመጠየቅ ጀምሮ የከተማችንን ችግር እኛው በራሳችን ተነጋግረን መፍታት አለብን፤ የሚሉ የተለያዩ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ግን፣ የማረጋጋት ዓላማ ያላቸውን ስብሰባዎች እንደቀጠሉ መኾናቸውን ተናግረዋል፤ መንሥኤውንና ተጠያቂውን አካል በትክክል ለይቶ መፍትሔ ለመስጠት የሚደረገው ጥረት ባለመቋጨቱም እንዲህ ነው የሚል መረጃ ለመስጠት እንደሚያስቸግር አስታውቀዋል፡፡
የከተማዋን ፖሊስ እና የአስተዳደር ሓላፊዎች በስልክ ለማነጋገር ተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም ጥሪው ስለማይመልስ አስተያየታቸውን ለማካተት አልቻልንም፡፡






ሼክ መሀመድ አሊ አላሙዲ ለመቄዶኒያ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ 16 ሚ. ብር ለገሱ፡፡ እርዳታውን ለማዕከሉ ያስረከቡት የሞሀ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ስራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ሲሆኑ የተረከቡት ደግሞ የማዕከሉ መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቢኒያም በለጠ እንደሆኑ ታውቋል፡፡
ከርክክብ ስነስርዓቱ በኋላ የመቄዶኒያ መስራች አቶ ቢኒያም በለጠ ባደረጉት ንግግር፤ ሼክ አሊ አላሙዲ ከዚህ ቀደም እንደነ ደርባ ሲሚንቶ፣ ኒያላ ሞተርስ፣ የላይኛው አዋሽ አግሮ ኢንዱስትሪ፣ አዲስ ፓርክ፣ አዲስ ጐማ፣ ኤልፎራ፣ ኩዊንስ ሱፐር ማርኬትና ሚድሮክ አንሊሚትድ ፓኪንግ ፋክተሪ በመሳሰሉ ድርጅቶቻቸው በኩል ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ መለገሳቸውን አስታውሰው፤ በሼኩ የተለገሱት አምቡላንሶችም ከ800 በላይ ተጨማሪ እርዳታ የሚፈልጉ ደካሞችን ከየጐዳናው ለማንሳት እንዳገዟቸው ተናግረዋል፡፡
አቶ ቢኒያም አክለውም መቄዶኒያ በአሁኑ ወቅት በማዕከሉ ከአንድ ሺህ በላይ አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማንን እየረዳ መሆኑን ጠቅሰው ለዕለት ፍጆታ ብቻ በየወሩ ከ1ሚ. ብር እንደሚያወጣ ገልፀዋል። ከ300 ሚ.ብር በላይ ለሚያስፈልገው ማዕከል ግንባታ ማህበረሰቡ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አድንቀው ድጋፉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የተማፀኑት መስራቹ፤ ሼክ አላሙዲ የለገሱት 16 ሚ. ብርም ለማዕከሉ ግንባታ እንደሚውል ተናግረዋል፡፡
የሞሃ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ባደረጉት ንግግርም፤ መቄዶኒያ እያከናወነ የሚገኘውን በጐ ተግባር አላሙዲን እንደሚያደንቁ ገልፀው ወደፊትም እርዳታቸው ከማዕከሉ እንደማይለይ ጠቁመዋል፡፡

Saturday, 07 May 2016 13:37

ይበለኝ በገዛ እጄ!

    ያዕቆብ ይባላል፡፡ ሙሉ ቀን መለሰ “ሰንደቅ ያሰቅላል”ን ለሴት ቢያዜመውም ያዕቆብን በሚገባ ይገልፀዋል፡፡ የአርባዎቹን አጋማሽ እየተሻገረ ቢሆንም ግርማ ሞገሱ፣ቅልጥፍናውና ሽንቅጥቅጥ ማለቱ ገና በሰላሳዎቹ ማለዳ ላይ ያለ ያስመስለዋል፡፡ ተምሯል፤የገንዘብም የዲግሪዎችም ሀብታም ነው፡፡ በአንድ አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ በሚንቀሳቀስ ትልቅ ተቋም ውስጥ በኃላፊነት ደረጃ ይሰራል፡፡ ዘወትር ሙሉ ልብስ ግዴታው ነው፡፡ እንደሱ የሚያምርበትም አላየሁም፡፡ ታዲያ በዕረፍት ቀኖቹ ቀለል ያለ ልብስ ሲለብስ ሌላ ሰው ይመስላል፡፡ ልውጥ ይላል፡፡ባሌ ነው፤ የምወደው ባሌ፡፡ ምን ዋጋ አለው? ጥሎኝ ሄዷል፡፡ ሁለት ሳምንቱ … በገዛ እጄ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ጥሎኝ መሄዱን እንጂ ጠልቶኝ መሄዱን አላምንም፡፡ ጠልቶኝ ካልሆነ ደሞ ክዶኝ ሊሆን አይችልም፡፡ የጋብቻችንን ዘጠነኛ ዓመት ለማክበር የቀረንም ሁለት ሳምንት ብቻ ነበር … ዝግጅታችንን በጋራ አቅደን ጨርሰንም ነበር፡፡
“ካልሆነልን ለምን እንጨነቃለን አቡቲዬ” ውይ ቁልምጫው ሲጥመኝ….አበባ ብሎ ጠርቶኝ  አያውቅም፡፡
“ምንም አይሰማህም?”
“አልዋሽሽም … በቃ ማመን ካለብን ማመን ወይም ተማክረን አማራጭ …”
ቀለል ሲያደርገው ማን አክብጂው አለኝ … በገዛ እጄ!
ከዘጠኝ ዓመት በፊት ወደ ምሰራበት ግብረሰናይ ድርጅት ቢሮ መጣ፡፡ የኛን ድርጅት የሚረዱ … የውጭ ተቋማት ከነሱም ጋር ይሰራሉ፤ ተመሳሳይ ዓላማዎች ሲገጥሙን አብረን እንሰራለን፡፡ እኔ ደሞ የድርጅታችን ዋና ኃላፊ ነኝ፡፡ ወደ ቢሮዬ ሲገባ ዓይኖቼ ከቁጥጥሬ ወጥተው አጠር ያለች ቁመቴ ረዝማብኝ እየሳብኳት ብድግ ብዬ ተቀበልኩት፡፡ ዘንጣፋ ሰውነቱን እጥፍ አርጎ በአክብሮት ጨብጦኝ ተቀመጠ፡፡ ቢሮዬን እንደሱ የሞላው ሰው አልገጠመኝም፡፡ በግርማው ተጥለቀለቀች፡፡ ለስንትና ስንት ጥላ ቢሶች የሚተርፍ ግርማ፣ የቀልቤን መዝረክረክ ይወቅብኝ አይወቅብኝ እንጃ፡፡ እንደ ምንም የመጣበትን ጉዳይ ተነጋግረን ሄደ፡፡ ለሱ ነው የሄደው፤ ለኔ ቢሮዬ ነበር የዋለው፡፡
ጉዳዮች አመላለሱት፤ቀጥሎም እኔ ጉዳዩ ሆንኩና … ልቤ ላይ በድብቅ ስትንፈራፈር የነበረችውን የፍቅር ፅንስ ነፍስ ዘራባት፡፡
እኔን ድንገት ላየኝ ሰው፣ ክልስ ልመስለው እችላለሁ፡፡ “ቀይ ሰው መልክ አይፈጅም” ቢባልም ሳይጋነን ፈጅቻለሁ፡፡ ከ27 ወደ 28ኛ ዓመቴ በመሸጋገር ላይ ነበርኩ፡፡ አስጨናቂ የዕድሜ ዳገት ነው ለኛ ለሴቶች፡፡ ብዙ ወንዶች እንዳዩኝ ቢሸነፉም እኔ በቀላሉ አልሸነፍም፡፡ እየፈለግሁ እንኳን አይሆንልኝም፡፡ ዕውቀት፤ ስራ፤ ጥሩ ደሞዝ፤ ጥሩ ኑሮ አለኝ፡፡ ለእህቶቼ ተርፌያለሁ፡፡ በየመንገዳቸው ሄደው ርቀዋል … የእናቴን ድህነት ታሪክ አድርጌ ቀብሬዋለሁ፡፡
 ጎድሎኝ የነበረውን ያቆብ ሞላው … ስንላመድ እንደ ልጅ ያደርገን ጀመር፡፡ ያልኖርነውን እንደ መኖር … በኋላም ምርጫ አጣን፤ ከመጋባት በቀር፡፡ … በቃ አደረግነው፡፡ ተጋባን፡፡  በቅርብ ጓደኞቻችንና ወላጆቻችን ብቻ ታጅበን … በእማዬ “እልልታ” ደምቀን፣ “በወልዳችሁ ሳሙ” ምርቃት እየሰፈፍን ወደ ያቆቤ የሪል ስቴት ቪላ ገባን፡፡ ኑሮ ደመቀ … ጣፈጠ … ግን አልሞላም … ሁሉም ላይሞላ ቢችልም ደርበብ የሚያደርገው የእማዬ ምርቃት ሰሚ አጣ፡፡ በየወሩ ጠባዬን … ሆድ ሆዴን ትከታተላለች፡፡ ያቆቤም ይጠብቃል፡፡ ሁለት ጊዜ እያሳየ ነሳኝ፡፡ ደስታችንን ሳናጣጥም ጨንግፎ አጨነገፈን … ከዚያ በቃ ዝም ሆነ፡፡ እናቴም “ፈጣሪ ያልፈቀደውን እሷን ምን አርጊ እላታለሁ?” ብላ ነው መሰል ዝም …. እምምምም ብላ ቀረች፡፡ ያቆብም አመነ፡፡ ከዕውነቱ ጋር ታረቀ፡፡ እኔ ግን ጭንቀት የውስጥ ልብሴ ሆነ፤ከላይ ድምቅ ፅድት ውስጤ ግን …
ሰሞኑን ሃዘን ላይ ነኝ፤ ከፍራሽ ላይ ሳልወርድ እንባዬን ደብቄ አወርደዋለሁ፡፡ የሰርጋችንን ቪዲዮ ማየት የዘወትር ስራዬ ሆኗል፡፡ ያቺን ብርቅ ቀን፣ ያንን ድንቅ የፍቅር ሰው እያሰብኩ እንባዬ ሊያልቅ ነው፤ ሚዚዬ ሔዋንም የለችም፤ አብሮ አደጌ፣ ከራሴ እኩል ከማያቸው ሰዎች አንዷ ናት፡፡ ያሉኝም እነዚሁ ናቸው፡፡  እናቴ --- ያቆብ --- ሔዋን!!
… እናቴ የያቆቤን መጥፋት ማወቅ የለባትም፤ሌላ ህመም ይሆንባታል፡፡ በገዛ እጄ ራሴን ክፉኛ ቀጣሁት፡፡
“አቡቲ”
“ወዬ..”
“ራስሽን እያስጨነቅሽ ነው”
“ደህና ነኝ”
“እያየሁሽ …. ለምን በጉዲፈቻ አናሳድግም” ለስሜቴ እየተጠነቀቀ
“ከስራሽም ጋር ስለሚያያዝ….”
“እስኪ … አንድ የማሰላስለው ነገር አለ … እሱን …”
“ምንድነው አቡቲዬ?”
“ሰሞኑን እነግርሃለሁ”
ቢሮ ገባሁ አልገባሁ ለውጥ አልነበረውም፡፡ የስራ መንፈሴ ሸሽቶኛል፤ የአዕምሮዬም አቅም ተዳክሟል፡፡ ስልኩ ላይ መደወል መደወል … ዝግ ነው፤ ቢዚ ነው፤ ሊገኝ አይችልም …ይለኛል፡፡ አንዴ በመሃል ላይ ድምጹን ሰማሁት፡-
“ሃሎ አቡቲ” ጥሎኝ ሄዶም አቡቲ ማለቱ ገረመኝ፡፡
“ያቆቤ” ሳግ እየተናነቀኝ አወራሁት …
“ኬንያ ነኝ … ስመለስ እደውላለሁ” አጣድፎኝ ሥልኩን ዘጋው፡፡ ስራው ከሀገር ሀገር እንደሚወስደው አውቃለሁ፡፡ ሳይነግረኝ ግን የትም ሄዶ አያውቅም፡፡ ወደ ቢሮው ስሄድ መውጣቱን ይነግሩኛል፡፡ ዝም ብዬ ግራ ስጋባ ሰነበትኩ፡፡
ከጉዲፈቻው አማራጭ በፊት ያሰብኩትን ይዤ ሔዋን ጋ ሄጄ ነበር፡፡ እኩያዬ … ከወዲያኛው ጫፌ እስካለሁበት የምታውቀኝ፡፡ ቆንጆ ነች፤ደስ የምትል ቆንጆ፡፡ ትምህርት ዕጣ ክፍሌ አይደለም ብላ ሁለተኛ ደረጃን ጀምራ ትታዋለች፡፡ በማያዛልቁ ስራዎች ወጣ ገባ ስትል ወንዶች አዩዋት፡፡ ሁሉንም ነገር ቀድማን ነው ያደረገችው፡፡ ቸኩላ አገባች፤ ሁለት ወለደች፤ ሳይቆይ ባሏ በሞት ተለያት፡፡ ብዙም አላዘነችም፤ ኑሮዋንም አለስልሶላት ነበር ያለፈው፡፡ ወጣ ገባዋን ቀጠለች፡፡ የባሏ ዘመዶች በቅርብ ርቀት አዩዋት፤ ገመገሟት፡፡ በመጨረሻ “አንቺ ጥሩ ወላጅ እንጂ ጥሩ እናት አይደለሽም” ብለው ልጆቿን ወሰዱባት፡፡ ጭራሽ ተመቻት አማረባት፤ ተስማማት፤ ያለውን ወንድ የመረቧ ሲሳይ ማድረግ ሆነ ስራዋ፡፡
“ሔዊ ምን ይሻለኛል?” ስላት … እየሳቀች፤ “ወልጄ ልስጥሽ እንዴ?” አለችኝ፡፡ ደንታ የሌላት ናት፡፡ በላች ጠጣች፤ ይዛ ወደቀች .. በቃ ኖረች…
“እኔም ያሰብኩት …”
“አትቀልጅ …”
“ተመሳሳይ ነው ---” ልጅነታችንን … መወለድ ቋንቋ እንደሆነ ያየንባቸውን ዓመታት … ፍቅራችንን እያሰብኩ አማከርኳት …
የዛኑ ቀን … ማታ … መኝታ ክፍላችን ውስጥ … ክንዱን አንተርሶኝ ከሔዋን ጋር የተመካከርነውን ስነግረው … እመር ብሎ ተነሳና አየኝ፡፡ መቆጣት አይችልበትም፡፡ ሄዋንን  እንዳገኛት አይፈልግም ነበር፡፡ “አብሮ ማደግ አብሮ ማርጀት መሆን አለበት” ይለኛል … ሌላ ጊዜ ደሞ “ያኔ እኩል ነበራችሁ … አሁን ግን አይደላችሁም” እያለ ግንኙነታችንን ይቃወም ነበር፡፡
 እኔ ግን ሔዋንን እንደሱ ላያት አልቻልኩም፡፡ ላስረዳው ሞከርኩ፡፡ በማግባባት--- በመለመን --- ረታሁት፡፡
“የግድ ካልሽ … ይሁና” አለና ዞሮ ተኛ፡፡ በግድ ሳዞረው የቀይ ዳማ ፊቱ ላይ ጭንቀት፤ ፍርሃት፣ ግርምት … በየተራ እየበሩ ሲጠፉ አየሁ
ዛሬ አስራ ሰባተኛ ቀኑ ከጠፋ፡፡ አቅሜ ተዳክሟል፡፡ ስልኩ አይመልስም፤ ቢሮዬን ትቼ ወጣሁ፡፡ ባልደረቦቼ የሚያደርጉልኝ ጠፍቷቸው እንጂ ጭንቀቴ አስጨንቋቸዋል፡፡ መኪናዬ ራሷ ትምራኝ ደመነፍሴ እንጃ … ብቻ እየበረረች ነው፡፡ ያለ ቀልቤ መኪናዬን ዳር አውጥቼ ሳቆማት፣ ከፊቴ የማውቃትን መኪና ያየሁ መሰለኝ፡፡ ወረድኩ፡፡ አዎ የማውቃት መኪና ናት … ሰውነቴ ባንዳፍታ አልታዘዝ አለኝ፡፡
እግሬ እየመራኝ ጥቂት ተራመድኩ፡፡ የልጅነት ጓደኛዬ፣ሚዜዬ ቤት በራፍ ላይ ደረስኩ፡፡
ሳላንኳኳ በሩን ገፍቼው ገባሁ፡፡ ከደፉ ግን ማለፍ አልቻልኩም፡፡ ዓይኔን ማመን አቃተኝ፡፡ እውትና ቅዠት ተምታታብኝ፡፡ ቅዠት ቢሆንልኝ ተመኘሁ፡፡ ምኞቴ ግን አልሰመረም፡፡
የማፈቅረው ባሌ ያቆቤ----ከራሴ እኩል የማያት የልጅነት ጓደኛዬ ሔዋን---- አንድ ላይ የተሰፉ መስለዋል፡፡ ጠፍተዋል፡፡ አንጎሌ ለአፍታ ማሰብ ያቆመ መሰለኝ፡፡ ሁሉነገሬ ዝም አለ፤ጭጭ፡፡ “ሔዊ ለአንድ ቀን ከያቆቤ ጋር …” ብላት … የልጅነቴን ፀጋ … በረከቴን ሁሉ ነጠቀችኝ፡፡ በአንዲት ቀን ጦስ ባሌን በሞገደኛዋ ሔዋን ጭን ስር አስቀረሁት፡፡ ጓደኛዬንም ባለቤቴንም አጣኋቸው፡፡ ፊቴን አዙሬ ወደ መኪናዬ መራመድ ጀመርኩ፡፡ ያየሁት አስክሮኛል፤ አፌም አይኔም ደርቀዋል፡፡ እነሱ ግን ምን አጠፉ? የራሴ ጠላት ራሴ ነኝ፤ ሁሉም የሆነው በገዛ እጄ ነው፡፡ መኪናዬ ውስጥ ከገባሁ በኋላ እንዲህ የሚል ሃሳብ በግድ መጣብኝ፡- “ያንን ሁሉ ዓመት በኔ ደስተኛ አልነበረም ወይስ ከሁሉም ሾራ የምታሾረው ሔዋን ሌላ ተዓምር አሳየችው ?!”
ይበለኝ፤በገዛ እጄ ነው! የራሴ ጠላት ራሴ ነኝ !!







ዓለማቀፍ የፕሬስ ቀን ባለፈው ማክሰኞ ሚያዝያ 25 በሀገራችን የተከበረ ሲሆን በመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት አዘጋጅነት በፍሬንድሺፕ ሆቴል የግማሽ ቀን
የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በፓናል ውይይቱ ወቅት የሀገሪቱን የመገናኛ ብዙኃን ሁኔታ የሚዳስሱ ሶስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው በሠፊው ውይይት ተደርጐባቸዋል፡፡
“የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር - ኢትዮጵያ” የሚል መሪ ቃል የተሰየመለትን የዘንድሮ የፕሬስ ቀን መነሻ በማድረግ፣ በተለይ በአገራችን ያለውን ተጨባጭ እውነታ
በተመለከተ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የጋዜጠኝነት መምህራንን፣ የጋዜጠኛ ማህበራት አመራሮችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችንና ምሁራንን አነጋግሯል፡፡
ሃገሪቱ በመሪ ቃሉ ላይ እንደተጠቀሰው በእርግጥም የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር ናት? አስተያየት ሰጪዎቹ በጉዳዩ ላይ ሃሳባቸውንና ዕይታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

“ብዝሃነት መሬት ላይ ያለን ሃቅ
ለመደፍጠጥ የዋለ ቃል ነው”
በ1920 እና 30ዎቹ ጆርጅ ኦዌል “1984” የተሰኘ መፅሃፍ ነበረው፡፡ በዚህ መፅሃፍ ውስጥ “ፖለቲካና ቋንቋ” በሚል ርዕስ ባሰፈረው ፅሁፍ፤ “መሬት ላይ ያለን የፖለቲካ ችግር በቋንቋ ለመሻገር መሞከር” ይለዋል፡፡ ቋንቋን በመጠቀም የተወሰነ ርዕዮተ ዓለማዊ ግብን መምታት ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ያለውን የሚዲያ ሁኔታ ገምግም ከተባልኩ በሁለት መንገድ ነው የማየው፡፡ አንደኛው ክፍል ራስን ሳንሱር በማድረግ (ሰልፍ ሴንሰርሺፕ) ውስጥ ያለ ነው፡፡ ሰልፍ ሴንሰርሺፑ አንዳንዴ ከመንግስት ጫና በላይም ሊሻገር ይችላል፡፡ አሁን እያየነው ያለው ያንን ነው፡፡ ደርግና ኢህአዴግ የሚለያዩት እዚህ ላይ ነው፡፡ ደርግ በግልፅ አታድርግ ይልሃል፡፡ ኢህአዴግ የሴንሰርሺፕ ተቋም አላቋቋመም፤ ነገር ግን “ይሄን ካደረግህ ዋ ኮንትራት አንሰጥህም” ይላሉ፡፡ “ብዝሃነት” የሚለው ቃል እንግዲህ ቋንቋ ሰርቆ መሬት ላይ ያለን ሃቅ ለመደፍጠጥ የዋለ ቃል ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ምንም አይገልፀውም፡፡ ይሄን ካልን ብዙም “ብዝሃነት አለ፣ የለም” የሚል ክርክር ውስጥ መግባት አይጠበቅብንም፡፡

              ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ
(የፍልስፍና ምሁር)

=========================================

“ሚዲያው የሃሣብ ብዝሃነትን
የሚፈራ ነው”

ኤልያስ ገብሩ
(የ“አዲስ ገፅ” መጽሔት ዋና አዘጋጅ)

የፕሬስ ብዝሃነት ማለት የተለያዩ አስተሳሰቦች የሚስተናገዱበት ማለት ነው፡፡ ኢህአዴግን ደግፎም ሆነ ነቅፎ መፃፍ መቻል ማለት ነው፡፡ ብዝሃነት ቃሉን እንዲሁ ለፕሮፓጋንዳ ተጠቀሙት እንጂ አሁን መሬት ላይ ካለው ሃቅ ጋር ፈጽሞ የማይሄድ ነው፡፡ እስከ ዛሬ እንደውም ሚዲያው የሃሣብ ብዝሃነትን የሚፈራ ሆኖ ነው የሚታየው፡፡ ኢቢሲን ብንመለከተው ለአንድ ወገን ወግኖ የሚሠራ ነው፡፡ የተለያዩ ሃሳቦችን የሚያስተናግድ አይደለም፡፡ በምርጫ ክርክር እንኳ ተቃዋሚዎች በጣት የምትቆጠር ደቂቃ ነበር የተሰጣቸው፡፡ ይሄ ኢህአዴግን በሃሳብ የበላይነት አሸንፈን ስልጣን እንይዛለን ለሚሉ ተቃዋሚዎች ምን ይጠቅማቸዋል? ራሳቸውን እንኳ ለማስተዋወቅ የማይበቃ ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ነው የሚዲያ ብዝሃነት ተፈጥሯል ልንል የምንችለው? መንግስት ብዝሃነትን አስቦ ቢንቀሳቀስ ኖሮ፣ እነ እስክንድር ነጋ፣ እነ ውብሸት ታዬ፣ እነ ተመስገን ደሣለኝና የመሳሰሉ ጋዜጠኞች አይታሠሩም ነበር፡፡ በሃሳብ ብዝሃነት የሚያምን መንግስት ቢኖር ኖሮ፣ ፖለቲከኞች በየጊዜው እየታሠሩ ባልተፈቱ ነበር፡፡
አለማቀፍ ተቋማት የሀገሪቱን የፕሬስ ሁኔታ አስመልክቶ የሚያወጡት ሪፖርት መሬት ላይ ያለውን ሃቅ የሚገልጽ ነው፡፡ እኛም ሪፖርት እንስራ ብንል ከዚህ የተለየ አይሆንም፡፡ በሚዲያ ጉዳይ ጥናት የሚያደርግ የሀገር ውስጥ ተቋም ቢኖር፣ ከእነሱ የከፋ ሪፖርት ሊያወጣ እንደሚችል አልጠራጠርም፡፡ ዛሬ ጋዜጠኝነት የአደጋ ቀጠና ሆኗል፡፡ በሙያው ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎች እንኳ ወደ ሙያው መቀላቀል አደገኛ መሆኑን እያዩ እየሸሹ ነው፡፡

================================

“ሚዲያዎች በሞኖፖሊ ስር ነው ያሉት”
አቶ ወንድወሰን ተሾመ
(የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚዳንት)

  በየአመቱ የሚከበረውን የፕሬስ ቀን በፊት ያከብር የነበረው የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር (ኢነጋማ) ነበር፡፡ እለቱ ታሣቢ የሚያደርገው የታሠሩትን የተሰደዱትን፣ በሙያቸው ጫና እያረፈባቸው ያሉትን ነው፤ መከበር ያለበትም ከዚህ አንፃር ነው፡፡ አሁን ሞኖፖሊ የሠፈነበት ጊዜ ላይ ነው ያለው፡፡ የግል ፕሬስ አለ ማለት የማይቻልበት ደረጃ ላይ እየተደረሰ ነው፡፡ ሞኖፖሊ ሲበዛ የሚዲያ ብዝሃነት የምንለው ነገር ይጠፋል፡፡ የግል ፕሬሶች በወረቀት ዋጋ መናርና በሌሎች ምክንያቶች እየተዳከሙ ነው፡፡ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች በግል የተያዙ ያሉ ቢሆንም ብዝሃነት ያለው ሃሣብ የማንሸራሸር አቅም ሲፈጥሩ አልታዩም፡፡ በሞኖፖሊ ስር ነው ያሉት፡፡ በሙያቸው ጋዜጠኛ ሆነው የምናቃቸው ሰዎች፤ መንግስት በሌላ ጉዳይ ወንጀለኛ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ በማለቱ አሁን በእስር ቤት የሚገኙ አሉ፡፡ መንግስት በዚህ ቀን እነዚህን ሙያተኞች ቢለቃቸው ምን ይጐዳል? እንደውም ክብር ያገኝበታል፡፡ የተከሰሱት በሌላ ቢሆንም እኛ የምናውቃቸው በጋዜጠኝነታቸው ነው፤ ቢለቀቁ በሙያው ላይ የራሳቸውን ድርሻ ያበረክታሉ፡፡ የመንግስትን ገጽታ በአለማቀፍ ደረጃ የሚያበላሸውና የተለያዩ ሪፖርቶች ላይ የሚንፀባረቀውም ይኼው ነው፡፡

==================================

“ሁሉም አመለካከቶችና ሃሳቦች የሚንፀባረቁበት እድል አልተፈጠረም”

አቶ አንተነህ አብርሃም
(የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚደንት)
   የፕሬስ ቀን አከባበሩ ላይ እንድንገኝ ተጠርተን ነበር፤አልተገኘንም፡፡ ያልተገኘነው ክብር ስለነፈጉንና ስላዋረዱን ነው፡፡ አንደኛ፤ ተገቢውን እውቅና ነስተውናል፡፡ በበአሉ ላይ መጥታችሁ ቁጭ ትላላችሁ፤ከዚያ ሲያልቅ ትሄዳላችሁ ነው ያሉት፡፡ ስለዚህ ነው የተውነው፡፡ እኛ ተሳታፊዎች ብቻ መሆን አይገባንም፤ ባለድርሻዎች ነን፤ ንግግር ለማድረግ አስበን ነበር፡፡ እነሱ ግን እንደ ማንኛውም ሰው ትመጣላችሁ፤ የሚባለውን ሰምታችሁ ትሄዳላችሁ ነው ያሉን፡፡ እኛ ደግሞ ይሄ አምባገነንነት ነው፤አምባገነንነትን መሸከም አንችልም ብለናቸዋል፡፡ እኛ እስከ ዛሬ ከመንግስት ጋር በጋራ ስንሰራ ነበር፡፡ አሁን እኛን ከስርአቱ ጋር የማጋጨት ሥራ ነው የተሰራው፡፡ መንግስት በፊት ያደርግልን የነበረውን ድጋፍም አሁን እየነፈገን ነው፡፡ ድጋፍ ማድረግ አቁሟል፡፡ ለምን አቆመ? መንግስት ራሱ ነው የሚያውቀው፡፡ የፕሬስ ነፃነት ቀን አከባበር ላይም አያገባችሁም ተብለን ተገፍተናል፡፡  
ይሄ መገፋት ግን እኛን ለሀገራችን ከምናደርገው አስተዋፅኦ አያግደንም፡፡
አንዳንድ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የመንግስትን አቋም አይደለም እያንፀባረቁ ያሉት፤ የራሳቸውን ነው፡፡ ወደ ርዕሰ ጉዳዩ ስመለስ፤ “የሚዲያ ብዝሃነት” ማለት የተለያዩ ሃሳቦችና አመለካከቶች የሚንሸራሸሩበት ምቹ ሁኔታ መፍጠር ማለት ነው፡፡
በዚህም ሁሉም እኩል የመናገር፣ የመደመጥና ሃሳቡን የማንፀባረቅ መብት ያገኛል ማለት ነው፡፡
 ከዚህ አንፃር ካየነው አሁን ላይ ሁሉም የዚህ እድል ተጠቃሚ ሆኗል ብዬ አላምንም፡፡ ሁሉም አመለካከቶችና ሃሳቦች የሚንፀባረቁበት እድል አልተፈጠረም፡፡ ይሄን ስል ክልከላ አለ ማለቴ አይደለም፤ ክልከላው ባይኖርም የበለጠ ሙሉ የሆነ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ይቻል ነበር፡፡ አሁን ጭራሽ ያለውና የነበረው ነገር እየኮሰመነ ነው፡፡
በተወሰኑ የመንግስት ኃላፊዎች የሚፈለገው፣የጋዜጠኞች ማህበራት እንዲዘጉ ነው፡፡ ይሄ የመንግስት አቋም አይደለም፤የግለሰቦች ነው፡፡ ውይይት የሚፈልግ ጉዳይ ነው፡፡
 ውይይት እናድርግ ስንል ደግሞ ፍቃደኛ አይደሉም፡፡
እነዚህ ሁኔታዎች የአምባገነንነት አዝማሚያ ፍንጮች ናቸው፡፡ እነዚህን ሁኔታዎች ደግሞ እኛ ልንሸከማቸው አንችልም፡፡

================================

“ብዝሃነት ያለው ሚዲያ ቢኖርማ እኛም ባልተከራከርን”
ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ
(የመድረክ ሊቀመንበር)

  እኛም ከተያያዝናቸው የትግል አጀንዳዎች አንዱና ዋነኛው ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ ጉዳይ ነው፡፡ ባለፉት የፖለቲካ ትግላችንም ለዚህ ስንከራከር ቆይተናል፡፡ ብዝሃነት ያለው ሚዲያ ቢኖርማ እኛም ባልተከራከርን፤ በዚህ ላይ ጊዜያችንን ባላጠፋን ነበር፡፡ ህገመንግስቱ የሚዲያ ነፃነት እንደሚከበር ደንግጓል፡፡ ነገር ግን ስርአቱ በጉልበት ህገ-መንግስታዊ መብቱን ገድቦታል፡፡ የፕሬስ ነፃነት ጉዳይ ዝም ብሎ የሚታይ አይደለም፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ መቀየር አለበት፡፡ መሬት ላይ ያለው ሃቅና በመንግስት የሚነገረው የተለያየ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ አለማቀፍ ሪፖርቶችም በየጊዜው የሃገሪቱ የፕሬስ ሁኔታ አደጋ ውስጥ እንዳለ እንጂ በመልካም ሁኔታ ላይ መሆኑን አያንፀባርቁም፡፡ ጋዜጠኞች ጠንከር ብለው መንግስትን ሲተቹ፣ ሽብርተኛ ተብለው እንደሚታሠሩ እናውቃለን፡፡
ይሄን ሽሽት ጋዜጠኞች ያልተሰደዱበት የአለም ሃገርም የለም፡፡ ይሄ እንዲህ ባለበት ሁኔታ “የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር” ማለት የህዝብ ንቀት ነው፡፡

==============================

“በሌላው ሀገር መንግስት በፕሮፓጋንዳ አይፎክርም”

በፍቃዱ ኃይሉ (የዞን 9 ብሎገርና
የ“ውይይት” መፅሄት ዋና አዘጋጅ)

   በአገሪቱ የሚዲያ ምህዳር ውስጥ እየኖርኩበት ነው፤ዋጋም የከፈልኩበት ነው፡፡ ስለዚህ እኔ ከአለማቀፍ ሪፖርት ሳይሆን በዚህ መንገድ የሀገሪቱን የሚዲያ ምህዳር አውቀዋለሁ፡፡ “የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር - ኢትዮጵያ” የሚለውን መፈክር ስሰማ እንደ ስላቅ ነው የወሰድኩት፡፡ ፀሐፊዎቹ ራሳቸው አምነውበት የፃፉት አይመስለኝም፡፡ መፈክር ራሱ የፕሮፓጋንዳ ስራ ነው፡፡ በሌላው ሀገር መንግስት እንደዚህ በፕሮፓጋንዳ አይፎክርም፡፡ እኔ ከምኖርበት አንፃር ይሄን መፈክር ከስላቅ ለይቼ አላየውም፡፡ በምርጫ ማግስትና በምርጫ ዋዜማ ላይ የሚዲያዎች ቁጥር እኩል አይደለም፡፡ በምርጫ ዋዜማ ላይ ጠንካራ ፕሬሶች ይዘጋሉ፣ ይከሰሳሉ፣ ጋዜጠኞች ይሰደዳሉ፡፡ ይሄን በ2007 ምርጫ አይተነዋል፡፡ የፕሬሱ አስተዋፅኦ አስፈላጊ በሚሆንበት ሰአት ላይ በፍጥነት እንዲወገዱ ይደረጋል፡፡ ተፅዕኖ መፍጠር በማይችሉበት ወቅት ደግሞ ዝም ይባላሉ፡፡ በሀገሪቱ ያለው የሚዲያ ሃቅ ይሄ ነው፡፡ ይህም ሆኖ ዛሬ ከ10 ሺህ በላይ ኮፒ ያለው ጋዜጣ የለም፡፡ በየቀኑ የሚወጣ ጋዜጣ የለም፡፡ ሬዲዮ ጣቢያዎችም የግል ቢኖሩም ራስን በራስ በመመርመር የሀሳብ ተአቅቦ ያደርጋሉ፡፡ ፖለቲካ ሽሽት መዝናኛና ስፖርት ላይ ያተኩራሉ፡፡ ከዚህ አንፃር የሚዲያ ብዝሃነት ፅንሰ ሀሳብን ራሱ መንግስት በቅጡ የተረዳው አይመስለኝም፡፡


===============================

“የሚዲያ ብዝሃነት አለመኖር ለመንግስት ውድቀት ነው”

እንግዳወርቅ ታደሰ
(በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ፣ የጋዜጠኝነት መምህር)

ባለፉት 25 ዓመታት ፕሬሶች ቁጥራቸው አንዴ ይጨምራል፣ ሌላ ጊዜ ይቀንሳል፡፡ የመንግስት ሚዲያዎችን ካየን በቁጥር እየጨመሩ ነው፡፡ የብሮድካስት ዘርፍ በቁጥር ደረጃ ከፕሬሱ የተሻለ እየተስፋፋ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ለኛ ሀገር የሚያስፈልገን የሃሳብ ብዝሃነትን ሊያመጣ የሚችል ሚዲያ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የግል ፕሬስ በቁጥር ሊያድግ ይገባዋል፡፡ በብሮድካስቱ ከሚገኙ የግል ጣቢያዎች ውስጥ እንኳ መረጃ ከማግኘት አንፃር ግልፅ ልዩነት ይታይባቸዋል፡፡ ፋና ከመንግስት የሚያገኘውን መረጃ ያህል ሌሎቹ አያገኙም፡፡ ያሉትን ውስን የግል ጋዜጦችም ብንመለከት መረጃ አያገኙም፤ራሳቸውን በራሳቸው ሳንሱር የማድረግ ችግርም አለባቸው፡፡ የሃሳብ ልዩነት በሰፊው የሚያንሸራሽሩ ጋዜጦች እድሜያቸው አጭር ሲሆን አይተናል፡፡
በብሮድካስት በኩል እየበዛ ያለው በቁጥር እንጂ የተለያዩ አስተሳሰቦችን በማንፀባረቅ ደረጃ አይደለም፡፡ በየክልሉ የተመሰረቱ ብሮድካስት ሚዲያዎች ከኢቢሲ ጋር ተመሳሳይ ይዘት ነው ያላቸው፡፡ እንደኔ በቁጥር መስፋፋታቸው ጥሩ መስሎ የሚታየኝ፣ ስቱዲዮዎች ከመገንባታቸውና መሰረተ ሚዲያው ከመዋቀሩ አንጻር ነው፡፡ ኢቢሲን ነጥለን ብንመለከት ብሮድካስት ኮርፖሬት ሲሆን ራሱን እያስተዳደረ መንግስትን ሳይሆን ህዝብን እንዲያገለግል ተብሎ የተዋቀረ ነው፡፡ ግን አሁን ይሄን በተግባር እየሰራ ነው ወይ? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ከህትመት ሚዲያው፣ጠንካራ ጉዳዮችን የሚዘግቡት ከሁለት አይበልጡም፡፡ ይሄን ስናይ በቁጥርም በይዘትም ብዝሃነት አለው ለማለት እንቸገራለን፡፡ የሚዲያ ብዝሃነት ከሌለ ደግሞ መንግስት ድክመቶቹን መረዳት የሚችልበት አማራጭ አያገኝም፡፡ ይሄ ለመንግስት ውድቀት ነው፡፡ ብዝሃነት ስንል የሃሳብ ብዝሃነት እንጂ ቁጥር ላይ ካተኮርን ስህተት ነው፡፡ ለምሳሌ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች በአሁን ሰአት ሃሳባቸውን የሚያቀርቡበት አማራጭ የላቸውም፡፡ ፕሬሱም የሚገባውን ያህል ቦታ እየሰጣቸው ያለ አይመስለኝም፡፡ በጥቂቱ የማየው አንዳንድ ጋዜጦች በተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ሲያወያዩዋቸው ብቻ ነው፡፡ ይሄ ጥቂትም ቢሆን የነሱን ሀሳብ ማግኘት ለሚፈልግ ህዝብ እጅግ ጠቃሚ ከመሆኑም በላይ መንግስት አቋማቸውን በተዘዋዋሪ እንዲረዳና ምክራቸውን የሚቀበል ከሆነ እንዲቀበል ይረዳዋል፡፡ በዚህ መንገድ ውስጥ ያሉ ፕሬሶች የሃሳብ ብዝሃነት ትርጉሙ የገባቸው ይመስለኛል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤የሚዲያ ፖሊሲውን ልማታዊ ብሎ ጠቅልሎ ጨርሶታል፡፡


===============================


“ራስን በራስ ሳንሱር የማድረግ ችግር አለ”

ዶ/ር ነገረ ሌንጮ
(በአ.አ.ዩ.የጋዜጠኝነትና ኮሚኒኬሽን ት/ት ክፍል ዲን)

የአንድ ሚዲያ እድገት የሚለካው አንደኛ የተቋሙ ብቃት፣ የህግ ማዕቀፉ አሠሪነት ምን ያህል አሳታፊ ነው የሚሉት መታየት አለባቸው፡፡ የባለሙያ ደረጃውስ ምን ይመስላል የሚለውንም ማየት አለብን፡፡ ከፕሬስ ነፃነት ጋር ተያይዞ የሚነሳው የፖለቲካል ኢኮኖሚው ለሚዲያ የሚሰጠው ግምት ምንድን ነው የሚለውን ማየት ይኖርብናል፡፡ ከዚህ አኳያ የኛን ሀገር ስንመለከት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ስለ ሚዲያ ነፃነት መናገር ከጀመርን ሁለት አስርት አመታት ብቻ ነው ያስቆጠርነው፡፡
ስርአቱ ራሱ የሚዲያ ጉዳይን ህጋዊ አድርጓል፡፡ በህገመንግስቱም፣ በሚዲያ ህጐችም የሚዲያ ነፃነት ተደንግጓል፡፡ መረጃ ማግኘት የዜጐች መብት እንደሆነ፣ መንግስት ደግሞ ስልጣኑን የሚያገኘው ከህዝብ እንደሆነ ተደንግጓል፡፡ ይሄ እንዴት ነው ተግባር ላይ እየዋለ ያለው ስንል፣ የጋዜጠኞች ብቃትንና የሚዲያ ተቋማትን ጥንካሬ ይጠይቃል፡፡ በአተገባበሩ ላይ ክፍተቶች እንዳሉ የማይካድ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ሁሉም ሃላፊነት ተሠምቷቸው በትክክል ይሠራሉ ብለን ብንጠይቅ፣ የሚሠሩም አሉ የማይሰሩም አሉ፡፡ ከመንግስት ባለስልጣናትም ህጉን በተገቢው የማያስፈጽሙ ይኖራሉ፡፡ በአለማቀፍ ሪፖርቶች፣መንግስት ሚዲያን ያፍናል የሚል ሪፖርት ይወጣል፡፡ እንደዚህ አይነት ችግር ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን በትክክል የጋዜጠኝነትን ሙያዊ መሠረቱን ጠንቅቀው አውቀው የሚሠሩት ናቸው የሚታሠሩት? የሚሰደዱት? ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ እንደኔ ጋዜጠኞቹም መንግስትም ጋ ችግር አለ፡፡ አንዳንድ ጋዜጠኞችም ራሣቸውን በራሳቸው አላስፈላጊ ሳንሱር ያደርጋሉ፡፡ ይሄ ሲሆን ለህዝብ የተሰጠው መረጃን የማግኘት መብት ይጨፈለቃል፡፡ እኔ ችግር ያለው ከህገ-መንግስታዊ ስርአቱ አይመስለኝም፤የግለሰቦች ችግር ነው፡፡ ባለፉት 20 አመታት በእነዚህ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፎ የመጣ ፕሬስ እየተገነባ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡
“የሚዲያ ብዝሃነትን በእርግጥስ ያከበረች ሀገር ነች ወይ” የሚለው ጥያቄ፣ በኢትዮጵያ ይቅርና አደጉ በተባሉ ሃገሮች እንኳ “አዎ” እና “አይደለም” በሚል የሚመለስ አይደለም፡፡ ለምሣሌ መጽሐፍት የፈለጋቸውን ሃሳብ እያንፀባረቁ ይታተማሉ፡፡ አልፎ አልፎ ደግሞ ገደብ የሚጣልበት ሁኔታ አለ፡፡ ይሄ ተገቢ አይሆንም፡፡ የህዝብ ሚዲያዎች ላይ ሃሳብ ምን ያህል ብዝሃነት አለው የሚለውን ስናይ፣ ትንሽ ችግር አለ፤ተከልክለው አይደለም፡፡ የግለሰቦች ራስን በራስ ሳንሱር የማድረግ ችግር ነው፡፡ በመርህ ደረጃ ብዝሃነት ይኑር የሚል አመለካከት አለ፤ ይሄን ወደፊት በተግባር ማምጣት አለብን፡፡