Administrator

Administrator

የሰሜን ኮርያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፣ አሜሪካ በሰሜን ኮርያ ላይ ወታደራዊ እርምጃ ልወስድ እችላለሁ  በሚል በይፋ ማስጠንቀቋ፣ አገራቸውን ፍርሃት ውስጥ እንደማይከታትና የኒውክሌርና የሚሳየል ፕሮግራሞቿን ከማካሄድ እንደማይገታት ማስታወቃቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሬክስ ቲለርሰን ባለፈው አርብ በሰጡት መግለጫ፣ አገራቸው በሰሜን ኮርያ ላይ ጠበቅ ያለ ማዕቀብ እንደምትጥልና ወታደራዊ እርምጃ ልትወስድ እንደምትችል ማስጠንቀቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ የሰሜን ኮርያው ቃል አቀባይ በበኩላቸው ለአገራቸው የዜና ወኪል በኩል በሰጡት ምላሽ፣ አገራቸው በአሜሪካ ዛቻ እንደማትደናገጥ መግለጻቸውን አስታውቋል፡፡
የሰሜን ኮርያ ኒውክሌር አገሪቱንና ህዝቦቿን ከጥፋት የሚታደግ ሁነኛ መሳሪያ ነው ያሉት ቃል አቀባዩ፤ ሰሜን ኮርያ ከአሜሪካ ሊቃጣባት የሚችልን ወታደራዊ ጥቃት በብቃት ለመመከት በሚያስችል ሁኔታ ኒውክሌር የታጠቀች አገር መሆኗን መሪዎቿ ሊገነዘቡ ይገባል ማለታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
ከንግድ ወደ ፖለቲካ ፊታቸውን ያዞሩት የአሜሪካ ባለስልጣናት፣ ሰሜን ኮርያን በዛቻና በማስፈራሪያ ትሸማቀቃለች ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል፤ መሳሳታቸውንም በቅርቡ ይገነዘባሉ ሲሉም አክለዋል፡፡
ምንም አይነት የኒውክሌርም ሆነ የሚሳኤል ሙከራ እንዳታደርግ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ክልከላ የተደረገባትና በኒውክሌር ፕሮግራሟ ሳቢያ ከአሜሪካ ጋር ግጭት ውስጥ የገባቺው ሰሜን ኮርያ፤ ባለፈው የፈረንጆች አመት ብቻ ለሁለት ጊዚያት የኒውክሌር ሙከራ ፍንዳታዎችን፣ ለ24 ጊዚያት ያህል ደግሞ የባለስቲክ ሚሳኤል ሙከራዎችን ማድረጓን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ከሰሞኑ ይፋ የተደረገው የ2017 የአለማችን አገራት የደስተኛነት ደረጃ ሪፖርት፣ ኖርዌይን ከ155 የአለማችን አገራት በቀዳሚነት ሲያስቀምጥ፣ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ደግሞ በመጨረሻ ደረጃ ላይ ትገኛለች ማለቱን ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል፡፡ ስድስት ያህል የአገራትን ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ መመዘኛ መስፈርቶችን በመጠቀም በየአመቱ የአገራትን የደስተኛነት ደረጃ ይፋ የሚያደርገው ሰስቴኔብል ዲቨሎፕመንት ሶሊዩሽንስ ኔትወርክ የተባለው አለማቀፍ ተቋም፣ በ2017 ሪፖርቱ ዴንማርክን በሁለተኛ፣ አይስላንድን በሶስተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡
ስዊዘርላንድ፣ ፊላንድ፣ ኒዘርላንድስ፣ ካናዳ፣ ኒውዚላንድ፣ አውስትራሊያ እና ስዊድን ተከታዮቹን ደረጃዎች መያዛቸው የተነገረ ሲሆን፣ ዴንማርክ ለአራት አመታት የአለማችን ቁጥር አንድ ደስተኛ አገር ሆና መመዝገቧንም አስታውሷል፡፡
የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ዜጎች ጥናቱ ከተሰራባቸው 155 የአለማችን አገራት ህዝቦች ሁሉ በኑሯቸው የማይደሰቱ ህዝቦች ናቸው፤ አገሪቱም በአመቱ የአለማችን አገራት የደስተኛነት ዝርዝር ውስጥ የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች ያለው ሪፖርቱ፤ ብሩንዲና ታንዛኒያ እንደ ቅደም ተከተላቸው ከመጨረሻ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጣቸውን አመልክቷል፡፡
የአገር ውስጥ ጠቅላላ ምርትና የነፍስ ወከፍ ገቢ፣ አማካይ በህይወት የመኖር ጣራ፣ የህይወት ምርጫን የማድረግ ነጻነትና የመሳሰሉት ጉዳዮች የአገራቱን የደስተኛነት ደረጃ ለመገምገም በጥቅም ላይ ከዋሉ መስፈርቶች መካከል ይጠቀሳሉ ያለው ሪፖርቱ፤ ደስተኛነት ገንዘብ የመያዝና ያለመያዝ ጉዳይ አይደለም፤ ለዚህም አንዳንድ ሀብታም አገራት ዝቅ ያለ የደስተኝነት ደረጃ ይዘው መገኘታቸው ማረጋገጫ ነው ብሏል፡፡

 ድንገተኛ እሳት በሚፈጥረው ኖት 7 ምርቱ የከፋ ቀውስ ውስጥ ገብቶ የከረመው ሳምሰንግ ኩባንያ፣ አዲሱን ስማርት ፎን ምርቱን ጋላክሲ ኤስ 8ን በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ይፋ በማድረግ ለገበያ ያበቃል መባሉን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ሳምሰንግ ኩባንያ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረውንና ከዚህ ቀደም ለገበያ ከቀረቡት የጋላክሲ ስማርት ፎኖች የተለየ ይዞታና ገጽታ ይኖረዋል የተባለውን አዲሱን ምርቱን ጋላክሲ 8ን እስከ ሚያዝያ ወር መጨረሻ ለገበያ እንደሚያበቃ የሚጠቁሙ መረጃዎች መውጣታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ የመሸጫ ዋጋውም 799 ፓውንድ ይሆናል ተብሎ መገመቱን ገልጧል፡፡
ሳምሰንግ በጥቁር፣ በብርማ እና በሃምራዊ ቀለም እንደሚመረትና በካሜራ፣ በባትሪና በሌሎች ከዚህ ቀደም ከነበሩት ምርቶች የተለየ እንደሚሆን የተነገረለትን ይህን አዲስ የስማርት ፎን ምርቱን ለገበያ ለማብቃት ያቀደው ቀደም ብሎ ቢሆንም፣ በኖት 7 ምርቱ ሳቢያ የገባበት ቀውስ ዕቅዱን እንዲያራዝም እንዳስገደደው ዘገባው አስታውሷል፡፡
ኩባንያው ከጋላክሲ 8 በተጨማሪ ጋላክሲ 8 ፕላስ በሚል ስያሜ ያመረተውን አዲስ የስማርት ፎን ምርቱን ለገበያ ያበቃል መባሉን ያስታወቀው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ የጋላክሲ 8 ፕላስ የመሸጫ ዋጋ ደግሞ 899 ፓውንድ ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት አብራርቷል፡፡

 የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ በኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት የተዘጋጀው  “ኢዮሃ ፋሲካ” ኤክስፖ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ይከፈታል፡፡
ኤክስፖው ሻጭና ገዢን ከማገናኘት ባለፈ ለ22 ቀናት የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በወጣትና አንጋፋ ድምፃዊያን በማቅረብ የመዝናኛና የፌስቲቫል ድባብ እንዲኖረው መደረጉን የኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዩ አለሙ ገልፀዋል፡፡
ከ400 በላይ የውጭ፣ 8 የአገር ውስጥ የንግድ ድርጅቶች ይሳተፉበታል የተባለው ይሄው ኤክስፖ፤አራት እውቅ ባንዶች የሚሳተፉበትና ከ100 በላይ ታዋቂ ዘፋኞች የሚያቀነቅኑበት የሙዚቃ ኮንሰርት፣ በዝነኛ ዲጄዎች የሚቀርብ ሙዚቃ፣ ከ80 በላይ ወጣቶችን የሚያሳትፍ  ዘመናዊና ባህላዊ የዳንስ ውድድር እንደሚቀርብበት ተጠቁሟል፡፡  
የፋሲካ ኤክስፖውን በየቀኑ ከ30 ሺህ በላይ፣ በጠቅላላ ግማሽ ሚሊዮን ህዝብ ይጎበኘዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ዋና ሥራ አስኪያጁዋ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡  
 ኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት፤ በየቀኑ ወደ ኤክስፖው የሚመጡ ጎብኚዎች የሚገቡበትን ትኬት ቁጥር ለሽልማት ወደ 86 በአጭር መልዕክት በመላክ መኪና፣ ሞተር ሳይክልና ሌሎች ሽልማቶችን የሚያገኙበትን ዘመናዊ አሰራር ማመቻቸቱም ተነግሯል፡፡ የዚህን ዓመት የገና ኤክስፖ ጨምሮ ያለፈውን ዓመት የገናና የፋሲካ ኤክስፖዎች ያዘጋጀው ኢዮሃ፤ የዘንድሮን የፋሲካ ኤክስፖ ጨረታ በ13.6 ሚሊዮን ብር ማሸነፉ ታውቋል፡፡

ሩሲያ ካፈራቻቸው ታላላቅ የሥነ ጽሑፍ ሰዎች ውስጥ ገጣሚና ተርጓሚ የሆነችው ማሪና ኢቫኖቫ ስቬታየቫ አንደኛዋ ናት፡፡ ማሪና ኢቫኖቫ ሳይንስና የኪነ ጥበብ ዕውቀት ከአላቸው ቤተሰቦች ሞስኮ ውስጥ የተወለደቺው እ.ኤ.አ መስከረም 26 ቀን 1892 ዓ.ም ነው፡፡
ያረፈችው ደግሞ እ.ኤ.አ በ1941 ዓ.ም ላይ ነው። አባቷ ኢቫን ብላዲሚሮቪች ስቬታየብ የሞስኮ ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር፣ የታወቀ ፈላስፋ፣ ዲሬክተርና የኪነ ጥበብ ሙዚየም መሥራች (በአሁኑ ሰዓት በፑሽኪን ስም በሚጠራው ከተማ የሚገኘው ሙዚየም) ነበር፡፡
ወላጅ እናቷ እመት ማሪያ ኔ ሜንም የተለየ ዕውቀት የነበራትና የኮንሰርት ፒያኖ ተጫዋች ነበረች፡፡
ማሪና ሞስኮ ውስጥ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን የተማረቺው በግል ት/ቤት ነው። በልጅነቷ ቤተሰቧ የተለያየ ጉብኝት ለማድረግ ወደ ጀርመን፣ ስዊዘርላንድነሰ ወደ ሶርቦን ፓሪስ በሚሄድበት ወቅት አብራ በመሄድ ትምህርቷን ትከታተልና ቋንቋም ታጠና ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ1908 ደግሞ በራስዋ ፍላጎት ወደ ፈረንሳይ (ፓሪስ) ሄዳ ሶርቦን ውስጥ የጥንት ፈረንሳይኛ ሥነ ጽሑፍ ኮርስ መከታተል ጀመረች፡፡ በ16 ዓመቷ ግጥም መግጠም የጀመረቺው ስቤታየቫ፤ 18 ዓመት ሲሞላት ወደ ሩሲያ ተመልሳ የመጀመሪያዋ የሆነ የሥነ ግጥም ስብስብ መጽሐፍ ‹‹ የምሽት አልበም›› (EVENING ALBUM) በሚል ርዕስ አሳተመች። በኋላም ማለት እ.ኤ.አ በ1912፣በ1913፣በ1916 ዓ.ም የተጋጋለ ውስጣዊ ስሜቷንና የሩሲያን ነባራዊ ሁኔታ የሚያንፀባርቁ ሌሎች ሥራዎቿን ለህትት አበቃች፡፡ በተለይም “ከፍታ” የተሰኘው ግጥሟ ለሩሲያና ለሩሲያ ገጣሚዎች የተበረከተ ሲሆን ኩራትን፣ ጀግንነትን፣ የበለፀገ እውቀትንና ፍፃሜ የሌለው ስሜትን ያመለክታል፡፡
‹‹የምሽት አልበም›› የሚለው ግጥም ስለ ልጅነቷና ስለ ወጣትነቷ ዘመን ያትታል፡፡ ማስታወሻ አድርጋ ያበረከተችውም ለዚሁ ዘመኗ ነው፡፡
እ.ኤ.አ በ1912 ዓ.ም ማሪና ሰርጌይ ኢፎርን የተባለና የዛሩ መንግሥት ወታደር የነበረ ሰው አግብታ ሁለት ሴቶችንና አንድ ወንድ ልጅ ወልዳለች፡፡ የማሪና ሰቬተየቫ ሕይወት ከሩሲያ አብዮት ጋር የያያዘ ነበር፡፡ ባለቤቷ ኢፎርን ነጩ ጦር (the white guard) እየተባለ ከሚታወቀው የዛሩ መንግሥት ጦር ሰራዊት ጋር ተሰልፎ አብዮተኞችን/ ሶቭየቶችን ወይም ቦልሸቪኮችን/ ሲወጋ ነበር፡፡
ማሪና ‹‹ገርልፍሬንድ›› በሚለው ግጥሟ ተደንቃና ተመስጣ ገጣሚና የኦፔራ ቲአትር ባለሙያ ከሆነችው ከሶፍያ ፓሞክ ጋር ተዋወቀች። ምክንያቱም ሶፍያ ፓሞክ በወቅቱ በዚህ ግጥሟ ዝናን አትርፋ ነበር፡፡ ቀጥላም በዛሩ ዘመነ መንግሥት የቀይ ጦር ሽምቅ ታዋጊ ወታደር ከነበረና ኮንስታንቲን ፎዜቪች ከተባለ ገጣሚ ጋር ትውውቅ አደረገች፡፡ ኮንስታንቲን ‹‹የተራራ ግጥሞች›› እና ‹‹ የመጨረሻ ግጥሞች›› የተሰኙ ሥራዎች ስለነበሩት እነዚህን አንብባ አድናቆቷን ገለጸለችለት፡፡
እ.ኤ.አ በ1917 የኦክቶቨር ሪቮሉሽን ወቅት ተይዛ ለ5 ዓመት ታሥራለች፡፡ ከአብዮቱ ጋር በተያያዘ በተከታታዮቹ ዓመታት ድርቅና ረሀብ በሩሲያ በተከሰተበት ወቅት አንደኛዋ ሴት ልጇ በረሀብ ምክንያት ሞታበታለች፡፡
እ.ኤ.አ በ1922 ዓ.ም ማሪና ባለቤቷንና ቤተሰቧን ይዛ ወደ በርሊን፣ ከዚያም ወደ ፕራግ፣ ቀጥላ በ1925 ወደ ፓሪስ ተሰደደች፡፡ በፓሪስ የሩሲያ ማኅበረሰብ አባላት ጋርም መኖር ጀመረች። ነገር ግን አብዛኞቹ ስደተኞች የቀድሞው የዛር መንግሥት ወታደሮች ስለነበሩ የማሪና ባለቤት ሰርጌይ ኢፎርን የቦልሸቪኮች ሰላይ ሳይሆን አይቀርም ብለው ስለገመቱ እርሱን መፍራት ጀመሩ፡፡ በኋላም ነገሩ እውነት ሆኖ ተገኘ፡፡ ከጊዜ በኋላ ሰርጌይ ኢፎርን ወደ ሩሲያ ተመለሰ፡፡ ሞስኮ እንደደረሰም ታሥሮ ከቆየ በኋላ ተገደለ፡፡ ማሪና በስደት ዘመኗ ወጎችንና የትረካ ሥራዎችን ደርሳ ለማሳተም ችላለች፡፡ የአብዛኞቹ ግጥሞቿ ጭብጥ የሚነሳው ከአፈ-ታሪክና ከኅብረ ዝማሬ ሲሆን የአገጣጠም ስልቱ ደግሞ በታላቁ ሩሲያዊ ገጣሚ በአሌክሳንደር ብሎክና በታላቂቱ የኪነ ጥበብ ሰው በአና አህማቶቫ የአጻጻፍ ቴክኒክ የተቃኘ ነው፡፡ በሥራዎቿ ውስጥ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ሃይማኖትና ጸሎተኞች፣ የእምነት ዕሴቶች ከዘመናዊ አስተሳሰብ ጋር ተቃኝተው ይታያሉ፡፡
ማሪና ከብዙ ነገር ተገልላና ብቸኛ ሆኖ በስደት ብትቀመጥም የነፍስ ጥሪዋን ግን አልረሳችም። በከፍተኛ ስሜት ተነሳስታ ብዙ የጻፈችው በስደት ጊዜዋ ነው፡፡ ‹‹መለያየት››፣ ‹‹ንግድ››፣ ‹‹ሥነ ልቡና››፣ ‹‹ከሩሲያ በኋላ››፣ ‹‹ይድረስ ለልጄ››፣ ‹‹የአገር ናፍቆት››፣ ‹‹ቼቺያ›› /በወቅቱ ፖለቲካ ላይ የሚያተኩር ሥራ / የተባሉትን ሥራዎች ደርሳ ያሳተመቻቸው በስደት ዘመኗ ነው፡፡ ከማሪና ታላላቅ የግጥምና የልቦለድ ሥራዎች ውስጥ
በፖሪስ ውስጥ፣ ጸሎተኛው፣ ለእናቴ፣ ስብሰባ፣ ኒና ይቅርታ አድርጊልኝ … የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡
ማሪና እ.ኤ.አ ከ1939 ዓ.ም ጀምራ ወደ ሀገሯ በመመለስ ሞስኮ ውስጥ ለመኖር ብትፈልግም በፖለቲካ አመለካከቷ ምክንያት የሥነ ጽሑፍ አፍቃርያንና በማኅበረሰቡ ዘንድ የተገለለች ሆነች። ከዚህም የተነሣ እ.ኤ.አ በ1941 ዓ.ም ራስዋን አጥፍታለች፡፡
ታላቁ ገጣሚ ቦሪስ ፖስተርናህ አሟሟቷን አስመልክቶ ሲናገር፡-
‹‹ማሪናን ቀደም ብሎ የሥነ ጽሑፍ ቢሮክራቶች ልበቢስ በሆነ መንገድ ባይቀርቧት ኖር ራስዋን አታጠፋም ነበር›› ብሏል፡፡
የጽሑፍ ሥራዎቿ የሰላ አእምሮ፣ በጥልቀት የሚያይ ዐይንና አስተዋይ ልቡና የነበራት ታላቅ ሴት የነበረች መሆኗን አስመስክረዋል፡፡
በ20ኛው ክፍለ ዘመን በወጥነት ከቀረቡት የግጥም ሥራዎች ውስጥ የማሪና ስቤታየቫ በዋነኛነት ይጠቀሳል፡፡ የእርስዋ የሥነ ግጥም ምንጭ የፈለቀው ተቃርኖ ከበዛበት የግል ሕይወቷ ነው፡፡ የቋንቋ አጠቃቀሟ የተመጠነ፣ በጥቂት ቃላት ብዙ የምትናገርነ ገጣሚ ናት፡፡ በጭብጥ ረገድ ካነሳቻቸው በርካታ ርእሰ ጉዳዮች ውስጥ የሚበዛው ሴታዊነት፣ ወሲብ፣ የሴቶች ግላዊ ሕይወትና በማኅበራዊ ኑሮ ስለአላቸው ሚና ነው፡፡
ለማሪና ስቬታየቫ በአሁኑ ሰዓት የሩሲያ መንግሥት በመኖሪያዋ አካባቢ በሚገኘውና ቦሪስግሌቭስኪ ተብሎ በሚጠራው ሠፈር ሐውልት አቁሞላታል፡፡

Monday, 27 March 2017 00:00

አንብባችሁ እንድትስቁ!!

  አባት ሰዎች ሲዋሹ በጥፊ የሚማታ ውሸት የሚለይ ሮቦት ይገዛል፡፡
አንድ ማታ እራት ላይም ሮቦቱን ሊሞክረው ይወስናል፡፡.
አባት ልጁ ከሰዓት በኋላ ምን ሲሰራ እንደነበር ይጠይቀዋል፡፡
ልጅም “የቤት ሥራ ስሰራ ነበር” ይላል፡፡
ሮቦቱ ልጁን ጥፊ ያቀምሰዋል፡፡
ዋሽቷል ማለት ነው፡፡
“እሺ--እሺ--ጓደኛዬ ቤት ፊልም ስመለከት ነበር” ብሎ ንግግሩን ያርማል፡፡
“ምን ዓይነት ፊልም ነው ስትመለከቱ የነበረው?” አባት ይጠይቃል፡፡
ልጅም፡- “የካርቱን ፊልም”
ሮቦቱ ልጁን በጥፊ ይመታዋል፡፡
“በቃ የወሲብ ፊልም ነው” ይላል ልጅ፡፡
አባትም፡- “ምን አልክ?
እኔ እኮ ባንተ ዕድሜ ወሲብ ምን እንደሆነ እንኳን አላውቅም”
ሮቦት ቀልድ አያውቅም፤ አባትየውን በጥፊ፡፡
እናት ሳቀችና፡- “የአባቱ ልጅ! በራስህ ነው የወጣው” አለች፤ ሳይቸግራት፡፡
ሮቦቱ እናትየውንም በጥፊ አቀመሳት፡፡
ወዲያው ሮቦቱ እንዲሸጥ ተፈረደበት፡፡
***
አንድ ቀን ፈጣሪ ወደ አዳም ዘንድ ብቅ ብሎ፤
“ጥቂት መልካም ዜናና ጥቂት መጥፎ ዜና ልነግርህ ነው የመጣሁት” ይለዋል፡፡
አዳምም ፈጣሪውን ትክ ብሎ ተመለከተና፤ “እንግዲያውስ መልካሙን ዜና አስቀድምልኝ” አለው፡፡
ፈጣሪም ፈገግ አለና ጉዳዩን ማብራራት ጀመረ፡-
“ሁለት አዳዲስ የአካል ክፍሎችን (ኦርጋን) ይዤህልህ መጥቼአለሁ፡፡
 አንደኛው አዕምሮ ይባላል፡፡
በጣም ብልህ እንድትሆን ያደርግሃል፤ አዳዲስ ነገሮችን ለመፍጠርና ከሄዋን ጋርም በአስተውሎት እንድታወጋ ይረዳሃል፡፡
ሌላኛው ያመጣሁልህ የአካል ክፍል ደግሞ ብልት ይባላል፡፡
እንደ ራስህ ብልህ የሆነ አዲስ ህይወት ለመፍጠርና እቺን ፕላኔት በዘርህ ለመሙላት ያስችልሃል፡፡
ለሄዋንም ልጆች ስለምታፈራላት ደስታዋ ይጨምራል፡፡”
አዳምም በደስታ ተጥለቅልቆ የሚሰራው የሚያደርገው ጠፋው፡፡
“በጣም ድንቅ ስጦታዎችን ነው ያበረከትክልኝ፤ ከዚህ ዕጹብ ድንቅ ገጸ በረከት በኋላ ምን ዓይነት መጥፎ ዜና ልትነግረኝ እንደምትችል አይቼ?” አለው ፈጣሪን፡፡
ፈጣሪም፤ “መጥፎው ዜና ምን መሰለህ፣ ስፈጥርህ የሰጠሁህ የደም መጠን እነዚህን ሁለት አካላት (ኦርጋንስ) በአንድ ጊዜ ማሰራት የሚችል አይደለም፤ተራ በተራ እንጂ” አለው በሃዘን ስሜት ተውጦ፡፡
(አንዱ ኦርጋን ሲሰራ አንዱ ሥራ ያቆማል)
*   *   *
ቀኑን ሙሉ የቢራ አምራቾች ጉባኤ ሲካሄድ ይውላል፡፡
ጉባኤው ሲጠናቀቅ የሁሉም ኩባንያዎች ፕሬዚዳንቶች ወደ አንድ መጠጥ ቤት ጎራ ብለው ቢራ ለመጎንጨት ይስማማሉ፡፡
የበድዋይዘር ቢራ ፕሬዚዳንት በድዋይዘር ያዝዛል፡፡ የሚለር ቢራ ፕሬዚዳንትም ሚለር ያዝዛል።
የኩርስ ቢራ ፕሬዚዳንት እንዲሁ ኩርስ ቢራ ያዝዛል፡፡
በመጨረሻም አስተናጋጇ የጊነስ ቢራ ባለቤትና ፕሬዚዳንት የሆነውን አርተር ጊነስን ምን እንደሚጠጣ ትጠይቀዋለች፡፡ ሚስተር ጊነስም፤ “ኮካኮላ” በማለት ሁሉንም አስገረማቸው፡፡
“ጊነስ ቢራ ለምን አላዘዝክም?” ሲሉ ጠየቁት ባልደረቦቹ፡፡
እሱም፡- “እናንተ ቢራ ካልጠጣችሁ እኔም አልጠጣም” ሲል መለሰላቸው፡፡
(ቀላል ነገራቸው!)
*   *   *
አንድ አዲስ አስተማሪ ወደ ክፍል እየገባች ሳለ፣በሳይኮሎጂ ኮርስ የተማረችውን በጥቅም ላይ ለማዋል አሰበች፡፡
እናም የዕለቱን የትምህርት ክፍለ ጊዜ እንዲህ በማለት ጀመረች፡-
“በዚህ ክፍል ውስጥ ደደብ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሁሉ ተነስቶ ይቁም”
ከጥቂት ሰከንዶች በኋላ ህጻኑ ጆኒ ተነስቶ ይቆማል፡፡
አስተማሪዋም፡- “ጆኒ፤ ደደብ ነኝ ብለህ ታስባለህ?; ጠየቀችው፡፡
“በጭራሽ፤ እርስዎ ብቻዎን መቆምዎ አናዶኝ ነው”
*   *   *
ችግሩ ያለው ማ ጋ ነው?
ሰውየው ሃኪሙ ዘንድ ይሄድና፡-
“የሚስቴ የመስማት አቅም የደከመ ይመስለኛል፤ እንደ ድሮው አይደለም፤ ምን ባደርግ ይሻለኛል?” ሲል ምክር ይጠይቀዋል፡፡
ሃኪሙም፡- “እርግጠኛ ለመሆን ይህን ሞክር፤ ሚስትህ ወጥ ቤት ሆና ምግብ ስታሰናዳ ከኋላዋ 15 ጫማ ርቀት ላይ ሆነህ የሆነ ነገር ጠይቃት፡፡ መልስ ካልሰጠችህ እየቀረብካት መልስ እስክትሰጥህ ድረስ መጠየቅህን ቀጥል” አለው፡፡
ሰውየው ወደ ቤቱ ተመለሰና ሚስቱ እራት ማዘጋጀት ስትጀምር የተባለውን ይሞክር ገባ፡፡
ከኋላዋ 15 ጫማ ርቀት ላይ ቆሞ፤ “ማሬ፤ ዛሬ እራታችን ምንድን ነው?” ሲል ጠየቃት፡፡ ነገር ግን ከሷ ምላሽ አላገኘም፡፡ 10 ጫማ ተጠግቶ በድጋሚ ሚስቱን ጠየቃት፡፡
አሁንም መልስ የለም፡፡
5 ጫማ ቀረበና ጥያቄውን አቀረበ፡፡
ግን ምላሽ አላገኘም፡፡
በመጨረሻ ከኋላዋ ቆሞ፤
“ማሬ÷ዛሬ እራታችን ምንድን ነው?” አላት፡፡
ሚስትም ፡-
“ለአራተኛ  ጊዜ   እነግርሃለሁ፤  
ዶሮ ነው!” አለችው፡፡
ችግሩ ያለው ማ ጋ ነው ? ከእሱ ወይስ ከእሷ?
*   *   *
አንዲት በመካከለኛ ዕድሜዋ ላይ የምትገኝ ሴት በድንገተኛ የልብ ህመም ራሷን ስታ ሆስፒታል ትገባለች፡፡
የቀዶ ህክምና እየተደረገላት ሳለም ነፍሷ ከስጋዋ ተለይታ ሰማይ ቤት ትሄዳለች፡፡
እዚያም እግዚአብሄርን ታገኘውና፤ “ቀኔ ደርሷል እንዴ?” ስትል ትጠይቀዋለች፡፡
እግዚአብሄርም፡- “አልደረሰም ገና 40 ዓመት ከ4 ወር ይቀርሻል” ይላታል፡፡
ከህመሟ ስታገግም ታዲያ እዚያው ለመቆየት ትወስንና የፕላስቲክ ቀዶ ህክምና እንዲሰራላት ትጠይቃለች፡፡
ብዙ ዕድሜ ስለሚቀራት ዓለሟን ልታይ ተመኝታለች፡፡
እናም ፊቷን አስቀየረች፣ ቦርጯን አስቀነሰች፣ ዳሌዋን ማራኪ እንዲሆን አድርጋ አሰራች፡፡
የጸጉሯንም ቀለም አስቀየረች፡፡
የማታ ማታም አንድ ፍሬ ኮረዳ መስላ ቁጭ አለች፡፡
የምትሻውን መልክና ገጽታ ከተጎናጸፈች በኋላ በደስታ ተጥለቅልቃ ከሆስፒታሉ ወጣች፡፡
ነገር ግን ወደ ቤቷ እየሄደች ሳለ መንገድ ስትሻገር አምቡላንስ ገጭቷት ትሞታለች፡፡
ለሁለተኛ ጊዜ ከእግዚአብሄር ጋር ስትገናኝም፡-
“ሌላ 40 ዓመት ይቀርሻል ብለኸኝ አልነበር፤ ለምን ከአምቡላንሱ አደጋ አላተረፍከኝም?” ስትል ተቆጥታ ጠየቀችው፡፡
እግዚአብሄርም መለሰላት፡-
“አዝናለሁ፤ አንቺ መሆንሽን አላወቅሁም ነበር”
*   *   *
ሰውየው የቅርብ ጓደኛው ሚስት ሞታ ሊያስተዛዝነው ወደ ቤቱ ይሄዳል፡፡
በሩን ቢቆረቁር ግን የሚከፍትለት ያጣል፡፡ ምን ተፈጠረ በሚል ስጋት በሩን ገፋ አድርጎ ይገባል፡፡
ጓደኛውን ያገኘው ግን ከሌላ ሴት ጋር ሲሳሳም ነበር፡፡
“ጃክ” አለ ሰውየው በመገረም ተሞልቶ÷ “ሚስትህ እኮ ከሞተች ገና 24 ሰዓት አልሞላትም”
ጓደኝየው ቀና ብሎ ተመለከተውና፤ “በዚህ ሃዘን ውስጥ ሆኜ የምሰራውን የማውቅ ይመስልሃል?” አለው፡፡
*   *   *
ባል፡- ሎተሪ ቢደርሰኝ ምን ታደርጊያለሽ?
ሚስት፡- ግማሹን ወስጄ የራሴን ህይወት ለብቻዬ እጀምራለሁ
ባል፡- ይኸውልሽ 100 ዶላር ደርሶኛል፤እባክሽን 50 ዶላርሽን ውሰጂና አሁኑኑ ሂጂልኝ!
*   *   *
የሰላዮች ፈተና -----
የጀርመን፣ የጣሊያንና የሩሲያ ሰላዮች በሥራ ላይ ሳሉ በቁጥጥር ስር ይውሉና ምርመራ ይደረግባቸዋል፡፡
የታሰሩት መስኮት በሌለው ጠባብ ወህኒ ቤት ውስጥ ሲሆን ምግብ የሚሰጣቸው ነፍሳቸውን ለማቆየት ያህል ብቻ ነበር፡፡
መጀመሪያ ለምርመራ የተጠራው የጀርመኑ ሰላይ ነው፡፡
እጆቹ ታስረውና ወንበር ላይ ተቀምጦ ነበር የተመረመረው፡፡
ለሁለት ሰዓት ያህል ድብደባና ስቃዩን ችሎ ለማን እንደሚሰራ ሳይናገር ከቆየ በኋላ የማታ ማታ ተረታ፡፡
ወደ እስር ክፍሉ ሲመለስ ግን ሌሎቹ ሰላዮች ይሄን ያህል ሰዓት መከራውን ችሎ በመቆየቱ አደነቁት፡፡
በመቀጠል የሄደው የሩሲያው ሰላይ ነበር፡፡ እሱ ደግሞ ለ12 ሰዓታት ከፍተኛ ድብደባና ስቃይ ከደረሰበት በኋላ ለማን እንደሚሰራ ተናገረ፡፡ ወደ እስር ክፍሉ ሲመለስም ለዚያ ሁሉ ሰዓታት በጽናት በመቆየቱ ሌሎቹ ሰላዮች በእጅጉ ተደመሙበት፡፡
በመጨረሻም ጣሊያናዊው ሰላይ ወደ ምርመራ ክፍሉ ተላከ፡፡ እጁን ታስሮ ለ4 ቀናት እየተደበደበ ቢሰቃይም ለማን እንደሚሰራ ትንፍሽ ሳይል ወደ እስር ክፍሉ ተመለሰ፡፡ ሌሎቹ ሰላዮች እንዴት ለ4 ቀናት ሳይናገር መቆየት እንደቻለ ጠየቁት፡፡
እሱም፤ “ለመናገር እኮ ሞክሬ ነበር፤ነገር ግን እጆቼን ማንቀሳቀስ አልቻልኩም; አላቸው፡፡
(ጣልያን እጆቹን ካላንቀሳቀሰ ማውራት አይችልም ይባል የለ!)
*   *   *
አባት፡-እኔ የመረጥኩልህን ሴት እንድታገባ እፈልጋለሁ
ልጅ፡- አላደርገውም!
አባት፡- የቢል ጌትስ ልጅ እኮ ናት
ልጅ፡- እንደሱ ከሆነ እሺ
አባት ወደ ቢል ጌትስ ዘንድ ይሄዳሉ፡፡
.አባት፡- ልጅህ ልጄን እንድታገባው እፈልጋለሁ
ቢል ጌትስ፡- ፈጽሞ አይሆንም!
አባት፡- ልጄ እኮ የዓለም ባንክ ዋና ሃላፊ ነው
ቢል ጌትስ፡- እንዲያ ከሆነ እሺ
አባት የዓለም ባንኩ ፕሬዚዳንት ዘንድ ይሄዳሉ፡፡
አባት፡- ልጄን የባንኩ ዋና ሃላፊ አድርገህ ሹምልኝ
ፕሬዚዳንቱ፡- የማይሞከረውን!
አባት፡- ልጄ እኮ ያገባው የቢል ጌትስን ልጅ ነው
ፕሬዚዳንት፡- እንደሱ ከሆነ ይቻላል!
ይሄ ነው እንግዲህ ቢዝነስ ማለት!
*   *   *
አንድ ሩሲያዊ አሜሪካ ኤርፖርት ውስጥ ከቀረጥ ነጻ (duty free shop) መደብር ጎራ ይላል፡፡
የመደብሩን አስተናጋጅም፤ “የሩሲያ ቋንቋ ትችያለሽ?” ሲል ይጠይቃታል፡፡
“አዎ፤ ትንሽ ትንሽ እችላለሁ” መለሰችለት፡፡
ሩሲያዊው “እፎይ” አለና “ማርልቦሮ” አላት፡፡
(ለዚሁ ነው በሬዬን ያረድኩት አለ አበሻ!)
*   *   *
በሩሲያ የት/ቤት ክፍል ውስጥ ነው አሉ፡፡
አስተማሪ፡- ጎበዝ ልጆች ያሉት የት ነው?
ተማሪዎች፡- በሩሲያ!
አስተማሪ፡- ጣፋጭ ከረሜላዎች የት ነው የሚመረቱት?
ተማሪዎች፡- በሩሲያ!
አስተማሪ፡- ምርጥ ከተሞች የት ነው ያሉት?
ተማሪዎች፡- በሩሲያ!
ድንገት በክፍሉ ውስጥ ካሉት ተማሪዎች ትንሷ ናድያ ማልቀስ ጀመረች፡፡
አስተማሪው፡- ናድያ፤ ለምንድን ነው የምታለቅሺው?
ናድያ፡- ሩሲያ የምትባለው አገር መኖር እፈልጋለሁ!
(እኔም ሁሌ የኢቢሲ ጦቢያ ትናፍቀኛለች!)
*   *   *
ወህኒ ቤት ወይስ ት/ቤት?
ቻይና ውስጥ ነው አሉ፡፡ የሆነ ፕሮጀክት ተሰርቶ ከተጠናቀቀ በኋላ በዛ ያለ ገንዘብ ይተርፋል፡፡ የአካባቢው ቋሚ ኮሚቴ ተሰብስቦ የተረፈው ገንዘብ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤትን ለማደስ ይዋል ወይስ ወህኒ ቤት ይታደስበት በሚለው ላይ ይወያያል፡፡ ነገር ግን ወደ አንድ ውሳኔ ለመምጣት አልተቻለም፡፡
በመጨረሻ ግን አንድ በቋሚ ኮሚቴው ውስጥ ለረዥም ጊዜ በአባልነት የቆዩ ሰው ሁሉንም ያስገረመ አስተያየት ሰነዘሩ፡- “በዚህ ዕድሜያችን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት የመከታተል ዕድል እናገኛለን እንዴ?”
ለአፍታ ዝምታ ነገሰ፡፡
ከፊሉ ሻይ መጠጣት፣ ከፊሉ ደግሞ ከቅንድቡ ላይ ላቡን መጠራረግ ያዘ፡፡ ከዚያም ሁሉም አባላት “ወህኒ ቤት ይታደስበት” በሚለው ተስማሙ፡፡
(ከዕለታት አንድ ቀን ሁሉም ወህኒ ቤት መግባታቸው አይቀርማ!)
*   *   *
ብላክሜይል!
ትንሹ ሳሚ ለገና ቢስክሌት እንዲገዛለት ለእናቱ ጥያቄ ያቀርባል፡፡ እናቱም ለአባ ገና ደብዳቤ ቢጽፍላቸው እንደሚሻል ትነግረዋለች፡፡ ሳሚ ግን ደብዳቤውን ለህጻኑ ኢየሱስ ብጽፍ እመርጣለሁ አለ፡፡
እናቱም በዚሁ ሃሳብ ተስማማች፡፡
ሳሚ ወደ ክፍሉ በመግባትም እንዲህ ሲል
ጻፈ፡- “ውድ ኢየሱስ፤ በጣም ጥሩ ልጅ ስለሆንኩ ለገና ቢስክሌት እፈልጋለሁ፡፡”
ሆኖም የጻፈውን ደግሞ ሲያነበው ብዙም ሳያስደስተው ቀረ፡፡ ስለዚህም እንደገና ለመጻፍ ሞከረ፡- “ውድ ኢየሱስ፤ አብዛኛውን ጊዜ ጥሩ ልጅ ነኝ፤ እናም ለገና ቢስክሌት እፈልጋለሁ፡፡”
አሁንም ግን ሲያነበው አላስደሰተውም፡፡
ለሦስተኛ ጊዜ ለመጻፍ ሙከራ
አደረገ፡- “ውድ ኢየሱስ፤ አዲስ ቢስክሌት ካገኘሁ ጥሩ ልጅ ለመሆን እሞክራለሁ”
ይሄኛውም የልቡን አላደረሰለትም፡፡
በመጨረሻ የተሻለ ሃሳብ ለማመንጨት በማሰብ፣ ከቤቱ ወጥቶ በእግሩ መጓዝ ይጀምራል፡፡ ጥቂት እንደተጓዘም አንድ መኖሪያ ቤት በረንዳ ላይ በነሀስ የተሰራ ትንሽዬ የድንግል ማርያም ምስል (ቅርጽ) ተሰቅሎ ይመለከታል፡፡ አንድ ሃሳብ ከመቅጽበት ብልጭ አለለት፡፡ ሳሚ በቀጥታ ወደ ቤቱ ያመራና የማርያምን ምስል ከተሰቀለበት አውርዶ ኮቱ ውስጥ በመሸሸግ በጥድፊያ ወደ ቤቱ ያመራል፡፡ እክፍሉ ውስጥ ገብቶም አልጋው ስር ይደብቀዋል፡፡
ከዚያም የሚከተለውን ደብዳቤ ጻፈ፡- ”“ውድ ኢየሱስ፤ እናትህን ዳግም ማየት የምትፈልግ ከሆነ አዲስ ቢስክሌት ላክልኝ”
*   *   *
ቀናተኛዋ ሚስት!
ሚስት በሥራ ላይ ለሚገኘው ባሏ ስልክ ለመደወል ትሞክርና ሞባይሏ ሂሳብ እንደሌለው ትረዳለች፡፡
ወዲያው ትንሹ ልጃቸው በራሱ ሞባይል አባቱ ጋ ደውሎ የፈለገችውን አስቸኳይ መልዕክት እንዲያደርስ ታዘዋለች፡
ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ልጅ ለእናቱ እንዲህ ይላታል፤ “ሶስት ጊዜ ደውዬ ሴት ነው ያነሳችው”
ሚስት ባሏ እስኪመጣ መታገስ አቅቷት በንዴት ስትንቆራጠጥ ትቆይና የመኪናውን ድምጽ ስትሰማ ከቤት ዘላ ትወጣለች፡፡ ከመኪናው ሲወርድ ጠብቃም ምንም ሳትናገር ጥፊ ታቀምሰዋለች፡፡
ባል ተደናግጦ ምክንያቱን ሊጠይቃት ሲል ሌላ ጥፊ ትደግመዋለች፡፡
በዚህም ጠብ ይነሳና ጎረቤት ይሰባሰባል፡፡
ይሄኔ ወደ ልጇ ዞር ትልና አባቱ ጋ ሲደውል ያነሳችው ሴትዮ ምን እንዳለችው ለተሰበሰበው ሰው እንዲናገር ትጠይቀዋለች፡-
ልጁም እንዲህ አለ፡-
“የደወሉላቸው ደንበኛ ከአገልግሎት ጥሪ ውጭ ስለሆኑ እባክዎ ትንሽ ቆይተው ይሞክሩ”
(ሚስት እንዴት ታፍር!

Saturday, 25 March 2017 12:42

“የቡና ቤት ሥዕሎችና …”

 አንድ ቡና ቤት ውስጥ ግድግዳው ላይ የተሣለ ነው፡፡ ሰውዬው በአንበሳው ላይ ይነጣጥራል። በሰውዬውና በአንበሳው መካከል ጅረት አለ። አዳኙን እግሩ ቀጥ እንዳለ ስታዩት ሣሩ ላይ ተኝቷል ብላችሁ ታስባላችሁ፡፡ ነገር ግን መሆን አለበት ብላችሁ ስለምትገምቱ ነው እንጂ ሥዕሉ ላይ የሚታየው በሣሩ ላይ ሲንሳፈፍ ነው፡፡
እሺ ብሎ አይዞርላችሁም እንጂ ግድግዳውን ዞር ብታደርጉት ደግሞ ቆሞ እሚተኩስ ይመስላችኋል። አንበሳው በተዝናና ሁኔታ ሰውዬውን ትኩር ብሎ ያየዋል። አስተያየቱን ለመግለጽ ያስቸግራል፡፡ ብቻ፣ ‹‹እውነት አሁን ልትተኩስ ነው እስቲ ወንድ!›› የሚል ይመስላል፡፡
የሥዕሉ ምጣኔ ነገር አይወራም፡፡ የፊት እግሮቹ እኩል አይደሉም፡፡ አንዱ ወፍራም አንዱ ቀጭን ነው፡፡ የጅራቱን ማጠር ስታዩ፣ ሥዕሉ ሲሣል ግድግድጋው ጠባብ ነበር እንዴ ማለታችሁ አይቀርም፡፡ የወገቡም ቅጥነት፣ ‹‹ሽንጧ ስምንት ቁጥር›› የሚለውን ዘፈን ያስታውሳችኋል፡፡ የቅርበት-ርቀቱ ሚዛን እንዳልተጠበቀ በግልጽ ይታያል። ለምሳሌ ጠመንጃው ከሰውዬው በልጦ ጅረቱን አቋርጦ አንበሳው አፍንጫ ሊደርስ ትንሽ ቀርቶታል። ከወዲያ ማዶ ያለው ጋራ ደግሞ አንበሳው ጀርባ ላይ ያረፈ ይመስላል፡፡ ከሁሉም ይልቅ የሚገርመው አውሬው ጥቂት እንኳ እንደ መዝለል ወይም እንደ መሸሽ ሳይል በኩራት ዝም ብሎ አዳኙን ማስተዋሉ ነው፡፡ ይኸን ሥዕል ሳይ የአንዳንድ አርበኞች ሥዕል ትዝ አለኝ፡፡
ወረቀቱ ስለማይበቃ ነው እንዳይሉን እንጂ የአርበኛው ጠመንጃ የጣልያኑን ዓይን እየወጋ፣ ‹‹ደጃች እገሌ ጠላት ላይ ሲያነጣጥሩ›› የሚል ከሥሩ እየተለጠፈበት፣ እንደ እንቁጣጣሽ አበባ እየዞረ ሲሸጥ፣ የእነ አብየ ገብረ መንፈንስ ቅዱስ፣ የቅዱሳን፣ የሰማዕታት፣ ያ ያ ሁሉ ታየኝ፡፡›› ታዲያ አሁን እዚህ ለምናነሣቸው መሰረቱ እነሱ ይመስሉኛል፡፡ ጥንት ከምዕተ ዓመታት በፊት የተሣሉትን ግን ለጥናት ሊጠቅሙ ስለሚችሉ ለታሪክና ቅርስ ተመራማሪዎች ቢተው ጥሩ ነው፡፡
ሌላው ያየሁት የፋሲል ግንብ ነው፡፡ ይኸ ሥዕል በብዛት በየቦታው ይታያል፡፡ አሣሣሉ አንድ ይምሰል እንጂ አጠቃላይ መልኩ የተለያየ ነው። አጥር ያለው፣ አጥር የሌለው፣ ዛፍ ያለው ዛፍ የሌለው፣ በጽጌረዳና በሀረግ ያጌጠ፣ በለምለም ሣር ያሸበረቀ፡፡ የአንዳንዱ ጥላ አጣጣል ፍጹም ቅጥ ያጣ ከመሆኑ የተነሣ ፀሐይዋ ሁለት የሆነች ሊመስላችሁ ይችላል፡፡ አንዳንዱ ከበረንዳው በታች ዘንባባ፣ ባሕር ዛፍ፣ ጥድ፣ በያይነቱ በሰልፍ ይተከልበታል፡፡ ምን ያህል እውነት እንደሆነ አላውቅም እንጂ ፓፓያ የተሣለበትም አለ ሲባል ሰምቻለሁ፡፡
የግንቡ የአካባቢ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን፣ ቀለሙም ብዙ ዓይነት ነው፡፡ ቢጫ፣ ሰማያዊ፣ ሮዝ፡፡ የአራት መቶ ዓመት ህንፃ በፒያሳ ቀለም መታደሱ እንኳን አይከፋም፡፡ እኔን በጣም ያስገረመኝ ግን፣ ከግንቡ ፊት ለፊት፣ ከቤተ መንግሥቱ ፊት ለፊት አንዲት ሹርባ የተሠራች የሀገር ልብስ የለበሰች ውብ ወይዘሮ፤ ጃንጥላዋን ከፍ አርጋ ይዛ ገበያ አዳራሽ እምትሄድ ይመስል በቄንጥ ስትራመድ የሚያሳየው ሥዕል ነው፡፡ እስቲ ሴትየዋ እዚያ ምን ታደርጋለች? ላልጠፋ ግድግዳ … ለብቻዋ መሳልስ ይቻል የለም!
በተለይ የፋሲል ግንብን፣ የአክሱም ሐውልትን፣ ጢስ ዐባይን፣ ላሊበላን የሚሥሉ ሰዎች፣ ባዶ ቦታ ለምን ባዶውን ይቅር እያሉ ነው መሰለኝ፤ ደስ ያላቸውን ነገር ይጨምራሉ፡፡ ባዶ ቦታ ማስፈለግ አለማስፈለጉን ሳያስተውሉ፡፡ ለምሳሌ፣ ወፎችፐ ከሩቅ እየበረሩ ሲመጡ እንዲያውም ሰማይ ካለ ወፎች በግድ ይኖራሉ፡፡ ወንዝ ወይም ኩሬ ከተነሳ ዳክዬዎች ሲዋኙ መታየት አለባቸው፡፡ ዛፍ ደግሞ ጦጣ ከሌለችበት ዛፍ ሊሆን አይችልም። ሣሩም ሁልጊዜ አረንጓዴ ነው፡፡ ምናልባት ለዚህ የሚገፋፋቸው የኢትዮጵያ ልምላሜ ይሆን? በአጠቃላይ የቡና ቤት ሠዓሊያዎች ትልቅ ድክመት ዝምድና ወይም ግንኙነት የሌላቸውን ነገሮች ጎን ለጎን ማስቀመጣቸው ነው፡፡ ማን ያውቃል፣. ከፍ ብሎ የተጠቀሰችዋ ሴትዮ ሲገርመን፣ ላሊበላ ቤተክርስቲያን ላይ ጂንስና ቢትልስ ለብሶ ኳስ የሚያነጥር ልጅ እንድ ቀን እናይ ይሆናል፡፡
(ከደራሲ መስፍን ሀብተማርያም
“የቡና ቤት ሥዕሎች እና ሌሎችም ወጎች”
መፅሃፍ ላይ የተቀነጨበ)

Saturday, 25 March 2017 12:38

የክብር ዶክትሬት ጥያቄ?!

  አንድ ባለጸጋ በአካባቢያቸው ወደሚገኝ አንድ ኮሌጅ ጎራ ይሉና ለተቋሙ 1ሚ.ብር ለመለገስ እንደሚሹ ይናገራሉ፡፡ “ነገር ግን በአንድ ቅድመ-ሁኔታ ነው÷ ይኸውም የክብር ዶክትሬት የሚሰጠኝ ከሆነ ነው” ይላሉ፡፡
የኮሌጁ ፕሬዚዳንትም፤ “ታዲያ ምን ችግር አለ፤ ይሰጥዎታላ” ይላቸዋል፡፡
 “የክብር ዶክትሬቱ ግን ለአህያዬ ነው” አሉ፤ ባለጸጋው፡፡
ፕሬዚዳንቱ በድንጋጤና በአግራሞት መሃል ሆኖ፤ “ለአህያዬ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
ባለጸጋውም፤ “አዎ--- አህያዬ ለብዙ ዓመታት እኔን ተሸክማ ከቦታ ቦታ በመውሰድ ከባድ ውለታ አድርጋልኛለች፡፡ ለዚህም የትራንስፖርት የክብር ዶክትሬት እንዲሰጣት እሻለሁ; በማለት ኮስተር ብለው አስረዱ፡፡
“ግን እኮ---- ኮሌጃችን ለአህያ የክብር ዶክትሬት ሰጥቶ አያውቅም” አለ ፕሬዚዳንቱ፡፡
“እንግዲያውስ ገንዘቡን ለሌላ ተቋም እለግሰዋለሁ” አሉና ከመቀመጫቸው ተነሱ-ባለሃብቱ፡፡
ዓይኔ እያየ 1ሚ.ብር ሊያመልጠኝ ነው ብሎ ያሰበው ፕሬዚዳንት፤ “ቆይ እስቲ ከኮሌጁ ቦርድ ጋር ልማከርበት” ሲል ጥቂት ጊዜ እንዲሰጡት ይጠይቃል፡፡
ባለጸጋው፤ “በል በቶሎ አሳውቀኝ” ብለውት ይሄዳሉ፡፡
(በልባቸው “ብትማከር ነው የሚሻልህ” ሳይሉት አይቀሩም!)
ፕሬዚዳንቱ፤ ወዲያው የኮሌጁን ቦርድ አስቸኳይ ስብሰባ ይጠራና በጉዳዩ ላይ ውይይት ይጀምራሉ፡፡ ብዙዎቹ አባላት የገንዘቡ መጠን የፈለገውን ያህል ብዙ ቢሆን፣ ለአህያ የክብር ዶክትሬት አንሰጥም ብለው ተፈጠሙ፡፡
አንድ በኮሌጁ ለረዥም ዓመታት ያገለገሉ ብልህ አዛውንት ግን ለፕሬዚዳንቱ የተለየ ሃሳብ አቀረቡ፡፡
“ገንዘቡን ተቀበልና ለአህያዋ የክብር ዶክትሬቱን ስጥ ባክህ; አሉት፡፡
ፕሬዚዳንቱም ደንገጥ ብሎ፤ “ይሄን ማድረግ ለኮሌጃችን ውርደት አይሆንም?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
“በፍጹም አይሆንም; አሉ አዛውንቱ፤ “እንደውም ክብር ነው፤ ለምሉዕ አህያ የክብር ዶክትሬት ስንሰጥ በኮሌጁ ታሪክ የመጀመሪያችን ይሆናል!!”
(እስከዛሬ ድረስ ከአህያ ለማይሻሉ ሰዎች ስንሰጥ ከርመናል ማለታቸው ነው!!)

  • በክልሉ የተጀመረው እንቅስቃሴ ባለሃብቶችን ዋስትና የሚያሳጣና ሥጋት ላይ የሚጥል ነው
                • ቢዝነስ ከኢንቨስተሮች እየቀሙ ለወጣቶች መሸለሙ ዘላቂ መፍትሄ አይሆንም
                • ከባለሀብቶች የማዕድን ማውጫዎችን መንጠቅ የኮሚኒስቶች አካሄድ ነው

        የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ይፋ ያደረገው “የኢኮኖሚ አብዮት” እያነጋገረ ሲሆን ሰሞኑን ኦዳ ትራንስፖርት
ኩባንያን ለመመሥረት በግማሽ ቀን በተካሄደ የአክሲዮን ሽያጭ 617 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ አክሲዮኖች መሸጣቸው ታውቋል፡፡ የኦዳ ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር በሙሉ አቅሙ ሲመሰረት ከወጣቶች ጋር በጋራ የሚያስተዳድራቸው የነዳጅ ማደያዎችና የነዳጅ ዲፖዎች እንደሚኖሩትም ተጠቁሟል፡፡ በሌላ በኩል የክልሉ መንግስት 1.2 ሚሊዮን ለሚደርሱ የኦሮሚያ ሥራ አጥ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር በሚል በባለሃብቶች ይዞታ ሥር የነበሩ የማዕድን
ማውጫ ቦታዎችን እየነጠቀ ለተደራጁ ወጣቶች ማከፋፈል የጀመረ ሲሆን ባለሃብቶች በዚህ እርምጃ መከፋታቸውን ገልፀዋል፡፡ ከ15 ዓመት በላይ በክልሉ በጠጠር ማዕድን ማውጣት ስራ ላይ ተሰማርተው ሲሰሩ እንደነበር የገለጹ አንድ ባለሀብት፤ “በዘርፉ የተሰማሩ አልሚዎችን አስወጥቶ ለኪሳራና ለውድቀት በመዳረግ ምንም ላልለፉ ወጣቶች ማከፋፈል በፍፁም ተቀባይነት የለውም” ሲሉ የክልሉን መንግስት እርምጃ ተቃውመዋል፡፡ ሌሎች የማዕድን ማውጫ ቦታቸውን የተነጠቁ ባለሀብቶችም “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የግል ሀብት የማፍራት መብት አለው” የሚለውን የህገ
መንግስቱን አንቀፅ 40 በመጥቀስ፣ህገ መንግስታዊ መብታቸው መጣሱን ጠቁመው አቤቱታቸውን ለመንግስት እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በጉዳዩ ዙሪያ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችን፣ምሁራንና ጋዜጠኞችን አነጋግሮ አስተያየታቸውን እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡

                 “የሥራ ዕድል መፍጠር ያለበት መንግስት አይደለም”
                         ስዩም ተሾመ (ጦማሪና የዩኒቨርሲቲ መምህር

      ከባለሀብቶች የማዕድን ማውጫዎችን መንጠቅ የኮሚኒስቶች አካሄድ ነው፡፡ በስነ ምጣኔ አመክንዮ ስንመለከተው፤ መንግስት በተለያዩ ቢዝነሶች መግባቱም የሚደገፍ አይደለም፡፡ ከግለሰቦች የኢንቨስትመንት ቦታ መውረስም ሆነ መንግስት ነጋዴ መሆኑ በየትኛውም መንገድ አይደገፍም፡፡ ይሄ የኮሚኒስት ስርአት ባህሪ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ይሄን በማድረጉ ግለሰብ ባለሀብቶችን እየቀጣ ነው ማለት ነው፡፡
የስራ ዕድል መፍጠር ያለበት እኮ መንግስት አይደለም፡፡ የስራ ዕድል በገንዘብ አይገዛም። መፍጠር የሚችለው ማህበረሰቡ ራሱ ነው፡፡ መንግስት ኃላፊነቱ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ የፋይናንስ ስርአቱን፣ ቢሮክራሲውን ማስተካከል፣ የቢዝነስ ስልቶችን ማስተማር የመሳሰሉት ናቸው የመንግስት ኃላፊነቶች፡፡ ከባለሀብቶች ላይ ሀብት ቀምቶ ለስራ አጥ ወጣቶች ማከፋፈል ፈፅሞ ተቀባይነት የሌለው ነው፡፡ ይሄ ማለት እናለማለን ያሉትን ኢንቨስተሮች እንደ መቅጣት ነው፡፡ እነዚህ ተነጥቆ የሚሰጣቸው ወጣቶችም ቢሆኑ በሙሉ ፍላጎታቸው ሳይሆን በመንግስት ግፊትና ድጎማ ወደ ስራው ስለሚገቡ ውጤታማ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ በግላቸው ተሯሩጠው አዲስ የስራ መስክ የፈጠሩትን ሰዎች እየቀጡ፣ የቢዝነስ ክህሎት ለሌላቸው ስራ አጦች መሸለም በየትኛውም አካሄድ አይደገፍም፡፡ ቢዝነስ ከግለሰቦች እየቀሙ ለስራ አጥ መሸለሙ ወጣቶችን ምርታማ አያደርግም። ምክንያቱም እነሱ ስለ ቢዝነሱ በቂ እውቀት አይኖራቸውም፡፡ ለወጣቶች የስራ ዕድል መፍጠር የሚቻለው በዚህ መርህና አካሄድ አይደለም፡፡ ተወዳዳሪና ብቁ የቢዝነስ ሰዎችንም በዚህ አካሄድ መፍጠር አይቻልም፡፡ የአለም ተሞክሮም ይሄን አያሳይም፡፡ ሰዎች በሚሰሩት ስራ በቂ እውቀት፣ ፍላጎትና ክህሎት ሲኖራቸው ነው ውጤታማ ሊሆኑ የሚችሉት፡፡
በሌላ በኩል መንግስት ከባለሀብቱ ልጣመርና ቢዝነስ ላቋቁም የሚለውም የሚያስኬድ አይደለም፡፡ ከዚህ በፊትም ታይቶ ውጤት ያላመጣ አካሄድ ነው። በነዚህ አካሄዶች ቀደም ሲል ህዝቡ ሲጠይቃቸው ለነበሩ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት አይቻልም፡፡ ተወዳዳሪ የቢዝነስ ሰዎችን ለመፍጠር በመጀመሪያ የሚደራጁት ሰዎች ብቃትና ፍላጎት ወሳኝነት አለው፡፡ ዝም ብሎ አደራጅቶ ሀብት ውረሱ ማለት እንዴት ውጤት ያመጣል? እነዚህ ሰዎች በምንም መመዘኛ ተወዳዳሪ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ እየጨመረ ለሚሄደው የስራ ዕድል ፍላጎትም ተጨማሪ የስራ ዕድል አይፈጥርም፡፡
በሌላ በኩል በኦሮሚያ በነበረው ተቃውሞ ወደ አደባባይ የወጡት ወጣቶች ጥያቄ በእርግጥስ የስራ ማጣት ጥያቄ ብቻ ነው? የሚለውንም መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ እንደ‘ኔ የነበረው ጥያቄ የእኩልነትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጥያቄ ነው፡፡ ይሄን ደግሞ ከአንዱ ነጥቆ ለሌላው በመስጠት ማስታገስ አይቻልም፡፡ በአመፁ ወቅት በዋናነት የተነሳው ጥያቄ፤ ከፊንፊኔ ዙሪያ የሚፈናቀሉ ሰዎች መብትና ጥቅማቸው አልተከበረላቸውም የሚል ነው፡፡ ይሄን ደግሞ በዚህ መንገድ ለመፍታት መንቀሳቀስ ከስነ ምጣኔ መርህ አንፃር አያስኬድም፡፡ የመብት ጥያቄዎች ባልተመለሱበት ሁኔታ ይሄን ቁንፅል እርምጃ ለመውሰድ መሞከር ትክክል አይደለም፤ ውጤትም አያመጣም፡፡   

-------------------

                          “ባለሃብቶች የሚወረሱ ከሆነ ምን ዋስትና ይኖራቸዋል?”
                         አቶ ጥሩነህ ገሞታ (የኦፌኮ አመራር)

        የኢኮኖሚና የፖለቲካ ሪፎርም ማድረግ የሚደገፍ ጉዳይ ነው፡፡ ይሄን ማንም አይቃወምም፡፡ ዋናው ሪፎርሙ የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት ይችላል ወይ የሚለው ነው፡፡ አሁንም አድሮ ቃሪያ አይነት ከሆነ ግን ምንም ውጤት ስለሌለው አይደገፍም። በኦሮሚያ ክልል በመንግስት በሚገለፀው ደረጃ የሪፎርም ስራ ሲሰራ አላየንም፡፡ የሚታይ ነገር ካለ ግን የምንቀበለው ይሆናል፡፡
ለወጣቶች በሚል ከባለሀብቶች የሚነጠቁ ፕሮጀክቶችን በተመለከተ አንድ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል፡፡ በ1967 ደርግ የገጠር መሬትና የከተማ ቤትና ቦታ እንዲሁም ፋብሪካዎችንና ኢንዱስትሪዎችን ወረስኩ ሲል የነበረውን ያስታውሳል፡፡ ደርግ በወቅቱ የግለሰቦችን ወፍጮ ቤቶች ሳይቀር ወርሷል፡፡ የተቧደኑ ግለሰቦች ማህበር በሚል እየተቋቋሙ ወፍጮ ቤትና የተለያዩ የሰው ንብረቶችን የወሰዱበት ጊዜ ነበር፡፡ ይሄም አካሄድ ያንን የሚያስታውስ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ስርአቱ የግል ባለሃብቶች ኢንቨስት አድርገው ሀብት ማፍራት ይችላሉ የሚል ፖሊሲ በማስቀመጡ ነው ግለሰቦች ዋስትና አለን ብለው ተማምነው ኢንቨስት የሚያደርጉት፡፡ እነዚህ ግለሰቦች በህግ አግባብ ግዴታቸውን እየተወጡ ያሉ ከሆነና ይህን ችላ ብሎ ልማታቸውን የሚነጥቅ ከሆነ የሚደገፍ አይደለም፡፡ ቀድሞውኑ በህገ ወጥ ሁኔታ የያዙት ከተወረሱ ግን እንደተወረሱ አይቆጠርም፡፡ ህጋዊዎች በዚህ መንገድ ዋስትና አጥተው የሚወረሱ ከሆነ ግን ለወደፊት ኢንቨስተሮች ምን ዋስትና ይኖራቸዋል? የሀገራችንን የሰው ኃይል ቀጥረው ሊያሰሩና ስራውን ሊያሳድጉ የሚችሉ ኢንቨስተሮች ከየት ሊመጡ ይችላሉ? የሚል አስደንጋጭ ጥያቄም ያስነሳል፡፡ ስለዚህ ባለሀብቶች በዚህ መልኩ ሀብታቸውን እየተነጠቁ ከሆነ በግልም ሆነ በፓርቲያችን ደረጃ አንቀበለውም፡፡
ወጣቶችን ወደ ስራ ማስገባት ከተፈለገ‘ኮ ካፒታል መድቦ አዳዲስ የቢዝነስ እቅዶችን አውጥቶ ማሰማራት ይቻላል፡፡ ይሄ ከተደረገ ብቻ ነው የምንደግፈው፡፡ የሰው ሀብት ነጥቆ ለሌላ መስጠት ግን የማይደገፍ ነው፡፡ ወጣቶችን በፓርቲ ደረጃ ጠርንፎ ከመያዝ ወጣቱን ለቀቅ አድርጎ፣ በፈለገበት የስራ መስክ እንዲሰማራ ማድረግ ነው የሚያስፈልገው፡፡ የወጣቶችን አቅም አጎልብቶ ወደ ስራ እንዲገቡ ከማድረግ ይልቅ የሌሎችን ሀብት ወርሶ መስጠት ተገቢ አይደለም፡፡ አላስፈላጊ ከሆኑ በጀቶች እየቀነሱ የተለያዩ ዘርፎች ላይ ማሰማራት ይቻል ነበር፡፡ ይሄ የሚደረገው ለህዝባዊ እንቅስቃሴው ምላሽ ለመስጠት ከሆነ፣ ህዝቡ ያነሳው የኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን የመብት ጥያቄም ነው፡፡ በዚህ ብቻ ለማስተንፈስ ከተፈለገ ዘላቂ ውጤት ያመጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡

----------------------

                       “ከአንዱ ነጥቆ ለአንዱ መስጠት አይበረታታም”
                          አቶ ቶሎሣ ተስፋዬ (የኦሮሞ ብሄራዊ ኮንግረስ ሊቀመንበር)

       እኛ በህዝቡ የሚሰሩትን የልማት ስራዎችና ህዝቡ የሚቀበላቸውን ነገሮች ሁሉ እንደግፋለን። ወጣቱ የስራ እድል ጥያቄ እንዳለው ይታወቃል፡፡ ለዚህ የወጣቶች ጥያቄ እንደ ሀገርም እንደ ኦሮሚያ ክልልም እየተቀመጡ ያሉ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በበጎ እንቀበላቸዋለን፡፡ በተለይ የኦሮሚያ “የኢኮኖሚ አብዮት” ብዙ ወጣቶችን ያሳትፋል የሚል እምነት አለን፡፡ መንግስት ቆም ብሎ አስቧል፤ ችግሩን አይቷል፤ የህብረተሰቡን ክፍል በየደረጃው አወያይቷል፡፡ በዚህም ችግሩን ለይቶ አውቋል የሚል ግምት አለን፡፡ ችግሩን ለይቶ ካወቀ በኋላ እየወሰደ ያለው የመፍትሄ እርምጃ የሚበረታታ ነው፡፡ ህዝብም ድጋፍ እየቸረው ነው፡፡ ሰሞኑን በተደረገው የአክሲዮን ሽያጭ ላይ ከፍተኛ ገንዘብ መገኘቱ፣ ህዝቡ ለዚህ ድጋፍ እንዳለው ያመላክታል፡፡
ከዚህ ቀደም እንደ ፓርቲ ስንለው የቆየነውን ነው አሁን መንግስት እየሰራ ያለው፡፡ በተደጋጋሚ ወጣቱ ስራ አጥ ሆኗል፤ ጥቂቶች ሀብት ያለአግባብ እያካበቱ ነው ስንል ነበር፡፡ በተለይ ከአመራሩ ጋር ቅርበት ያላቸው ጥቂት ሰዎች፣ በኦሮሚያ ውስጥ ከፍተኛ ሀብት እያካበቱ የሀብት ክፍፍሉ ከፍተኛ ልዩነት እያሳየ ነው፡፡ አብዛኛው የሚበላው እያጣ ነው፡፡ በተለይ ወጣቱና የተማረው ክፍል ተረስቷል እያልን ስንጮህ ቆይተናል፡፡ ለዚህ ጩኸት ምላሽ እየተሰጠ ይመስላል፤ የተጀመረው ነገር ጥሩ ነው፣ ውጤት ያመጣል የሚል እምነትም አለን፡፡
ይህን ስንል ግን ከአንዱ ነጥቆ ለአንዱ መስጠትን አናበረታታም፡፡ መጀመሪያውኑ ከባለሀብቶች ጋር በኦሮሚያ ውስጥ ሲሰራ የቆየው ፍትሃዊነት የሌለው ነበር፡፡ አንድ ባለሀብት የህዝብ መሬት ይዞ አጥሮ፣ አስርና ከዚያ በላይ ዓመት ያለምንም ጥቅም ማቆየትና መሬቱን አትርፎ ለመሸጥ ገበያ የመጠባበቅ አዝማሚያ ነበር፡፡ በእነዚህ ዓይነቶቹ ላይ እርምጃ መወሰዱ የሚበረታታ ነው፡፡ ነገር ግን በህጋዊ መንገድ ከሚሰራው ላይ የሚነጠቅ ከሆነ ተቀባይነት የለውም፡፡ ብዙ የተማሩና ልምዱ ያላቸው ወጣቶች አሉ፤ እነዚህ ወጣቶች መነሻ ካፒታል ማግኘታቸው ስራቸውን ውጤታማ ለማድረግ ያስችላቸዋል፡፡
በህጋዊ መንገድ እየሰራ፣ ሀገርን እየጠቀመ ያለን ኢንቨስተር መሬትና ሀብት እየነጠቁ ለወጣቱ እንሰጣለን የሚባለውን እኛ አንቀበለውም፡፡ ሁሉም እኩል ተጠቃሚ የሚሆንበትና በቀጣይ ጥያቄ የማይነሳበት አሰራር ነው መፈጠር ያለበት። ባለሀብቶችን ከስራ ውጪ አድርጎ ለሌላ ወገን መስጠት በየትኛውም መመዘኛ የሚበረታታ አይደለም፡፡ ሁሉም ዜጎች ፍትሃዊ ተጠቃሚ መሆን አለባቸው፡፡

------------------

                          “የኢኮኖሚ አብዮት እንደቃሉ ቀላል አይሆንም”
                             በፍቃዱ ኃይሉ (ጦማሪና ጋዜጠኛ)

          ኢህአዴግ የሚከተለው የፖለቲካል ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በየወቅቱ የሚቀያየር በመሆኑ በግልፅ አይገባኝም፡፡ በአሁን ወቅት በዓለም ላይ ያለውን ሰፊ ሁኔታ ስንመለከት፣ ወደ ነፃ ኢኮኖሚ ያዘመመ በመሆኑ፣ ይህን ብንከተል የተሻለ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚህ አንፃር ባለሀብቶች በህጋዊ መንገድ ያገኙትን የኢንቨስትመንት እድል ለወጣቶች ስራ ፈጠራ በሚል መንጠቅ ወንጀልም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ኢንቨስተሮችን ዋስትና አሳጥቶ ኢንቨስት ከማድረግ እንዲቆጠቡ ያደርጋል። ይሄ አካሄድ ወጣቶች ኢንቨስትመንቶችን አቃጠሉ ከተባለውም የባሰ ነው፡፡ ኢንቨስተሮች ይሄንን እያዩ ከዚህ በኋላ እንዴት ኢንቨስት ሊያደርጉ ይችላሉ? ከዚህ አንፃር አካሄዱ ፈፅሞ ትክክል አይደለም፡፡ በጣም አስደንጋጭና አሳዛኝ ነው የሚሆነው፡፡
በእርግጥ ለወጣቶች የስራ ዕድል መፈጠር አለበት፤ ነገር ግን አዳዲስ እድል መፍጠር እንጂ የሌላውን መሻማት አግባብ አይሆንም፡፡ ለምሳሌ የማዕድን ማውጫዎችን በተመለከተ ወጣቶቹ ከባለሀብቶቹ ጋር በሰንሰለታማ የንግድ ስርአት ተቀናጅተው እንዴት መስራት እንደሚችሉ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ማስቀመጥ እንጂ ንብረት እየነጠቁ መስጠት አያዋጣም፡፡ ነገ ከነገ ወዲያም ሌላ መዘዝ ይዞ ነው የሚመጣው፡፡
በተለይ ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ ዘላቂነት ስናስብ፣በዚህ አካሄድ ኢንቨስተሮችን እያቀጨጩ እንዴት መጓዝ ይቻላል? የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡
የኦሮሚያ ክልል ያመጣው “የኢኮኖሚ አብዮት” ቃሉ በጣም ማራኪ ነው፡፡ የኢኮኖሚ አብዮት በእርግጥም ያስፈልገናል፡፡ ግን እንደ ቃሉ ቀላል አይሆንም፡፡ እርግጥ ነው ማህበረሰቡ ከአካባቢው ከሚገኘው ሀብት ተጠቃሚ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ነገር ግን ኢንቨስተሮች በሚሰሩት ልማት ወጣቶች ተቀጥረው በመስራት ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እነዚህን ጥቅሞች ለየአካባቢው ወጣቶች ማስጠበቅ ነው የሚሻለው፡፡  

• የግል ቤት የሌላቸው የክልሉ ተወላጆችና የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
• የመጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖች ለክልሉ ተወላጆች ይቀርባሉ

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት፣ ተወላጆቹ በሙሉ በክልሉ ከተሞች የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ ወሰነ፡፡
በክልሉ የሚገኙ አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ የግል መኖሪያ ቤት የሌላቸው የከተማ ነዋሪዎች፣ ወጣቶች፣ መምህራንና የመንግስት ሰራተኞችን ጨምሮ የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች በሙሉ የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ መወሰኑን የኦሮሚያ የከተማ ቤቶች ልማት ም/ሃላፊ አቶ ሽመልስ አብዲሣ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ከዚህ ውሣኔ ላይ የደረሰው የክልሉ ከተሞች የተወላጆችን ጥቅም ባማከለ መልኩ እንዲያድጉና ተወላጆች በከተሞች ድርሻ እንዲኖራቸው ለማድረግ መሆኑም ተገልጿል፡፡ የክልሉ መንግስት ባደረገው ግምገማ፤ የቤት ኪራይ ዋጋ ውድነት ነዋሪዎችን ላልተፈለገ ወጪ መዳረጉንና እንዳይረጋጉ ማድረጉን፣ ቀደም ሲል በነበረው አካሄድ የክልሉ ከተሞች እድገትም በሚፈለገው መጠን አለመሆኑን እንዲሁም የክልሉን መሬት ለህገ ወጥ ደላሎች ያጋለጠ አሰራር እንደነበረ ደርሶበታል፡፡ እነዚህን ችግሮች ከግምት ውስጥ በማስገባትም ዜጎች የቤት መስሪያ የከተማ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችለው ደንብና መመሪያ ሊወጣ መቻሉን ም/ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡
‹‹ህብረተሰቡ የከተማ ህይወት እንዲኖር ይፈለጋል›› ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ይህ የክልሉ መንግስት እቅድ ይሄን ለማሳካት ያለመ በመሆኑ አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ በዚህ ማዕቀፍ እንዲካተቱ መደረጉን አብራርተዋል፡፡ ከመከላከያ ሰራዊት ጡረታ የወጡ ግለሰቦችና ሌሎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡  
በአካባቢው ለሁለትና ከዚያ በላይ ዓመት የኖሩ፣ የቤት መስሪያ ገንዘብ መቆጠብ የሚችሉና ቀሪ ገንዘብ መንግስት በሚያመቻቸው ብድር ለማግኘት ፍቃደኛ የሆኑ ግለሰቦች የቤት መስሪያ ቦታ ለማግኘት መደራጀት እንደሚችሉ ሃላፊው አስረድተዋል፡፡
ቦታ ፈላጊዎች የሚደራጁት በ4 አይነት አማራጮች ነው ተብሏል፡፡ በጋራ አፓርትመንት ለመገንባት የሚፈልጉ፣ G+1 እና ከዚያ በላይ መገንባት የሚፈልጉ እንዲሁም ቪላ ቤት መስራት የሚችሉ በሚል ሲሆን ይሄን ለማድረግ አቅም የሌላቸው መለስተኛ ቤቶችን ለመስራት የሚችሉባቸው አማራጮች መቀመጣቸውን አቶ ሽመልስ አብራርተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት በዝቅተኛ ወጪ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው የሚገነቡ የቤት አማራጮችን እያጠና መሆኑም ተገልጿል፡፡ አንድ ግለሰብ ለመኖሪያ ቤት መስሪያ የተሰጠውን ቦታ መሸጥ መለወጥና ከህጋዊ ወራሾች በስተቀር ለ3ኛ ወገን ማስተላለፍ እንዲሁም በውክልና ማሰራት አይችልም ብለዋል፤ ሃላፊው፡፡ እስከ 10 ዓመት ድረስም ካርታ እንደማይሰጥ አክለው ገልፀዋል፡፡ በነዚህ ጥብቅ መመሪያዎች እንዲታጠር የተደረገው የመሬት ብክነትንና ያለአግባብ መገልገልን ለማስቀረት በማሰብ ነው ተብሏል፡፡  
በክልሉ ከ9 ዓመት በላይ መሬት በዚህ መልክ ተሰጥቶ እንደማያውቅ የጠቆሙት አቶ ሽመልስ፤ የክልሉ መንግስት ይሄን ሰፊ እቅድ ሲተገብር ሊያጋጥሙ የሚችሉ ተግዳሮቶችንም በዝርዝር መለየቱን አስታውቀዋል፡፡ ከተለዩ ተግዳሮቶች መካከል የመሬት አቅርቦት አንዱ መሆኑን የጠቀሱት ሃላፊው፤ በተለይ ለአርሶ አደሮች የሚከፈል የመሬት ካሳና መንግስት መሬቱን ያለምንም የሊዝ ክፍያ ገቢ ሳያገኝበት በነፃ ለፈላጊዎች ማስተላለፉ ጫና ሊፈጥርበት እንደሚችል ጠቁመው፣ ለዚህም የተለያዩ አማራጮች እየተፈተሹ መሆኑን አስረድተዋል። ሌላው ተግዳሮት ለብድር አቅርቦት የሚሆን የፋይናንስ አቅም ሲሆን ይህንንም የቁጠባ ባህልን በማሳደግ ለመፍታት ጥረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ለዚህ ፕሮጀክት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ሰፊ ዝግጅት ማድረጉ የተገለጸ ሲሆን በአሁን ወቅትም ቤት የሌላቸውን ሰዎች ለይቶ የማደራጀት ስራ እየተሰራ ነው ተብሏል፡፡ የመሬት አቅርቦቱም ሰዎች በፈለጉት የቤት አይነት ተደራጅተው ሲቀርቡ ወዲያው የሚፈፀም መሆኑ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል የክልሉ መንግስት ይፋ ባደረገው ‹‹የኢኮኖሚ አብዮት››፣ ከኦዳ ትራንስፖርት አክሲዮን በተጨማሪ በቅርቡ የተለያዩ መጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖችን ለክልሉ ተወላጆች በሽያጭ ለማቅረብ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ የመንገድ ትራንስፖርት ሃላፊ አቶ ታከለ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡