Administrator

Administrator

 · ዶ/ር ዐቢይ የህዝቡን ጥያቄ ለመመለስ የሚያደርጉትን ጥረት አደንቃለሁ
  · የማረምያ ቤት ሰዎች፣ እየተደረገ ያለው ለውጥ የገባቸው አይመስለኝም

     ፍቅረማርያም አስማማው ይባላል፡፡ የ31 ዓመት ወጣት ነው፡፡ ወደ ፖለቲካው ዓለም ከገባ አምስት አመት እንዳስቆጠረ ይናገራል፡፡ በእነዚህ ዓመታት ከ“ሠማያዊ” ፓርቲ የጀመረው የፖለቲካ ተሣትፎው፤ እስከ “አርበኞች ግንቦት 7” ፍለጋ አድርሶታል፡፡ የማታ ማታም ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ክስ ሊመሰረትበት ችሏል፡፡ ወጣቱ፤ ከፓርቲ የፖለቲካ ተሣትፎው እስከ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ክስና እስር ድረስ ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ አውግቶታል። በምርመራ ወቅት የገጠመውን ሥቃይም ይገልጻል። እንዴት ወደ
ፖለቲካ ህይወት እንደገባ በመግለፅ ፍቅረማርያም እንዲህ ታሪኩን ይጀምራል፡-


   ከ2005 ዓ.ም በፊት ምንም አይነት የፖለቲካ ተሣትፎ አልነበረኝም፡፡ በኋላ ግን የማያቸውና የምሰማቸው ነገሮች፣ ውስጤን ወደ ፖለቲካው ይገፋፉኝ ጀመር፡፡ ዳር ላይ ቆሞ፣ “ፖለቲከኞች ብቁ አይደሉም፤ አይረቡም” እያሉ መተቸት ተገቢ አይደለም ብዬ አምናለሁ፡፡ ከዚህ እምነት በመነሣትም፣ እስቲ ፓርቲዎች ውስጥ በመሣተፍ፣ ሁኔታውን ልየው ብዬ በመወሰን፣ ወደ ፓርቲ ፖለቲካ ገባሁ፡፡ በወቅቱ ጠንካራ እንቅስቃሴ ያደርጋሉ ተብለው የሚታመኑት ፓርቲዎች፡- አንድነት፣ ሠማያዊና መኢአድ ነበሩ፡፡ እኔም ሁሉንም ካጠናሁ በኋላ ሠማያዊ የተሻለ ሆኖ ስላገኘሁት ፓርቲውን ተቀላቀልኩኝ፡፡ ወጣቶችም ስለሆኑ ተግባብቶ ለመስራት ጠቃሚ ነው በሚል ነበር የመረጥኩት፡፡
በሽብር የተፈረጀውን “ግንቦት 7” ለመቀላቀል ጉዞ ጀምረህ ነበር---?
ሠማያዊ ፓርቲ ውስጥ ሆኜ ብዙ ነገሮች እመለከት ነበር፡፡ እነዚህ በግልፅ የሚታዩ፣ ለሠላማዊ ትግል አመቺ ያልሆኑ ሁኔታዎችን እንዴት ነው መቋቋም የሚቻለው፣ የሚለው በውስጤ ይፈጠርብኝ ነበር። በሠላማዊ መንገድ ስንታገል እስር፣ ድብደባና ወከባ ይፈጸማል፡፡ ስርአቱ ይሄን የሚፈፅመው በምርጫ ሣይሆን በደምና በአጥንት የተገነባ መሆኑን ተረዳው፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ በምርጫ ለውጥ ማምጣት አይቻልም የሚል እምነት አደረብኝ፡፡ እውነተኛ ምርጫ ማድረግ እንደማይቻል ስረዳ፣ አሁን በስርአቱ ቁንጮ ላይ የተቀመጡ ሰዎች፣ ወጣቶች ሆነው ያደረጉትን ነገር ማድረግ እችላለሁ በሚል፣ “ግንቦት 7”ን ኤርትራ ሄጄ ለመቀላቀል ወሠንኩ፡፡ እነሡ በግንቦት 20 ውስጥ ተደብቀው፣ ሌላ ሰው ግን እነሱ ያደረጉትን ማድረግ እንደማይችል ነበር የሚያስቡት፤ ስለዚህ በዚህች ሃገር ላይ የምፈልገውን ለውጥ ለማግኘት፣ እኔ በመረጥኩት መንገድ መታገል አለብኝ ብዬ ነው ያመንኩት፡፡ እኔ እንኳን ነፃነቱን ባላገኝ፣ልጆቼ የልጅ ልጆቼ፣ ይህ ጭቆና እንዳይጫንባቸው ማድረግ ይገባኛል በሚል ቁርጠኝነት ነው፣ ከዚህ ውሣኔ ላይ የደረስኩት፡፡ የትጥቅ ትግሉ የመጨረሻው አማራጭ በመሆኑ፣ ወስኜ ወደዚያው ጉዞ ጀመርኩ፡፡  
ለእኔ “ግንቦት 7” አሸባሪ የተባለበት ሂደት አሣማኝ አልነበረም፡፡ ድርጅቱ ለኔ የነፃነት ታጋይ ነው፡፡ በዚህ መነሻ ነው የመጨረሻው የመታገያ አማራጭ ያደረግሁት፡፡ በውስጡ የተሠባሠቡት ሰዎች ኢትዮጵያ…ኢትዮጵያ የሚሉ እንጂ አንድም ቀን በኢትዮጵያ ላይ ሞትን ደግሠው አያውቁም፡፡
እንዴት ነበር ወደ ኤርትራ ጉዞ የጀመራችሁት?
ከዚህ ከአዲስ አበባ ነው የተነሣነው፣ በየብስ ትራንስፖርት ባህርዳር …. ጎንደር እያልን እስከተያዝንበት ማይካድራ ድረስ 6 ቀን ነበር የፈጀብን። ጉዟችን በህዝብ ትራንስፖርት ነበር፡፡ ትልቅ ጥንቃቄ ይጠይቅ ስለነበር ነው፣6 ቀን የፈጀብን፡፡ በኋላ ትግራይ ውስጥ የምትገኘው ማይካድራ ስንደርስ፣ በደህንነቶች ተያዝን።
ኤርትራ ለመድረስ ምን ያህል ይቀራችሁ ነበር?
ብዙ አይደለም፡፡ እርግጥ ከማይካድራ እስከ ኤርትራ ልንሄድ የነበረው በእግራችን ነው፡፡ እኛን ለማሻገር የተስማማው ልጅ፣ ቢበዛ የአንድ ሠዓት የእግር መንገድ ርቀት ቢቀረን ነው ብሎን ነበር። እንግዲህ ደህንነቶች የያዙንም የእግር ጉዞውን ለመጀመር በተሰናዳንበት አጋጣሚ ነው፡፡ በወቅቱ ልንያዝ እንደምንችል በመገመታችን፣ ተይዘን ከተከሰስን ሌሎች እንደሚሉት፣ “ወደ ሱዳን ወይም ወደ ሌላ ሃገር ስደት ልንወጣ ነው አንልም፤ በግልፅ “ግንቦት 7”ን ልንቀላቀል ነው እንላለን” ብለን ተነጋግረን ነበር፡፡ ከኔ ጋር በወቅቱ ኢየሩሣሌም ተስፋው፣ ብርሃኑ ተ/ያሬድ እና አሸጋጋሪያችን ልጅ ነበረ፡፡ የሚመጣውን ሁሉ ለመቀበል ተስማምተን ስለነበር፣ ደህንነቶቹ ይዘውን፤ “የት ልትሄዱ ነው?” ሲሉን፤ ኤርትራ አልናቸው፤ “ምን ልታደርጉ?” አሉን፤ “ግንቦት 7ን ልንቀላቀል” አልናቸው፡፡
ከዚያስ ---?
ከተያዝን በኋላ አንድ ሁለት ቀን ሁመራ አካባቢ የሚገኝ የደህንነት ቢሮ አቆዩን፤ ጎንደር ሁለት ቀን አደርን፡፡ ከዚያ አዲስ አበባ አምጥተው፣ ማዕከላዊ አስገቡን፡፡ በወቅቱ እኛ አምነንላቸው ስለነበር፣ ድብደባና ግብግብ አልገጠመንም፡፡ በምርመራ ወቅትም፣ በግልጽ “ግንቦት 7ን ልንቀላቀል ነው” ስላልናቸው፣ ብዙ ጫና አላደረጉብንም፡፡
ፍ/ቤትስ የነበረው ሂደት ምን ይመስላል?
ለፍ/ቤቱም ድርጊቱን መፈፀማችንን አምነናል። “ያው ወጣቶች ነን፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያሉት ሠዎች፤ ግፍ ይፈፅማል ያሉትን ስርአት ለማስወገድ የወሠዱትን አማራጭ ነው እኛም የወሠድነው፡፡ እኛም ለሃገራችን፣ ለወገናችንና ለራሣችን የምንፈልገውን ዲሞክራሲያዊ ስርአትና ፍትህ ለማምጣት ስንዘምት ነው የተያዝነው” የሚል ቃል ነው ለፍ/ቤት ያስረዳነው፡፡ ሌላው ሠላማዊ የተባለው አማራጭ፣ የውሸት ስለሆነ፣ የወሠድነው አማራጭ ትክክል ነው ብለን ተናገርን፡፡
ፍ/ቤቱ ክሳችሁን ተከላከሉ ሲለንም፣ የቀድሞ ታጋዮችንና እነ ጀነራል ሣሞራ የኑስን፣ እነ አቶ አባይ ፀሃዬን፣ እነ አቦይ ስብሃትን ነበር በምስክርነት የጠራነው። በሃገሪቱ ያለው ስርአት ያለበትን ደረጃ ከዲሞክራሲና ከፍትህ አንፃር እንዲያስረዱም ምሁራንን አዘጋጅተን ነበር፡፡ ፍ/ቤቱ ለምስክሮቻችን መጥሪያ ከላከልን በኋላ ማረሚያ ቤቱ መጥሪያውን ወሠደብንና እንዳንከላከል ተደርገን ተፈረደብን፡፡ እኔ አራት አመት፣ ብርሃኑ ተ/ያሬድ አምስት አመት፣ ኢየሩሳሌም ተስፋው ደግሞ አራት አመት ከአምስት ወር እንዲሁም ወደ ኤርትራ ሊያሻግረን የነበረው ደሴ አራት አመት ከአምስት ወር ነው የተፈረደብን፡፡
በማረሚያ ቤት ቆይታህ ምን ታዘብክ?
እኔ በማረሚያ ቤት ስቆይ የተረዳሁት፣ ወደ ኤርትራ ተሻግሬ፣ “ግንቦት 7”ን ለመቀላቀል የወሠንኩት ውሣኔ ትክክል እንደነበር ነው፡፡ በፊት ማረሚያ ቤት ሲባል፣ አጥፊዎች ከስህተታቸው ታርመው፣ መልካም ዜጋ ሆነው የሚወጡበት ይመስለኝ ነበር፡፡ ግን በኋላ ማረሚያ ቤቶቻችን የስነ-ምግባር ቦታ አለመሆናቸውን ተረዳሁ፡፡ ሰዎች ይዘረፋሉ፣ ይደበደባሉ፣ ኢ-ሠብአዊ ድርጊት ይፈፀምባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ አስተማሪ ሳይሆን ሰዎችን ወዳልሆነ መንገድ የሚመራ ሆኖ ነው ያገኘሁት፡፡ ለምሣሌ አንድ ጊዜ ግቢ ውስጥ ረብሻ ተነስቶ፣ “ረብሻውን አስነስታችኋል” ተብለን፣ በካቴና አስረውን፣ መሬት ላይ አስተኝተው፣ ሲደበድቡን ነበር የዋሉት፡፡ በዚህ ድብደባ አንድ ልጅ እዚያው ነው ደም የተፋው፡፡ ህክምና ባለማግኘቱም ከ12 ቀናት ቆይታ በኋላ ህይወቱ ሊያልፍ ችሏል፡፡ በማረሚያ ቤት ሙስና ህጋዊ ነው የሚመስለው፡፡ ገንዘብ ያለው ጥሩ ሁኔታ ሊገጥመው ይችላል፡፡ በዚያ ላይ “እኛ ይሄን ስርአት ያቆምነው እንዳንተ ነጭ ጤፍ እየበላን አይደለም” በሚል  የስነ ልቦና ጉዳት ይደርስብን ነበር፡፡ ይሄ ደግሞ ሥርአቱን የበለጠ እንዲጠላ የሚያደርግ ነው። ለፍትህና ለዲሞክራሲ መስፈን የወደቁ ጓዶቻቸውን ረስተው፣ ጭቆናን ነው ለኛ የተረፉት፡፡ ይሄ ያሣዝናል። አሁን እነዚህ ሰዎች ከስህተታቸው ተምረው፣ በሃገሪቱ እየተጀመረ ያለውን የለውጥ ተስፋ ሊደግፉ ይገባል፡፡ መለወጥ አለባቸው፡፡ ህዝቦቿ የሚዋደዱባት፣ ፍትህና ዲሞክራሲ የሠፈነባት፣ ሁሉም ዜጋ እኩል የሆነባትን ሃገር መገንባት እንድንችል እድል ሊሠጡን ይገባል። የዚህ ለውጥ አጋዥ መሆን ያለባቸውም ለራሣቸው ሲሉ ነው፡፡
በቂሊንጦ ቃጠሎ ከተከሰሱት ውስጥ አንዱ ነበርክ። በእርግጥ በቂሊንጦ ቃጠሎ ተሣትፈሃል?
የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከመቃጠሉ ሁለት ሣምንት በፊት፣ እኔ ወደ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ተልኬ ነበር፡፡ ከዚያ በፊት ግን የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደሮች፤ እኔን ጨምሮ ዘጠኝ ሰዎችን “እስረኛ ታሳምፃላችሁ” በሚል ከሌሎች እስረኞች ለብቻ ነጥለው፣ ዞን 4 የሚባል ቦታ አስረውን ነበር፡፡ በእዚህ ቦታ እነ አቶ በቀለ ገርባ፣ ዮናታን ተስፋዬ ነበሩ፡፡ በኋላ እኔ ወደ ዝዋይ ተላኩ፡፡ እዚያ ደግሞ እነ ጀነራል አሣምነው ፅጌ የታሠሩበት ልዩ ጥበቃ የሚባል ቦታ ነው የገባሁት፡፡ ዝዋይ ሆኜ ነው የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የተቃጠለው፡፡ በወቅቱ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የነበረው እስረኛ በእጅጉ የሚበደል በመሆኑ በየጊዜው ያማርር ነበር፡፡ ቃጠሎ ከደረሠ በኋላ በተለያዩ መድረኮች መንግስትን ተጠያቂ የሚያደርጉ ነገሮች ሲነገሩ፣ መንግስትን ከተጠያቂነት ለማዳን ሁላችንንም ከያለንበት ሠብስበው ነው ክስ ያዘጋጁልን። ለምሣሌ ዶ/ር ፍቅሩ  ማሩ፤ ከቃጠሎ አንድ ቀን በፊት ሣንባቸውን ታመው ሆስፒታል ገብተው ነበር፡፡ ግቢ ውስጥ በስኳር ህመም ስለሚታወቁ፣ ክሡ ሲዘጋጅ፣ “ቸኮሌት ሆን ብለው በልተው ስኳራቸው ሲነሣባቸው ነው ሆስፒታል የገቡት” ብለው ነበር፡፡ የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል ነው - ክሣቸው፡፡ ዶክተሩ ግን፣ ሆስፒታል የገቡት በሣንባ ህመም ነበር፡፡
የናንተስ ክስ  ምን ነበር?
ያው የቂሊንጦ ማረሚያ ቤትን አቃጥለው፣ በር ላይ በሚጠብቋቸው 60 አውቶቡሶች ተሳፍረው፣ “ግንቦት 7”ን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ፣ ሌሎች ደግሞ በሞያሌ አድርገው አልሸባብን ለመቀላቀል አስበው ነበር በሚል ነው የተከሰሰነው፡፡ 60 አውቶቡስ ይሄን ኦፕሬሽን ለማሣካት እንደተዘጋጀ፣ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ ገንዘብ ለዚህ እንዳወጡ፣ እኛም እንደተደራጀን ተደርጎ ነው ክሡ የቀረበው፡፡ በተጨማሪም የማረሚያ ቤት ሃላፊዎችንና ውስጥ ያሉ በተለምዶ “አስጠጪዎች” የሚባሉ ከማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች ጋር ቅርበት ያላቸው ታሣሪዎችን ገድለን ለመውጣት እንዳቀድን ጭምር ነው ክሡ፡፡ እውነታው ግን ሌላ ነው፡፡ አስጠጪ ከሚባሉት በአደጋው የሞተው አንድ ሠው ነው፡፡ ሌሎቹ በተለያየ ሽብር ክስ የነበረባቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ይሄ አሳዛኝ ነበር። የኔ ክስ አንዱ፣ “እኛ ዝዋይን ለማቃጠል ተዘጋጅተናል፤ እናንተ ቂሊንጦን አቃጥሉ” የሚል ደብዳቤ ፅፈሃል የሚል ነበር፡፡ “ይሄ ሲሆን ደግሞ መጀመሪያ አቅደህ ነው ወደ ዝዋይ የሄድከው” የሚል ነገር ነው ያመጡት። የቀረቡብኝ ምስክሮችም፤ “በብዛት ከአማራ ልጆች ጋር ተሰብስቦ ይቆማል፣ መፅሐፍ ያነባል፣ የይስማዕከ ወርቁን ዴርቶጋዳ--” በማለት ነው የመሰከሩት፡፡
በምርመራ ወቅት ምን የተለየ ነገር አጋጠመህ?
በአዲስ አበባ በቆመው የቀይ ሽብር ሠማዕታት መታሠቢያ ሃውልት ላይ “አይደገምም” ተብሎ የተፃፈውን በኛ ላይ ደግመውታል፡፡ የኢትዮጵያ ሠብአዊ መብት ኮሚሽንም ምርመራ አድርጎ፤ በደሎች መፈፀማቸውን ለፍ/ቤት አቅርቧል፡፡ ከአካላዊ ጥቃቱ ባለፈ ባልዋልንበት ባላደረግነው ነገር፣ ክሡ እጃችን ላይ ሲደርስ፣ የተቃጠለ ሬሣ ፎቶ ስናይ ስነልቦናችን መንፈሣችንን በእጅጉ ነው የተጎዳው፡፡ ጉዳቱ እንዲህ ነው ተብሎ የሚገለፅ አልነበረም፡፡ የብዙ ሰው አዕምሮ ስለተጎዳ ነበር ፍ/ቤት ውስጥ እንደዚያ አይነት ንትርክና እሠጣ ገባ የነበረው፡፡ ከአካላዊ ጉዳቱም በላይ ነው የመንፈስ ጉዳቱ፡፡
ሌሎች ደግሞ በዚህ ተጠርጥራችኋል ተብሎ ጥቅምት 4 ቀን 2009 ዓ.ም ወደ ሸዋ ሮቢት ነው የተላኩት፡፡ በወቅቱ የገባሁ ቀን ማታ አሠቃቂ የስቃይ ጩኸት እሠማ ነበር፡፡ በኋላ እኔንም ወደ ምርመራ ወሠዱኝ፡፡ “ሰው ገድለሃል” አሉኝ፡፡ “ይሄን አላደረግሁም” አልኳቸው…በቃ ገልብጠው አስረው ደበደቡን፡፡ ይሄ አልበቃ ሲላቸው፣ የአንድ እግሬ አውራ ጣት በትንሹ መሬት እንዲነካ አድርገው፣ ሌላውን እግሬን ወደ ጎን ወጥረው፣ ሁለት እጆቼን ወደ ላይ ወጥረው አስረው ሲደበድቡኝ ነበር፡፡ ይሄ በጣም ከባድ ነበር፡፡ ደብድበውኝ ሲደክማቸው አውርደው አሣረፉኝ፡፡ በኋላ አንድ መርማሪ፣ “ፍቅረ ማሪያም ሞኝ አትሁን፤ ይሄ ከላይ የመጣ ስለሆነ የሚሉህን እሺ ብለህ ተቀበል!” አለኝ፡፡ “ይሄ እኔ የማላምንበት ነው” አልኩ፡፡ ግን በቃ የሆነ ነገር መዝገብ ላይ ጽፈው፣ በማናይበት ሁኔታ፣ እያስፈራሩ ያስፈርሙን ነበር። የሆነውን ነገር ያለ አማራጭ ነው የተቀበልኩት፡፡ እጄ ከአልጋ ጋር ታስሮ ነበር የማድረው፣ ሽንት ቤት፣ ሻወር  ቅንጦት ነበር፡፡ እጆቼ በካቴና ነበር ታስሮ ውሎ የሚያድረው። ለሁለት አጋጥመውም ያስሩናል፡፡ ሽንት ቤት ስንጠቀም፣ አንዱ ቆሞ ነበር የሚያስጠቅመው። በቃ በደንብ ነው ያጠቁን፡፡ እኔ ስለዚህ ነገር ሣወራ በእጅጉ አዝናለሁ፡፡
ክሣችሁ በመጨረሻ እንዴት ተቋረጠ?
የቃጠሎው ክስ የተቋረጠው፣ የውሸት ክስ እንደሆነና እንደማያዋጣቸው ስላወቁ ነው፡፡ በምርመራ ወቅት በሚገርም ሁኔታ “ማንን ገድልሃል” ሲባል ተጠያቂ፣ እከሌን ሲል  “አይ እሡ በህይወት አለ” ይባል ነበር… ይደርስብን ከነበረው ድብደባ ለመዳን፣ በቃ ስሙን የማላውቀውን ሰው ነው የገደልኩ እንድንል ይደረግ ነበር፡፡ ለአስራ አንድ ሰው ሞት ተጠያቂ ነህ ተብሎ የነበረ ልጅ፤ በኋላ ሁለት ሰዎች በህይወት ስለተገኙ ተብሎ፣ ሁለቱ ሰዎች ተቀንሠውለታል፡፡ ይሄን ይመስል ነበር ጉዳያችን፡፡ በዚህ ምርመራ በደረሠብን ድብደባ፣ አብዛኞቹ በእጅጉ ተጎድተው መሄድ፣ መቀመጥ፣ መራመድ አቅቷቸው ነበር፡፡ ለመናገር የሚከብዱ አሠቃቂ በደሎች ናቸው የተፈፀሙብን፡፡ ብልቱ የተኮላሸ፣ እግሩ ከጥቅም ውጪ የሆነ ሁሉ አለ፡፡
አሁን በአገሪቱ ላይ እየታየ ስላለው የለውጥ ነፋስ ምን ትላለህ?
እርግጥ እኛ ከእስር ወጥተናል፤ ግን ዛሬም አብረውን የተከሠሱ ሠዎች ከእስር አልወጡም። ሌሎችም መፈታት ያለባቸው አሉ፡፡ በተረፈ ዶ/ር አብይ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ የትግል ውጤት ናቸው፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ የትግል ጥያቄ ተከትለው እየሄዱ ነው ያሉት፡፡
አሁንም ግን በፊት የነበረው የኢህአዴግ ጉልበተኛነት በማረሚያ ቤት አለ፡፡  እውነቱን ለመናገር፣ የማረሚያ ቤት ሰዎች ሃገሪቱ ለይ እየተደረገ ያለው ለውጥ የገባቸው አይመስለኝም፡፡ ዶ/ር አብይ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ጥያቄን ለመመለስ የሚያደርጉትን ጥረት አደንቃለሁ፡፡ ኢትዮጵያዊነት እንደ ሃጢያት በሚታይበት ሃገር ላይ እሣቸው ይሄን ሃሣብ አጉልተው መምጣታቸው ጥሩ ነው፡፡ አሁን የሚታየው ነገር ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ፈጣሪ ከረዳን የተሻለ ነገር ይመጣል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

• “ሥራቸው የሞራል ልዕልና መፍጠር ነው፡፡ የሌብነት ምሽግ መኾን አይችሉም፤”
• “ሃይማኖት በመንግሥት፣ መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ አይገባም የሚለው ሚዛን ያስፈልገዋል፤”



    የሃይማኖት ተቋማት በውስጣቸው የተሰገሰገውን የሌብነት ድር በመበጣጠስ፣የሞራል አስተማሪነታቸውን በተግባር እንዲያሳዩ ያስገነዘቡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ከእንግዲህ መንግሥታቸው  በተቋማቱ ውስጥ የሚፈጸምን ዘረፋና ሌብነት በቸልታ እንደማያልፈው አስጠነቀቁ፡፡
“ሃይማኖት በመንግሥት፣ መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ አይገባም፤”የሚለው የሕገ መንግሥቱ ድንጋጌ ትክክለኛ መርሕ ቢኾንም፣ የሃይማኖት ተቋማት የሚሰበስቡት መባ እና ዘካ የሕዝብ ሀብት እስከኾነ ድረስ መንግሥት አጠቃቀሙን የመቆጣጠር ርምጃ እንደሚወስድ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡
የሃይማኖት ተቋማት ገንዘብ የሕዝብ ሀብት እንደኾነና በየትኛውም ዓለም ኦዲት እንደሚደረጉ የጠቀሱት ዶ/ር ዐቢይ፣ትንሽ የሌብነት ምልክት ካዩ ፈቃዳቸውን እስከመቀማት እንደሚደርሱ አስረድተዋል፡፡ የሃይማኖት ተቋማት ከመሬት ጀምሮ ለመንግሥት ለሚያቀርቡት ጥያቄ ባለሥልጣናቱ በእኩልነት ምላሽ መስጠት የሚገባቸውን ያህል፣ በአጸፌታው የመንግሥት ጥያቄ “ምከሩ፤ ገሥጹ፤ ሰላም አምጡ” በማለት ብቻ እንደማይወሰንና እንደማይቀጥል አስረድተዋል፡፡ “በዕለት ተዕለት የሃይማኖት ሥራ መንግሥት አይገባም፤ በመንግሥት የዕለት ተዕለት ሥራ ሃይማኖት አይገባም፤ ግን ደግሞ ቀይ መሥመርና ድንበራችን ሁሌ የቆመና የማይገናኝ አይደለም፤” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ አጠቃላይ መርሑ ትክክል ቢኾንም ዘወትር እንደማይሠራና ሚዛን እንደሚያስፈልገው አስገንዝበዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አያይዘውም፣“የሃይማኖት ተቋማት ዋነኛ ሥራቸው፣የሞራል ልዕልና መፍጠር ነው፤ የሌብነት ምሽግ መኾን አይችሉም፤ የለባቸውም፤ አላግባብ መባ እየሰበሰቡ ምን ላይ እንዳዋሉት የማይታወቅ ከኾነ ከእነርሱ የሚጠበቀው የሞራል ልዕልና ይጠፋና የሚያስተምሩትም ምእመን ሌባ ይኾናል፤”በማለት በውስጣቸው የተሰገሰገውን የሌብነት ድር በመበጣጠስ እንዲሁም ሃይማኖት በጥበብና በዕውቀት በባለሥልጣናት ላይ የሚፈጥረውን ተጽዕኖ በመጠቀም፣ መንግሥትን በተግባር ለማስተማር ቀዳሚውን ድርሻ እንዲወስዱ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡ ባለፈው ረቡዕ፣ በሼራተን አዲስ የተካሔደውን 4ኛውን ሀገር አቀፍ የፀረ ሙስና ጥምረት ጠቅላላ ጉባኤ በንግግር የከፈቱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣መንግሥታዊና ሕዝባዊ ተቋማትን ከተደራጁ ሌቦች ለመከላከልና ለማጠናከር የሚደረገው ትግል፣ በመንግሥት ብቻ ከዳር የማይደርስ በመኾኑ፤ የሃይማኖት አባቶችን ጨምሮ ሲቪል ማኅበራት፣ የአገር ሽማግሌዎችና ታዋቂ ግለሰቦች፣ ዘርፎ መክበርንና ሰርቆ አለማፈርን የሚያበረታታውን ባህልና አስተሳሰብ እያወገዙና እያጋለጡ በምሳሌነት በመዋጋት ለሕዝቡ ትምህርት እንዲኾኑ ጠይቀዋል - “እስኪ ምሳሌ ኾናችሁ ተገኙ፤ምሳሌ ኾናችሁም ታገሉ፤የሠራችሁትንም ለትምህርት እንዲኾን ለሕዝብ አሳዩ፡፡”

 ግጥም በጃዝ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ የ “ደብተራው” አጭር ተውኔት አንደኛ ዓመት ክብረ በዓልን ያከብራል፡፡
በዚህ ምሽት ባለፈው አንድ አመት ውስጥ ከተላለፉት የ “ደብተራው” ተውኔቶች የተመረጡ ክፍሎች ተቀናብረው ለተመልካች የሚቀርብ ሲሆን፤ አንድ አዲስ የ “ደብተራው” ተውኔትም ይቀርባል ተብሏል፡፡ በተጨማሪም ገጣሚ በድሉ ዋቅጀራ (ዶ/ር)፣ በእውቀቱ ስዩም፣ አርቲስት ጌትነት እንየውና ሙአዘ ጥበባት ዳንኤል ክብረት የተመረጡ የጥበብ ስራዎቻቸውን ለታዳሚያኑ ያቀርባሉ፡፡
የመግቢያ ዋጋ 100 ብር ሲሆን ትኬቱ በጃፋር መፅሐፍት መደብር (ኮሜርስ ተወልደ ህንፃ) እንዲሁም ዮናስ መፅሐፍት መደብር (ብሔራዊ ትያትር በረንዳ) ይገኛል፡፡ በዕለቱም ራስ ሆቴል በሚገኘው፣ ጦቢያ ግጥምን በጃዝ ቢሮ ማግኘት እንደሚቻል አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡


Saturday, 02 June 2018 11:58

ሴት ስትሆን

ሴትነት ምንድን ነዉ;
ብለህ የሰጠሀኝ ከባድ የቤት ስራ
መልሱ እኔንም ከብዶኝ ቃላት እመርጣለሁ
ሀሳብ አወጣለሁ ሀሳብ አደራለዉ
ሴትነት ምንድን ነዉ;
ሲመስለኝ
በሴትነት ጥልቅ ዉስጥ እጅግ የተለየ ሁለት
አለም አለ
እሷ
ከሁለቱ መካከል ከድንበሩ ስፍራ
ለሁለት ተወጥራ የምትኖርበት
ከሁለት የደቀለ ሶስተኛ አለም አላት::
ሌላ እንዴት ነበረ ሴትነት ትርጉሙ;
ሴትነት መንፈስ ነዉ፡፡
ልክ ... እርኩስ ደግ ብለህ እንደምትፈርጀዉ
እንደምትለምነዉ… ወይ እንደምታበረዉ
አማትበህ አርባ ክንድ
እንዲህ ነዉ ቅኝቱ ሴትነት ሲነጋ ሴትነት ቀን
ሲረፍድ፡፡
እንጂ ሴት ህይወት የላትም
ወይ ቀድሞ አልተሰጣትም
ወይንም ስጦታዋን ኋላ ነፍገዋታል
ትኖር ትምሰል እንጂ እስትንፋስዋ የታል::
ዉስጧ የነገሰዉ በአይን የሚታየዉ…
የሌላ ሰዉ አጥንት፤ የሌላ ሰዉ ስጋ፤ የሌላ ነፍስ
ነዉ::
እጆቿ ሲቆርሱ አፍዋ ቢከፈትም
የገባዉ ካንጀቷ ይበተናል የትም::
ስትባክን ብትታይ ቀንሌት በጎዳና
ስታመላልስ ነዉ ሌሎችን ተጭና::
ብቻ ይህ ሴትነት ባህል ካረቀቀዉ፤ አባባል
ካነጸዉ ቁንጽል ትርጉም ዉጪ
ሴትን ሆነዉ ሲያዩት
በስጦታ ሲሰጥ ፤ በነፍስ ሲገባ ብቻ የሚገለጥ
ብዙ አንድምታ ያለዉ
ዉስብስብ ቅኔ ነዉ፡፡

Saturday, 02 June 2018 11:57

የግጥም ጥግ


 የአንዳንድ ቀን ግጥሞች
መዓዛ
አንዳንዴ
መክተቢያ ቀለሙን በጅ ባልያዙበት
ማስፈሪያ ወረቀት በማይገኝበት
ጭው ያለ በረሀ
ቀን እየጠበቁ በዉልብታ መጥተው
ዉብ ሆነው ለመግጠም በሀሳብ ተፀንሰው
ሳይደምቁ ሳይሰፍሩ
መልሰው ላይመጡ ቀልጠው የሚቀሩ
በጅ ያልተጨበጡ ያልታዩ ያልጠሩ
ብቻ … ቀልብ የሚያሸፍቱ
የሚያቁነጠንጡ
ስሜት የሚያነጥሩ
የአንዳንድ ቀን ግጥሞች
የምናብ ስንኞች፡፡

 ለህጻናት ምቹ አገራት፡- ሲንጋፖር፣ ስሎቬኒያ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን

   በመላው አለም ከሚገኙት ህጻናት ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ወይም 1.2 ቢሊዮን ያህሉ የድህነት፣ ግጭት ወይም ጾታዊ መድልኦ ሰለባዎች መሆናቸውን አለማቀፉ የረድኤት ተቋም ሴቭ ዘ ችልድረን፤ ባለፈው ረቡዕ ባወጣው አለማቀፍ ሪፖርት አስታውቋል፡፡
በአለማችን አንድ ቢሊዮን ህጻናት በድህነት በተጠቁና 240 ሚሊዮን ህጻናት ግጭት ባለባቸው አገራት ይኖራሉ ያለው ሪፖርቱ፤ 575 ሴት ህጻናት ደግሞ ጾታዊ መድልኦ በተንሰራፋባቸው አገራት ውስጥ እንደሚኖሩ አመልክቷል፡፡
ከግማሽ በላይ የሚሆኑት የአለማችን ህጻናት ድሃ በመሆናቸው፣ በጦርነት አካባቢዎች በመኖራቸውና ሴት በመሆናቸው ሳቢያ የከፋ ህይወት እየመሩ ይገኛሉ ያለው የተቋሙ ሪፖርት፣ ያለ ዕድሜ ጋብቻ፣ የጉልበት ስራና የምግብ እጥረትም የአለማችንን ህጻናት ክፉኛ እየፈተኑ ከሚገኙ ተግዳሮቶች መካከል እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
ሴቭ ዘ ችልድረን በ175 የአለማችን አገራት ላይ የሰራውን ጥናት መሰረት አድርጎ ባወጣው ሪፖርት፤ ምንም እንኳን ካለፈው የፈረንጆች አመት ጋር ሲነጻጸር ዘንድሮ በአብዛኞቹ የአለማችን አገራት፣ የህጻናት የችግር ተጋላጭነት ቢቀንስም፣ በ40 አገራት ግን ችግሩ ተባብሶ መቀጠሉን አስታውቋል፡፡
ህጻናት በከፍተኛ ሁኔታ ለድህነት፣ ግጭትና ጾታዊ መድልኦ የተጋለጡባቸው ቀዳሚዎቹ የአለማችን አገራት ሁሉም ከአፍሪካ ናቸው ያለው ሪፖርቱ፤ ኒጀር፣ ማሊና ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ደረጃን መያዛቸውን አመልክቷል፡፡ ለህጻናት ምቹ የተባሉት የአለማችን አገራት በአንጻሩ ሲንጋፖር፣ ስሎቬኒያ፣ ኖርዌይና ስዊድን ናቸው፡፡

ይድረስ ለሁለቱም አገራት  መሪዎች፡-
ግብፅና ኢትዮጵያ የቆየ ታሪካዊ ግንኙነት አላቸው፤ ከሰማኒያ በመቶ በላይ ከኢትዮጵያ የሚፈልቀው ጥቁር አባይ፣ ከነጭ አባይ ጋር ተጨምሮ፣ ለግብፃውያን የህልውናቸው መሰረት ነው፡፡ የጥንትም ይሁን ዘመናዊ የግብፅ መሪዎች፤ ይህንን የግብፃውያን የህልውና  መሰረት መጠቀምና ማስቀጠል የሚፈልጉት በኢትዮጵያውያን ኋላ ቀርነት፣ ደካማነትና ኪሳራ ላይ ብቻ ሆኖ መዝለቁ፣ የሁለቱን ሃገሮች ግንኙነት እስከ ዛሬ አሉታዊ አድርጎታል፡፡ ይህ በዲፕሎማሲ ቋንቋ፣ በተሸናፊነት መንፈስ፣ በኢትዮጵያ መሪዎችና ፖለቲከኞች የሚሸፋፈን ቢሆንም፣ በኢትዮጵያውያን ዜጎች ልቦና ሁሉ እንደ ሰማዩ ፀሃይና ጨረቃ፣ በግልፅ ለዘመናት ለተያዘ ቅሬታና የቁጭት ስሜት ምክንያት ነው፡፡
ቀደም ብሎ ግብፃውያን መሪዎች ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ፣ ጥንታዊውን የሁለቱን ሃገሮች የሃይማኖት ግንኙነት ይጠቀሙ ነበር፤ ውጤታማም ነበሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ግን የቀጠሉት የሃገራችንን የውስጥ ጉዳይና ቅራኔ፣ ኋላ ቀርነታችንን በመጠቀም፣ እሳቶቻችንን በመቆስቆስ፣ በማንደድና ቤንዚን በመጨመር ሲሆን ውጤታማ ሆነው ዘልቀዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ግብፃውያን ዘመን የፈጠረላቸውን፣ ለፍትሃዊ ተጠቃሚነት ግድ የሌለውን ዓለምና በተለይ የአረብ ሃገሮችን አጋርነት ተጠቅመው፣ የሃገራችንን የመልማት፣ የተፈጥሮ ሃብቷን የመጠቀም መብቷን ሙሉ ለሙሉ አፍነው ቆይተዋል፡፡
እስካሁን በዚህ አጠቃላይ አውድ የቀጠለው የአገራቱ ግንኙነት፣ ትላንትም ዛሬም፣ ለወደፊቱም ለሁለቱም አይጠቅምም፡፡ በተለይ ለግብፃውያን ደግሞ የበለጠ አይበጅም፡፡ ዛሬ ሁኔታዎች እያዘገሙም ቢሆን መቀየራቸውን መታዘብ ይቻላል፣ ወደፊትም መቀየራቸውም ግዴታ ነው፡፡ አዝጋሚው ሂደትና በተለይ የግብፅ መሪዎች ፍላጎት ግን ሁለቱንም እየጎዳ መቀጠሉን፣ ወደፊት ደግሞ የበለጠ ጉዳትና ኪሳራ እንደሚሆን መረዳት ተገቢ ነው፡፡
የሁለቱ ሃገሮች አጀንዳ ዛሬ ለሃይል ምንጭ ብቻ ነው ተብሎ እየተገነባ ካለው፣ ከህዳሴው ግድብ የውሃ አሞላልና ከውሃ ክፍፍል በላይ፣ በወቅቱ የውሃ ሃብቱን የመጠቀም፣ በተለይ በኢትዮጵያ በተፈጥሮ ላይ ያለው ጥገኝነት በወቅቱ የቀነሰ ህዝብና ኢኮኖሚ ዕውን የማድረግ፣ ተፈጥሮን የመጠበቅና ግብፃውያን መሪዎች በኢትዮጵያውያን ስሜት ላይ የፈጠሩትን ቁስል የሚያሽር ግንኙነት፣ እውነተኛ ትብብርና ዕርቅ መሆን ይኖርባቸው ነበር፡፡ በሁለቱም ሃገሮች መሪዎች እየተደረጉ ያሉ ድርድሮች፣ ውይይቶችና ስምምነቶች የጋራ ሆነው፣ በዚህ መሰረት ላይ ካልተፈፀሙ፣ ለሁለቱም ህዝቦች ችግርን የሚያራዝሙ፣ ከላይ የተጠቀሰውን የኢትዮጵያውያን ስሜት የሚያስቀጥሉ ብቻ ይሆናሉ፡፡ አለባብሰው ቢያርሱ ደግሞ ነገ በአረሙ መመለስ አይቀርም፡፡ እርሻውን በሁለቱ ሃገሮች በእየተራ እንመልከተው፡፡
አባይ፣ የህዳሴው
ግድብና የኢትዮጵያ መሪዎች
የኢትዮጵያ መሪዎች የወቅቱን ትኩሳትና ግርግር ብቻ ከማብረድ በላይ፣ ታሪካዊውንና ወቅታዊውን የግብፅ መሪዎችን ፍላጎቶችና ችግሮቻቸውን፣ ለሁለቱም ሃገር ህዝቦች ያተረፉትንና ወደፊት የሚያተርፉትን ችግር፣ የቀጠለውን የኢትዮጵያውያንን እውነተኛ ስሜት፤ ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ፣ ለእራሳቸው ለግብፃውያን ሁሉ ለማስገንዘብ  መስራት ይገባቸው ነበር፡፡ ለሁሉም ስለሚጠቅም፡፡
የዛሬውን የህዳሴ ግድብ ጨምሮ የአባይ ውሃን በኢትዮጵያ ለልማት ለመጠቀም ዕቅዱ የተዘጋጀው በንጉሱ ዘመን ቢያንስ ከዛሬ ሃምሳ ዓመታት በፊት በአሜሪካኖች ድጋፍ ነበር፡፡ የአሜሪካኖች የድጋፍ ጅምር ለግብፅ የርዕዮተ ዓለም አሰላለፍ የተመዘዘ ቢጫ ካርድ ብቻ ስለነበር፣ ግብፅ አሰላለፏን ስታስተካክል፣ ለዓመታት የተደረገው ጥናት፣ በሁለት ቀናት ተቋርጦ፣ ዕቅዱ ከግማሽ መቶ አመታት በላይ አቧራ ሲጠጣ ቆይቷል፡፡
ከምስራቁ ወደ ምዕራቡ ዞረው ለጊዜው የተሳካላቸው የግብፅ መሪዎች፣ ኢትዮጵያ በእራሷ አቅም ልትሰራ የምትችለውን ልማት ለመከላከል የመረጡት ስልት፣ በሃገሪቱ ችግሮች ስንጥር በማስገባት ማዳከምን ነበር፡፡ ጀብሃን፣ ሻዕቢያን፣ ወያኔንና ሌሎችንም መሳርያና ችግሮቻችንን ብቻ ከላይ (መሰረታዊ መንስኤዎቻቸውን ሳይሆን) ማስታጠቃቸውን፣ ዛሬም የአኩራፊዎቻችን አለኝታና መጠጊያ ሆነው መዝለቃቸው ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ለሶማሊያ አሸባሪዎች፣ለወራሪው ሻዕቢያ መሳርያ አቅራቢም ነበሩ፤ ዘርዝሮ መጨረስ አይቻልም። ከዚህ ጋር ግብፅ፣ ኢትዮጵያ ዓባይን ለሚመለከቱ ማንኛውም ዕቅዶች፣ ከየትኛውም ሃገር የገንዘብ ተቋም ብድር፣ እርዳታና የቴክኒክ ድጋፍ እንዳታገኝ ሳታመነታ በመስራቷና ስለተሳካላት ጭምር፣ ዛሬ የሃገራችን መሪዎች ግፉን አሜን ብለው ሊቀበሉት ችለዋል፡፡
በዚህ ሂደት ኢትዮጵያ በረጅም የእርስ በእርስ ጦርነት፣ በችጋርና በመከራ ውስጥ እየተንፏቀቀች፤ በድርቅና በርሃብ የሰው ህይወት እየጠፋ፣ ለስድሳ ዓመታት ስትዘልቅ፣ የተገነጠሉትን ትተን፣ የህዝብ ቁጥሯ ዛሬ ከመቶ ሚሊዮን በላይ ሆኗል፡፡ ከሃምሳ ዓመታት በፊት ሃያ አምስት ወይም ሰላሳ ሚሊዮን ስለነበር የህዝብ ቁጥሯ በአራት እጥፍ ሲያድግ፣ እንደ ጥንቱ ሙሉ ለሙሉ የተፈጥሮ ጥገኛ እንደሆነ ነው፡፡ ቀደም ብሎ የተሻለ ውጤታማ የሆነውን የአባይ ውሃ በተወሰነ መጠን የማልማት ዕድል ቢኖራት፣ሃገሪቱ የጦርነት አውድማ ባትሆን፣ትምህርት ቢስፋፋና እድገት ብታስመዘግብ ኖሮ፣ዛሬ ሃገሪቱ የተመጠነ የህዝብ ቁጥር፣በተወሰነ መልኩ ከተፈጥሮ ጥገኝነት የተላቀቀ ኢኮኖሚና ህዝብና ሌሎች የተፈጥሮና የውሃ ሃብቶቿን ለመጠቀም የሚያስችል አቅም ይኖራት እንደነበር ግልፅ ነው፡፡ ዛሬ ለግብፅም ለኢትዮጵያም የተሻለ ይሆን ነበር፡፡
ባለቤቶች ራሳችን ብንሆንም፣ በግብፅ መሪዎች የሚደገፈው ኋላ ቀር ጉዞ ግን ሌሎችን ጨምሮ የተፈጥሮ ሃብት የሆነውን አባይ ውሃ በመጠኑ ቀንሶታል፡፡ የተፈጥሮ ሃብቶች (ውሃን ጨምሮ) ለሃገራችን ያላቸውን አስፈላጊነት ደግሞ ከነበረው በአራት እጥፍ ጨምሮታል ማለት ይቻላል፡፡
የግብፅ መሪዎችን አፍራሽና አፋኝ ፍላጎት ለመቋቋምና መብታችንን መጠቀም ለመጀመር ደግሞ ዘገየን፤ ዋጋ አስከፈለን እንጅ እስከ መጨረሻው ሊገታን አልቻለም፡፡ የህዳሴውን ግድብ ጥርሳችንን ነክሰን ጀምረነዋል፤  ወደፊትም እንቀጥላለን፤ የቆመ መራመዱ ስለማይቀር፣ መቀጠሉ ግዴታ ይሆናል፤ በተለያየ ዓይነትና መጠን፡፡ የኢትዮጵያውያን በተፈጥሮ ሃብታቸውና በአባይ ውሃ የመጠቀም መብት፤ ወቅቱንና ጊዜውን፣ መልኩን፣ ወርዱንና ስፋቱን የሚወስኑት፤ ዓለም አቀፍ ህጎችና ስምምነቶች፣ እንዲሁም  የእራሳችን ሃገር ውስጣዊ አቅም ናቸው፡፡
ከነዚህ ሁሉ በታች ግን በኢትዮጵያ ያለውና ወደፊት የሚኖረው የተፈጥሮ ሃብቶች፣ የውሃ ሃብቱ ተጨባጭና ወቅታዊ አስፈላጊነት፣ ከታችኛው ተፋሰስ ሃገሮች በተለይ ከግብፅና ከሱዳን ጋር ያሉን ታሪካዊና ወቅታዊ ግንኙነቶች፣ ታሪካዊ ቁርሾዎችና ጠባሳዎች ድርሻ አይኖራቸውም ማለት አይቻልም፡፡ ይህንን ለግብፅ መሪዎች በግልፅ ቋንቋ ማስረዳት ተገቢ ነበር፡፡ በተለያዩ ስልቶች ለሃገራችን ጉዞ ዕንቅፋት መሆናቸውን ማቆም፣ እርም ማለት እንደሚገባቸው ዛሬ ሳይሆን በፊትም ሊነገራቸው ይገባ ነበር፡፡ ከህዳሴው ግድብ ግንባታ በፊትም፣ በኋላም፣ ሁልጊዜ እስካልታረሙ ድረስ፣ የመሰረት ድንጋዩ ሲጣልም ቢሆን አብዩ መልዕከት መሆን ነበረበት፡፡
ይቻላል ተብሎ የተጀመረው የህዳሴው ግድብ መሰረት ሲጣል፣ ሃገራችን ሃብቷን ለምን ሳትጠቀም እንደዘገየች፣ ዛሬም እንዴት እንደምትገነባው ተገልፆ፣ ከታሪካችን የወደፊቱን ማመላከት ለሁሉም ጠቃሚ ነበር፡፡ ኢትዮጵያውያን የመልማትና የመጠቀም መብታቸውን በግብፅ ታፍነው ለዘመናት ከዘለቁ በኋላ ይህንን አፈና ለመቀልበስ የተጀመረውን የህዳሴ ግድብ ግንባታ፣ የአፈናውን አንዳንድ ስልቶች ከተቀበለ፣ የተሸናፊነት ስሜት ላይ የመሰረት ድንጋይ ማስቀመጥና ከዚያ በኋላ ማስቀጠል ስህተት ነው፡፡ ለወደፊቱም አቅም አይሆንም፡፡
የግብፅ መሪዎችን ግፍ አሜን ብላ የተቀበለችው ሃገር፣ የአባይን ውሃ መጠን በጣሳ የሚቀንስ ዕቅድን ይዛ የብድር፣የእርዳታና የቴክኒክ ድጋፎች ለማግኘት ሙከራ የምታደርግ አይመስልም፡፡ ባይገኝም ግን ችግሩን ለማስገንዘብ ሙከራው መደረግ፣ አጀንዳውን ሁልጊዜ ወቅታዊ ማድረግ ነበረብን፡፡ ይህን ትተን ለሃይል ማመንጫ ብቻ ብለን፣ የያዝነውን ዕቅድ የሚደግፍ ሃገርና ተቋም ዓለም ላይ ሲጠፋ እኛ የት እንዳለን፣ዓለም ምን እንደሆነች፣ የግብፅ መሪዎችንና ፍላጎቶቻቸውን ልናጠይቅበት፣ልንረዳበትና የጋራ አቋም ልንይዝበት ይገባ ነበር - ከታሪካዊ ጅምር ጋር፡፡
በውጭ ሃገር ስራ ተቋራጭ፣ በከፍተኛ ብድር ላይ የተደገፈና በእርዳታ በሚደጎም  አጠቃላይ ኢኮኖሚ የሚገነባን አንድ ፕሮጀከት የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር፤ “መሀንዲሶችም፣ ግንበኞችም፣ የፋይናንስ ምንጮችም እኛው  ነን” ብለው በኩራት መናገራቸው፣ ተገቢ ሳይሆን ከፍተኛ ስህተትም ነበር፤ ይህ የተጫነብንን ግፍ፣ በፈቃዳችን እንደመረጥነው ምርጫና ችሎታችን የሚያስገነዝብ ንግግር ዛሬም ድረስ ይደጋገማል፡፡ አስተሳሰቡ ሲቀጥል መንግስት ለስኳር ፋብሪካዎች ግንባታ ይውላል በማለት ለዓለም ገበያ ያቀረበውን የቦንድ ብድር የተበደረው ገንዘቡ ለምን እንደሚውል (ዛሬ ቢባክንም) ከመግለፅ በተጨማሪ ለህዳሴው ግድብ ግንባታ በጭራሽ እንደማይውል አበክሮ፣ ደጋግሞ፣ በመግለፅ ምሎ ተገዝቶ ነበር፡፡ በፍርሃት፣ በራስ ስሜት ብቻ መሸነፋችንን፤ ግፍን አሜን ብሎ መቀበላችንን ያረጋግጣል፡፡ ከዚህ ስሜት መውጣት እጅግ በጣም ጠቃሚ ነው፡፡
በመንግስት ብቻ ተገድቦም አልቀረም፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ስለ ህዳሴው ግድብ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ቀርበው ሲናገሩ፣ ታሪክን አንስተው የገለፁትም ተመሳሳይ ነበር፤ ቆቅ ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ የሆነ፡፡ ዲያቆን ዳንኤል፤ “የአክሱም ህንፃን ስናቆም፣ ላሊበላን ስናንፅ የአለም ባንክ፣ አይ.ኤም.ኤፍ ነበሩ?” ሲሉ ራሳቸው ጠይቀው “አልነበሩም፤” ብለው ራሳቸው መልሰዋል፤- ዲያቆን ዳንኤል፡፡ በአወንታ እራሱን ለሚነቀንቀው ጋዜጠኛ “የህዳሴውን ግድብ ለመገንባትም ዛሬ እነዚህ ተቋማት ግዴታ አይደሉም፣ አያስፈልጉንም፣ በእራሳችን አቅም መገንባት እንችላለን፤” ሲሉ በስሜት ተናግረዋል፤ ከስሜት ጋር ደግሞ ስህተቶች አሉ፡፡
ዓለም ላይ ስመ ገናና የነበረውን አክሱም፣ የመን ድረስ ተሻግሮ አስተዳድሯል፣ ህንድ ድረስ የንግድ ግንኙነት ነበረው፣ ለግብፅ ክርስቲኖች ጭምር አለኝታ ነበር፤ የምንለውን ሃገርና ህዝብ ሃውልት ሲያቆም፣ ግብፃውያን ንቀውት፣ በአለም ሃገሮች አይን አይሞላም፣ ብቻውን ነበር ማለት ከፍተኛ ስህተት ነው፡፡ መነሻቸው ከመካከለኛው ምስራቅ የሆኑት፣ በእየጊዜው ከምንጫቸውና ከሌሎች ሃገራት ጋር ግንኙነቶች የነበራቸው ክርስትናችንና ንጉሱ ላሊበላ፣ ቤተ-መቅደስ ሲገነቡ፣ ብቻቸውን ነበሩ ማለት አለማገናዘብ ብቻ ነው፡፡
ዛሬ እኛ አሽቆልቁለን ዓለምና ተቋማት ተራምደው፣ እነዚህ ሁሉ አያስፈልጉንም ማለት ሞክራ ያልቻለችውን ጦጣ የሚያስታውስ ብቻ ነው፡፡ ዛሬ በግብፅ መሪዎች ፍላጎት ጫማ ስር ወድቀን በሌሎች ሃገሮች፣ በአለም ባንክ፣ በአይ.ኤም.ኤፍ አይን መሙላት አለመቻላችንን በተለይ ከአክሱም ስልጣኔ ጋር ማነፃፀር ነው ተገቢም፤ የሚጠቅመንም፡፡
በዘመናቸው ያላስፈለጋቸውን አባይ፤ አክሱማውያን ለግብፅ ወንድሞቻቸው ብቻ ቢተውት ትክክል ነበሩ፤ አባይን ተቀባይነታቸውን፣ ጥቅማቸውንና ፍላጎቶቻቸውን ለማረጋገጥ የተጠቀሙበት ግን ውሃውን መቀነስ ፣ማቀብ (መገደብ) ስለሚችሉ ነበር። ዛሬ የውሃ ሃብቱ እጅግ አስፈላጊ ቢሆንም ለዘመናት ሳንጠቀምበት የሰው ህይወት እየጠፋ፣ በችጋርና በመከራ ውስጥ ቆይተናል፡፡ ይህንን ታሪክ ለመቀየር እንደምንችል፣እንደጀመርነው ከዚህ በኋላ መቀጠል ይቻላል፡፡ ለህዝቡ ሞራል ተብሎ ከተገለፀም መቅደም የነበረበት ችግሩ ነው፡፡ ለህዝቡ ሞራል፣ መነሳሳትና እርብርብም ምክንያቱ እነዚህ የውሸትና የማስመሰል ንግግሮች አይደሉም - ከላይ የተገለፀው የዘመናት ቁጭቱ እንጅ፡፡  በሃገራችን መሪዎች የተሸናፊነት አቋም ምክንያት የግብፅ መሪዎች፣ አንድ ጊዜ ሰው፣ አንድ ጊዜ አፈር እየሆኑ እንዲቀጥሉ የልብ ልብ ሰጥቷቸዋል ማለት ይቻላል፤ እንመልከተው፡፡
ናይል፣ የህዳሴው ግድብና የግብፅ መሪዎች
ከግብፃውያኑ መሪዎች ዛሬ ደግሞ የሚጠበቀው፤ የትላንቱን ስህተት ሁሉ የሚያራግፍ፣ አፍራሽ ተልዕኮቻቸውን ሁሉ ማቆም ብቻ ሳይሆን በእውነተኛ ስሜትና ቁርጠኝነት፣ ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ሃብታችንን የመጠቀም፣ የማልማት መብቶቻችንን በማክበርና በማረጋገጥ የታሪካዊውን ግንኙነት መስመር በወቅቱ ማስተካከል ነበር፡፡ ግብፃውያን መሪዎች የዛሬውን የኢትዮጵያ መሪዎች ፖለቲካና ዲፕሎማሲ ትተው፣ ዘላለማዊውን ከላይ የተገለጠውን፣ የፀሃፊውን ጨምሮ የዜጎችን ስሜት መረዳት አለባቸው፤ ፖለቲከኞችም ከዚህ የተለየ ስሜት ይኖራቸዋል ብሎ መጠበቅ ሞኝነት ነው፡፡
ግብፅና መሪዎቿ በቅርቡም በሃገራችን የተከሰተውን ችግር ለማራገብ ሞክረዋል፤ የህዳሴውን ግድብ ግንባታ በቅኝ ግዛት ውል ለመሞገትና ንቀታቸውን ለመቀጠል ሞክረዋል፡፡ ቀደም ብለን እንደገለፅነው፤ ኢትዮጵያ በአዝጋሚ ሂደትም ቢሆን መቆም ጀምራለች፤ ተመስገን ነው፤ ግብፅና መሪዎቿ ያራገቡት ችግር ዛሬ አዲስ ተስፋን አምጥቷል፤ዶ/ር አብይ አህመድን የመሰለ መሪ። ምንም ቢሆን ግን ነገን በኢትዮጵያ በተሻለ ተስፋ መጠበቅ ግዴታ ስለሆነ፣ አቋምን በወቅቱ ማስተካከል የግብፅና መሪዎቿ ወቅታዊ ግዴታ ነበር፡፡  
ከኢትዮጵያ መሪዎች የተሸናፊነት ስሜትና ፈራ - ተባ ብለው በያዙት የዲፕሎማሲ አቋም ምክንያት የህዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ ከተጣለና በኢትዮጵያ ህዝብ እርብርብ ግንባታው ከቀጠለ በኋላም የግብፅ መሪዎች አቋም የተለያየ መልክ ነበረው፤ በመጨረሻ የነበረው ሊቀጥልበት ቢችልም፡፡
የመሰረት ድንጋዩ በተጣለ ማግስት የግብፅ መሪ የነበሩት ሁስኒ ሙባረክ ያቀኑት ወደ ምስኪኗ ኢትዮጵያ ሳይሆን ወደ ጣልያን ነበር፤ በንቀታቸው ምክንያት። ግድቡን የሚገነባው ሳሊኒ የጣልያን ስራ ተቋራጭ ስለሆነ፣ በጣልያን መንግስት በኩል እንደተለመደው እንቅፋት ለመሆን የተደረገ ሙከራ ነው፡፡ የጣልያን መንግስት፤ “ሳሊኒ ከመንግስት ቁጥጥር ውጭ የሆነ ተቋም ስለሆነ ጣልቃ መግባት አንችልም፤” በማለት ሙከራውን አልተቀበለውም፡፡ ሙከራው ወደ ሳሊኒ አልቀጠለም ወይም ቀድሞ አልተሞከረም ብሎ የሚያስብ ገልቱ የለም፤ ስለዚህ ጣልያናዊው ሳሊኒ ግን ከሃገራችን ጎን ቆሞ መቀጠሉን ለማድነቅ እንገደዳለን፡፡
እኔ በግሌ የስራ ተቋራጩን አቋምና ወቅታዊ ስሜት ለመከታተል ሞክሬያለሁ፤ በአይናቸው ከማንሞላው የመገናኛ ብዙኋን፤ ሳሊኒ የህዳሴውን ግድብ የሚገነባበት ክፍያ (ከምስኪኗ ኢትዮጵያ) በወቅቱ እየደረሰው እንደሆነና ለወደፊትም ስጋትና ጥርጣሬ እንዳለው ተጠይቆ፣ በመገናኛ ብዙሃን አንብቤያለሁ፡፡ በሳሊኒ አመራሮች የተሰጠው መልስ አንጀቴን አርሶታል፡፡ ጣልያንንም ሳሊኒንም እጅ እንደነሳሁ አለሁ፡፡ ሁስኒ ሙባረክን የተኩት የሙስሊም ወንድማማቾች ሙርሲ፤ከዚህም በላይ የግብፃውያንን ህልውና ለማስጠበቅ እዘምታለሁ፣ የጦር መሪዎቻቸውን ሰብስበው፣ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲሉ ታዝበን ነበር፡፡ በተለያዩ የውስጥ ቀውሶች በቀጠለችው ግብፅ፤ ከሙርሲ በኋላ ወደ ስልጣን ከመጡት አልሲስ፣ መጀመርያ ላይ የለውጥ አዝማሚያ ታይቶ ነበር። አል.ሲ.ስ የኢትዮጵያውያንን የመልማት ፍላጎት እንረዳለን፣ እንደግፋለን ብለው፤ ከመሪዎች አልፎ የሁለቱ ሃገሮች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትም ተጀምሮ ነበር፡፡ በሊብያ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፣ በግብፅ በኩል ወደ ሃገራቸው እንዲገቡ ከመተባበርም አልፈው መሪው፣ በአውሮፕላን ማረፍያ ተገኝተው፣ አቀባበል አድርገውላቸው ነበር፡፡ ለሁለቱ ሃገሮች የሚበጀው ተመሳሳይ ግንኙነት፣ መተባበርና መከባበር ስለሆነ፣ ተስፋን ያጫረ ጅምር ቢሆንም የቀጠለና የጎለበተ ግን አልነበረም፡፡
በሁለቱ ሃገሮች ከዚህ በኋላ የቀጠለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፤ ውይይትና ድርድሩ ሁሉ በትክክለኛው መሰረት ላይ ያልቆመ፣ በጥርጣሬና ባለመተማመን ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡ በአጠቃላይ ሱዳን የነበራትን አቋም ያስተካከለችበት፣ የግብፅ መሪዎች ግን ዛሬ የኤሌክትሪክ ሃይል ብቻ አመንጭተን የምንለቅበት ነው የምንለውን ግድብ እንኳ በሙሉ ልባቸው ለመቀበል ተቸግረዋል፡፡ እስከ ዛሬ የባከነው ጊዜ፣ ኢትዮጵያውያን ጥቂት መብቶቻችንን ለመጠቀም ሳንችል የቆየንበትን ታሪክ አልተረዱትም፡፡ አንድ ጊዜ ዝቅ ስላደረጉን የወደፊቱን ተገቢ ፍላጎቶቻችንን ከወዲሁ አልገመቱትም፡፡ ስለዚህ በዚህ የምንቀጥል ከሆነ መጨረሻው ለማንም የማይጠቅም፣ በተለይ ግብፃውያንን ዋጋ የሚያስከፍል ብቻ ይሆናል፡፡ ትላንትን ወደ ኋላ ማስታወስና ዛሬን መመልከት፣የወደፊቱን መዘዝ ለመተንበይ ያስችላል፡፡
አባይ ኢትዮጵያውያንና ግብፃውያን - እንደ መደምደሚያ
የግብፅ መሪዎች ኢትዮጵያን እንደ ጥንቱ አፍነው መቀጠል አይችሉም፤ ቢችሉም ግን አይጠቅማቸውም። ከዛሬ ሃምሳ ዓመት በፊት በነበርንበት ጉዞ ብንቀጥል፣ ከሃምሳ ዓመት በኋላ የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር አራት መቶ ሚሊዮን ይሆናል፤ እንደነበረው የተፈጥሮ ብቻ ጥገኛ ሆኖ ማለት ነው። በዚህ ወቅት ግድቡንና መስኖውን ትተን፣ ህዝቡ  ከብቶቹን ይዞ ወደ ተራሮቻችን ይወጣል፤ የውሃ ቅሉን ይዞ ወደ አባይና ገባሮቹ ይወርዳል፤ ግዴታው ነው፡፡ የሰው ዱካና የከብት ኮቴ ተፈጥሮን፣ዕፅዋትንና ውሃን ምን እንደሚያደርጉ መመልከት ይቻላል፤ ባለፉት ሃያ አምስት ዓመታት ብቻ፡፡ ያኔ ለሁላችንም አጀንዳ ላይኖር ይችላል፤ የበለጠ የምትጎዳው ሃገር ደግሞ ግብፅና ግብፃውያን ይሆናሉ፡፡
ከዚህ በመለስ የግብፅ መሪዎች በዚሁ ቀጥለው፣ ሃገራችን የጀመረችውን በተለያዩ መንገዶች የተፈጥሮ ሃብቷን  የመጠቀም መብቷን እያረጋገጠች ስትቀጥል አቅማችን ያድጋል፡፡ ያልነበረን ወንድማማችነትና ትብብር ድንገት ማምጣት ስለማይቻል፣ግብፃውያን እንደ አክሱም ዘመን፣ በወንድማማች ህዝቦች መካከል በሚኖር የትብብር መንፈስ፣ ከኢትዮጵያ ጋር የመስራት ዕድላቸው እየጠበበ ይሄዳል፡፡ በዚህ ወቅት በመካከላችን የሚኖረው ዓለም አቀፉ ህግና ስምምነት ብቻ ይሆናል፡፡ በዚህ ሁኔታም ግብፃውያን አያተርፉም፤ ስለዚህ ያዙኝ ልቀቁኝ አማራጭ ሆኖ ሊታያቸው ይችላል፡፡
በንጉሳችን የተመራውን ጉንዴትና ጉራን አናነሳውም፡፡ የሩቅ ታሪክም ቢሆን ሃገራችን ግን በዘመነ መሳፍንት ተከፋፍላ ነበር፡፡ አፄ ቴዎድሮስ ሃገሪቱን በቀላሉ አንድ አድርገው ቢነሱም፣ መጨረሻቸው እንደ ዘመነ መሳፍንት ወቅት ነበር፡፡ ንጉሱ በመቅደላ ተወስነው፤ በትግራይ በዝብዝ ካሳ፣ በሸዋ አፄ ምኒልክ፣ በላስታ ዋግሹም ጎበዜ ነግሰው ነበር፡፡ እንግሊዝ በአፄ ቴዎድሮስ የተያዙ ዜጎቿን ለማስፈታት ዕቅድ ስትነድፍ፣ የተያዘ አንድ ግንዛቤ ነበር፡፡ እንግሊዞች ለኢትዮጵያ ቅርብ ከሆኑት ቅኝ ግዛቶቻቸው፣  ግብፅና ሱዳን ጦር ለማዝመት ሃሳብ ነበራቸው፡፡ ኢትዮጵያውያንን ምን ቢከፋፍሉ፣ ከእነዚህ ሃገሮች የሚሰነዘር ጥቃት አንድ ላይ እንደሚያቆማቸው ስለተረዱ፣ ከህንድ ነበር ጦር ያዘመቱት፡፡ ሶማሊያና ዛይድ ባሬ እስካፍንጫቸው ታጥቀው፣ ኤርትራና ሻዕብያ በራሷ በግብፅ እስፖንሰርነትም በቅርቡ አይተውታል፡፡ ዛሬ ደግሞ ሁኔታዎች፣በኢትዮጵያ ተቀይረዋል፣ የተፈጠረ አቅም፣ የተያዘ ግንዛቤና ስምምነት አለ፤ ይቀጥላል፡፡


      አንዲት የቆቅ ልጅ የስንዴ እሸት ትርክክ ብሎ በስሎ በሚገኝበት እርሻ አጠገብ ወጥመድ ተጠምዶ አይታ እናቷን፤
“እናቴ ሆይ፤ እሸት አምሮኝ ነበር፣ ከዚህ ማሣ ገብቼ እንዳልበላ ወጥመድ እንዳይዘኝ ሰጋሁ፣ ምን ይሻለኛል?” ስትል ጠየቀቻት፡፡
እናቷም፤ “ተይ ልጄ ይቅርብሽ ትያዣለሽ አይሆንም” ብላ መከረቻት፡፡
 ልጅቷ ግን “ግድየለሽም አይዙኝም፣ ትንሽ ተክ ተክ አድርጌ ልውጣ” አለቻትና ገብታ ስትበላ ያ ወጥመድ እናቷ እንደፈራችው እግሯን ጥርቅም አድርጐ ያዛት፡፡
መቼም መከራ በመጣ ጊዜ በመጀመሪያ የሚታሰቡት ወላጆች ስለሆኑ፤ ያቺ የእናቷን ምክር አልሰማ ያለች ልጅ፤ “እናቴ ኧረ ተያዝኩልሽ” አለቻት፡፡
እናትየዋም፤ “ምነው ልጄ አስቀድሜ ነግሬሽ አልነበረም? አሁን ምን ላደርግልሽ እችላለሁ?” አለቻት፡፡
እማምዬ እባክሽ እርጂኝ? ፍቺልኝ ገመዱን?”
“በምን እጄ?”
“ታዲያ እንዴት ልሁን? ምን ይበጀኝ የኔ እናት?”
በዚህ ጊዜ እናት ለልጁዋ ምንጊዜም ምክር አዋቂ ናትና፤
“ዝም ብለሽ የሞትሽ መስለሽ ተኝ፤ ባለወጥመዱ ሲመጣ ሞታለች ብሎ ፈትቶ ይለቅሻል፡፡ ያኔ ታመልጫለሽ” አለቻት፡፡
ልጅ እንደተባለችው አደረገች፡፡
ባለወጥመዱ ሰው ሰብሉን ጐብኝቶ መጣና ቢመለከት ዝልፍልፍ ብላ ተኝታ ዐይኗን ጨፍና አገኛት፡፡ አጅሬ የሞተች መሰለውና፤ “አዬ ጉድ ወጥመዴ ቆቅ ይዞልኝ ነበረ፡፡ ነገር ግን ሞተች” አለና አዘነ፡፡
ጓደኛው ከበላዩ ሰብል ይጠብቅ ነበርና፤
“ወንድም” ብሎ ተጣራ “ወጥመዴ ቆቅ ይዞልኝ ነበረ፡፡ ነገር ግን በክታ አገኘኋት”
ባልንጀራውም፤ እስቲ ወደ ላይ አጉናት” አለው፡፡
ባለወጥመዱ ወደ ሰማይ ወርወር አደረጋት፡፡
ቆቋ ቱር ብላ ከጫካው ጥልቅ አለች፡፡
* * *
ምክር መቀበልና ማክበር ይገባል፡፡ አደጋ ላይ ሊጥል የሚችልን ነገር አስቀድሞ ማሰብ፣ ማውጠንጠንና መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ብዙ አደጋዎችን፣ ብዙ ችግሮችን፣ ብዙ ውጣ - ውረዶችን ያየችው አገራችን መከራዋን ትወጣው እንጂ አብዛኛዎቹ የተከሰቱት ምክር በማይሰሙ መሪዎች፣ ኃላፊዎችና ሥራ አስኪያጆች ሳቢያ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ የታለፉ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ አጋጣሚዎች ደግመን ማጣት ከእንግዲህ ብርቱ ዋጋ ያስከፍለናልና ጥንቅቅ ብለን ማሰብ ይገባናል፡፡ የድህነት ነገር ሆኖብን ሁሌ ሥራችንን በዘመቻ እንድንሠራ እንገደዳለን፡፡
አንድን ሥራ በነጥብ መብራት አተኩረን መሥራት ትልቅ ጉልበት በማከማቸት ግብ እንድንመታ ይረዳናል፡፡ ሆኖም ዘላቂና የኔነት ስሜት ያለው ሥራ እንድንሠራ በሙያዊ ብቃት፣ በሥራ ክፍፍልና በሙሉ ስሜት እንድንራመድ ካልሆነ፣ ለብዙ ችግር እንጋለጣለን፡፡ ጦርነትም ቢሆን እንኳ በኃይል በኃይሉ፣ በክህሎት በክህሎቱ ሲሰደር ነው ለግብ ይበቃል የሚባለው፡፡
የጋራ ጥቅም ላይ ያነጣጠሩ መስሎ የግል ጥቅምን በጐን ማሳደድ ሊነቃበት የሚገባ ጨዋታ ነው፡፡ “ሌላ ጊዜ አንቺ ይላል፤ ጠላ ስትጠምቅ እሜቴ ይላል” የሚለውን የወላይታ ተረት ከልብ ማስተዋል ዋና ነገር፡፡
መቼም የሀገራችን ነገር አንዱ ሲወርድ አንዱ ሲወጣ ያለበት ነው፡፡ ከሥራውም ይልቅ ሰውዬውን ለሚያይ ዘላቂነት ያለውና ያለፈውን ስህተት ለማረም የቻለ ጉዞ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ የሠራተኛው፤ የፓርቲ አባሉ፣ የበታች ኃላፊው ሁሉ፣ ሁልጊዜ “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው” የሚልበት ዘመን ያከተመ ይመስላል፡፡ “ተሰናባች አይርገምህ፤ ተተኪው አይጥላህ” የሚለውን በጥንቃቄ ካዩት፣ ትርጉም ያለው ቁምነገር ያስጨብጠናል።
ተሰናባች በግፍ፣ በምቀኝነት ወይም በአድልዎ ተባሮ ከሆነ፣ እርግማኑ ይደርስብኛል ብሎ ማሰብ የአባት ነው፡፡ ተተኪው በተንጋደደ ዐይን የሚያይ ከሆነና፤ “ለዚያኛው ያልተኛ እኔን አይምረኝም”
ብሎ ያሰበ ከሆነም ሲሰጉ መኖር ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡ የሚመጣውን ሁሉ ተዘጋጅቶ መጠበቅ ያለ ነው፡፡ ጦር መጣ፣ ጦር መጣ እያሉ በጣም ያስፈራሩት ጀግና፤ በዝግታ እየተዘጋጀ፤ “ይምጣ ከመጣ ሞቼ ልጠብቀው እንዴ ልዘጋጅ እንጂ!!” አለ የሚባለውንም አንዘንጋ፡፡
ጉዳዩን የሚያቅ፤ የበሰለ፣ ባለገድልና ባለታሪክ ሰዋችንን አንናቅ፡፡ ከየቦታው ሰብስበን ሥራ ላይ እንዲቀመጥ እናድርግ፡፡ ልታይ ልታይ የሚለውንና የአደባባይ ጌጥ የሆነውን ትተን፤ ከልቡ ለሀገር የሚያስበውን እናስተውል፡፡ “ይቺ እንዴ ትጨፍራለች?” ቢባል፤ “ልብስ አጥታ እቤት የቀረችውን ባየህ!” አለ፤ የሚባለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡

አንጋፋው ሀገር ፍቅር ቴአትር፤ በቶፊቅ ኑሪ ተደርሶ፣ በዳግማዊ አመለወርቅ ፈይሳ የተዘጋጀውን “ከመጋረጃው በስተጀርባ” የተሰኘ ቴአትር የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 8፡30 ጀምሮ እንደሚያስመርቅ ገለጸ፡፡
ጭብጡን በአገር ጉዳይ ላይ ባደረገው በዚህ የሙሉ ሰዓት ቴአትር ላይ አንጋፋና ወጣት ተዋንያን የሚሳተፉበት ሲሆን በምርቃቱ ላይ የባህልና ቱሪዝም ኃላፊዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚታደሙ ሀገር ፍቅር ቴአትር አስታውቋል፡፡   


Saturday, 26 May 2018 13:04

እንደ መግቢያ

  እንደ መግቢያ
                   ነቢይ መኮንን

ምነው ዛሬ እንባዬ፣ ለሰው ሳይታይ ይወርዳል
ምነው ዛሬስ ልቅሶዬ ሰው - አይሰማው - ሙሾ ሆኗል
ምን ታላቅ ሰው ሙቶብኝ ነው
እንዲህ ድምፄ ድምፁን ያጣው?
ዋ! ጋሽ አብይ!
ጋሽ አብይኮ ሰው ነበር፣ ከሰውም ሰው የቅን ማማ
የረቂቅ ተምሳሌት በላይ፣ ዕፁብ ምስል የነብስ አርማ፡፡
እሱስ አዕምሮውን አዞ፣ ማወቅ ያለበትን አውቋል፡፡
ሳያውቅ ዱታው - ዘራፍ የሚል፣ ባገሬ ስንት ዐብይ ሞልቷል!
ከዚህ በላይ እርግማን አለ? በአገር ላይ አለመታደል?
ይህ ነው መሰል ያስለቀሰኝ
ድምፅ - አልባ እዬዬ ያስቃኘኝ?!
ነበር አይባልም እሱ!
ጋሽ ዐቢይ!
ሰፊ ነው የዕውቀት አትሮንሱ
ነበር አይባልም እሱ!
“አለ”ም ቢባል፣ ተራ “አለ” አደል
ፈልጉለት ሌላ ዕፁብ ቃል
ጥበብ ነው ጥሩሩ ልብሱ
ነበር አይባልም እሱ
ሌላ የነፃነት እኩል፣ ገድል - አከል ቃል አስሉ
ነበር አይባልም እሱ!
“አለ”ም ቢባል ተራ “አለ” አደል
ፈልጉ ሌላ ህያው ቃል!!
ከህይወት ከራሱ እሚሻል!!
እናም “ቢሞት ሞተ አትበሉ”
ለእሱ ሞተ አይደለም ቃሉ
ልዩ ኑሮ ኖሮ ኖሮ
ልዩ ጥበብ ፈጥሮ አፋጥሮ
አልፎ ሄደ በሉ እንግዲህ፣ እራሱን በዕውቀት አኑሮ
እንደአየር ኃይል ባየር በሮ
እንደጠቢብ ፊልም ፈጥሮ
እንደኮሙኒኬሽን ሰው፣ የየክህሎቱን ቸሮ
የልባም አዋቂን ገድል፣ ፈፅሞና አስከብሮ
እራሱን አውርሶን ሄዷል፣ የልካችንን ቀምሮ!
ዕውነት እንበል ካልን …
እንደማንም መሞትማ ለማንስ ምኑ ያቅታል
እንደምንም መኖርማ ለማንስ ምኑ ይሳናል፡፡
ሰው ሆነን ሰው ሆነን መሞት፣ የባጀን ለታ ነው ጭንቁ
እንደጋሽ ዐቢይ ሰው ፈጥሮ፣ ማለፍ ነው የልባም ሳቁ!!
ሞተ ካፋችን አይውጣ
ሞትማ ዕውቀት አይገልም
ምሥጥ ጥበብ አያኝክም
የዘለዓለም ነው ሥሪቱ
አትሮንስ አይቆረጠምም!
“From ashes to ashes”
Such a mind never allows!
ከትቢያ ወደ ትቢያማ፣ ብሎ ሐረግ ለሱ የለም
    እንደ ዐቢይ ላለው አይሰራም!
ሰፊ ነው የሊቅ አድማሱ
አየር ኃይል ህዋ ፈረሱ
ኪነ - ፊልም ጥበብ ግላሱ
የሐዋርድ አዋጅ መለከት፣ የጥቁር ድምፅ ምስል ቅርሱ
ነበር አይባልም እሱ፣ ነውም ያንሳል ቃለ - ግሡ
አይለካም ወርደ - አትሮንሱ!
ዩኒቨርስ በሰው ቢመሰል፣ ዐቢይ ነበር የምድር ዋሱ
ነቢብ - ገቢር ውቂያኖሱ!
ፒያኖ ማዕጠንት መቅደሱ
ኮንጋና ጀምቤ ከበሮ፣ የካሪቢያን ዳሱ
የፎርት ዋሺንግተን ጀማ፣ የሙዚቃ ደቦ ምሱ
የሰው ፍቅሩ፣ የሰው ሱሱ
ምን ቃል ይበቃዋል ለሱ?!
እልፍ ነውና መለኪያው
ስውር ነውና ሚዛኑ
ሳይለይ አበባ እሳቱ
አይሞላምና ቋቱ
ለዚህ ነው ታላቅ ሰው ሲሞት
ፀሐይ ዕንባዋ እሚያጥራት
ከምድር ምህዋሯን እምትስት
ፍጥረታት ጉዞ እሚገቱት
ላም መታለብ የምታቆም
ወፍም መዘመር እምትሰንፍ
ሲሰሙ ነው የሊቅ ማለፍ
ሲዘጋ ነው የዕውቀት ደጃፍ!!
ጋሽ አብዬ … የዘር ግንዱ የአገር ፍቅር
    የእናት ኢትዮጵያ አፈር መከር
የእሱም ጥሪ ሆኖ ይሄው
በእናቱ መሬት አየነው!
ያም ሆኖ ነበር አይባል፣ ኗሪም - ቢባል ነገ አይበቃው
የፓን - አፍሪካው ነጋሪት፣ ገና የመጪ ድምፅ ነው!!
ዋ! ጋሽ አቢይ! …
(ለፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ፤
ግንቦት 8፣2010)