Administrator

Administrator

• መንግስት በዓመት ለውጭ እዳ ከ900 ሚሊዮን ዶላር በላይ ይከፈላል
• የወለድ ክፍያው ብቻ በዓመት ወደ 300 ሚ. ዶላር ይጠጋል
• የአገር ውስጥና የውጭ ጠቅላላ እዳ 770 ቢ. ብር ሆኗል

     ባለፉት አምስት አመታት በፍጥነት እየገዘፈ የመጣው የመንግስት የውጭ እዳ 20 ቢ. ዶላር እንደደረሰ ሰሞኑን ከገንዘብ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ያስረዳል፡፡ በስድስት ወራት ውስጥ ለውጭ እዳ ክፍያ 450 ሚ. ደላር ተከፍሏል፡፡ ከዚህም ውስጥ 140 ሚ. ዶላር የወለድ ክፍያ ነው፡፡
በ2001 ዓ.ም የመንግስት የውጭ እዳ ከአምስት ቢሊዮን ዶላር በታች እንደነበረ የሚታወስ ሲሆን፤
በታህሳስ ወር የእዳ ክምችቱ ሃያ ቢሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡ ከዚያ ወዲህ ባሉት ወራት እስከ ሰኔ የበጀት መዝጊያ ድረስ የሚመጡ ብድሮች ሲጨመሩበት፣ እዳው ወደ 22 ቢሊዮን ዶላር ሊጠጋ ይችላል፡፡
በአምስት አመታት ውስጥ ወደ አራት እጥፍ ከገዘፈው የእዳ ክምችት ጋር፤  እዳ ከነወለዱ
ለመመለስ አገሪቱ የምታጣው ገንዘብም በእጅጉ ጨምሯል፡፡ በ2001 ዓ.ም፣ እዳ ለመመለስ ኢትዮጵያ የከፈለችው 80ሚ. ዶላር አይሞላም ነበር፡፡የዘንድሮው ክፍያ ከ900 ሚ. ዶላር በላይ ይሆናል፡፡
 ከዚህም ውስጥ የብድር ወለድ ለመክፈል የሚውለው ገንዘብ ወደ 300 ሚ. ዶላር ይጠጋል ተብሎ
ይገመታል፡፡ ከአምስት ዓመት በፊት ግን የወለድ ክፍያው ከ30 ሚ ዶላር በታች ነበር - አምና 250 ሚ.ዶላር፡፡ በሌላ በኩል፤ የመንግስት የአገር ውስጥ ብድርም እንዲሁ፤ በአምስት ዓመታት ውስጥ፣ ከመቶ
ቢሊዮን ብር ወደ 350 ቢሊዮን ብር ጨምሯል፡፡ እስከ ታህሳስ ወር ድረስ ጠቅላላ የመንግስት የአገር ውስጥና የውጭ እዳ 770 ቢ. ብር እንደደረሰ የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ይገልጻል፡፡  



      ካንሰር እያደገ የመጣ የጤና ችግር መሆኑንና በአገሪቱ በየአመቱ 44 ያህል ሺህ ሰዎች በካንሰር ሳቢያ ለሞት እንደሚዳረጉ፤ 77 ሺህ የሚደርሱ ሰዎችም በካንሰር እንደሚጠቁ “አናዶሉ ኤጀንሲ” ዘገበ፡፡በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የካንሰር መከላከልና ቁጥጥር ፕሮግራም የቴክኒክ አማካሪ ዶክተር ኩኑዝ አብደላን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የካንሰር ችግር በመስፋፋት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ከሚከሰተው የሞት መጠን 5.8 በመቶ የሚሆነውን የሚሸፍነውም በካንሰር በሽታ ሳቢያ የሚከሰት ሞት ነው፡፡ በአገሪቱ ለካንሰር ተጋላጭ በመሆን ረገድ ሴቶች ቅድሚያውን እንደሚይዙና ይህም እጅግ አሳሳቢእንደሆነ ለ“አናዶሉ ኤጀንሲ” የተናገሩት ዶክተር ኩኑዝ አብደላ፣ በካንሰር ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት ተዳርገዋል በሚል ሪፖርት ከተደረጉት መካከል ሁለት ሶስተኛ የሚሆኑት ሴቶች ናቸው ብለዋል፡፡ በአገሪቱ በአዋቂ ሴቶች ላይ ከሚከሰቱት የካንሰር አይነቶች መካከል ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘው የጡት ካንሰር እንደሆነም አስረድተዋል፡፡መንግስት ካንሰርን ለመከላከልና ለማከም ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ በተመረጡ 118 ሆስፒታሎች የማህጸን በር ካንሰር ምርመራና ህክምናን ለማስፋፋት እየተሰራ እንደሚገኝ፤ የመድሃኒት አቅርቦትና ለካንሰር ህክምና የሰው ሃይል ማሟላትም ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች መካከል እንደሚገኙበት ገልጿል፡፡

    አርጀንቲናዊው የአለማችን የእግር ኳስ ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ፤ ከዚህ በፊት ይጠቀምበት የነበረውን ጫማውን በግብጽ ለበጎ አድራጎት የሚውል ገንዘብ ለማሰባሰብ በሚደረግ ጨረታ ላይ ለሽያጭ እንዲቀርብ በስጦታ መልክ ማበርከት እንደሚፈልግ መናገሩ በርካታ ግብጻውያንን ማበሳጨቱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ሜሲ መልካም ነገር በማሰብ ጫማውን በስጦታ ለማበርከት እንደሚፈልግ በአንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ቢናገርም፣ ጉዳዩ በግብጻውያን ዘንድ በንቀት መተርጎሙንና ሰሞንኛ የመነጋገሪያ አጀንዳ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ ፓርላማ አባል የሆኑ ግለሰብም አልአሲማህ በተባለው ብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ቀርበው የሜሲን ድርጊት በማውገዝ፣ለሜሲና ለአርጀንቲና የራሳቸውን ጫማ እንደሚሰጡ መናገራቸውን ገልጧል፡፡
የግብጽ እግር ኳስ ማህበር ቃል አቀባይ አዝሚ መጋሄድ በበኩላቸው፤ የሜሲን ድርጊት በማውገዝ፣ግብጻውያን የእሱን ድጋፍና እርዳታ እንደማይፈልጉና ጫማውን ራሱ እንዲጫማው አልያም የድሆች መናኸሪያ ለሆነች የአርጀንቲና ምንዱባን እንዲሰጥ መክረውታል፡፡
የእግር ኳስ ተጫዋቹ ድርጊት በግብጽ ላይ የተደረገ ብሄራዊ ንቀት ነው በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው የጠቆመው ዘገባው፣ ይህም ሊሆን የቻለው ጫማ በግብጽና በሌሎች የአረብ አገራት እንደ አንድ የንቀት ምልክት ተደርጎ የሚታይ በመሆኑ ነው ብሏል፡፡

       ከአለማችን ዘመን አይሽሬ የእግር ኳስ ከዋክብት አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ብራዚላዊው የእግር ኳስ ተጫዋች ፔሌ፣ ያለፈቃዴ የምርቶች ሽያጭ ማስታቂያ ሰርቶብኛል በማለት የደቡብ ኮርያውን የኤሌክትሮኒክስ አምራች ኩባንያ ሳምሰንግ በ30 ሚሊዮን ዶላር መክሰሱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ፔሌ ቺካጎ ውስጥ ለሚገኝ ፍርድ ቤት ባቀረበው ክስ፣ ኩባንያው እጅግ ዘመናዊውን የቴሌቪዥን ምርቱን በኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ባስተዋወቀበት ወቅት ምስሌን ያለፍቃዴ ተጠቅሟል፤ ለዚህም ቢያንስ 30 ሚሊዮን ዶላር ካሳ ሊሰጠኝ ይገባል ሲል መጠየቁን ዘገባው ገልጧል፡፡
ሳምሰንግ ከዚህ ቀደም የፔሌን ምስል ለምርቶቹ ማስታወቂያነት ሲጠቀም እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በተጫዋቹና በኩባንያው መካከል የነበረው የማስታወቂያ ስራ ውል ከ3 አመታት በፊት መቋረጡን ጠቁሟል፡፡
ፔሌ ሳምሰንግ ምስሌን ተጠቅሞ ማስታወቂያ ሰርቶብኛል ቢልም፣ በማስታወቂያው ላይ የወጣው ፎቶ ግን የራሱ የፔሌ ሳይሆን ከፔሌ ጋር እጅግ የሚመሳሰል የፊት ገጽታ ያለው ሌላ ግለሰብ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡  
ይሄም ሆኖ ግን ኩባንያው ከዚህ በፊት በፔሌ ምስል ምርቶችን ከማስተዋወቁ ጋር በተያያዘ፣ ይህንን ምስልም ተመልካቾችንና ሸማቾችን ለማሳሳትና ሽያጩን ለማሳደግ ባልተገባ ሁኔታ እንደተጠቀመበት ከግምት ውስጥ በማስገባት ፍርድ ቤቱ ለእሱ ሊወስንለት እንደሚችል ተነግሯል፡፡

የደቡብ ኮርያን ቤተ-መንግስት እንደምትደበደብም ዝታለች

         ባለፈው ሳምንት በደቡብ ኮርያ ቤተ መንግስት ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም ያስጠነቀቀቺው ሰሜን ኮርያ፤ ባለፈው ማክሰኞ ደግሞ በአሜሪካ ላይ የኒውክሌር ጥቃት ለመፈጸም መዘጋጀቷን እንዳስታወቀች ዴይሊ ሜይል ዘገበ፡፡ ለወራት የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎች ሙከራ ስታደርግ የቆየቺው የሰሜን ኮርያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሊ ሱ ዮንግ፣ የጦር ሃይላቸው በአሜሪካ ላይ የኒውክሌር ጥቃት ለመፈጸም የሚያስችለውን ዝግጅት ማከናወኑን እንዳስታወቁ ዘገባው ገልጧል፡፡
ሰሜን ኮርያ፤አሜሪካና ደቡብ ኮርያ በጋራ የሚያከናውኑትን ወታደራዊ ልምምድ በአፋጣኝ ካላቋረጡ በአካባቢው ሰላም አይሰፍንም ስትል እንደቆየች ያስታወሰው ዘገባው፣ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃንም የጦር ሃይሉ በደቡብ ኮርያ ቤተ መንግስትና በኒውዮርክ ላይ የኒውክሌር ጥቃት ለመፈጸም ዝግጁ እንደሆነ የሚያሳዩ የፕሮጋንዳ መረጃዎችን ማሰራጨታቸውን ገልጧል፡፡
የደቡብ ኮርያ ባለስልጣናት፣ሰሜን ኮርያ በአገሪቱ ምስራቃዊ ድንበር አቅራቢያ በሚገኝ ስፍራ ማክሰኞ ዕለት የአጭር ርቀት ተኩስ ሙከራ ማድረጓን እንደገለጹ የጠቆመው ዘገባው፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከትናንት በስቲያ ዋሽንግተን ውስጥ በተካሄደው የአለማቀፉ የኒውክሌር ደህንነት ጉባኤ ላይ ከቻይናው ፕሬዚዳንት ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መምከራቸውን ገልጧል፡፡
ሲኤንኤን በበኩሉ፤ሰሜን ኮርያ ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ውስጥ ልትገባ እንደምትችል የሚያሳይ የማስፈራሪያ የፕሮጋንዳ ቪዲዮ መልቀቋን ዘግቧል፡፡

 በ23 ሚ ዶላር የህዝብ ገንዘብ ቤታቸውን አድሰዋል ተብሏል
    23 ሚሊዮን ዶላር የህዝብ ገንዘብ ያለአግባብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል ክስ የቀረበባቸውና ከሳምንታት በፊት ካባከኑት ገንዘብ የተወሰነውን ለመመለስ ቃል ገብተው የነበሩት የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ፣ በገቡት ቃል መሰረት ገንዘቡን ባለመመለሳቸው የአገሪቱን ህገ-መንግስት ጥሰዋል፣ ያባከኑትን ገንዘብ መመለስ ይገባቸዋል ሲል የደቡብ አፍሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ እንዳስተላለፈባቸው ተዘገበ፡፡
የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ተከትሎ የአገሪቱ መንግስት ባወጣው መግለጫ፣ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ እንደሚያከብሩና በቅርቡ በጉዳዩ ዙሪያ ያላቸውን አስተያየት በይፋ እንደሚሰጡ ማስታወቁም ተነግሯል፡፡
ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፕሬዚዳንቱ ከመንግስት ካዝና ገንዘቡን ወጪ በማድረግ የግል መኖሪያ ቤታቸውን አሳድሰዋል በሚል ክስ የመሰረቱባቸው ሲሆን ጉዳዩን ሲከታተል የነበረው የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤትም፤ ፕሬዚዳንቱ ካባከኑት ገንዘብ የተወሰነውን ለመመለስ የገቡትን ቃል ባለመፈጸማቸው ጥፋተኛ መሆናቸውን ገልጾ፣ የሚመለከተው የመንግስት አካል መመመለስ የሚገባቸውን የገንዘብ መጠን አስልቶ በ2 ወራት ጊዜ ውስጥ እንዲያሳውቅ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡
ፐብሊክ ፕሮቴክተር የተባለው የአገሪቱ የጸረ ሙስና ተቋም፣ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ ከመንግስት ካዝና 23 ሚሊዮን ዶላር ወጪ በማድረግ በኩዋዙሉ አውራጃ የሚገኘውን የመኖሪያ ቤታቸውን፣ የቅንጦት እቃዎችን ባሟላና በዘመናዊ መልክ አሳድሰዋል በሚል ተጠያቂ እንዳደረጋቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ ኢኮኖሚክ ፍሪደም ፋይተርስ እና ዲሞክራቲክ አሊያንስ የተባሉ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በፕሬዚዳንቱ ላይ ክስ መመስረታቸውን ገልጧል፡፡ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፍርድ ቤቱ በፕሬዚዳንቱ ላይ ያስተላለፈው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳስደሰታቸው የጠቆመው ዘገባው፣ አፍሪካን ክርስቲያን ዲሞክራቲክ ፓርቲም ፍርድ ቤቱ በገዢው ፓርቲ ተጽዕኖ ስር ሳይውል ነጻና ፍትሃዊ ውሳኔ ማስተላለፉ እንዳስደሰተው ገልጾ፣ የጃኮብ ዙማ ፓርቲ ስልጣን ላይ እስካለ ድረስ አገሪቱ ከአደጋ አትወጣም ሲል ማስጠንቀቁንም ዘገባው አስረድቷል፡፡

Monday, 04 April 2016 08:54

ተናዳፊ ግጥም

በዕውቀቱ የተቀኘው “የባይተዋር ገድል”
               ምርጫና ሂስ ፥ ዕዝራ አብደላ
                        [ተናዳፊ ሥሩ ነደፈ ነው። ተሰማ ሀብተ ሚካኤል ሲተረጉሙት የቃሉ ጨረር አይመክንም። (ገጽ 667) “ ንብ ነደፈ፥ በመርዙ ጠዘጠዘ ወጋ ጠቀጠቀ ” ወይም “ በፍቅር ተነደፈ ተያዘ ተቃጠለ ” እንዲሁም“ ባዘቶውን አፍታታ በረበረ ” ..... ግጥም ለጭብጡ፥ ለስንኝ አደራደሩ ወይም ለቋንቋው ምትሀት ምናባችንን ከቧጠጠ ተናዳፊ ነው፤ አንብበነው የምንዘነጋው፥ ጥፍሮቹ የተከረከመው ግን ኢ-ግጥም ነው።]
-- ቁጥር 4 --
-------------------------------
የባይተዋር ገድል

በቁም መስተዋት ፊት መቆምኽ ሲጨንቅህ
የቁም መስተዋቱ፥ “ሰውነትህ የታል?” ብሎ
ሲጠይቅህ
ግድግዳው ላይ ያለች፥ የገደል ማሚቶ፥ ዝም
ማለት ፈርታ
ሳሎንህን ስትሞላው ዝምህን አባዝታ
ሕልም የቀላቀለ፥ የዝናም ነጠብጣብ፥ ጣራኽን
ሲመታ
ከመስኮትኽ ማዶ፥ የሌሊት ወፍ ሞታ
የጊዜ ስውር ክንድ
የጓሮህን ዋርካ ያላጋር ሲያስቀረው
በሌሊት ወፍ ምትክ፥ የኑሮ ገባር ወንዝ፥ አልጋህን
ሲገምሰው
“መንሳፈፉስ ይቅር፥ መስጠም ያቅተዋል ሰው?”
ሲያሰኝህ ዕድልህ
ያኔ ይጀምራል፥ የባይተዋር ገድልህ።
-------------------------------
©በዕውቀቱ ስዩም
 [ስብስብ ግጥሞች፥ ገፅ 72]
-------------------------------
ገድል፥ የፃድቃንና የሰማእታት ሣይሆን አንድ ግለሰብ ከማኅበረሰቡ ሲፋተግ፥ አለበለዚያ ሥነልቦናዊ ቁስሉ፥ ስጋቱ ሲመዘምዘው ገና የሚጠብቀውን ዕንግልት ይጦቅማል። የተወለድንበት ቀዬ ናፍቆት እና የመንደራችን ትዝታ አገርሽተው ከአዲስ አካባቢ መኖር ስንጀምር ባይተዋር ያደርጉናል። አዲሱን ስንላመድ ናፍቆት እየፈዘዘ፥ ትዝታም እያፈገፈገ መንፈሳችን ወከክ ተርከክ ይላል። ይህ የስፍራ ባዳነት ትንፋሽ ያጥረዋል፤ ከራስ ጋር መላተም ነው ጥልቅ ስሜት። በዕውቀቱ የተቀኘለት ግለሰብ ግን የስፍራ ለውጥ፥ የናፍቆት የትዝታ ሰለባ አይደለም። ውስጡ የደቀቀ ንቃተ-ህሊናው ለመርገብ ያልፈቀደለት ብቸኛ ይመስላል። በሁለቱም -በብቸኝነት እና በብቻነት- የሚማቅቅ ነው። ብቻነት ከሌላው ለመቀላቀል ጉጉት እያለው ተገፍትሮ ሌጣውን የቀረ ነው። ማኅበራዊ መተሳሰር፥ ፍቅረኛ ወዳጅ ቢያገኝ ሊተርፍ ይችላል። `ብቸኝነት` ግን ከሰዎች መካከል ሆኖ፥ ቤተሰብም ኖሮት ጣዕማቸው ሲሟጠጥ፥ ከነሱ ጋር መኖር የግድ ሆኖበት ሲጐመዝዘው ባይተዋር ነው። አንድ ግለሰብ ብቸኝነት ሲመዘምዘው፥ ሲገለል፥ ለራሱ ለሌላውም ባዳ ሲሆን ለአካላዊ ሆነ ሥነልቦናዊ እንግልት ይዳረጋል። ለዚህ ባይተዋር ነው በዕውቀቱ ገለልተኛ ተራኪ መልምሎ የተቀኘው። ዝነኛ አሜሪካዊቷ ገጣሚ Sylvia Plath ባለቤቷን ተከትላ ሁለት ህፃን ልጆቿን እያባበለች ለሥነጽሑፍ አድራ ማቀቀች። ለጥልቅና ውብ ግጥሞች ወይስ ለትዳሯና ለልጆቿ ትኑር? አቃስታለች። ስለ ኅላዌ ብሎም ዕጣ ፈንታዋ እየተብሰከሰከች ግራ ተጋብታ፣ ለራሷም ጭምር ባይተዋር ሆነች፤መሸሸጊያ የሆነ ጥግ ተነፈገች። በዕውቀቱ እንዲሚለው፤ “መንሳፈፉስ ይቅር፥ መስጠም ያቅተዋል ሰው?” ሲልቪያ ጭንቅላቷን ከጋዝ ምድጃ ወትፋ ትሞታለች። ብርሃኑ ድንቄ ከኑሮ ልምድ ያጠነፈፈው ሀቅ አለ። “ብቻህን ለመቆም ተዘጋጅ፤ ልጅ፥ ወንድም፥ እህት፥ ዘመድ የሚባሉት ነገሮች የምቾት ጊዜ ጌጦችና አጫፋሪዎች ናቸው።” [አልቦ ዘመድ፥ ገፅ 1] ይህ አባባል ሰክነው የልጃቸውን ምስል እያዩ ለሚፈነድቁ ይጐመዝዛል፤ ለእንደነ ሲልቪያ ግን የርዕይ መነጠቅ ውጤት ነው። አበራ ለማ በአንድ ግጥሙ ተመስጦበታል። “ያ መረቡ ልቤ ረገበ እምቢ አለ/ አንድ እራሱን ማስገር አቃተው ዋለለ።” ይህ ነው የባይተዋር ዕንቆቅልሽ።
ተራኪው አንባቢን ነው የሚያናግረው። አንተ/አንቺ ባይተዋሩን ብትሆኑ ኖሮ እያለ ከገፀባህሪዩ ተላቆ እኛን ያሳስበናል። ገላቸው እያለቀ፥ ክፍላቸው በዝምታ ተውጦ -የሌላ ሰውን አለመኖር የሚያጐላ- ብሎም በሌላው መረሳት ሰቆቃው መዘመዛቸው። የሳርተር ህልውናነት ተከታይ ይመስል፥ አንድ ውጫዊ ሃይል -እግዜር- አለ ይደርስልኛል ብሎ የሚያምን አይመስልም፤ መንፈሳዊ ምርኩዙን የተቀማ አይነት ነው። ስለት፥ ተማፅኖ፥ ፀሎት ... እንደ የተስፋ ስንቅ አይታወሱም። ገጣሚው በጥቅስ ያደመቀው መፍትሄ አሳሳቢ ነው። “`መንሳፈፉስ ይቅር፥ መስመጥ ያቅተዋል ስው?`/ ሲያሰኝህ ዕድልህ/ ያኔ ይጀምራል የባይተዋር ገድልህ።”  እዚህ ላይ ተወሳሰበ። ራስን እስከማጥፋት እንደ የደነበረ በሬ ያሚያሯሩጥ፥ የሚፈገትር ብቸኝነት ሆነ። ገጣሚው ከደረደራቸው የሰቆቃ ምስሎች በኋላ “መስመጥ ያቅተዋል ሰው?” ብሎ ይጠይቃል። ከዕለታዊ ሥነልቦናዊ ማኅበራዊ ስቃይ -the pain of life- ለመገላገል ራስንም የማጥፋት ምርጫ እንዳለ ጠቋሚ ነው።
በግል ጉዳይ ሰው ተነጥቆ ከመንደሩ በብቸኝነት የተተበተበ ግለሰብ ሲማቅቅ ልብ አይል ይሆናል:: አለማየሁ ገላጋይ በ<ኩርቢቷ> አጭር ልቦለድ ሰዎች መካከል ሆና ብቸኝነት የቆረፈዳት ወጣት እናት ስሏል:: ድንገት የሞተው ባሏ ቤቱንና ንብረቱን በእናት አባቱ ስም ስላስመዘገበ ለልጇ ብላ ሁሉን ነገር ተነፍጋ፣ ተቸግራ ዝምታን ለምዳ አለማምዳም እንደ ጥላ ያለ ኮሽታ ትንቀሳቀሳለች:: ህፃን ልጇም ታዘበቻት። “እዚህ አያቶቼ ግቢ ዉስጥ የኖረችዉ በመንፈስ ህልውና ነው ማለት እችላለሁ:: ስትሄድ ኮቴዋ አይሰማም:: ለዚህ ዓለም ሙቀትና ቅዝቃዜ ምንም አይነት ምላሽ ስትሰጥ አይታይም:: አትስቅም፣  አታለቅስም:: ሆዷ ተከፍቶ ስትበላና ስትጠጣ አጋጥሞኝ አያውቅም::”[ ገፅ 53] ብቸኝነት የመጠጣት እናት አንድ ጠዋት ብድግ ብላ ጠፋች:: የባይተዋር ገድሏ የጀመረው፥ ትዳር እንደ ቀለሰች ነበር።
ስለ ባይተዋር እንግልት በወግ በትረካ ለመፃፍ አያዳግትም፤ የበዕውቀቱ ግጥም ልዩ የሆነበት ምክንያት ምንድነው? በሥነግጥምና በዕውነታ መካከል መመሳሰልስ አለ ወይ? ግጥም የተለያዩ ገሃዶች (ማኅበራዊ፥ ሃይማኖታዊ፥ ፖለቲካዊ ...) ማንዘፍዘፍ ይችላል ወይ? የምናፈጥበት ሳይሆን የምናዋቅረው ቃላዊ-ዕውነታ -constructed verbal reality- ከምናብ ያንሰራራል፤ ጥበባዊ ነው። ሥነግጥም የሚዳሰስ አይደለም፤ ፈጠራ ነው። የስንኝ ትርታ፥ የተወለወለ አንጓ፥ ግጥማዊ ቅርፅ፥ ሙዚቃዊ ምት የግድ በውብ ምስላዊ ቃላት መወርዛት አለበት። ባለአንድ አንጓ ግጥም አስራ ሶስት ስንኞች ነዘሩበት። በስንኞች መካከል ክፍተት ወይም ቦግታ ሣይኖር መታፈጉ የባይተዋሩን የጭንቀት ድድርነት ይወክላል። ገፅ ላይ ተኮራምተው እንጂ ተበታትነው ስንኞቹ ለብርሃን -ለነጭ ባዶ መስመር- ስፍራ ነፍገውታል፤ የባይተዋር ገድሉ ጀመረ።
የበዕውቀቱ ስዩም ስብስብ ግጥሞች ለአማርኛ ሥነጽሑፍ ፈርጥ ናቸው። “ግድግዳው ላይ ያለች፥ የገደል ማሚቶ፥ ዝም ማለት ፈርታ/ ሳሎንህን ስትሞላው ዝምህን አባዝታ” በዓሉ ግርማ የዛሬ አርባ አመት “ከአድማስ ባሻገር” ልቦለዱን በዝምታ ነው የበረገደው። “ቤቱን የዝምታ አዘቅት ውጦታል” በማለት ከዝምታ ሙዚቃ  ሲመነጭም ይሰመዋል። ደበበ ሰይፉ “ባለአደራ” በሚለው ግጥሙ በዘመን ጭራ ታስራ ስለተጐተተች የገደል ማሚቶ ተቀኝቷል። በየግጥሙ የሚያባባው ምስል ነው። “የገደል ማሚቶ ትንቃ፥ ከእንቅልፍ ትራሷ ትከንበል/ ከቦዘን ህልሟ ትፈንገል/ አንደበታችንኮ ዝጓል እማምዬ፥ አእምሯችን በክሎ/.../ የጆሮን ታሪክ በዝምታ አብጠልጥሎ” የበዕውቀቱ ገደል ማሚቶ እንደ ግዙፍ ተናዳፊ ሸረሪት ድሯን ስትተበትብ ቤቱን በዝምታ ታፍነዋለች። ይህ ተንቀሳቃሽ ዝምታ፥ የገደል ማሚቶ ምስል ብዙ ሊያወያይ ይችላል። መስተዋት ግዑዝ ሳይሆን በጥያቄ ሲያፋጥጥህ፥ የገደል ማሚቶ ግድግዳው ላይ በመንፏቀቅ ድምፅ ተነፍጋ ስታፍንህ፥ የሌሊት ወፍ ከበራፍህ ሲሞት (አስፈሪነቱ)፥ ጊዜ እንደብል እድሜን ሲያደቀው፥ እንቅልፍ ሲሸሽህ፥ በሌሎች መረሳት ሲመዘምዝህ ባይተዋር ነህ።
“መንሳፈፍ ይቅር፥ መስጠም ያቅተዋል ሰው?” መንሳፈፍ እንደ ነገሩ መኖር ከሆነና ይህ ከሰቀቀህ፥ ይህ ሥነልቦናህን ቀጥቅጦ ካንገላታህ መፍትሄው -የማያቅትህ- መስጠም ነው፤ ራስን አጥፍቶ የመገላገል ምርጫም አለ ባይ ነው። ግለሰብ እንዲህ ለማሰብ ሲነሳሳ “ያኔ ይጀምራል፥ የባይተዋር ገድልህ” ሲል ገድል ደግሞ የስቃይ ታሪክ ከሆነ የገድል መጀመር፥ የእንግልት ቅፍለት ያስደነግጣል። የዘመነኛ ንቁ ሰው እጣ ፈንታው በህይወት መፍካት ሣይሆን ለኅላዌ ጭንቀት ይገጣጠባል። በሌሎች መገለል መረሳት ነባር የቃል ግጥም ያስታውሰናል። “እህል ዱር አደረ፥ ብቻውንም ዋለ/ ጠላት እንደሌለው፥ ሰው እንዳልገደለ” ለባይተዋሩ ከእህል በበለጠ የሰው -የብጤው- ረሃብ ያንገላተዋል። በዕውቀቱ ግለሰብ ከራሱ ሲላተም ነው በበለጠ የሚያሰጋው። “መሽቷል አትበል” በተሰኘ ግጥሙ የባይተዋርን ገድል ከግለሰብ ውስጠት አፍርጦታል። “በውስጥህ ላለው ብርሃን/ ግርዶሽ የኾንህ ለ`ታ/ ያን ጊዜ ኾኗል ጽልመት/ ያን ጊዜ ኾኗል ማታ።”  ከግጥሞቹ ፈቀቅ ብለን “ከአሜን ባሻገር”ን ብናነብ በዕውቀቱ አሁንም ባለቅኔና ጥልቅ እንጂ ግልብ አይደልም።

Monday, 04 April 2016 09:00

የኪነት ጥግ

(ስለ ፒያኖ)
ለእኔ ፒያኖ እንደ ሙሉ ኦርኬስትራ ነው፡፡
ዴቭ ብሩቤክ
ምንም ነገር ባልነበረኝ ጊዜ እናቴና ፒያኖ ነበሩኝ፡፡ አይገርማችሁም? ያኔ የሚያስፈልጉኝ እነሱ ብቻ ነበሩ፡፡
አሊሺያኪስ
ህይወት እንደ ፒያኖ ነው፤ ነጫጮቹ ቁልፎች ደስታን ይወክላሉ፤ ጥቁሮቹ ደግሞ ሃዘንን፡፡ ነገር ግን አስታውስ! በህይወት ጉዞ ውስጥ ስትነጉድ ጥቁሮቹ ቁልፎችም ሙዚቃ ይፈጥራሉ፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
ስትጫወት ስለሚያደምጥህ ሰው ፈፅሞ ደንታ አይስጥህ፡፡
ሮበርት ሹማን
መንግስት ብቃት ለሌላቸው ሰዎች፣ በፒያኖ ላይ ግብር እንዲጥል እመኛለሁ፡፡
ኢዲዝ ሲትዌል
ፒያኖ ስጠኝና ሙዚቃ እሰጥሃለሁ፡፡
ዮሃን ዳፌዮ
አባቴ ግንበኛ እንዲሁም ተሰጥኦ ያለው አማተር ፒያኖ ተጫዋችና ድምፃዊ ነበር፡፡
ጆን ኢ.ዎከር
ህይወት እንደ ፒያኖ ነው፤ ከውስጡ የምታገኘው በአጨዋወትህ የሚወሰን ነው፡፡
ቶም ሎህረር
እኒህ የእኔ ጣቶች በውስጣቸው አዕምሮ አላቸው፡፡ ምን መስራት እንዳለባቸው መንገር የለባችሁም - ራሳቸው አውቀው ይሰሩታል፡፡
ጄሪ ሊ ሌዊስ
አብዛኞቹን ቀናት ጠዋት ፒያኖ እለማመዳለሁ፤ ቀሪውን ጊዜ ስዕል በመስራት አሳልፋለሁ፡፡
ቻዮ ፎኔስካ
ፒያኖን በጣቶቻችን አይደለም የምንጫወተው፤ በአዕምሮአችን እንጂ፡፡
ግሌን ጉልድ

 የጋዜጠኛና ደራሲ ተሾመ ገብረሥላሴ “ባልታሰሩ ክንፎች” የተሰኘ መጽሐፍ የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ በዋቢሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡  መጽሐፉ፤ ወጐችን ተረኮችን፣ የታሪክ ማስታወሻዎችን፣ ዝርው ግጥሞችንና አጭር ልብወለዶችን ያካተተ ሆኖ በ184 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ60 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
“ጋዜጠኝነትን ሙያዬ ብዬ የጀመርኩት በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ነው” ያለው ተሾመ፤ ከዚያም በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት፣ በሸገር ሬዲዮና በሌሎች መገናኛ ብዙሃን ፕሮግራሞችና አምዶችን ከአዘጋጅነት እስከ አርታኢነት እንደሰራ ይናገራል፡፡  ደራሲው “የባህር ጠብታ” የተሰኘውን የመጀመሪያ መጽሐፉን ከ10 ዓመት በፊት ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡  

   በዶ/ር መስከረም ለቺሳ የተደረሰውና ከሁለት ዓመት በፊት ለንባብ የበቃው “(ኢ) ዮቶፕያ” የተሰኘው መጽሐፍ ዛሬ ከቀኑ 10 ሰአት፣አምስት ኪሎ በሚገኘው ብሔራዊ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ይመረቃል፡፡ መጽሐፉ በባህል፣ በፍልስፍናና በሃይማኖት ዙሪያ የካበተ ልምድ ባላቸው አንጋፋ ሃያሲያን ተገምግሞም ለውይይት እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡  
መጽሃፉ፤ለእንግሊዝ መንግስታዊና ሃይማኖታዊ ተሃድሶ ምክንያት የሆነው የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ስርአተ መንግስትንና የህዝቧን አኗኗር የሚያሳይ ነው ተብሏል፡፡ የትርጉም ስራና የምርምር ማስታወሻዎችን ያካተተው መጽሐፉ፤በ348 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን ዋጋው 85 ብር ነው፡፡