Administrator

Administrator

  • ድርጊቱን ያጋለጡት፣ “የሥራ ዋስትናችን ለስጋት ተጋልጧል” እያሉ ነው
                      • የማጸደቂያ ‘ስጦታው’ በሌሎችም አድባራት የተለመደ መሆኑ ተጠቁሟል

      በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ የደብረ ተኣምራት ጻድቃኔ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ሠራተኞች፤ ለተፈቀደላቸው የደመወዝ ጭማሬ ማጽደቂያ በሚል፣ ለሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ለሒሳብና በጀት ዋና ክፍሉ ሓላፊ በስጦታ ለመክፈል፣ የተጠየቁትን የ50 ሺሕ ብር ጉቦ(የሁለት ወራት ጭማሬ) ማጋለጣቸውን ተከትሎ፤ ገንዘቡ እንዲመለስላቸው ታዘዘ፡፡
የደብሩ አስተዳዳሪ፣ ዋና ጸሐፊ፣ ሒሳብ ሹም፣ ቁጥጥርና የገንዘብ ቤት ሓላፊ፤ “ደመወዙን ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አጸድቀን ያመጣነው የስጦታና የማጸደቂያ ገንዘብ ከፍለን በመሆኑ የታኅሣሥና የኅዳር ወር ጭማሬያችሁን 50 ሺሕ ብር ለእኛ ትለቁልናላችሁ፤” እንዳሏቸው አቤቱታ አቅራቢዎቹ ገልጸዋል፡፡
“ለምን እንለቅላችኋለን?” ብለው መጠየቃቸውን የጠቀሱት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ “እንዲህ ዓይነቱ ነገር በሌሎችም አብያተ ክርስቲያናት የተለመደና የሚደረግ መሆኑን ታውቃላችሁ፤ ይህ ብር ካልተከፈለ ደመወዙ ሊጸድቅ አይችልም፤” በማለት ሓላፊዎቹ እንደመለሱላቸው አስረድተዋል፡፡
አቤቱታ አቅራቢዎቹም፣ በወቅቱ የሓላፊዎቹን ምላሽ በአንድ ድምፅ ቢቃወሙም፣ የኅዳር ወር ጭማሬያቸው ብር 25ሺሕ፣ ለሥራ አስኪያጁ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ እና ለሒሳብና በጀት ዋና ክፍሉ ሓላፊ አቶ ገብረ ሕይወት አስገዶም ስጦታ ተቀንሶ በባንክ መከፈሉን አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይም፣ የታኅሣሥ ወሩ ብር 25ሺሕ ሊቆረጥባቸው በመታሰቡ፣ በቀጥታ ደብሩ ለሚገኝበት የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ፣ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ማመልከታቸውን አስረድተዋል፡፡
የክፍለ ከተማው ቤተ ክህነትም፣ አቤቱታውን ተቀብሎ በመደባቸው ልኡካኑ በማጣራት ድርጊቱ ሕገ ወጥ መሆኑን ገልጾ፤ ከሠራተኞቹ የደመወዝ ጭማሬ ላይ በስጦታ የተወሰደባቸው ገንዘብ፣ ለሁሉም ካህናትና ሠራተኞች ከጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም ጀምሮ ተመላሽ እንዲሆንና የአፈጻጸሙ ሪፖርት እንዲገለጽለት የደብሩን አስተዳደር አሳስቧል፤ ደብሩም በሕግ አግባብ እንዲመራ የክፍለ ከተማው ጽ/ቤት አሳስቧል፡፡ ይህም ሆኖ፣ “ድርጊቱን በማጋለጣችን ከሥራ ለማዘዋወርና ለማገድ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ይይኑ ደብሩ ድረስ በመምጣት ከጽ/ቤቱ ሓላፊዎች ጋር በመሆን መክረውብናል፤” ያሉት ካህናቱና ሠራተኞቹ፣ “ቀጣይ የሥራ ዋስትናችንም ለስጋት ተጋልጧል፤”  ሲሉ ባለፈው ማክሰኞ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት በጻፉት አቤቱታ አመልክተዋል፡፡
ለተፈጸመባቸው በደል አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጣቸው የተማፀኑ ሲሆን፤ በደብሩ ሓላፊዎች የተፈጸመው የሙስና ወንጀል የቤተ ክርስቲያንን ክብር የሚነካ በመሆኑ እንዲጣራና ጥፋተኞችም ለሕግ እንዲቀርቡ በአቤቱታቸው ጠይቀዋል፡፡

Monday, 30 January 2017 00:00

እኔ፣ ሽክናና ቅኝ ግዛት

  ‹‹ወታደሩን በምን ያህል መጠን እናጠናክረው? ለእናት አገራችን በአስቸኳይ አንድንደርስ፣ ይሄ ቀዳዳ ሳይከፈት…ነገር ግን በሕግ አንበይናለን፤ እናስፈፅማለን እንላለን…ገና ጦር ሜዳ ሄዶ ጠላቱን አይቶ መግደሉን ወይም መሞቱን ሳያውቅ ከመኪና ላይ በራሱ እየወረደ የሚሞት ወጣት ነው ያለው፡፡ ምንድን ነው ይሄ? ከኢትዮጵያ ነው እንዴ የበቀለው?...››
አሉ አሉ ጓድ ፕሬዚዳንት መንግሥቱ ኃ/ማርያም፡፡
ከፍርሃታችን አለማፈራችን፡፡
ከእሳቸው በላይ እኔ አርሬአለሁ፡፡ ‹‹ምንድን ነው ይሄ ታለ? ከኢትዮጵያ ነው አንዴ የበቀለው?›› ብያለሁ፡፡ እሳቸው አጣለሁ ብለው ከሰጉት በላይ እኔ ሰግቻለሁ፡፡ ‹‹ፍቅራችንን በምን ያህል መጠን እናጠናክረው? ለሲፈን በአስቸኳይ እንድንደርስ፣ ይሄ ቀዳዳ ሳይከፈት…›› ብያለሁ፡፡
የቱ ቀዳዳ? መንግሥቱ እኛን የሚፈልጉን እንደ ጋሽ ሩፌ ጭቃ፣ ቀዳዳ ለመድፈን ነው እንዴ? እያነሱ ሊመርጉን፤ ትንሽ ሽንቁር ላይ ልክክ ስንል ‹‹ለእናት ሀገሩ አኩሪ መስዋዕትነት ከፍሎ…›› እንባላለን እንደ አባቴ፤ አይ ወንድ!
እነ ሸክና እኔ ቤት ሦስት ቀን አደሩ፡፡ ሽክና በእናቱ ሀገሩ እጅግ አድርጎ ተበሳጨ፤ በተለይ የጠጅ አቅርቦት ከተቋረጠ የኢትዮጵያን የሶስት ሺህ አመት ነፃነት ይገፍፋል፡፡
‹‹ተገዝተናል!›› ይላል ቀበኛ ያኘከው ጨርቅ በመሰለ ፊቱ ላይ ብስጭት እያስነበበ፡፡
ፈርተን የተሸሸግን ቢሆንም አንዳንዶች ይሄንን ሀሳብ በጀግንነት ይዋጋሉ፡፡
‹‹አሲዙ፣ እኔ እረታችኋለሁ›› ይላል ሸክና፡፡
ጨዋታ ሞቅ ሲል ሴቶቹ አብዮት ጠባቂ ከሚጠብቁበት ከዋርድያ ነቅለው ይመጣሉ፡፡
‹‹አንተ ምን ታሲዛለህ?›› ምንም እንደሌለው ያወቁ፡፡
‹‹እስክሞት ቀጥቅጡኝ›› ይላል፡፡
ሽክናን ለመምታት ሰበብ የሚፈልገው ሳኮ የመጀመሪያዋን ሃያ አምስት ሳንቲም ይጥላል፡፡
‹‹ይኸው፣ እዩ ደሞ!››
‹‹እንምርህም ግን››
‹‹አትማሩኝ››
‹‹ከሁለተኛ ፎቅ እንደመዝለል ይቆጠራል››
‹‹ንፋስ ይወስደዋላ››
ሣቅ!!
ሽክና ለውርርድ የቀረበውን ፍራንክ አይቶ ‹‹‹ለዚችማ ብዬ ውርርዴን አላበላሽም›› አለ፡፡
እልህ የያዛቸው ጨመሩ፡፡
‹‹አሁን ይቻላል! ስምንት ብርሌ ጠጅ በቂ ነው።››
‹‹በውርርዱ ካላሸነፍክ ተመላሽ ነው አትጠጣ››
‹‹ለሱ ግድ የለም፡፡›› አለና ቀጠለ፡፡ ‹‹እዚህ ሰፈር ያሉትን ስሞች ስነግራችሁ መዝግቡ››
‹‹እሺ›› መዝጋቢ ተመደበ
‹‹ሩፌ›› አለ
‹‹ሩፌ›› ተመዘገበ
‹‹ዎሌ፣ መዘገባችሁ? ቸሩ፣ ዶሪ፣ ሳኒ፣ መዘገባችሁ? ድገሙልኝ፤››
‹‹ሩፌ›› ሲሉ
‹‹ሩፍ ከሚለው እንግሊዘኛ ነው የተገኘው፡፡ ጣሪያዬ ማለት ነው››
‹‹ዎሌ››
‹‹ዎል ከሚለው እንግሊዝ ቃል የተገኘ ነው ወለሌ››
‹‹ቸሩ››
‹‹ቸር ወንበር ነው፡፡ ወንበሬ››
‹‹ዶሪ››
‹‹ዶር፤ በሪሁን ማለት ነው››
‹‹ሳኒ››
‹‹ሰን፣ ፀሀይ አይደል ፀሐዬ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያ የእንግሊዝ ቅኝ ተገዢ እንደነበረች በዚህ ይታወቃል፡፡››
የሚስቀው ሳቀ፤ የሚናደደው ተከራከረ፡፡
‹‹በእንግሊዝ ቀኝ አልተገዛንም ካለች እንደ እኔ በማስረጃ ተከራከሩ››
‹‹ነው እንዴ? አንተ? እንግሊዝ ገዝታናለች?›› አለ ሳኮ፡፡ ‹‹ወይኔ የሙዜን አሰበሉኝ፣ ምን አሰዋሻቸው? ወይኔ የሻሜታዬን…››
ሽክና ጠጁን በሴቶቹ አስላከ፡፡
በሁካታ መካከል እናቴ ትመጣና አንዴ በግልምጫ ታነሳናለች፡፡ ‹‹እኔ እዚህ ነፍስና ስጋዬ ይቦጨቃል እናንተ ታወካላችሁ? እንዴት ያሉ ሀሳብ የለሾች!
ቻይና ስለእሷ የተጀመረው ወሬ እንዳይቀጥል ብቻ ለጥበቃ የተቀመጠች ይመስላል፡፡ ለመሳቅ ትሞክርና ሽክና ሲያያት ትኮሳተራለች፡፡ ያ ማር ነጋዴ ማን ይሆን? ከእኔ የባሰ ሳይፈርድበት አልቀረም፡፡ ማር የነካካ እጁን ወደኋላ አድርጎ ይሄኔ…
ምንጭ ፡- ‹‹በፍቅር ስም›› መፅሀፍ የተቀነጨበ
በደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ ከተፃፈው

ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ሩት ነጋ ለምርጥ መሪ ተዋናይነት ታጭታለች

     ጋለሪያ ቶሞካ ለ22ኛ ጊዜ በሚያካሂደው የስዕል ትርኢት፤ “ነፃና ንፁህ” በሚል ርዕስ የሰዓሊ ይስሃቅ ሳህሌን የሥዕል ስራዎች ለእይታ አቀረበ፡፡የሥዕል ትርኢቱ በትናንትናው እለት የተከፈተ ሲሆን የህፃናትን አለምና ህይወት የሚገልፁ የተለያዩ ስዕሎች የተካተቱበት ነው ተብሏል፡፡ “እንደ ህፃናቱ አሳሳል በወፍራም መስመራት የተሰመሩ፤ በሰፋፊ ዝርግና ደማቅ ህብረ ቀለማት የተቀቡ ነፃ፣ ንፁህና የዋህ ኪነ ቅቦች ናቸው” ብለዋል ሰዓሊ እሸቱ ጥሩነህ፤ ስለ ሰዓሊው ሥራዎች ባሰፈሩት አስተያየት፡፡ “በህፃናት ዓለም ውስጥ መገኘት፣ ያንን ዓለም መተንተን፣ በህፃናት ህሊና ውስጥ የሚፈሱ ቀለማትን ማጫወት ደስ ይለኛል” የሚለው ሰአሊው፤ ከልጅነቱ ጀምሮ በኪነ ሥዕል ሙያ ራሱን ያዳበረ መሆኑ በሥዕል ትርኢቱ መግለጫ መፅሄት ላይ ተጠቁሟል።
ሰዓሊው ከዚህ ቀደም በፈረንሳይ የባህል ማዕከል፣ በብሄራዊ ሙዚየም፣ በብሄራዊ ቴአትርና በአስኒ ቤተ ሥዕል ስራዎቹን ለዕይታ ማቅረቡ ታውቋል፡፡ “ነፃና ንፁህ”፤ ለሁለት ወራት ለተመልካች ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡ ጋለሪያ ቶሞካ የሚገኘው ሳር ቤት ካናዳ ኤምባሲ ፊት ለፊት ነው፡፡

ከ14 በላይ መፃህፍት አሳትመዋል
     ቼምበር ማተሚያ ቤትን የመሰረቱትና በኢትዮጵያና በአፍሪካ ታሪኮች ላይ ያተኮሩ መፃህፍትን የፃፉት እንዲሁም ለትምህርት የሚሆኑ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች የተፃፉ ከ14 በላይ መፃህፍትን ያሳተሙት አቶ
አስፋው ተፈራ በ88 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ በኢትዮጵያ መፅሐፍ ቅዱስ ማህበር በፕሬዚዳንትነት፣ በአዲስ አበባና በምስራቅ አፍሪካ ላይንስ ክለብ በፕሬዚዳንትነት እንዲሁም በኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር በተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች ያገለገሉት አቶ አስፋው፤ ከህልፈታቸው በፊት 10 የሚደርሱ መፃህፍትን ለህትመት እያዘጋጁ እንደነበር ታውቋል፡፡ በብሔራዊ ዩኔስኮ በድርሰት ክፍል ኃላፊነት፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በህዝብ
አስተዳደር ምርምርና ክፍል ጥናት፣ እንዲሁም በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በናይጄሪያ  በኢትዮጵያ  ኤምባሲ በዲፕሎማትነት የሰሩት አቶ አስፋው፤ የኢምፔሪያል ሆቴል መስራችና ባለቤትም ነበሩ፡፡ አቶ አስፋው ተፈራ ባደረባቸው ህመም በአገር ውስጥና በውጪ አገር ህክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው፣ ሰኞ ጥር 15 ቀን 2009 ዓ.ም ያረፉ ሲሆን የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም ባለፈው ረቡዕ በአማኑኤል ቤተክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡ አቶ አስፋው ተፈራ ባለትዳርና የ5 ልጆች አባት ነበሩ፡፡

Sunday, 29 January 2017 00:00

የቢዝነስ ጥግ

- ድሃ ሆነህ ብትወለድ ጥፋቱ ያንተ አይደለም፤ ድሃ ሆነህ ብትሞት ግን ጥፋቱ ያንተ ነው፡፡
    ቢል ጌትስ
- ሁሉንም እንቁላሎች በአንድ ቅርጫት ውስጥ አትክተት፡፡
     ዋረን በፌ
- ለገንዘብ አትስራ፤ገንዘብን ላንተ እንዲሰራልህ አድርገው፡፡
     ሮበርት ኪዩሳኪ
- በእውቀት ላይ የሚፈስ መዋዕለ ንዋይ ምርጥ ወለድ ይከፍላል፡፡
     ቤንጃሚን ፍራንክሊን
- ትምህርት የዕድል መወጣጫ መሰላል ብቻ አይደለም፤ የመጪው ጊዜአችን ኢንቨስትመንትም ጭምር ነው፡፡
     ኢድ ማርኬይ
- ኢንቨስተር ለመሆን የተሻለ ነገ እንደሚመጣ የምታምን መሆን አለብህ፡፡
     ቤንጃሚን ግራሃም
- ድሃ ሰው በሚሰጥህ ምክር ገንዘብህን ኢንቨስት አታድርግ፡፡
     የስፔናውያን አባባል
- ገንዘቤ በሙሉ ያለው በቁጠባ ሂሳብ ውስጥ ነው፡፡ አባቴ የአክሲዮን ገበያን ምናልባት 75 ጊዜ ያህል አስረድቶኛል፡፡ አሁንም ግን አልገባኝም፡፡
     ጆን ሙላኔይ
- በአክሲዮን ገበያ ላይ ኢንቨስት ማድረግን እየነቀፍኩ አይደለም፤ እኔ ኢንቨስተር ነኝ፡፡
     ግሬስ ናፖሊታኖ
- የሳምንቱን የዕረፍት ቀናት አልወዳቸውም፤ ምክንያቱም የአክሲዮን ገበያ የለም፡፡
     ሬኔ ሪቭኪን

 አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ባለፈው የአገሪቱ ምርጫ፣ ከመራጮች ምዝገባ ጋር በተያያዘ የማጭበርበር ድርጊት መፈጸሙ እንዲጣራ የሚያደርግ ትዕዛዝ እንደሚሰጡ አስታውቀዋል፡፡
ትራምፕ ባለፈው ማክሰኞ በትዊተር ገጻቸው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ በሁለት ግዛቶች በመራጭነት የተመዘገቡ አሉ፣ ህጋዊ ያልሆኑ መራጮች ተመዝግበዋል፣ በህይወት የሌሉ ሰዎች ድምጽ ለመስጠት ተመዝግበዋል የሚሉትን ጨምሮ ከመራጮች ጋር በተያያዘ ተፈጽመዋል የተባሉ መጭበርበሮችን እንዲጣራ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። በምርመራው የተገኘውን ውጤት መሰረት በማድረግም፣ የአገሪቱን የምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ስርዓት የምናስተካክል ይሆናል ብለዋል ትራምፕ፡፡
ትራምፕ ተፈጽሟል የተባለውን መጭበርበር አጣራለሁ ይበሉ እንጂ፣ የመንግስት ባለስልጣናትና የምርጫ ሃላፊዎች በምርጫው ሂደት መጭበርበር መፈጸሙን የሚያመለክቱ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃዎች አለመቅረባቸውን ሲናገሩ መቆየታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህን መግለጫ ያወጡት ባለፈው ማክሰኞ በተደረገው የዋይት ሃውስ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ቃል አቀባዩ ሻን ስፓይሰር፤” በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህገወጥ ስደተኞች በምርጫው ድምጻቸውን ሰጥተዋል” ብለው መናገራቸውን ተከትሎ እንደሆነ ዘገባው ገልጧል፡፡
ቢቢሲ በበኩሉ፤ ትራምፕ የምርጫው ሰሞን ጀምሮ መጭበርበር መፈጸሙን በትዊተር ገጻቸው ላይ ባስተላለፏቸው መልዕክቶች ሲገልጹና “በምርጫው አምስት ሚሊዮን ያህል ህገ-ወጥ መራጮች ለሄላሪ ድምጻቸውን ሰጥተዋል” የሚል ክስ ሲያቀርቡ እንደነበር አስታውሶ፣ ይህን ክሳቸውን የሚደግፍ ምንም አይነት ማረጋገጫ አለማቅረባቸውን ዘግቧል፡፡

   ኢትዮጵያ በሙስና ከ176 የአለማችን አገራት 68ኛ ደረጃን ይዛለች

     ላለፉት ዘጠኝ ተከታታይ አመታት በሙስና ክፉኛ በመዘፈቅ አለምን ስትመራ የዘለቀቺው ሶማሊያ፣ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016ም ቀዳሚነቷን ማስጠበቋን ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም አስታውቋል፡፡
ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የአመቱ የዓለማችን የሙስና ሁኔታ ሪፖርት፣ ኢትዮጵያ ጥናቱ ከተሰራባቸው የአለማችን 176 አገራት በሙስና 68ኛ ደረጃ ላይ መቀመጧንም ጠቁሟል፡፡
ተቋሙ በአለማችን ከፍተኛ ሙስና የተንሰራፋባቸው አገራት በሚል ባወጣው ዝርዝር ውስጥ፡- ደቡብ ሱዳንና ሰሜን ኮርያ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ያገኙ ሲሆን  ሶርያ፣ የመን፣ ሱዳን፣ ሊቢያ፣ አፍጋኒስታን፣ ጊኒ ቢሳኦ እና ቬንዙዌላ በቅደም ተከተል እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸው ተነግሯል፡፡
ጥናቱ ከተሰራባቸው የዓለማችን 176 አገራት መካከል ዴንማርክና ኒውዚላንድ እጅግ አነስተኛው ሙስና የሚታይባቸው ቀዳሚዎቹ አገራት ናቸው ያለው የተቋሙ ሪፖርት፤ ፊንላንድና ስዊድን በሁለተኛና በሶስተኛነት መቀመጣቸውን ገልጧል። አነስተኛ ሙስና ያለባቸው የአለማችን አገራት ተብለው የተዘረዘሩት ቀሪዎቹ አገራት ደግሞ፣ ስዊዘርላንድ፣ ኖርዌይ፣ ሲንጋፖር፣ ኒዘርላንድስ፣ ካናዳና ጀርመን ናቸው፡፡
ሙስና መጠንና ስፋቱ ይለያይ እንጂ በሁሉም የአለማችን አገራት እንደሚታይ ያስታወሰው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል፤ በርካታ የአለማችን አገራት ከአንድ አመት በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር፣ በ2016 መሻሻል ከማሳየት ይልቅ የባሰ ሙስና ውስጥ ተዘፍቀው ተገኝተዋል ተብሏል፡፡

 የወቅቱ የአለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ እና የማይክሮሶፍት መስራቹ አሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስ፣ በመጪዎቹ 25 አመታት ጊዜ ውስጥ የአለማችን የመጀመሪያው ትሪሊየነር ይሆናሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አንድ የጥናት ውጤት አመለከተ፡፡
የቢልጌትስ ሃብት በፍጥነት እያደገ መሄዱ ከቢሊየነርነት ወደ ትሪሊየነርነት ያሸጋግራቸዋል ቢባልም፣ በመዝገበ ቃላት ውስጥ ግን ትሪሊየነር የሚባል ቃል እስካሁን እንዳልሰፈረ ተዘግቧል። ኦክስፋም ኢንተርናሽናል ይፋ ያደረገው ይህ የጥናት ውጤት እንደሚለው፣ እ.ኤ.አ ከ2009 አንስቶ የሃብት መጠናቸው በአማካይ በ11 በመቶ እያደገ እዚህ የደረሰው ቢል ጌትስ፣ እድገቱ በዚሁ መጠን እየጨመረ ከቀጠለ እድሜያቸው 86 አመት ሲሞላቸው፣ የአለማችን የመጀመሪያው ትሪሊየነር ይሆናሉ ተብሎ ይገመታል፡፡
እ.ኤ.አ በ2006 የቢል ጌትስ የሃብት መጠን 50 ቢሊዮን ዶላር እንደነበር የዘገበው ፎርብስ፤ በአስር አመታት ጊዜ ውስጥ የተጣራ ሃብታቸው ከፍተኛ ጭማሪ በማሳየት፣ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016 ላይ 84.4 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንም ገልጧል፡፡

  በተለያዩ ድረገጾች የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የመሆን ዕቅድ አለው የሚል መረጃ በስፋት ሲሰራጭበት የከረመው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ፣ መረጃው ሃሰተኛ መሆኑን በመግለጽ፣ ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት የመወዳደር እቅድ እንደሌለው አስታውቋል፡፡
ዙክበርግ በቅርቡ ባልተለመደ ሁኔታ ፖለቲካ ቀመስ አስተያየት መስጠቱን ተከትሎ፣ ወደ ፖለቲካው አለም የመግባትና ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት የመወዳደር እቅድ እንዳለው የሚጠቁሙ መረጃዎች በስፋት ሲሰራጩ መሰንበታቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፤ ግለሰቡ ግን ሰሞኑን ከአንድ ድረገጽ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ መረጃውን ማስተባበሉን ዘግቧል፡፡
“የሚወራው ነገር ሃሰት ነው፡፡ እኔ ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት የመወዳደር እቅድ የለኝም፡፡ ሙሉ ትኩረቴን የማደርገው የፌስቡክን ማህበረሰብ በመገንባትና ከባለቤቴ ጋር ባቋቋምነው ቻን ዙክበርግ ኢኒሺየቲቭ የተሰኘ ድርጅት አማካይነት የበጎ አድራጎት ስራዎችን በመስራት ላይ ነው” ብሏል ዙክበርግ፡፡
ዙክበርግ ለፕሬዚዳንትነት የመወዳደር እቅድ እንደሌለው ያስታውቅ እንጂ፣ ወደ ፖለቲካ የመግባትም ሆነ በመንግስት መዋቅር ውስጥ የመስራት እቅድ ይኑረው አይኑረው በግልጽ ያለው ነገር እንደሌለ ዘገባው ገልጧል፡፡
ዙክበርግ ፕሬዚዳንት የመሆን እቅድ አለው የሚለውን ጭምጭምታ ያጠናከረው ደግሞ፣ የፌስቡክ ኩባንያ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ በቅርቡ ባደረገው ማሻሻያ፣ ዋና ስራ አስፈጻሚው በፖለቲካዊ ምርጫ የመወዳደር መብት እንዲኖረው በሚያስችል መልኩ ማስተካከሉ ነው ተብሏል፡፡

 አለማቀፉ ማህበረሰብ እየጨመረ ለመጣው የናይጀሪያ የሰብዓዊ ድጋፍ ፍላጎት አፋጣኝ ምላሽ የማይሰጥ ከሆነ፣ በመጪዎቹ 12 ወራት ጊዜ ውስጥ 90 ሺህ ያህል የአገሪቱ ህጻናት በምግብ እጥረት ሳቢያ ለሞት ሊዳረጉ እንደሚችሉ ዩኒሴፍ አስጠንቅቋል፡፡
በአገሪቱ የተከሰተው ሰብዓዊ ቀውስ ተገቢውን ድጋፍ ባለማግኘት በአለማቀፍ ደረጃ ቀዳሚው እንደሆነ ያስታወቀው ተቋሙ፤አሸባሪው ቡድን ቦኮ ሃራም ከሚያደርሰው ጥቃት ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ ስደቶችና መፈናቀሎች የአገሪቱን 450 ሺህ ህጻናት ለከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂ ሊያደርግ እንደሚችል ጠቁሞ፣ ተገቢው ድጋፍ ካልተደረገ በመጪዎቹ 12 ወራት ጊዜ ውስጥ በየቀኑ በአማካይ 240 ህጻናት ሊሞቱ እንደሚችሉ ማስጠንቀቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
ቦኮ ሃራም በስፋት ከሚንቀሳቀስባቸው የሰሜን ምስራቃዊ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ሰባት ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች አስቸኳይ የህይወት አድን እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው የጠቆመው ዘገባው፤ ከአነዚህ የአገሪቱ ዜጎች መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ህጻናት እንደሆኑም አመልክቷል፡፡
የምግብና የሰብዓዊ እርዳታ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው ዜጎችና ህጻናት ቁጥር እያሻቀበ ቢሄድም፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ ለችግሩ ተገቢ ምላሽ አልሰጠም ያለው ዩኒሴፍ፤መንግስታትና ለጋሾች አፋጣኝ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።