Administrator

Administrator

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ወላይታ ዞን ዳሞት ወይዴ ወረዳ፣ ባዴሳ ከተማ አካባቢ በዛሬው ዕለት በደረሰ የመኪና አደጋ የ15 ሰዎች ህይወት ማለፉን የዞኑ ፖሊስ አስታውቋል፡፡
መኪናው በአጠቃላይ 46 ሰዎችን አሳፍሮ ይጓዝ የነበረ ሲሆን፤ 5 ሰዎች ያለምንም ጉዳት ከአደጋው መትረፋቸው ታውቋል፡፡
ከአርባ ምንጭ ወደ ሻሸመኔ ይጓዝ የነበረ መኪና፣ ባዴሳ ከተማ አካባቢ ሲደርስ ፍሬን በመበጠስ ወንዝ ውስጥ ተገልብጦ በመግባት ገብቶ አደጋው መድረሱ ተነግሯል፡፡
አደጋው የደረሰባቸው ወደ አርባ ምንጭ ዚጊቲ ደብረ ሠላም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊ ጉዞ አድርገው ሲመለሱ በነበሩ ወጣት ምዕመናን ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡
ዛሬ ጠዋት 11 ሰዓት ገደማ በደረሰው በዚህ የትራፊክ አደጋ፣ ሹፌሩንና ረዳቱን ጨምሮ የ15 ሰዎች ህይወት ወዲያውኑ ሲያልፍ፤ በ21 ሰዎች ላይ ከባድ፣ በ6 ሰዎች ላይ ደግሞ ቀላል ጉዳት መድረሱን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ኮማንደር ንጋቱ ጌታቸው ገልፀዋል። ከባድና ቀላል ጉዳት የደረሰባቸው ተጎጂዎች ወደ ሆስፒታል ተወስደው ሕክምና እየተደረገላቸው መሆኑንም አክለዋል፡፡
አሸናፊዎቹ በጄኔቫ በሚካሄደው ውድድር ላይ ይሳተፋሉ
ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከሲያትል አካዳሚ ጋር በመተባበር፣ ‘’AI for Good Youth Challege Ethiopia’’ በሚል መሪ ቃል፣ በቴክኖሎጂ ፈጠራ ተሰጥኦ ያላቸው ከመጀመሪያ ደረጃ እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ በመማር ላይ የሚገኙ ሕፃናትና ወጣቶችን ያካተተ ውድድር ተካሂዷል።
በውድድሩ ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን፤ ተወዳዳሪዎቹ በሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንጂነሪንግና ዲዛይን የሠሯቸውን ፕሮጀክቶች አቅርበዋል።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የኢኖቬሽን ልማት መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሰላምይሁን አደፍርስ ባደረጉት ንግግር፤ የኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽ ትግበራ እውን እንዲሆን፣ ለኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ሥራዎች ዕድገትና ቀጣይነት የሚሠሩና አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ አካላትን በቀዳሚነት እንደግፋለን ብለዋል።
የSTEM Power ካንትሪ ዳይሬክተር ዶክተር ስሜነው ቀስክስ በበኩላቸው፤ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ጋር በማያያዝ ሕፃናትና ወጣቶችን በዲጂታል ቴክኖሎጂዎች ማሳተፍ፣ ብዙ ሳይንቲስቶችና ሥራ ፈጣሪዎች እንዲወጡ እንደሚያግዝ ተናግረዋል።
የውድድሩ አሸናፊዎች ሽልማት የሚበረከትላቸው ሲሆን፤ ከሃምሌ 8 – 11 ቀን 2017 ዓ.ም ጄኔቫ ላይ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት በሚያካሄደው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንጂነሪንግ ውድድር ላይ ኢትዮጵያን ወክለው እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡
(ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር)

ይኸውም ነገ መጋቢት 7 ቀን 2017 ዓ/ም ከቀኑ 5:00 ሠዓት ጀምሮ በመስቀል አደባባይ የሚከናወነውን የኢፍጣር ፕሮግራም ምክንያት በማድረግ፦
???? ከኦሎምፒያ ወደ መስቀል አደባባይ (ኦሎምፒያ አደባባይ ላይ )
???? ከጥላሁን አደባባይ ወደ ሳንጆሴፍ መብራት (ጥላሁን አደባባይ ሲሆን ከባድ ተሽከርካሪ አጎና ላይ )
???? ከለገሃር መብራት ወደ መሰቀል አደባባይ (ለገሃር መብራት)
???? ከቴሌ ማቋረጫ ወደ ስታድየም (ቴሌ ማቋረጫ ላይ)
???? ከሀራምቤ መብራት ወደ መስቀል አደባባይ (ሀራምቤ መብራት ላይ )
???? ከብሔራዊ ቤተ መንግሥት ወደ መስቀል አደባባይ (ብሔራዊ ቤተመንግሥት ላይ )
???? ከቅዱስ ዑራኤል አደባባይ ወደ መስቀል (ባምቢስ መቅረዝ ሆስፒታል መታጠፊያ ድረስ የሚዘጋ መሆኑን በመገንዘብ አሽከርካሪዎች አማራጭ እንዲጠቀሙ የአዲስ አበባ ፖሊስ ያሳስባል።

"ወታደራዊ ሃይልን ወደ ስልጣን የማምጣት ጉዳይ አይታሰብም"
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ፤ ከፌደራል መንግስትም ጋር ይሁን ከሌላ አካል ጋር ወደ ግጭት የሚያስገባ ነገር እንደሌለ አስታወቁ፡፡
“በምንም መልኩ በውስጣችን የሚፈጠር ግጭትና ጦርነት አይኖርም፣ የውስጥ ግጭት ይፈጠራል የሚለው ጉዳይ ዝግ ነው” ያሉት ጄነራሉ፤ “ግጭቱና ጦርነቱ በውስጣችን ይሆናል ወይም ደግሞ ከውጭ በሚኖር ግፊት ይጀመራል የሚለው ጉዳይ ሊያሳስብ አይገባም፣ አይኖርም” ብለዋል።
ባለፉት ቀናት በክልሉ የተካሄዱት ሁነቶች በምንም መልኩ ከወታደራዊ ድርጊት ጋር የሚያያዙ አይደለም ያሉት ጄነራል ታደሰ፤ “በምንም መልኩ ወታደራዊ ሃይልን ወደ ስልጣን የማምጣት ጉዳይ አይደለም፤ ይህ ፈጽሞ የማይሆን ነገር ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በህወሓት አመራሮች መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት የሀይማኖት አባቶችን ጨምሮ በተለያዩ አካላት የተለያዩ ጥረቶች ቢደረጉም ሊሳካ አልቻለም፤ ችግሩ ከአደራዳሪዎቹ ሳይሆን ከተዳራዳሪ አካላት የመነጨ ነበር ያሉት ጄነራሉ፤ ዋና ተግዳሮት የሆነው “አለመቀበልና እንቅፋት መፍጠር፣ አንዱ ወገን አንዱን ወገን አሸንፎ ለመውጣት ፍላጎት መኖሩ” እንደነበር አስረድተዋል፡፡
ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ ታደሰ ይህን ይበሉ እንጂ፣ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንት ጌታቸው ረዳ ከትላንት በስቲያ በአዲስ አበባ በሰጡት መግለጫ፤ ህገወጥ ያሉት የህወሓት ቡድን አመራሮች ሥልጣን በሃይል ለመንጠቅ እያደረጉት ያለው እንቅስቃሴ ወደ ጦርነትና ግጭት እንደሚያመራ ማስጠንቀቃቸው ይታወቃል፡፡ የፌደራል መንግሥትም ድርጊቱን ለመግታት አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡

በትግራይ የሕወሓት አንደኛው አንጃ ለራሱ ጥቅም ሲል እየፈጠራቸው ያሉ ድርጊቶች ተገቢነት የሌላቸውና ህዝብን ችግር ውስጥ የሚከቱ በመሆናቸው በጊዜ መቆም እንዳለባቸው የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር አረጋዊ በርሔ አሳስበዋል፡፡

በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ሁሉንም አካታች የሆነ አስተዳደር በክልሉ መተግበር እንዳለበት የገለጹት ሊቀመንበሩ፤ የትግራይ ህዝብ ከመጠን በላይ በጦርነት ተጎድቷል ብለዋል፡፡
ከፕሪቶሪያው ስምምነት ወዲህ በክልሉ የተቋቋመው ጊዜያዊ አስተዳደር በህወሓት አንጃ እንዲጨናገፍ መደረጉን የጠቆሙት ዶ/ር አረጋዊ፤ የፌደራል መንግስት በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ሁሉንም ያካተተ አስተዳደር ተመስርቶ፣ ህዝቡን ከዳግም መከራ ሊታደገው ይገባል ሲሉ ገልፀዋል።

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ “በትግራይ ክልል የሚፈጠረው ችግር ኢትዮጵያን የማተራመስ አቅም አለው” በማለት ተናግረዋል። ፕሬዚዳንቱ የፌደራል መንግሥቱ ለጊዜያዊ አስተዳደሩ ደጋፍ መስጠት አለበት ብለዋል፡፡
ዛሬ በሸራተን አዲስ ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ የትግራይ ክልልን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል። ፕሬዚዳንቱ፣ "የእኔ ፍላጎት ጦርነትን ማስወገድ ነው፡፡ ሌላ ጦርነት ማካሄድ ሳይሆን ጦርነትን ለማስወገድ የሚያስችሉ ሁሉም አስፈላጊ እርምጃዎች መወሰድ አለባቸው” ሲሉም ተደምጠዋል።
"እዚህ ውስጥ የእርስ በርስ ግጭትን ማስቀረት መቻል ስላለብን፣ እንዲሁም ሌሎች ጠላቶች ገብተው ይሄን ሊጠቀሙበት የሚችሉበትን ዕድልም መከልከል ስላለበት፣ ፌደራል መንግስት ለዚህ ‘በቂ ነው’ የሚለውን ድጋፍ መስጠት ‘አለበት’ የሚል ዕምነት አለኝ" ያሉት አቶ ጌታቸው፤ በትግራይ ክልል የሚፈጠረው ችግር ኢትዮጵያን የማተራመስ አቅም እንዳለው ጠቅሰዋል። አክለውም፤ “ከኤርትራ ጋር ግንኙነት መፍጠር ካስፈለገ፣ የተፈጸሙትን ጭፍጨፋዎች በመካድ አይደለም የሚፈጠረው” ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በዛሬ መግለጫቸው፤ የፕሪቶሪያ ስምምነትን ለማፍረስ “እየተደረገ ነው” ያሉት እንቅስቃሴ በፍጥነት እንዲገታም ጥሪ አቅርበዋል።
የአፍሪካ ወጣቶች የሮቦቲክስ ፈጠራ ችሎታቸውን የሚያሳዩበት 3ኛው የአፍሪካ ሮቦቲክስ ሻምፒዮንሺፕ ውድድር ዛሬ በአዲስ አበባ ሳይንስ ሙዚየም በታላቅ ድምቀት ተከፍቷል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ባይሳ በዳዳ በመክፈቻው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ "የአፍሪካ ሮቦቲክስ ሻምፒዮንሺፕ ውድድር ኢትዮጵያን ከድህነት ለማላቀቅ፣ ታዳጊዎችን በቴክኖሎጂ ለማብቃት ወሳኝ ምዕራፍ ነው" ብለዋል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ለወጣቶች የቴክኖሎጂ ክህሎት እድገት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብተዋል።
የኢትዮ ሮቦቲክስ መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰናይክረም መኮንን በበኩላቸው፤"ከዛሬ መጋቢት 4 እስከ 6 ቀን 2017 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በሚካሄደው በዚህ ውድድር ላይ የመጀመሪያ ደረጃ፣ የሁለተኛ ደረጃ፣ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በፈጠራ ችሎታቸው ይወዳደራሉ፤ ውድድሩም በዲዛይን፣ በኢንጂነሪንግና በአውቶኖሚ ኮዲንግ ላይ ያተኩራል" ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የውድድሩ ዓላማ ወጣቶች በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸውን ክህሎት ማዳበርና ማበረታታት እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ማድረግ ነው ያሉት አቶ ሰናይክረም፤ የውድድሩ አሸናፊዎች የዋንጫ ሽልማትና ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተፈረመ የምስክር ወረቀት ይበረከትላቸዋል ብለዋል፡፡
ዋና ሥራ አስኪያጁ አክለውም፤ "እንደ አህጉር መጪውን ትውልድ የሚያጎለብት የዲጂታል ቴክኖሎጂና የምህንድስና ትምህርት ባህል መፍጠር ላይ ማተኮር አለብን" ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የውድድሩ አሸናፊዎች ከነገ በስቲያ ቅዳሜ ይፋ የሚደረጉ ሲሆን፤ ለፍጻሜ የሚበቁ ተማሪዎች አገራቸውን ወክለው በአሜሪካ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡

ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከዩኤን ውመን ጋር የሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ “ይረዳል” የተባለለትን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል። በባንኮች ላይ በአመራርነት የሚሰሩ ሴቶች ቁጥር አነስተኛ ስለመሆኑም ተገልጿል።

ዛሬ መጋቢት 4 ቀን 2017 ዓ.ም. በሒልተን ሆቴል በተካሄደው የውይይት መድረክ ላይ የዩኤን ውመን የኢትዮጵያ ተወካይ ሲሲል ሙካሩባጋን ጨምሮ፣ ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ዕንግዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ ሴት ስራ ፈጣሪዎች ከመነሻ ካፒታል እና ሌሎች የፋይናንስ አገልግሎቶችን ከማግኘት አንጻር የተለያዩ ፈተናዎች እንደሚገጥማቸው ተጠቅሷል።

ባለፉት 30 ዓመታት ውስጥ በሴቶች አቅም ግንባታ፣ ዕኩል ተጠቃሚነት እና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከፍተኛ ስራዎች እንደተሰሩ ተገልጿል። ይሁንና ቀላል የማይባሉ ተግዳሮቶች ሴቶች በስራ ፈጠራ እና ኢኮሚያዊ ተሳትፎ ላይ ጠንክረው እንዳይወጡ እንዳደረጋቸው ተነግሯል።

በመድረኩ ላይ ከቀረበው ገለጻ ለመረዳት እንደተቻለው፣ በኢትዮጵያ ያሉ የፋይናንስ ተቋማት ለሴቶች ብድር የሚሰጡት ከ13 በመቶ ባነሰ መጠን ነው። ይህም ከወንዶች እንጻር ሲመዘን “አናሳ ነው” ተብሏል።

በተጨማሪም፣ አሁን በስራ ላይ በሚገኙ ባንኮች ላይ በሃላፊነት እየሰሩ ያሉ ሴቶች 12 ነጥብ 5 በመቶ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው የሴት ሃላፊዎችን ብዛት ከወንድ አቻዎቻቸው አንጻር 25 በመቶ ገደማ እንዲደርስ ካስቀመጠው ግብ አንጻር አናሳ መሆኑን ተጠቁሟል።

በዚህም ተጨባጭ ዕምርታዎችን የሚያሳዩ ስራዎች መስራት እንደሚያስፈልግ ተጠቅሷል። እንዲሁም ሴቶች የኢኮኖሚ አቅማቸውን ካጠናከሩ፣ አጠቃላይ መብቶቻቸውን ማስጠበቅ “ይችላሉ” ተብሏል።

ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በሚተገብራቸው፣ በተለይ ሴቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን አስመልክቶ አቶ በግዱ ሃይለመስቀል የዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፣ ባንኩ ከUN Women ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል።

የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ “ይረዳል” የተባለለት ይህ የመግባቢያ ሰነድ በባንኩ የዓለም አቀፍ ባንክ አገልግሎት ምክትል ቺፍ ኦፊሰር ወይዘሮ ሐረገወይን አምሳለ እና በUN Women የኢትዮጵያ ተወካይ ሲሲል ሙካሩባጋ አማካይነት ተፈርሟል።

• 2.5 ሚሊዮን ብር ፈጅቷል ተብሏል

በአጠቃላይ 2.5 ሚሊዮን ብር እንደፈጀ የተነገረለት "እንግዱ" የተሰኘ ልብ አንጠልጣይ ትሪለር ይዘት ያለው አዲስ ፊልም፣ ከመጋቢት 5 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡

በሳዳም ነጌሶ ተደርሶ ዳይሬክት የተደረገው ፊልሙ፤ በልባም ፒክቸርስ ተዘጋጅቶ በሳዳም ፊልም ፕሮዳክሽንና በሶሎዳ ስቱዲዮ መቅረቡ የተነገረ ሲሆን፤ የ1 ሰዓት ከ32 ደቂቃ እርዝማኔ ያለው ነው ተብሏል፡፡

ዛሬ ጠዋት ረፋዱ ላይ በፊልሙ ዙሪያ ፕሮዲዩሰሮቹና ተዋናዮቹ በሪፌንቲ ሞል (ቦሌ ቡልቡላ) ለሚዲያ ባለሙያዎች ጋዜጣዊ መግለጫ በጋራ ሰጥተዋል፡፡

"እንግዱ" የተሰኘውን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከ8 ወር በላይ እንደፈጀ የተገለጸ ሲሆን፤ በፊልሙ ላይ ከ35 በላይ ታዋቂና አጃቢ ተዋናዮች እንደተሳተፉበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከፊልሙ መሪ ተዋናዮች መካከል፡- አንጋፋው ተዋናይ ሰለሞን ሙሄ፣ ኤደን ገነት፣ ታዋቂው ኮሜዲያን ደረጄ ሀይሌ፣ ጌዲዮን ፍቃዱና አሰፋ ገ/ሚካኤል ይገኙበታል፡፡

የፊልሙ ቀረጻ እዚሁ አዲስ አበባ የተከናወነ ሲሆን፤ ከ65 በመቶ በላይ በሪፌንቲ ሞል ህንጻ ላይ መቀረጹ ተነግሯል፡፡

እንግዱ የተባለው ገጸባህርይ 7 ዓይነት ማንነቶችን ወይም ሰብዕናዎችን የያዘ መሆኑ ፊልሙን ለየት ያደርገዋል ያለው ደራሲና ዳይሬክተሩ ሳዳም ነጌሶ፤ የዚህን መነሻ ሃሳብ የወሰደው እ.ኤ.አ በ2016 ዓ.ም ከተሰራው Split የተሰኘ የሆሊውድ አስፈሪ ትሪለር ፊልም መሆኑን ጠቁሟል፡፡

በፊልሙ ላይ እንግዱን ሆኖ የተወነው ጌዲዮን ፍቃዱ በሰጠው አስተያየት፤ "ስክሪፕቱን ለመጀመሪያ ጊዜ ሳነበው ልሰራው የማልችለው ነበር የመሰለኝ፡፡ በአንደ ሰው ላይ ሰባትና ከዚያ በላይ ማንነቶችን ማሳየት ፈታኝ ነበር፡፡ እንደምንም ግን ተወጥቼዋለሁ" ብሏል፡፡

"እንግዱ" ፊልም በትላንትናው ዕለት በዓለም ሲኒማ ለአርቲስቶችና ለፊልሙ ቤተሰቦች ለዕይታ የበቃ ሲሆን፤ መጋቢት 5, 6 እና 7 እንዲሁም መጋቢት 12, 13 እና 14 ቀን 2017 ዓ.ም በሁሉም ሲኒማ ቤቶች በይፋ እንደሚመረቅ ታውቋል፡፡

ኦክሎክ ሞተርስና አንዳንድ ማህበራት በመካከላቸው ተፈጥሮ የነበረውን አለመግባባት በእርቅ መፍታታቸውን አስታውቀዋል፡፡

ይሄ ይፋ የተደረገው ዛሬ ጠዋት ረፋድ ላይ የኦክሎክ ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ፣ እንዲሁም የሽማግሌና የማህበራቱ ተወካዮች በተገኙበት በድርጅቱ ዋና መ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው፡፡

ኦክሎክ ሞተርስ ባሰራጨው መግለጫ እንዳመለከተው፤ ከጥቂት ወራት በፊት በተሳሳተ መረጃና ጉዳዩን በጥልቀት ካለመረዳት የተነሳ ከድርጅታችን ጋር የሽያጭ ውል በመግባት ተሽከርካሪዎችን ለመግዛት ተስማምተን በጋራ እየሰራን ካሉ በርካታ ማህበራት ውስጥ በተወሰኑ ማህበራትና ግለሰቦች አማካኝነት በድርጅቱ ላይ የስም ማጥፋት ተግባር ተፈፅሞ ነበር፡፡

ይሁን እንጂ ማህበራቱና አባላቱ ጉዳዩን በጥልቀት ከመረመሩና በጊዜው የተነገራቸውን መረጃዎች መለስ ብለው በማጣራትና ከድርጅታችን ጋር በመነጋገር፣ በሀገራችን ባህል ወግ መሰረት፣ ችግሩን በእርቅ ፈተን በመስማማት ወደ ትግበራ ስራ ገብተናል ብሏል፤ ድርጅቱ በመግለጫው።

ኦክሎክ ሞተርስና ማህበራቱን በሽምግልና ለማስታረቅ እልህ አስጨራሽ ጥረት መደረጉ የተገለጸ ሲሆን፤ የማታ ማታ ስምምነት ላይ መደረሱ ይፋ ተደርጓል፡፡ በዚህም መሰረት ገንዘብ የሚፈልጉ ገንዘብ፣ መኪና የሚፈልጉ ገንዘብ እንዲወስዱ የተስማሙ ሲሆን፤ በዛሬው ዕለት 20 ያህል አባላት መኪና እንደሚረከቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ገንዘብ የሚፈልጉ ደግሞ በ45 ቀናት ውስጥ ገንዘባቸውን እንደሚወስዱ ተነግሯል፡፡

በእርቅ ስምምነት ላይ የደረሱት የማህበራት ተወካዮች በሰጡት አስተያየት፤ "ወደ ህግ መሄድ ጊዜ የሚፈጅና አላስፈላጊ ወጪ የሚያስከትል በመሆኑ ችግራችንን በእርቅ ለመፍታት ተስማምተናል" ብለዋል፡፡

በኦክሎክና ማህበራቱ መካከል እርቅ ለማድረግ ተነሳሽነቱን የወሰዱት የሽማግሌዎቹ ተወካይ እንደገለጹት፤ መጀመሪያ ላይ ከሁለቱም ወገኖች ተቀባይነት አላገኙም ነበር፡፡ "በተለይ ማህበራቱ ከኦክሎክ የተላክን መስሏቸው ዕርቁን አሻፈረን ብለው ነበር፤ ዓላማችን በሁለቱ መካከል ሰላምና እርቅ መፍጠር መሆኑን ካረጋገጡ በኋላ ነው የተስማሙት" ብለዋል፤ በሰጡት መግለጫ፡፡

የኦክሎክ ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ካሣሁን በበኩላቸው፣ መጀመሪያ ላይ በማህበራቱ በኩል ስለድርጅቱ የተሳሳተ መረጃ ይሰራጭ እንደነበር አንስተዋል፡፡ ለአብነት ያህልም፡- ኦክሎክ ከማህበራቱ አባላት 1.2 ቢሊዮን ብር ሰብስቦ አንድም መኪና አላስመጣም የሚለው ነው ብለዋል፡፡ ሌላው ደግሞ በራሱ በድርጅቱ የተመዘገበ የመኪና መገጣጠሚያ ፈቃድ የለውም የሚል እንደነበር ጠቁመዋል፡፡

"እውነቱ ግን ኦክሎክ ሞተርስ በመቀሌና በአዲስ አበባ በስሙ የተመዘገበ የመኪና መገጣጠሚያ ያለው ሲሆን፤ ከመኪና ፈላጊዎች የማህበራት አባላት የተሰበሰበው ገንዘብ 1.2 ቢሊዮን ብር ሳይሆን 41 ሚሊየን ብር ነው፡፡" ብለዋል፤ ሥራ አስኪያጁ፡፡

ኦክሎክ ከአባላቱ ገንዘብ ሰብስቦ ምንም መኪና አላመጣም የሚለውም ትክክል አይደለም ያሉት አቶ ታመነ ካሣሁን፤ የማህበሩ አባላት እስካሁን 800 ተሽከርካሪዎችን በካሽና በብድር ወስደዋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

የሽማግሌዎቹ ቡድንም እኒህን የተሳሳቱ መረጃዎች በራሳቸው መንገድ አጣርተው፣ እውነታው ላይ መድረሳቸውን በራሳቸው አንደበት ያረጋገጡ ሲሆን፤ እርቅ ላይ የተደረሰውም ከዚህ ሁሉ ሂደት በኋላ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በሁለቱ ወገኖች መካከል የተፈጠረው ልዩነት በእርቅ መፈታቱን ያደነቁ የተለያዩ ማህበራት ተወካዮች፤ ሌሎችም በክስ ሂደት ላይ ያሉ ማህበራት ችግራቸውን በእርቅ የሚፈቱበት ሁኔታ ይመቻች ዘንድ ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡

ከኦክሎክ ሞተርስ ጋር የእርቅ ስምምነት ላይ መድረሳቸው የተገለጸው ከ60 ማህበራት ውስጥ 16 ያህሉ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከ20 ዓመት በፊት የተመሰረተውና በተለያዩ ዘርፎች ላይ የተሰማራው ኦክሎክ ሞተርስ፤ በትግራይ መቀሌ ከተማና በአዲስ አበባ ቃሊቲ አካባቢ ባስገነባቸው የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎቹ ከ16 በላይ የተለያዩ ሞዴል ተገጣጣሚ ተሽከርካሪዎችን ከውጭ በማስመጣት እየገጣጠመ ለደንበኞቹ በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡

Page 7 of 765